2015 ጃንዋሪ 2, ዓርብ

“ወብዙኀን ይትፌሥሑ በልደቱ በመወለዱም ብዙዎች ደስ ይላቸዋል” ሉቃ.1፥14



አትም ኢሜይል
ታኅሣሥ 25 ቀን 2005 ዓ.ም.
ዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ
st. tekela
  • በዘመነ ብሉይ የእግዚአብሔር ድምፅና የመልአክ ብሥራት ብርቅ በነበረበት ወቅት ካህኑ ዘካርያስና ቅድስት ኤልሳቤጥ ልጅ መውለድ አጥተው ባረጁበት ዘመን የእግዚአብሔር መልአክ ካህኑ ዘካርያስን እንዲህ አለው፡፡
መልአኩም እንዲህ አለው “ዘካርያስ ሆይ፥ አትፍራ፤ ጸሎትህ በእግዚአብሔር ፊት ተሰምቶአልና፤ ሚስትህ ኤልሣቤጥም ትፀንሳለች፤ ወንድ ልጅንም ትወልድልሃለች፤ ስሙንም ዮሐንስ ትለዋለህ፡፡ ደስታና ሐሤትም ይሆንልሃል፤ በመወለዱም ብዙዎች ደስ ይላቸዋል፡፡ እርሱ በእግዚአብሔር ፊት ታላቅ ይሆናልና የወይን ጠጅና የሚያሰክርም መጠጥ ሁሉ አይጠጣም፤ ከእናቱ ማሕፀን ጀምሮም መንፈስ ቅዱስ ይመላበታል፡፡ ከእስራኤልም ልጆች ብዙዎችን ወደ አምላካቸው ወደ እግዚአብሔር ይመልሳቸዋል፡፡ እርሱም የአባቶችን ልብ ወደ ልጆች፥ የከሓድያንንም ዐሳብ ወደ ጻድቃን ዕውቀት ይመልስ ዘንድ፥ ሕዝብንም ለእግዚአብሔር የተዘጋጀ ያደርግ ዘንድ በኤልያስ መንፈስና ኀይል በፊቱ ይሄዳል፡፡”ሉቃ1፥13-18 ይህ ለመጥምቁ ዮሐንስ የተነገረ ቃል ቢሆንም ወላጆቹ (ካህኑ ዘካርያስና ቅድስት ኤልሳቤጥ) በእግዚአብሔር ፊት ጻድቃን እንደነበሩ በቅዱስ ወንጌል ተገልጿል /ሉቃ.1፥6-7/ እንደዚሁ ሁሉ ካህኑ ጸጋዘአብና ሚስቱ እግዚእ ሐረያ በእግዚአብሔር ሕግና ሥርዓት ይመሩ የነበሩ ደጋግ ክርስቲያኖች ነበሩ፡፡ ይህም ሊታወቅ በትሩፋት ሥራ፣ በጾም፣ በጸሎት፣ በምጽዋት የታወቁ ነበር፡፡ በተለይም የሊቀ መላእክት የቅዱስ ሚካኤል በዓልን ምክንያት በማድረግ ይመጸውቱ ነበር፡፡ የመልአኩም ጥበቃ ባለ ዘመናቸው ሁሉ አልተለያቸውም ነበር፡፡ ጌታችን በቅዱስ ወንጌል ላይ “መልካም ዛፍ ሁሉ መልካም ፍሬን ያፈራል፣” /ማቴ.7፥17/ እንዳለ፣ ለዓለም ሁሉ የወንጌልን ብርሃን የሚያበስር ሐዲስ ሐዋርያ በቅድስናና በክብሩ ከሃያ አራቱ ካህናተ ሰማይ ሃያ አምስተኛ ሆኖ ያመሰገነውን ጻድቅ ወለዱ፡፡ በሰሜን ሸዋ ጽላልሽ ልዩ ስሙ ኢቲሳ በተባለ ቦታ የተወለዱት ጻድቁ ተክለ ሃይማኖት በ12ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የተነሡና የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ትምህርት ከየመን እስከ ኬንያ ከሶማሌ እስከ ሱዳን ድረስ የተስፋፋበትን ወርቃማ ዘመንን ያስገኙ ጻድቅ አባት ናቸው፡፡
“ነገርን ከሥሩ ውኃን ከጥሩ” እንዲሉ የጻድቁን ታሪክ በአጭሩ እንደሚከተለው አቅርበነዋል፡፡

ቅዱሳኑ በትሩፋት ሥራ የተጠመዱ ነበሩ
ልጅ አጥተው ሲያዝኑ ይኖሩ የነበሩት ካህኑ ፀጋ ዘአብና ቅድስት እግዚእ ሐረያ፣ በየወሩ የቅዱስ ሚካኤልን በዓል ያከብሩ ነበርና መጋቢት 12 ቀን የተራበን ሲያበሉ ሞቶሎሚ ንጉሠ ዳሞት ሀገራቸውን ወርሮ ከእነርሱ ደረሰ፡፡ ጸጋ ዘአብም እንደማይምራቸው አውቀው አንከርት ወደሚባለው ባሕር ሮጡ፡፡ ከሞተሎሚ ጭፍሮች አንዱ ተከተላቸው፣ የማይደርስባቸው ሲሆን ሰይፉን ሊወረውርባቸው ቃጣ፡፡ ሰይፉ ከእጁ ተጠቅልላ ቀረች፡፡ በሌላ እጁ ሁለተኛ ሊወረውር ቢቃጣ አሁንም ተጠቅልላ ቀረች፡፡ እሳቸውም እንዳልተዋቸው አይተው ዘለው ከባሕር ገቡ፡፡ ከባሕር ውስጥ ሆነው እንዲህ አያሉ ይጮሁ ጀመረ…” ኀይል የምትሆነኝ ቅዱስ ሚካኤል፣ አምባ መጠጊያ የምትሆነኝ ቅዱስ ሚካኤል፣ ኀይልህ ወዴት ነው? ከኃሊነትህ ወዴት ነው? ተአምራት ማድረግህ ወዴት ነው? እንሆ መሞቻዬ ደረሰ፡፡ ዛሬ የሽብር ቀን ነው፡፡ ዛሬ የመከራ ቀን ነው፡፡ ዛሬ ጥፋት ተፈርዶብኝ፡፡ በበዓልህ ደስ ሳታሰኘኝ ታሳዝነኛለህን? እያሉ ያለቅሱ ጀመረ፡፡ እስመ ለመላእክቲሁ ይኤዝዞሙ በእንቲአከ ከመ ኢትትዐቀፍ በዕብን፤ እግርከ በመንገድህ ሁሉ ይጠብቁህ ዘንድ መላእክቱን ስለ አንተ ያዛቸዋልና፣ እግርህ በድንጋይ እንዳትሰናከል በእጆቻቸውም ያነሡሃል፡፡ እንዲል /መዝ.90፥11/ ቅዱስ ሚካኤል በውስጥ ሆኖ ተቀብሏቸዋል፡፡ “ወባሕርኒ ኮነቶ ከመ ደብተራ ዘድለት ለማኅደር” ይላል ባሕርም እንደ ድንኳን ሆነላቸው “ኦ ፍቁርየ ጸጋ ዘአብ አስመ አነ አዐቅበከ በይነ ዘይወጽእ እምሐቁከ፤ ወዳጄ ጸጋ ዘአብ ሆይ፥ ከአብራክህ ስለሚከፈለው ቅዱስ እጠብቅሃለሁና አትፍራ” አላቸው፡፡ ከዚህ በኋላ በሦስተኛው ቀን አውጥቶ ቤተ ክርስቲያን አድርሷቸዋል፡፡

በሌላ በኩል በሞቶሎሚ ወታደሮች የተማረኩት እግዚእ ሐረያ ለንጉሡ ሚስት ሊያደርጓቸው፣ ከቤተ መንግሥቱ አገቧቸው፡፡ ቅድስት እግዚእ ሐረያ ግን “ጌታዬ ፈጣሪዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ስንፍናዬን ለምን ተመለከትክ፡፡ በንጹሕ ሆኖ የሚያገለግል ባሪያህ ጸጋ ዘአብን ለምን አላሰብከውም አንተን ለሚክዱ ኃጥአን ለሚሆኑ ጠላቶች አሳልፈህ ለምን ሰጠኸኝ ሕግህን ሥርዓትህን ከማያውቅ ከሚያጸይፍ ባሪያ ልጅ ትሰጠኝ ዘንድ ወደድክን? ከዚያም ከንጹሕ አገልጋይህም ቢሆን አንተን ደስ የማያሰኝ ልጅ ካለሆነ ማኅፀኔን ዝጋው እልሃለሁ፡፡ አቤቱ የትድግና ባለቤት ዛሬ በእኔ ላይ ትድግናህን ግለጽ” በማለት ያመለክቱ ነበር፡፡ ጠባቂ መልአካቸው፡- ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ተገልጦ ከሠራዊት ሞቶሎሚ በመንጠቅ በክንፉ ታቅፎ ከዳሞት ዞረሬ በሦስት ሰዓት አደረሳቸው፡፡ በመጋቢት ሃያ ሁለት ቀን ጸጋ ዘአብ ከቤተ መቅደስ ገብተው ሲያጥኑና ስለ እግዚእ ሐረያ ሲለምኑ፣ መልአኩ ቅዱስ ሚካኤል ከቤተ መቅደስ አግብቶ ከዚያ ትቷቸው ወደ ሰማይ ዐረገ፡፡ ገድለ ተክለሃይማኖት ምዕ.12

በዚህ ሁኔታ በእግዚአብሔር ቸርነት፣ በመልአኩ ቅዱስ ሚካኤል ተራዳኢነት ደግም የተገናኙት ሁለቱ ቅዱሳን /ጸጋ ዘአብና እግዚእ ሐረያ/ መጋቢት ሃያ አራት ቀን ከአብራካቸው የሚከፈለውን ጻድቁ ተክለሃይማኖትን ፀነሱ፡፡ እነሆም ታኅሣሥ 24 ቀን ቅዱስ አባታችን ተወለዱ፡፡

“ገድለ ተክለሃይማኖት” የተባለው መጽሐፍ አባታችን ተክለሃይማኖት በተፀነሱበት መጋቢት 24 ቀን ለእናትና አባታቸው እግዚአብሔር ራእይ እንዳሳያቸው ይገልፃል፡፡ ቅድስት እግዚእ ሐረያ ያዩት ራእይ “የብርሃን ምሰሶ ከቤታቸው ውስጥ ቁሞ የሞሶሶው ራስ ከሰማይ ደርሶ በዓለም ያሉ ሕዝብ ሁሉ ነገሥታቱም ጳጳሳቱም በዙሪያው ቁመው እኩሌቶቹም ይሰግዱለታል፤ እኩሌቱቹም እሱን ጥግ አድርገው ይቀመጣሉ፡፡ በሱም ላይ ብዙ አዕዋፍ ተቀምጠውበታል፡፡እኩሌቶቹ ነጫጮች፣ እኩሌቶቹም ቀያዮች፣ እኩሌቶቹ አመድ አመድ ይመስላሉ፡፡ ዝጉርጉርም ናቸው፡፡ በሌላ በኩል ካህኑ ጸጋ ዘአብ ደግሞ በዚሁ ሌሊት ስላዩት ሕልም ለእግዚእ ሐረያ ሲነግሩ እንዲህ ብለዋል፡- “ከምንተኛበት አጎበር ሥር ፀሐይ ሲወጣ፥ስፍር ቁጥር የሌላቸው ብሩሃን ከዋክብት በክንፉ ላይ ተቀምጠው ለዓለሙ ሁሉ ሲያበሩ፣ ከብርሃኑም ብዛት የተነሣ ሀገሩ ሁሉ አበራ፡፡ ይህን ራእይ ዐይቼ ደንግጬ አለቀስኩ”

ከዚህ በኋላ መልአኩ ቅዱስ ሚካኤል የሁለቱንም ህልም ይተረጉሙላቸው ዘንድ ከእግዚአብሔር ተልኳል፡፡ በትርጓሜውም፡- “ከጸጋ ዘአብ ቤት ሲወጣ የታየው ፀሐይ ከአብራኩ የሚከፈለው ልጁ ተክለ ሃይማኖት ነው፡፡ በብርሃኑ ከምእመናን ላይ የኃጢአትን ጨለማ የሚያርቅ ይሆናል፤ በክንፉም ላይ ታዝለው፥የታዩት ከዋክብት በመንፈስ ቅዱስ በእርሱ ትምህርት ይወለዱ ዘንድ ያላቸው ልጆቹ ናቸው፡፡ የእግዚእ ሐረያ ሕልም ትርጉሙ እንዲህ ነው በቤታቸው የብርሃን ምሶሶ ቁሞ ራሱ ከሰማይ ደርሶ ያያቸው ልጅህ ነው፡፡ ነገሥታቱ ጳጳሳቱ ሲገዙለት ያየችውም በእውነት ነገሥታቱ ይሰግዱለታል፡፡ አሕዛብም ይገዙለታል፡፡ ለሁሉም መጠጊያ ይሆናል፡፡ ከነገሥታቱ በላይ ሆኖ ይኖራል፡፡ ተአምራቱ ከዛፍ ፍሬ ይበዛል ሥፍር ቁጥር የለውም፡፡ እንደሣዕረ ምድር ጸንቶ ይኖራል፡፡ ስሙም ለዘለዓለም ሲመሰገን ይኖራል፡፡ ሰማይ ከምድር በላይ እንደሆነ የሱም ስም አጠራሩ እንደሱ ካሉ ከቅዱሳን ምእመናን በላይ ሆኖ ይኖራል፡፡ የሕልማችሁ ትርጓሜ ይህ ነው፡፡” በማለት የሕልሙን ፍች አስታውቋቸዋል፡፡

በሚያስደንቅ ልዩ ልዩ ተአምራት በቅዱስ ሚካኤል ጥበቃና በእግዚአብሔር ቸርነት ከብዙ መከራ ተጠብቀው የኖሩት ሁለቱ ቅዱሳን ባልና ሚስት /ካህኑ ጸጋ ዘአብና ቅድስት እግዚእ ሐረያ/ ታኅሣሥ 24 ቀን ፃድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖትን ወለዱ፡፡

ከሠተ አፉሁ
ታኅሣሥ 26 ቀን /በተወለዱ ሦስተኛው ቀን/ በዕለተ ሰንበት ከጧቱ ሦስት ሰዓት ላይ እጆቻቸውን አንሥተው ወደ ሰማይ እየተመለከከቱ “አሐዱ አብ ቅዱስ አሐዱ ወልድ ቅዱስ አሐዱ ውእቱ መንፈስ ቅዱስ፤ ማለትም፦ ከወልድ ከመንፈስ ቅዱስ ጋራ በባሕርይ በሕልውና አንድ የሚሆን አብ በአካል በስም ልዩ ነው፣ ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ ጋራ በባሕርይ በህልውና አንድ የሚሆን ወልድ በአካል በስም ልዩ ነው፣ በህልውና አንድ የሚሆን መንፈስ ቅዱስ በአካል በስም ልዩ ነው” በማለት ሰማያዊያን  መላእክት ምድራውያን ጻድቃን ፈጣሪን በሚያመሰግኑበት ሥርዓት ሆነው አመሰገኑ፡፡ እናትየው እግዚእ ሐረያ ግን ይህንን በልባቸው እያደነቁ “ልጄ ፍሥሐ ጽዮን ምን ትላለህ ይህ ቃል የአባትህ ሥራ ነው፡፡ ላንተ ግን የሚገባህ ጡት መጥባት ነው” በማለት ተናገሩ፡፡ ጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ግን ክቡር ዳዊት “እም አፈ ደቂቅ ወሕፃናት አስትዳሎከ ስብሐት፡፡ በእንተ ጸላዒ ከመ ትንሥቶ ለጸላኢ ወለገፋዒ፤ ከሕፃናትና ከሚጠቡ ልጆች አፍ ምስጋናን አዘጋጀህ ስለ ጠላትህ ጠላትንና ቂመኛን ለማጥፋት” በማለት የተናገረው ቃል ተፈጽሞላቸዋል፡፡ መዝ.8፥2

“በመወለዱም ብዙዎች ደስ ይላቸዋል” ተብሎ በመጋቢ ሐዲስ በቅዱስ ገብርኤል የተነገረለት ዮሐንስ መጥምቅ /ሉቃ.1፥14/ ከእናት አባቱ አልፎ ብዙዎችን ከመድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያገናኘ የደስታ ምንጭ የሆነ ነቢይም ሐዋርያም ነው፡፡ በጻድቁ አቡነ ተክለሃይማኖት መወለድም፣ ለጊዜው ልጅ ባለማግኘት ለብዙ ዓመታት ሲያዝኑ ለነበሩ ወላጆቻቸው ታላቅ የምሥራችና ደስታ ሆኗል፡፡በፍጻሜው ግን ፈጣሪያቸውን ባለማወቅ በአጋንንት አገዛዝ ሥር ወድቀው የነበሩ በብዙ መቶ ሺህ የሚቆጠሩ ሰዎች በጸሎታቸው ኀይልና ግሩም በሆነው ትምህርታቸው ብርሃን ኢየሱስ ክርስቶስን ከባሕርይ አባቱ ከእግዚአብሔር አብና፣ ከባሕርይ ሕይወቱ መንፈስ ቅዱስ ጋር በአንድነት አውቀው ተረድተው ለስሙ እንዲገዙ አድርገዋል፡፡

ነቢዩ ኤርሚያስን ፈጣሪያችን ልዑል እግዚአብሔር ከእናቱ ሆድ ጀምሮ ለቅድስና ለክብር በነቢይነት እንደጠራው በመጻሕፋችን ተገልጦአል፡፡ /ኤር.1፥5/ ጻድቁ አቡነ ተክለሃይማኖትም ለኢትዮጵያ ሰዎች ሐዋርያ ሆነው ያገለግሉ ዘንድ በባለቤቱ በመድኀኔዓለም በኢየሱስ ክርስቶስ አንደበት “እስመ ረሰይኩከ ሐዲስ ሐዋርያ፤ አዲስ ሐዋርያ አድርጌ ሾሜሃለሁ” ተብሎ የተነገረላቸው ናቸው፡፡ በዚህም በጌታችን ቃል “በእኔ የሚያምን እኔ የምሠራውን ሥራ እርሱም ይሠራል ከዚያም የሚበልጥ ይሠራል” /ዮሐ.14፥12/ ተብሎ በተነገረው ቃል መሠረት፤ በሰው ሰውኛ ሊደረጉ የማይችሉ ታላላቅ ተአምራትን በመፈጸም ኢ-አማንያንን ወደ ሃይማኖት መልሰዋል፡፡ ተጋድሏቸውን የመዘገበው መጽሐፍ /ገድለ ተክለ ሃይማኖት/ እንደተመዘገበው በዛፍ ላይ አድሮ ሲያሰግዳቸውና ሲያስመልካቸው የነበረ ጋኔኑን አዋርደው እርሱን ከኢትዮጵያ ምድር አርቀው በአምልኮተ ባዕድ የነበሩ ሰዎችን ወደ ቤተ ክርስቲያን ኅብረት ቀላቅለዋል፡፡

ባለብዙ ገድል ጻድቁ ተክለ ሃይማኖት “ዳግማዊ ዮሐንስ” የሚል ስያሜ የተሰጣቸው ሐዋርያ ናቸው፡፡ ዮሐንስ መጥምቁ በተፀነሰ ጊዜ የአባቱን አንደበት የዘጋ፣ ሲወለድ ደግሞ የአባቱን አንደበት ዳግመኛ የከፈተ ነው፡፡ (ሉቃ.1፥62-66) መምህር ወመገስጽ ዘኢያደሉ ለገድ የተባለለት፥ ዮሐንስ መጥምቁ ንጉሥ ሔሮድስን ሳይፈራና ሳያፍር የገሰጸ እንደሆነ ሁሉ፤ አባታችን ተክለ ሃይማኖትም  እንደ ሞቶሎሚ ያሉ ጣዖት አምላኪና አስመላኪ ነገሥታትና ኀያላንን ሳይፈራ የተጠራለትን አገልግሎት በጽኑ መታመን የፈጸመ ነው፡፡

ፈጣሪያችን ከጻድቁ አባታችን ከተክለሃይማኖት በረከት ረድኤት ያሳትፈን፡፡ አሜን

1 አስተያየት:

  1. የመድኃኒት ንግድ ሥራዬን ለማስፋፋት በተጠቀምኩበት ብድር ለመርዳት ሚስተር ቤንጃን ከሚያስፈልጓቸው በላይ አልፈዋል ፡፡
    እነሱ ለመስራት ወዳጃዊ ፣ ባለሙያ እና ፍጹም ዕንቁዎች ነበሩ ፡፡ እኔ ለማነጋገር ብድር የሚፈልግን ማንኛውንም ሰው እመክራለሁ ፡፡ Lfdsloans@outlook.com.WhatsApp ... +19893943740.

    ምላሽ ይስጡሰርዝ

                                   በአውሮጳ   የካህናት አንድነት ማኅበር ሊቋቋም መሆኑ ታወቀ በ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከመላዋ አውሮጳ   የተውጣጡ ካህናት፡” የ...