2013 ኦክቶበር 17, ሐሙስ

መንበረ ፓትርያርክ

የመንበረ ፓትርያርክ 32ኛው ጉባኤ የረቡዕ ዕለት ከሰዓት ውሎ ካለፉት የተለየ ነበር፡፡ ዋና አጀንዳው ‹መቻቻልን› የተመለከተ ሲሆን አቅራቢዎቹም ከፌዴራል ጉዳዮች የተወከሉ አካላት መሆናቸውን በዕለቱ የመርሐ ግብር ዝርዝር ላይ ተገልጧል፡፡ ከሰኞ ጀምሮ ይቀርብ በነበረው የአህጉረ ስብከት ሪፖርቶች ላይ የመብት ጥሰትና ሥልጣንን ለግል ሃይማኖት ማስፋፊያ የመጠቀም አዝማሚያዎች መኖራቸውን፣ በሕገ መንግሥቱ የተረጋገጠው እምነትን የመያዝ፣ የማስፋፋትና የአምልኮ ቦታ የማግኘት መብት እየተጣሰ መሆኑን የሚገልጡ ዘገባዎች ይሰሙ ነበር፡፡

በትናንትናው የከሰዓት ውሎ ስለ መቻቻል ገለጣ ከተሰጠ በኋላ ብጹዐን ሊቃነ ጳጳሳትና የጉባኤው ተሰብሳቢዎች የየአካባቢያቸውን ችግሮች በዝርዝር ነበር ያነሷቸው፡፡ ‹‹መቻቻል እስከ ምን ድረስ ነው›› ብለው ነበር ብጹዕ አቡነ ቄርሎስ የጠየቁት፡፡ ‹‹አሁን በምዕራብ ወለጋ ያለው ሁኔታ መንግሥት በአገሩ ያለ ይመስላል ወይ? ሰው እግሩን እሳት እየበላው ቻል ይባላል እንዴእንድንቻቻል አድርጉን፣ እንችላለን›› ነበር ያሉት፡፡
የምዕራብ ወለጋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብጹዕ አቡነ ሄኖክ ‹በነጆ ወረዳ በሕጋዊ መንገድ ተሠርቶ የነበረው ቤተ ክርስቲያን በአካባቢው ባለ ሥልጣናት ተጽዕኖ እንዲፈርስ መደረጉን፣ ለምን ታፈርሳላችሁ ብለው ድርጊቱን የተቃወሙ ስድሳ ምእመናን መታሠራቸውን›› በኀዘን ነበር የገለጡት፡፡ አያይዘውም ‹‹በባኮ ወረዳ የተመደቡ አንድ ካህን እያረሱ እያሉ የአካባቢው ባለ ሥልጣናት መጡ፤ ካህኑን በሰደፍ እየደበደቡ ‹ከዚህ ሀገር ልቀቁ፣ ይህ የነፍጠኛ መኖሪያ አይደለም› እያሉ አሰቃዩዋቸው፡፡ ካህኑን ሲደበድቧቸው አንበርክከው፣ ለ15 ደቂቃ አተኩረው ፀሐይዋን እንዲያዩ እያስገደዱ ነበር፡፡ ድብደባውን ሰምተው የወጡት ባለቤታቸው በድንጋጤ ታመው ከጥቂት ቀናት በኋላ ሕይወታቸው አለፈ››
‹‹በሰንበትና በቅዱስ ሚካኤል ቀን ምእመናን ሊያስቀድሱ ወደ ቤተ ክርስቲያን ሲሄዱ ‹ለቅዳሴ ካህናቱ ይበቃሉ፤ እናንተ ውጡ›› እየተባሉ እንዳያስቀድሱ ይደረጋሉ፡፡ ከእኛ ቤተ ክርስቲያን 70 ሜትር ርቀት ላይ ሆን ተብሎ እርስ በርስ ለማጋጨት ለፕሮቴስታንቶች የጸሎት ቦታ ተሰጠ፡፡ ለምን ታጨቃጭቁናላችሁ፤ ይህ ቦታ ለእነርሱ አይሆንም ብሎ በመከራከሩ አንድ ዲያቆን ተደብድቦ ሞተ፡፡ የሕክምና ውጤቱም ሆን ተብሎ በወባ በሽታ ሞተ ተብሎ ተሠራ፡፡ ለሁለት ዓመት ያህል ተከራክረን አሁን ቦታው ለእኛ ተወሰነ፡፡
ጊምቢና መንዲ ላይ የምእመናን ልጆች ትምህርት ቤት ውስጥ በፖሊስ ማተባችሁን በጥሱ እየተባሉ ነው፡፡ ለምን ስንላቸው ከላይ የወረደ መመሪያ አለ ይሉናል፡፡››
ቀጥለው የሀገረ ስብከታቸውን ችግር ያቀረቡት የጋሞጎፋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብጹዕ አቡነ ኤልያስ ነበሩ፡፡ ‹‹በጋሞ ጎፋ መቱ ወረዳ፣ ዋጁ ኡቆ ላይ የመስቀል ማክበሪያ ቦታችን ለሱቅ መሥሪያ ቦታ ተሰጠ፡፡ አቤት ብንል የሚሰማን በማጣታችን ዘንድሮ በኢትዮጵያ ውስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ መስቀል ሳናከብር ዋልን፡፡ ሀገሪቱ በችግር ላይ በነበረች ጊዜ እንኳን መስቀል ሳይከበር ቀርቶ አያውቅም ነበር፡፡ የቤተ ክርስቲያን የይዞታ ቦታ ለመንግሥት እየተሰጠ ነው፡፡ በአቡነ ጳውሎስ ዘመን በቅዱስነታቸው በኩል ለክልሉ ደብዳቤ ጻፍን፡፡ ክልሉ ወሰነልን፡፡ ነገር ግን እስካሁን አልተረከብንም፡፡››
ቀጥለው ሃሳባቸውን የሰጡት የባሰ ካልመጣ በቀር ድምጻቸው ማይሰማው ብጹዕ አቡነ ያሬድ የሶማሌ ክልል ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ነበሩ፡፡ ‹‹በሶማሌ ክልል አምስት አብያተ ክርስቲያናት ብቻ ናቸው ያሉን፡፡ ምእመናኑ ብዙ ናቸው፡፡ ሲወልዱ የሚያስጠምቁበት፣ ሲያርፉ የሚቀበሩበት ቤተ ክርስቲያን እንትከል ብንል የሚሰማን አጥተናል፡፡ ቤተ ክርስቲያንን የሚረዱ ምእመናን በግላቸው ጥቃት እየደረሰባቸው ነው፡፡ ለዚህ መልሳችሁ ምንድን ነው›› ብለዋል፡፡
በገለጻው ላይ ኢትዮጵያ ክርስትናን የተቀበለችው በ4ኛው መክዘ ነው የሚለውን የተቃወሙት ብጹዕ አቡነ ማርቆስ ‹‹ታሪክ ክፉም ሆነ በጎ እንደ ታሪክነቱ መተረክ አለበት፤ አቅራቢው ወንድማችን በ4ኛው መክዘ ክርስትና ገባ ያልከው ተሳስተሃል፡፡ ለመሆኑ ይህንን ለማለት ‹ላይሰንስ አለህ?› አባቱን የሚኮንን ልጅ ምን ያደርጋል? ነገሥታቱን ወቀሳችሁ፣ ቤተ ክርስቲያንን ነቀፋችሁ፤ ለመሆኑ ከማን ነው ይህቺን ሀገር የተረከባችሁት? ክርስትና ወደ ኢትዮጵያ የገባው ጌታ ባረገ ዓመት ባልሞላው ጊዜ ውስጥ ነው፡፡ በሐዋርያት ሥራ ምዕራፍ 8 ላይ አለ፡፡ ይህንን ዛሬ ‹ግራጁዌት አድርገው›፤ ልዑካኑ ስትመጡ ስለምትናገሩት ነገር ዕወቁ፤››
የደቡብ ጎንደር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብጹዕ አቡነ እንድርያስም ‹‹በቤተ መንግሥት የወርቅ ዕቃ ብቻ አይኖርም፣ የእንጨትም፣ የድንጋይም ዕቃ አለ፡፡ በቤተ ክርስቲያንም ሁሉም ጥሩ አይሆንም፣ መጥፎም ይኖራል፡፡ ነገር ግን እስከ መጨረሻው የጸና ይድናል ብሏል፡፡ በእኔ ሀገረ ስብከት ስድስት አብያተ ክርስቲያናት ተቃጥለዋል፡፡ ሦስቱ በአንድ አካባቢ፣ ሦስቱ በሌላ ቦታ፡፡ ይህንን ለክልሉ መንግሥት ብናሳውቅ አልረዱንም፡፡ የተበደለ ሰው ይጮኻል፤ ሲጮህ ደግሞ ፖለቲካ ነው ይባላል፡፡ ድሮ ያስቸገረን የንዋያተ ቅድሳት ዘረፋ ነበር፡፡ አሁን ደግሞ ቤተ ክርስቲያን ወደ ማቃጠል ተዛውሯል፡፡ አንዱ ባለ ሥልጣን እንዲያውም ችግሩን ሳቀርብለት ተቆጣኝ፤ ብዙ ብናገር ነፋስ ስለሚወስደው እዚህ ላይ ይብቃ››
ከብጹዐን ሊቃነ ጳጳሳት ቀጥሎ የተናገሩት የወላይታ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ ‹‹በበዴሳ ወረዳ ያለ አንድ የሌላ እመነት ተከታይ የሆነ ዳኛ ከኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ጋር ቄራ አንካፈልም፤ በመኪና አብረን አንሄድም› ብሎ ዐወጀ፡፡ በጋራ በመቻቻል የኖርንበትን ዕድር ሁሉ ለዩ ብሏል፡፡ ታድያ እንዴት መቻቻል ሊመጣ ይችላል፡፡››
ከጉባኤው የቀረበውን ቅሬታና ሃሳብ ያዳመጡት የፌዴራል ጉዳዮች የሥራ ኃላፊዎች የቀረቡት ቅሬታዎች በሰነድ ተደግፈው ቢደርሷቸው እነርሱም በመፍትሔው ላይ መሥራት እንደሚችሉ፤ ኢትዮጵያ የሃይማኖቶች ጉባኤም ጉዳዩ በየደረጃው ቢቀርብለት መፍታት እንደሚችል፡፡ ቅሬታዎችን እንደዚህ ባለ መድረክ ከሚሆን በየጊዜው እየተገናኙ መፍታት ቢቻል›. የሚሉ ሃሳቦችን ሠንዝረዋል፡፡
የዘንድሮው የሰበካ አጠቃላይ መንፈሳዊ ጉባኤ በአደረጃጀቱ ውበት፣ በተሳታፊዎቹ ብዛት፣ በአህጉረ ስብከቶች ቁጥር(50 ደርሰዋል)፣ በስብሰባው ቁም ነገረኛነት ካለፉት የተለየ ነበር፡፡ እነ ሊቀ ማእምራን ፋንታሁን ሙጬ የሰበካ ጉባኤ ስብሰባ ደረጃውን የጠበቀ እንዲሆን በብርቱ እንደ ደከሙበት ያሳያል፡፡ በየዘገባዎቹ የተሰሙትን የመብት ጥሰቶች፣ ሥልጣንን ተገን በማድረግ የሚፈጸሙ ጫናዎች፣ የአምልኮ ቦታ እጥረቶች፣ በካህናቱ ላይ የሚፈጸሙትን ግፎችና፣ የቤተ ክርስቲያንን ይዞታ የመንጠቅ ርምጃዎች ግን ሊገቱ ይገባቸዋል፡፡ ከአንዳንድ ክልሎች በቀር በብዙዎቹ የዞንና የክልል ባለ ሥልጣናት ችግሩን ተረድተው ለመፍታት እንደሚጥሩ ተገልጧል፡፡ በወረዳ ደረጃ የሚገኙት ግን ሥልጣንን ተገን በማድረግ የግል እምነታቸውን እያስፋፉ መሆኑን ያሳያል፡፡ በደቡብ ጎንደርና በምሥራቅ ጎጃም የተፈጸሙት የአብያተ ክርስቲያናትን የማቃጠል ርምጃዎች በጊዜው ተጣርተው መፍትሔ ካልተሰጣቸው ፍጻሜያቸው አያምርም፡፡
በየአካባቢው በሚገኙ ባለ ሥልጣናት የሚፈጸሙ ትንኮሳዎችም መቆም አለባቸው፡፡ ብጹዐን ሊቃነ ጳጳሳቱ ‹አታስቆጡን› እያሉ ደጋግመው የተናገሩት ነገር የዋዛ አይደለም፡፡ ኃላፊነት የማይሰማቸው አካላት የሚፈጽሙት ገደብ አልባ ትንኮሳና ጫና ወዴት እያመራ መሆኑን የሚያሳይ ነው፡፡
ቤተ ክርስቲያኒቱም አደረጃጀቷንና አሠራርዋን ይበልጥ የምትፈትሽበት፣ አሁን ለገጠማት ተግዳሮት ብቁ የሚሆን አሠራና አወቃቀር የምትይዝበት፣ ችግሮችን በስብሰባ ብቻ ሳይሆን በአካባቢያዊ ውይይት፣ በሕግ መሥመርና ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ተቀራርቦ በመሥራት የምትፈታበት መንገድ ሊኖር ይገባል፡፡  
ያለበለዚያ መጋቤ ምሥጢር ወልደ ሩፋኤል የተረተው ተረት መድረሱ የማይቀር ነው፡፡
በጣልያን ጊዜ ነው አሉ፡፡ ጎንደር ላይ ጣልያን በድማሚት አንዱን ተራራ ያናውጠዋል፡፡ ተራራው ‹እድም› እያለ ይፈርሳል፡፡ አንዲት የከብት እረኛ ልጅ ፈርታ ወደ እናቷ ሄደችና ‹እማዬ ኧረ ጣልያን ተራራውን እያፈረሰው ነው›› አለቻት፡፡ እናቷም ‹‹እነ ደጃዝማች እገሌ፣ እነ ፊታውራሪ እገሌ፣ እነ ራስ እገሌ እጅ አንሰጥም ብለው እየተጋደሉ ዐለፉ፡፡ ተራራውንስ ተይው ያፍርሰው፤ እርሱም መቀመጡን አብዝቶት ነበረ፡፡›› አለቻት አሉ፡፡ 

ምንም አስተያየቶች የሉም:

አስተያየት ይለጥፉ

                                   በአውሮጳ   የካህናት አንድነት ማኅበር ሊቋቋም መሆኑ ታወቀ በ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከመላዋ አውሮጳ   የተውጣጡ ካህናት፡” የ...