2015 ጃንዋሪ 27, ማክሰኞ

እመቤቴ ማርያም ሆይ፤ ምጡቅና ሩቅ ወደሚሆን የደስታ ቦታ ላረገ ሥጋሽ ሰላምታ ይገባል ይኸውም ኅብሩ ሊመረምሩት በማይቻል ዕንቊ የታነፀ ሕንፃ ይገኝበታል፡፡ መልክአ ማርያም





በዲያቆን ንጋቱ አበበ

 ቅዱሳን ሐዋርያት፤ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከእነርሱ በመለየቷ ፈጽመው ያዝኑ ነበር። ከእለታት በአንዱ ቀን ጌታችን መድሃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለቅዱሳን ሐዋርያቱ ተገለጠላቸውና እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን እንደሚያዩ ተስፋ ሰጣቸው። በዚያን ጊዜ ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌልን እየሰበከ፤ እያስተማረ፤ ሕዝበ ክርስቲያንን እያጽናና እስያ በምትባል ሃገር ነበር። ከዚያም በመንፈስ ቅዱስ ተነጥቆ፤ ተድላና ደስታ ከሰፈነባት ቦታ ወደ ገነት ሄደ። ጌታችን መድሃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን የ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሥጋዋ ካለበት ከዕፀ ሕይወት ሥር ተቀምጦ አየው። የንጽሕት አናቱንም ሥጋ ታወጣ ዘንድ ምድርን እንዲጠሯት ሰባቱን የመላእክት አለቆች አዘዛቸው። ቅድሳን መላእክቱም
እንደታዘዙት አደረጉ። ያን ጊዜም ከዕፀ ሕይወት በታች ካለ መቃብር የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሥጋ ወጣ። ጌታችንም

እንዲህ እያለ አረጋጋት። የተወደድሽ የወለድሽኝ እናቴ ሆይ ዘለዓለማዊ ወደ ሆነ መንግስተ ሰማያት አሳርግሽ ዘንድ ነይ። ያን ጊዜ በገነት ያሉ ዕፅዋት በሙሉ አዘነበሉ ሰገዱ። ቅዱሳን መላእክትም፤ ጻድቃን ሰማዕታትም እየሰገዱላትና ፈጽሞ አያመሰገኗት እያወደሷት በእልልታ ወደ ሰማይ አሳረጓት። ቅዱስ ዮሐንስም ከእርሷ በረከትን ተቀብሎ ሰግዶላት ተመልሶ ከሰማይ ወረደ። ቅዱሳን ሐዋርያትም ተሰብስበው ሳለ፤ ስለ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም እረፍት ፈጽመው እያዘኑ እየተከዙ ሳለ አገኛቸው። እርሱም እንዳየና እንደሰማ፤ ሥጋዋንም በታላቅ ክብር በምስጋና እንደ አሳረጓት ነገራቸው። ሐዋርያትም በሰሙ ጊዜ ቅዱስ ዮሐንስም አንዳየና እንደሰማ ባለማየታቸውና ባለመስማታቸው እጅግ አዘኑ። ፈጽመው እያዘኑ ሳሉ ጌታችን መድሃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተገለጠላቸውና ሰላም ለእናንተ ይሁን አላቸው። ሥለ እናቴ ማርያም ሥጋ ለምን አብዝታችሁ ታዝናላችሁ? እነሆ እርሷን በሥጋ ላሳያችሁ ልባችሁም ደስ ሊለው ይገባል አላቸው። ይህንንም ብሎ ከእርሳቸው ዘንድ ወደ ሰማያት አረገ። ቅዱሳን ሐዋርያትም አመት ሙሉ ቆዩ። የነሐሴም ወር በባተ ቀን ለሐዋርያት፤ ቅዱስ ዮሐንስ እንዲህ አላቸው። አምላክን የወለደች የእመቤታችንን ሥጋዋን ለማየት የተዘጋጀን አድርጎ ያሳየን ዘንድ ኑ ይህን ሁለት ሱባኤ በመጾም የክብር ባለቤት ጌታችንን ኢየሱስ ክርስቶስን እንለምነው። በልጇ በወዳጇ ቀኝ ተቀምጣ አይተን በሷ ደስ እንዲለን። በዚያን ጊዜም ቅዱስ ዮሐንስ እንዳላቸው ቅዱሳን ሐዋርያት ከነሐሴ ወር መጀመሪያ እስከ 16ተኛው ቀን ድረስ በጾም በጸሎት ሱባኤ ያዙ። ሱባኤ በያዙ በአስራ ስድስተኛው ቀንም ጌታችን መድሃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሁሉንም ቅዱሳን ሐዋርያት ወደ ሰማይ አወጣቸው። በታላቅ ክብር በተወደደ ልጇ ተቀምጣ፤ ከሥጋዋ ተዋሕዳ፤ ተነስታ እመቤታችንን አዩዋት። እጆቿንም ዘርግታ ቅዱሳን ሐዋርያትን ባረከቻቸው። እነርሱም ፈጽመው ተደሰቱ። ጌታችንም በከበረ ሥጋውና ደሙ ላይ ሠራዒ ሆነ። ቅዱስ እስጢፋኖስም አዘጋጀ። ቅዱስ ዮሐንስም በመፍራት ቁሙ አለ። ሁሉም ቅዱሳን ሐዋርያት በመሰዊያው ዙርያ ቆሙ። በዚያን ጊዜ ከቶ እንደርሱ ሆኖ የማያውቅ ታላቅ ደስታ ሆነ። ጌታችንም የቅዳሴውን ሥርዓት በፈጸመ ጊዜ ሥጋውንና ደሙን አቀበላቸው። ከዚያም በሱራፌልና በኪሩቤል ሠረገላ ተቀምጣ በምታርግ ጊዜ ጌታችን መድሃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እናቱ እመቤታችን ማርያምን እንዲህ ብሎ ተናገራት። በዚህች ቀን የሆነ የእርገትሽን መታሰቢያ በዓለም ውስጥ እንዲሰብኩ ልጆችስ ቅዱሳን ሐዋርያትን እዘዣቸው። መታሰቢያሽን የሚያደርግ ሁሉ ተጠብቆም በዚህች ቀን ቅዱስ ቁርባንን የሚቀበለውን ኃጢአቱን እደመስስለታለሁ። የእሳትን ሥቃይ ከቶ አያያትም። መታሰቢያሽን ለሚያደርግ ሁሉ፤ በዚህች ቀን ለድኆች በስምሽ ለሚመጸውት በቸርነቴ እጎበኘዋለሁ ብሎ ቃል ኪዳን ገባ። እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምም ልጇን ወዳጇን ጌታችንን እንዲህ አለችው። ልጄ ሆይ እነሆ በአይኖቻቸው አዩ፤ በጀሮቻቸውም ሰሙ፤ በእጆቻቸውም ዳሰሱ ሌሎች ታላላቅ ድንቅ ተአምራትንና ሥራዎችን አዩ ብላ ከነገረችው በኋላ ጌታችን ሰላምታ ሰጥቷቸው በታላቅ ደስታ ወደ ደብረ ዘይት ተመለሱ።
የተወደዳችሁ የእግዚአብሔር ልጆች ምዕመናን ሆይ የፈጣሪን እናት የ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን በፍጹም ደስታና በመልካም ምግባር መታሰቢያዋን እናደርግ ዘንድ ይገባናል እርሷ ስለ እኛ ወደ ተወደደ ልጇ ሁልጊዜ ትማልዳለችና።
ለልዑል እግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይሁን
በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት ይማረን። በረከቷ፤ ፍቅሯ፤ ጣዕሟ በእኛ በልጆቿ ላይ አድሮ ይኑር ለዘለዓለሙ አሜን።

1 አስተያየት:

  1. የመድኃኒት ንግድ ሥራዬን ለማስፋፋት በተጠቀምኩበት ብድር ለመርዳት ሚስተር ቤንጃን ከሚያስፈልጓቸው በላይ አልፈዋል ፡፡
    እነሱ ለመስራት ወዳጃዊ ፣ ባለሙያ እና ፍጹም ዕንቁዎች ነበሩ ፡፡ እኔ ለማነጋገር ብድር የሚፈልግን ማንኛውንም ሰው እመክራለሁ ፡፡ Lfdsloans@outlook.com.WhatsApp ... +19893943740.

    ምላሽ ይስጡሰርዝ

                                   በአውሮጳ   የካህናት አንድነት ማኅበር ሊቋቋም መሆኑ ታወቀ በ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከመላዋ አውሮጳ   የተውጣጡ ካህናት፡” የ...