2015 ኖቬምበር 2, ሰኞ

ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ: በአ/አበባ ሀ/ስብከት በቅዱስ ሲኖዶስ የተመደበቡትን ሓላፊነት እንዳይወጡ መደረጋቸውን ተናገሩ፤“ሥልጣንን አላግባብ በመጠቀም ዐቢይ የሕግ ግድፈት ተፈጽሟል


?
ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ፡-
  • ከቅዱስ ፓትርያርኩም ኾነ ከጠቅላይ ጽ/ቤቱ ጋር በመልካም የሥራ ግንኙነት ላይ ነበርኩ
  • የአ/አበባ ሀ/ስብከትን ኹለት ሥራ አስኪያጆች የመለመለውና ያቀረበው አካል አይታወቅም
  • ሒሳቡን እንዲያንቀሳቅሱ ሌላ ፈራሚ ሊቀ ጳጳስ የተመደቡበት ኹኔታ አሳዛኝ ክሥተት ነው
  • በረዳት ሊቀ ጳጳስነት የመደበኝ ምልዓተ ጉባኤው፣ ለቤተ ክርስቲያን የሚበጅ መፍትሔ ይስጠኝ
በምልአተ ጉባኤው ስብሰባ፡-
  • ልዩ ደንብና መመሪያ ባልወጣበት የፓትርያርኩ ልዩ ሀ/ስብከት መኾኑ ክፍተት ፈጥሯል
  • የፓትርያርኩ፣ የረዳት ሊቀ ጳጳሱና የሥራ አስኪያጁ ተግባርና ሓላፊነት መታወቅ አለበት
  • በሚሻሻለው ቃለ ዐዋዲ የሦስቱ ሓላፊዎች ሥልጣንና ተግባር ተካቶ እንዲቀርብ ተወስኗል
  • ፓትርያርኩ ያለረዳት ሊቀ ጳጳሱ ምርጫ ሥራ አስኪያጆችን በመሾም የሕግ ግድፈትና ጣልቃ ገብነት የፈጸሙበትን አካሔድ በመደገፍ “ሕመም ቢኖርብኝም የሥራ ፍላጎት አለኝ” በሚል በአዲስ አበባ ለመመደብ የጠየቁት ሊቀ ጳጳስ ክፉኛ ትዝብት ላይ ወድቀዋል
*            *            *
ጥቅምት 15 ቀን 2008 ዓ.ም.
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን
ለቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ
አዲስ አበባ
ጉዳዩ፡- በቅዱስ ሲኖዶስ በተሰጠኝ የሥራ ሓላፊነት ላይ ከሕገ ቤተ ክርስቲያኑና ከቃለ ዐዋዲው ውጭ በደል በመፈጸሙ፤ የተፈጸመውን የሥራና የሕግ ግድፈት በቅዱስ ሲኖዶሱ ለማሳረምና ትክክለኛ ፍትሕ እንዲሰጠኝ የቀረበ አቤቱታ ነው
ብፁዕ ወቅዱስ አባታችን፤ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት አባቶቼ፤ እንደሚታወቀው ኹሉ በጥቅምት 2007 ዓ.ም. በመንፈስ ቅዱስ መሪነት እና የበላይነት በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ለአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በቤተ ክርስቲያኗ ሕግ መሠረት የቅዱስ ፓትርያርኩ ረዳት ሊቀ ጳጳስ በመኾን መመደቤ ይታወቃል፡፡
እኔም በዚህ በመንፈስ ቅዱስ በሚመራው ታላቅ ጉባኤ እና በአባቶቼ የተሰጠኝን ሓላፊነትና አደራ ከተመደብኩበት ጊዜ አንሥቶ አቅሜ በፈቀደ መልኩ ያለውን ነባራዊ ኹኔታ በማገናዘብ ከቅዱስ ፓትርያርኩ ጋር በመመካከር የጠቅላይ ቤተ ክህነቱንም የሥራና የደረጃ መዋቅርን በመጠበቅ እያገለገልኩ እገኝ ነበር፤ ለዚህም እንደ ማሳያ፡-
ሀ/በሀገረ ስብከቱ የባለጉዳዮች መስተንግዶ ሥርዐት ዘመናዊና ቀልጣፋ እንዲሁም ተጠያቂነት ያለው እንዲኾን በማድረግ የተለያዩ አደረጃጀቶችን ሊጠቅም በሚችል መልኩ በማውጣት፤
ለ/የንብረትና የገንዘብ አጠባበቅ ኹኔታ በመረጃ የተደራጀ እና ዘመናዊ አሠራር እንዲኖረው በማድረግ፤
ሐ/በመንግሥት በኩል ቤተ ክርስቲያኗ ያላትን መብትና ጥቅም በመገንዘብ ከቀረጥ ነጻ በኾነ መንገድ ለቅዱስ ፓትርያርኩ እና ለሀገረ ስብከቱ የትራንስፖርት መገልገያ የሚውሉ መኪናዎች እንዲገቡ ጥረት በማድረግ፤
መ/ሀገረ ስብከቱ የሚያከናውናቸው ሥራዎች በአጠቃላይ በተጠና ዕቅድ እንዲሠራ፤ የየክፍሎቹ ሓላፊዎች በሚለካና ሊደረስበት በሚችል መልኩ ዕቅድ እንዲዘጋጅና የቀረበው ዕቅድም በአስተዳደር ጉባኤው ተገምግሞ ሥራ ላይ እንዲውል መመሪያ በመስጠት ስንሠራ ቆይተናል፡፡
ከላይ ለማሳያነት የጠቀስኋቸው ተግባራት ብዙ ጠለቅ ያለ የአፈጻጸም ሒደቶች ቢኖሯቸውም አቅም በፈቀደ መልኩ ስንቀሳቀስ ቆይቼ ነበር፡፡
ኾኖም ከቅዱስ ፓትርያርኩም ኾነ ከጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ጋር በመልካም የሥራ ግንኙነት፣ በቤተ ክርስቲያኗ ሕግና መመሪያ መሠረት አባቶቼ የሰጣችኹኝን የሥራ ሓላፊነት በመወጣት ላይ ነበርኩ፡፡
ይኹንና ዐቢይ የሕግ ግድፈት በመፈጸሙ ምክንያትና ሥልጣንን አለአግባብ በመጠቀም ጣልቃ ገብነት ሥራዬን በሓላፊነት እንዳላከናውን ተደርጌአለኹ፡፡ ከዕንቅፋቶቹና ከተፈጸሙት የሕግ ስሕተቶችም መካከል፤
1/ በጥቅምት ወር 2007 ዓ.ም. በቅዱስ ሲኖዶስ ጸድቆ በወጣው ሕገ ቤተ ክርስቲያን አንቀጽ 50፣ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ሀገረ ስብከት ነው፤ ካለ በኋላ በንኡስ ቁጥር ሦስት፣ ሀገረ ስብከቱ የሚገኘው የሀገሪቱ ርእሰ ከተማ ላይ እንደ መኾኑ መጠን ከሌሎች አህጉረ ስብከት የሚለይባቸው ልዩ ኹኔታዎች ስላሉ እኒኽን ኹኔታዎች ከግምት ያስገባ ለየት ያለ አደረጃጀት በቃለ ዐዋዲው እንዲኖረው እንደሚደረግ ይገልጻል፡፡
በዚህ መሠረት ልዩ መመሪያ ባልወጣበት ኹኔታ አንቀጹን በሌላ መንገድ በመተርጎምና ምክንያቱን በግልጽ ባላወቅሁት መንገድ ሕገ ቤተ ክርስቲያን አንቀጽ 53 ንኡስ ቁጥር 8ን በመተላለፍ፤
1.1) ሊቀ ጳጳሱ ለሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ መልምለው ለቅዱስ ፓትርያርኩ ሳያቀርቡና በሕጉም መሠረት የጋራ ስምምነት ሳይኖረን፤
1.2) በመቀጠልም በሕጉ መሠረት የረዳት ሊቀ ጳጳሱንና የቅዱስ ፓትርያርኩን ይኹንታ መሠረት አድርጎ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ማጽደቅ ሲገባው ይህ መሠረታዊ ሒደት ባልተፈጸመበት ኹኔታ፤
1.3) መልማዩና አቅራቢው በውል ማን እንደኾነ ባልታወቀበትና ሕግ በማይፈቅደው መልኩ በፓትርያርኩ ቀጥተኛ የሹመት ደብዳቤ ሥራ አስኪያጅ እና ምክትል ሥራ አስኪያጅ ለሀገረ ስብከቱ በመመደቡ ምክንያት ሀገረ ስብከቱ ከፍተኛ ቀውስ ውስጥ ገባ፡፡
2. እኒህን ዋነኛ የሕግ ግድፈቶች በመዘርዘር ጉዳዩ በቅዱስ ፓትርያርኩ እንዲታረም በመጀመሪያ በ11/07/2007 ዓ/ም በመቀጠልም በ16/07/2007 ዓ/ም በተጻፈ ደብዳቤ ጠይቄ ነበር፤ ነገር ግን ምላሽ አልተሰጠኝም፡፡ በተጨማሪም ጉዳዩ በቋሚ ሲኖዶስ ትኩረት ተሰጥቶት እንዲታረም በ17/7/2007 ዓ/ም አቅርቤ ነበር፡፡
3. ያለሊቀ ጳጳሱ አቅራቢነትና መልማይነት፣ ያለጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ጽ/ቤት ዕውቅናና አጽዳቂነት ከሕግ ውጭ በቀጥታ በቅዱስ ፓትርያርኩ ለሀገረ ስብከቱ የተሾሙት ሥራ አስኪያጅ፣ የቃለ ዐዋዲውን አንቀጽ 45 ንኡስ ቁጥር 7ን በመተላለፍ፣ አሳማኝ እና ምክንያታዊ ባልኾነ መንገድ በሀገረ ስብከቱ በክፍል ዋና ሓላፊነት ተመድበው የሚሠሩትን ሠራተኞች በ30/08/2007 ዓ/ም ያለሀገረ ስብከቱ ረዳት ሊቀ ጳጳስ ዕውቅናና ፈቃድ የተወሰኑትን ከደረጃ ዝቅ በማድረግ፣ የቀሩትንም እዚያው ባለው የሥራ ክፍል አዘዋወሩ፡፡
ከዋና ክፍል ሓላፊዎቹ በቀረበልኝ አቤቱታ፤ ሕጉን የጣሰና ምክንያቱ በትክክል ያልታወቀ ዝውውርና ከደረጃም ዝቅ ማድረግ በመኾኑ በተጨማሪም ሠራተኞች በተሰማሩበት የሥራ መስክ ላይ ተረጋግቶ የመሥራት መብትን የሚያሳጣ በመኾኑ ባለኝ ሥልጣንና ሓላፊነት መሠረት በ30/08/2007 ዓ/ም ዝውውሩንና ከደረጃ ዝቅ ማድረጉን አገድኩ፡፡ ይህም በሕጉ መሠረት ተጢኖ መታየትና መገምገም ሲኖርበት የቃለ ዐዋዲውን አንቀጽ 60 ቁጥር 2 ፊደል (ሰ)እና(ሸ) ያለአግባብ በመጥቀስና በመጠቀም በ4/9/2007 ዓ/ም በቅዱስ ፓትርያርኩ በተፈረመ ደብዳቤ እኔ ያስተላለፍኩት ሕጋዊ እግድ ያለአግባብ ተሻረ፡፡
4. ይህ በእንዲህ እንዳለ በ24/09/2007 ዓ/ም ከቅዱስ ፓትርያርኩ በተጻፈ ደብዳቤ በሥራ ገበታዬ ተገኝቼ ሥራዬን እንድቀጥል ደብዳቤ ደረሰኝ፡፡ እኔም በ25/09/2007 ዓ/ም ለደብዳቤው፣ በቅን ልቡና ሥራዬን እየሠራሁ መኾኑን፤ የሠራተኞችን ደመወዝ፣ የሚታወቁና አይቀሬ የኾኑትን የሀገረ ስብከቱን ዕለታዊ የሥራ ማስኬጃ ወጪዎችንም እየፈረምኩ ሥራዎች እየተከናወኑ እንደኾነ በመግለጽ ሥራዬን እንደምሠራ አሳወቅሁ፤ ነገር ግን ባልተለመደ አኳኋን ገንዘብን በሚመለከት ሌላ ሊቀ ጳጰስ እንደተመደበ ሰማኹ፤ ይህ አሳዛኝ ክሥተት ነው፡፡
ስለዚህም በረዳት ሊቀ ጳጳስነት መመደቤን በመወሰን ሥልጣኑንና ሓላፊነቱን የሰጠኝ ይህ ምልዓተ ጉባኤ እንደ መኾኑ፣ ለቤተ ክርስቲያናችን በሚበጅ አካሔድ መፍትሔ ይስጠኝ ዘንድ እጠይቃለኹ፡፡
እግዚአብሔር ኢትዮጵያን ይባርክ

2015 ኦክቶበር 29, ሐሙስ

ሰበር ዜና – አጥማቂ ነኝ ባዩ ግርማ ወንድሙ በፖሊስ ቁጥጥር ሥር ዋለ



(ኤፍ ቢ ሲ፤ አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 17 ቀን 2008 ዓ.ም.)
girma wondimu
የአዲስ አበባ ፖሊስ፣ አጥማቂ ነኝ ባዩን ግርማ ወንድሙን በቁጥጥር ሥር አዋለ።
የፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት ምንጮች፣ አጥማቂ ነኝ ባዩን ግርማ ዛሬ በፖሊስ በቁጥጥር ሥር ውሎ ምርመራ እየተደረገበት መኾኑን ተናግረዋል።
አጥማቂ ነኝ ባዩ ግርማ፣ በማጥመቅ እፈውሳለኹ በሚል በተለያዩ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያን ሕገ ወጥ ሀብት ሲያካብት እና በርካታ ምእመናንን ለተለያዩ ችግሮች ሲዳርግ ቆይቷል፡፡
ፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት ያነገጋረው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት፣ አጥማቂ ነኝ ባዩ ግርማ ዕውቅና እና ፈቃድ በይፋ የተነፈገው ሕገ ወጥ እንደኾነ አረጋግጧል።
የፋና ምንጮች፣ አጥማቂ ነኝ ባዩ ግርማ በፈውስ አገልግሎት ስም የማጭበርበር ወንጀል ሳይጠረጠር እንዳልቀረ ነው የተናገሩት።

2015 ኦክቶበር 28, ረቡዕ

ሰበር ዜና – ፈቃድ የሌላቸው የኢ.ቢ.ኤስ ፕሮግራሞች በቤተ ክርስቲያን ስም እንዳይጠቀሙ ተወሰነ፤ የ24 ሰዓት የቴሌቭዥን አገልግሎት ይጀመራል


  • የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ፈቃድ እና ዕውቅና የሌላቸው የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ አቀንቃኞቹ፣ ታዖሎጎስ እናቃለ ዐዋዲ  በምልአተ ጉባኤው ውሳኔ በስም ተለይተው ተጠቅሰዋል
  • በምልአተ ጉባኤው ውሳኔ መሠረት፣ በቋሚ ሲኖዶስ የተቋቋመው የብዙኃን መገናኛ ቦርድ ሥራውን ለመጀመር እየተንቀሳቀሰ ነው
  • በፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ኑፋቄ ላይ የቀረቡ ማስረጃዎች የበለጠ ተጠናክረው አጀንዳው በልዩ የምልአተ ጉባኤ ስብሰባ እንዲታይ ተወስኗል
synod tik2008 Edited
የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ፣ ከማእከል የተሰጠ ሕጋዊ ፈቃድ ሳይኖራቸው በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ስም፣ በኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ሰርቪስ(EBS) የቴሌቭዥን ጣቢያ“ሃይማኖታዊ ትምህርት” የሚያስተላልፉ ፕሮግራሞች፣ የቤተ ክርስቲያንን ስም እንዳይጠቀሙ ወሰነ፡፡
ምልአተ ጉባኤው በዛሬ፣ ጥቅምት 17 ቀን 2008 ዓ.ም. ስድስተኛ ቀን የቀትር በፊት ውሎው ያሳለፈው ውሳኔ ተፈጻሚ እንዲኾን፤ የፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር እና የኢ.ቢ.ኤስ ቴሌቭዥን በደብዳቤ እንዲያውቁት ይደረግ ዘንድ ትእዛዝ ሰጥቷል፡፡
በውሳኔው÷ የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ አቀንቃኞቹ፣ “ታዖሎጎስ” እና ቃለ ዐዋዲ”  በስም የተጠቀሱ ሲኾን በፕሮግራሞቹ አዘጋጅነት የሚታወቁት በተለይ የ“ታዖሎጎስ” ግንባር ቀደም ምንደኞች፣ ፕሮግራማቸው “ራሱን የቻለ የሚዲያ ተቋም” እንጂ  ከቅዱስ ሲኖዶሱ ይኹን ከጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ጋር ተቋማዊ ግንኙነት እንደሌላቸው በይፋ በሰጡት መግለጫ ማረጋገጣቸው ይታወሳል፡፡
ምልአተ ጉባኤው ከዚሁ ጋር በማያያዝ፤ በሊቃውንት ጉባኤ ሳይመረመሩ እና በማእከል ሳይፈቀዱ በግለሰቦች እየተዘጋጁ የቤተ ክርስቲያንን ስም ይዘው ስለሚወጡ የስብከት፣ የመዝሙር እና የመጻሕፍት ኅትመቶች እንዲኹም የአዳራሽ ጉባኤያት እና ስብሰባዎች ከተወያየ በኋላ ቀደም ሲል ያሳለፋቸውን ውሳኔዎች በማጽናት ተመሳሳይ ትእዛዝ መስጠቱ ታውቋል፡፡
ቅዱስ ሲኖዶሱ፣ “ስብከተ ወንጌል እና ሚዲያን በተመለከተ” በተራ ቁጥር ሦስት በያዘው አጀንዳ፤ ቤተ ክርስቲያን ማእከላዊነቱን ጠብቆ የራስዋን ድምፅ ለዓለም የምታሰማበት እና ስብከተ ወንጌልን የምታስፋፋበት የ24 ሰዓት የቴሌቭዥን አገልግሎት እንዲጀመርም ወስኗል፡፡
ለቤተ ክርስቲያን የብዙኃን መገናኛ ስርጭት የሚያስፈልገውና በስብከተ ወንጌል እና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ አስተባባሪነት ተጠንቶ የቀረበው በጀት ባለፈው ዓመት ግንቦት በምልአተ ጉባኤው የጸደቀ ሲኾን በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ የመክፈቻ ንግግር እንደተመለከተው፤ በዚኽ ዓመት በጀቱ በአፋጣኝ ሥራ ላይ እንዲውል የቀረበውን ጥያቄ በመቀበል የፋይናንስ ምንጮቹን ወስኖ ለነገ የሚያቀርብ ሦስት አባላት ያሉት የብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት(ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ፣ ብፁዕ አቡነ ሳሙኤል እና ብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ) ኮሚቴ በምልአተ ጉባኤ ተሠይሟል፡፡
ምልአተ ጉባኤው ባለፈው ዓመት ግንቦት ባጸደቀው የሚዲያዎች (የሬዲዮ እና የቴሌቭዥን አገልግሎት) ሥርጭት ደንብ መሠረት፤ በስብከተ ወንጌል እና ሐዋርያዊ ተልእኮ የበላይ ሓላፊ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ማርቆስ የሚመራ የብዙኃን መገናኛ የሥራ አመራር ቦርድ የተቋቋመ ሲኾን ተግባሩን ለመጀመር እየተንቀሳቀሰ እንዳለ ለ34ኛው የመንበረ ፓትርያርክ የሰበካ አስተዳደር አጠቃላይ ጉባኤ የቀረበው ሪፖርት ያስረዳል፡፡
በሪፖርቱ እንደተጠቀሰው፤ ቤተ ክርስቲያኒቱ ስብከተ ወንጌልን ከዐውደ ምሕረት ባሻገር በአጽናፈ ዓለም ለማስፋፋት እና ለማጠናከር ስለሚያስፈልጓት ሚዲያዎች፣ በመምሪያው አስተባባሪነት በብዙኃን መገናኛ ባለሞያዎች የተካሔደውን ጥናት መሠረት አድርጎ መተዳደርያ ደንብ፣ ኤዲቶሪያል ፖሊሲ እና የቴሌቪዥን ሥርጭት መመሪያ/ማኑዋል ተዘጋጅቷል፡፡
በተያያዘ ዜና፣ “የቤተ ክርስቲያኗን ወቅታዊ ኹኔታ በጥልቀት ማየት” በሚል ዐቢይ አጀንዳ ሥር በፊደል ተራ ቁጥር 4/መ፣ “የተሐድሶ እንቅስቃሴን በተመለከተ”፤ የተዘጋጀው ሰነድ በተጨማሪ ማስረጃዎች ተስፋፍቶ እና ተጠናክሮ ራሱን በቻለ ልዩ የምልአተ ጉባኤ ስብሰባ እንዲታይ ቅዱስ ሲኖዶሱ ወስኗል፡፡
የስብሰባው ምንጮች እንደተናገሩት፤ ከፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ግንባር ቀደም መሪዎች በሚሰጣቸው ተልእኮ እና ድጋፍ በቤተ ክርስቲያናችን የአስተዳደር እና የአገልግሎት መዋቅር ውስጥ በመስረግ የኑፋቄውን አስተሳሰብ እና ድርጊት የሚያራምዱ የ66 አካላት እና ግለሰቦች የሰነድ፣ የምስል እና የድምፅ ማስረጃዎች ከኃምሳ ገጾች ማብራሪያ ጋር ተደግፎ ተዘጋጅቷል፡፡
ከቤተ ክርስቲያናችን ዐውደ ምሕረት እና የአስተዳደር መዋቅር ባሻገር፣ የኑፋቄው ግንባር ቀደም መሪዎች እና ምንደኞቻቸው በከፍተኛ ትምህርት ተቋሞቻችን(መንፈሳዊ ኮሌጆች እና የካህናት ማሠልጠኛዎች) ውስጥ በተለያየ ሽፋን የሚያደርጉት እንቅስቃሴ ትኩረት እንዲደረግበት ምልአተ ጉባኤው ኮሚቴውን አሳስቧል፡፡
Beriyaበመካከለኛው ምሥራቅ አህጉረ ስብከት፣ ብፁዕ ሊቀ ጳጳሱ ሳያውቁት ከሥርዐተ ቤተ ክርስቲያን ውጭ በተቋቋመው የኑፋቄው መናኸርያ “ዱባይ ሚካኤል” እና “ቤርያ ቲኦሎጂካል ኢንስቲትዩት” በሚል መሪዎቹ የመሠረቱት ሕገ ወጥ ተቋም በከፍተኛ ደረጃ ያነጋገረ ሲኾን በምልአተ ጉባኤው ጥናት ተካቶ እንዲቀርብ መወሰኑ ተጠቁሟል፡፡
በተመሳሳይ ኹኔታ ጉባኤውን ያነጋገረው፣ በመንበረ ፓትርያርኩ የውጭ ጉዳይ መምሪያ በሓላፊነት የተቀመጡት መልአከ ሰላም አባ ቃለ ጽድቅ የተባሉ ግለሰብ፣ ከፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ኑፋቁ አንጻር ያላቸው ሃይማኖታዊ አቋም እና ሥነ ምግባራዊ ኹኔታ ነበር፡፡ የግለሰቡ አመጣጥ እና አመዳደብም ከፓትርያርኩ ልዩ ጸሐፊ ንቡረ እድ ኤልያስ ኣብርሃ ጋር ባላቸው የጥቅም ግንኙነት እንደኾነ መጠቆሙ ደግሞ ችግሩ ከግለሰቡም በላይ ልዩ ጽ/ቤቱ እንደ መዋቅር ያለበትን አስከፊ ደረጃና አሳሳቢነቱን ለምልአተ ጉባኤው አለብቧል፡፡ 
ከዚኽ ውስብስብነቱና ከሚያስፈልገው ጠንካራ ቅንጅት አኳያ፤ አጀንዳው ራሱን በቻለ አስቸኳይ እና ልዩ የምልአተ ጉባኤ ስብሰባ እንዲታይ ቅዱስ ሲኖዶሱ ሲወስን ጊዜው በመጪው ወርኃ ጥር ላይ ሊኾን እንደሚችል ከወዲኹ የተጠቆመ ቢኾንም በኮሚቴው ውጤታማ እንቅስቃሴ ላይ እንደሚመሠረት ነው፣ በብዙኃን የምልአተ ጉባኤው ዘንድ መግባባት የተደረሰበት፡፡
በሕገ ቤተ ክርስቲያን የቅዱስ ሲኖዶስ የስብሰባ ሥነ ሥርዐት መሠረት፤ አስቸኳይ እና ድንገተኛ ጉዳይ ሲያጋጥም ቅዱስ ፓትርያርኩ ወይም ቋሚ ሲኖዶሱ ወይም የቅዱስ ሲኖዶሱ ዋና ጸሐፊ በሚያደርጉት ጥሪ የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ሊካሔድ ይችላል፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስም በማናቸውም ስብሰባ ላይ ውሳኔዎችን ሲያሳልፍ፤ ሃይማኖትንና ቀኖና ቤተ ክርስቲያንን የሚመለከት ከኾነ በሙሉ ድምፅ ያልፋል፤ በሃይማኖት እና በቀኖና ጉዳይም ድምፀ ተዓቅቦ ማድረግም አይቻልም፡፡

 

  •  

                   by ሐራ ዘተዋሕዶ

2015 ኦክቶበር 22, ሐሙስ

የ34ኛው አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ የአቋም መግለጫ

አትም ኢሜይል
ጥቅምት 11 ቀን 2008 ዓ.ም
01 sebeka11በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የመንበረ ፓትርያርክ 34ኛው አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ከጥቅምት 8-10 ቀን 2008 ዓ.ም ሲካሄድ ቆይቶ ባለ 23 ነጥብ የጋራ የአቋም መግለጫ አውጥቷል፡፡

በቅዱስ ፓትርያርኩ ቃለ በረከት ጥቅምት 8 ቀን 2008 ዓ.ም የተጀመረው ጉባኤ ለሦስት ተከታታይ ቀናት የብፁዕ አቡነ ማቴዎስ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ የወላይታ ኮንታና ዳውሮ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የ2007 ዓ.ም አጠቃላይ ሪፖርት እና የየአህጉረ ስብከት ሪፖርቶች በቅደም ተከተል ቀርበዋል፡፡ በቀረቡት ሪፖርቶች መሠረትም ቃለ ጉባኤ ተነቦ በማጽደቅ ባለ 23 ነጥቦች የጋራ የአቋም መግለጫ አውጥቷል፡፡

የአቋም መግለጫውን እንደሚከተለው እናቀርባለን፡-
1.ቅዱስ ፓትርያርኩ ለ34ኛው አጠቃላይ ሰበካ ጉባኤ ያስተላለፉትን ቃለ ቡራኬና አባታዊ የሥራ መመሪያ ሙሉ ለሙሉ ተቀብለን ተግባራዊ ለማድረግና የሚጠበቅብንን ለመወጣት ዝግጁ መሆናችንን ቃል እንገባለን፡፡

2.በቅዱስነታቸው ቃለ ቡራኬ ከተላለፉት መሠረታዊ መልእክቶች ውስጥ ቅዱስነታቸው ዐቢይ ጉባኤው ትኩረት ሰጥቶ እንዲወያይባቸው ያሳሰቧቸው፡-
አንደኛ፡-ምእመናንን የመጠበቅ ተልእኮ በሚገባ እየተወጣን አይደለምና ባዶ እጃችንን ከመቅረታችን በፊት ለተደራጀና ለድንበር የለሽ ስብከተ ወንጌል ብንነሣ፡፡

ሁለተኛ፡-የአስተዳደር ሥራችን ለምእመናን ሕሊና እንቅፋት እየሆነ ነውና የሃይማኖቱን መርህ አስጠብቀን አስተዳደራችን የሕግ የበላይነትን ያረጋገጠ፣ ግልጽ፤ ተአማኒና ተጠያቂነትን ያሰፈነ የምእመናንን ልብ የሚያረካ፣ ምእመናን በቤተ ክርስቲያናቸው ኩራት እንዲሰማቸው የሚያስችል አሠራር ብናረጋግጥ ተጨባጭ ለውጥ ማስመዝገብ እንችላለን በማለት የሰጡትን መመሪያ በተግባር ለመለወጥ ቃል እንገባለን፡፡

3. የቅዱስ ሲኖዶስን ሉዓላዊነት የሚጋፉ፣ ለቤተ ክርስቲያን ማእከላዊ አመራር አንታዘዝም የሚሉ፣ ቤተ ክህነት ምን አገባው፣ ሀገረ ስብከት ምን አገባው፣ ቅዱስ ሲኖዶስ ምን አገባው፣ የጠቅላይ ቤተ ክህነት አስተዳደራዊ መዋቅራዊ ምን አድርጎልናል በሚል የማደናገሪያ ስልት መዋቅርን የሚንዱ ችግሮች በከፍተኛ ፍጥነትና ብዛት በተደራጀና በተጠና ስልት በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገር በከፍተኛ ፍጥነት እያደጉ ስለሆነ ቅዱስ ሲኖዶስ ለጉዳዩ ከፍተኛ ትኩረት በመስጠት እንዲወያበትና መፍትሔ እንዲሰጠው ለዘመናት ጸንቶ የቆየውን የቤተ ክርስቲያንን መዋቅር እንዲያስጠብቅ በከፍተኛ ስሜት እንጠይቃለን፡፡

4. በሁሉም አህጉረ ስብከት የታየው የብፁዓን አባቶች ሐዋርያዊ ጉዞ እጅግ ውጤታማ፣ ለምእመናን ጥንካሬ፣ ለቤተ ክርስቲያን ከፍተኛ እድገት አስተዋጽኦ ያለው ስለሆነ ተጠናክሮ እንዲቀጥል እንጠይቃለን፣ በእኛም በኩል የሚገባንን ለማድረግ ቃል እንገባለን፡፡

5. በብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁና በማደራጃ መምሪያው የተገለጹት የሁለትዮሽ የሒሳብ አያያዝ /Double Entry/ ሥርዓት የፋይናንስ ማእከላዊነትን በማረጋገጥ፣ የአገልጋዮችን የሥራ አቅም ብልጽግና በማሳደግ ብክነትነትን በማስወገድ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያለው ስለሆነ ከብዙ ጊዜ ማሳሰቢያ በኋላ ተግባራዊ መሆኑ ጉባኤውን አስደስቷል፡፡ ይህ አሠራር በቀጣይነት በየደረጃው እስከ ታች የቤተ ክርስቲያን መዋቅር ድረስ ተግባራዊ እንዲሆን ይልቁንም አሠራሩ ዘመኑ አሁን የደረሰበት የሥልጣኔ ደረጃ መሠረት በማድረግ በኔትዎርክ ተሳስሮ፣ በሥልጠና ተደግፎ፣ ግልጽና ተጠያቂ በሆነ መንገድ ተግባራዊ እንዲሆን ወጥና ቀጥ ያለ አመራር እንዲሰጥ እየጠየቅን እኛም ለተግባራዊነቱ የድርሻችንን ለመወጣት ቃል እንገባለን፡፡

6. ተቋርጦ የነበረው የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ስምሪት መጀመሩ ጉባኤውን እጅግ ያስደሰተ ሲሆን ስምሪቱ በተጠናከረ መንገድ አስተማማኝ የሆነ የራሱ በጀት ተመድቦለት በሥልጠናና በተደራጀ ውጤት ተኮር በሆነ መንገድ እንዲቀጥል የበኩላችንን ሁሉ ለማድረግ ቃል እንገባለን፡፡

7. የታየው የገቢ እድገት ጉባኤውን እጅግ ያስደሰተ ሲሆን ከበጀት እድገቱ ጎን ለጎን በልማት ሥራዎች ለቤተ ክርስቲያን ቋሚ ንብረት ለማፍራት የቀደሙት አባቶች ሠርተው እንዳወረሱን ሁሉ ቋሚና ዘላቂ ንብረት ለቤተ ክርስቲያን ለማፍራት በልማት ለመትጋት ቃል እንገባለን፡፡

8. ብፁዓን አባቶች ባደረጉት ጥረት ምእመናንና ካህናትን በማስተባበር የሚካሔደው የልማትና ለቤተ ክርስቲያን ንብረት የማፍራት ዘላቂ ገቢ የማስገኘት ሥራ ለሚመራው አህጉረ ስብከትም ሆነ ተቋማት ሕልውና ዋስትና ለብፁዓን አባቶች አብረዋቸው ለደከሙት የሥራ ሓላፊዎች የድካማቸው መዘክሮች ስለሆኑ ንብረቶቹ በየአህጉረ ስብከቱና በዋናው መሥሪያ ቤት ባሕር መዝገብ በአግባቡ ተቆጥረውና ተመዝግበው እንዲያዙ እንጠይቃለን ለአፈጻጸሙም የበኩላችንን ለማድረግ ቃል እንገባለን፡፡

9. ስብከት ወንጌልን ለማስፋፋት፣ የቤተ ክርስቲያንን ተልእኮ በተፈለገው መጠን ለማዳረስ ብቃትና ታዛዥነት ያላቸው አገልጋዮች እጥረት ትልቅ እንቅፋት ስለሆነ የአገልጋዮችን እጥረት በተለይም በልዩ ልዩ ብሔሮችና ብሔረሰቦች ቋንቋዎች የሚያስተምሩ መምህራነ ወንጌል በጥራትና በቁጥር ለማሳደግ የበኩላችንን ለማድረግ ቃል እንገባለን፡፡

10. ስብከተ ወንጌል አገልግሎት ከዐውደ ምሕረት ባሻገር በማረሚያ ቤቶች፣ በጤና ማእከላትና በመሳሰሉት ለማዳረስ በተለይም ዘመኑ በሚፈቅደው በብዙኀን መገናኛ ወይም ሚዲያ በመታገዝ በመላው ዓለም ቤተ ክርስቲያን ድምጿን በራሷ በኩል ማእከላዊነቷን ጠብቆ ለማሰማት የሚደረገውን ጥረት ከልብ በመደገፍ ለተግባራዊነቱ የበኩላችንን ለመወጣት ቃል እንገባለን፡፡

11. ለስበከተ ወንጌል እንቅፋት የሆኑ ሕገወጥ ሰባኪያን፣ ሕገወጥ አጥማቂዎች ነን ባዮችና መዋቅር ያልጠበቁ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ክብር የሚያስነቅፉ እንቅስቃሴዎች ለመግታት እስካሁን ከተሠራው በይበልጥ ለመሥራት ቃል እንገባለን፡፡

12. በየጊዜውና በየዘመኑ ወቅቱ በሚፈቅደው መጠን መስመሩን ሳይለቅ ሲሻሻልና ሲዳብር የኖረው ቃለ ዓዋዲ አሁንም በይበልጥና በጥራት የሕግ ጸባይ በመያዝ ለሀገር ውስጥም ሆነ ለውጭ ሀገረ መንግሥታት ተቀባነት በሚያገኝ መልኩ መሻሻሉ ሁሉም የሚጠብቀው ስለሆነ ቅዱስ ሲኖዶስ ለጉዳዩ ልዩ ትኩረት በመስጠት በተለይ እስካሁን ያልተደረገው በውጭ አህጉረ ስብከት ያሉ አብያተ ክርስቲያናት ማእከል ባደረገ መልኩ ጊዜ ሳይሰጠው ተዘጋጅቶ እንዲሻሻል በአጽንኦት እየጠየቅን ለሚደረገው ሁሉ የበኩላችንን ለመወጣት ቃል እንገባለን፡፡

13. ለማሰልጠኛዎችና ለአብነት ትምህርት ቤቶች እየተሰጠ ያለው ትኩረት ከምን ጊዜውም የተሻለ ቢሆንም በተቀናጀና ማእከላዊነቱን በጠበቀ መልኩ እንዲደራጅ፣ በጀት ያልተመደበላቸው በጀት እንዲያገኙ፣ በበጎ አድራጊ ምእመናን የተሠሩ ሁሉ በማእከል እውቅና እየተሰጣቸው የቤተ ክርስቲያን ባለቤትነት እንዲያገኙ እየጠየቅን ቅዱስ ሲኖዶስ በተለይ ለአብነት ትምህርት ቤቶችና ቀመዛሙርቶቻቸው ልዩ ትኩረት እንዲሰጥ በታላቅ አክብሮት እንጠይቃለን፡፡

14. ለሰንበት ትምህርት ቤቶች አደረጃጀት የተሰጠው ትኩረት ልዩ ልዩ ሥልጠናና የሥርዓተ ትምህርት ከመዝሙር መጽሐፍ ጋር ተዘጋጅቶ መሰራጨቱ ወጣቶችን በወጥነት ለማስተማር በሃይማኖትና ሥነ ምግባር ለማሳደግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያለው መሆኑን ጉባኤው ያመነበት ሲሆን ሂደቱ ተጠናክሮ እንዲቀጥል በመምሪያው በኩል የቀረቡ ችግሮች በተለይም ከልዩ ልዩ የወጣቶችና የጎልማሶች ማኅበራት ያለው ተጽእኖ እንዲቆም፤ የወጣቶች የሰንበት ትምህርት ቤቶች ቆይታ የእድሜ ገደብ እንዲከበር በቅዱስ ሲኖዶስ መመሪያ እንዲሰጥ እንጠይቃለን፡፡

15. በቅርስ ጥበቃና ምዝገባ በተመለከተ በአንዳንድ አህጉረ ስብከት የታየው ከመንግሥት ጋር የተቀናጀ የቅርሶች ምዝገባ፣ የቅርሶች ማስመለስ፣ የሙዚየሞች ማደራጀት፣ለቅርሶች ዋስትና ቢሆንም ሁሉንም ጥረቶች ለቤተ ክርስቲያኒቱ የቅርሶቿና የታሪክ ባለቤትነት በሚያረጋግጥ መልኩ እንዲፈጸሙ ቅዱስ ሲኖዶስ አስቸኳይና ወቅታዊ መመሪያ እንዲሰጥ በታላቅ አጽንኦት እንጠይቃለን፡፡

16. ወደ መናፍቃንና ወደ ኢአማኒነት ከሚፈልሰው ምእመን ቁጥር ባልተናነሰ አስተዋጽኦ የሚያደርገው ለአገልጋዮች ዋስትናና ከለላ ማጣት ለቤተ ክርስቲያን የወደፊት ሕልውና ከፍተኛ ስጋት የሆነው የመልካም አስተዳደር እጦትና ሙስና ለመቅረፍ በሥልጠና የታገዘ ሥራ፣ ሥራና ሠራተኛን በማገናኘት ላይ ያተኮረ አስተዳደርን፣ ችግሮችን በመፍታት ብቁ አገልጋዮችን ለማፍራት ያለመ መልካም አስተዳደርን ለማስፈን ቅዱስ ሲኖዶስ ልዩ ትኩረት እንዲሰጠው እየጠየቅን እኛም ለተግባራዊነቱ የበኩላችንን ለመወጣት ቃል እንገባለን፡፡

17.በተፈጠረው የአየር ለውጥ ምክንያት በወቅቱ ለተከሰተው ድርቅ በተጎዱ አህጉረ ስብከት ለሚገኙ አድባራት፣ ገዳማትና አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ምእመናን በርካታ በመሆናቸው ቅዱስ ሲኖዶስ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመነጋገር አስቸኳይ መፍትሔ እንዲሰጠው እንጠይቃለን፡፡

18. በልማት፣ በአረጋውያን እንክብካቤ፣ ወላጆቻቸውን ያጡ ሕፃናትን በማሳደግ፣ በአካባቢ ጥበቃ፣ በማኅበራዊ አገልግሎትና ለወገን ደራሽነት አብያተ ክርስቲያናት በማሳነጽ ቋሚና ዘላቂ ልማት በማስፋፋት የሚደረገውን ጥረት ለመደገፍ ቃል እንገባለን፡፡

19. የቤተ ክርስቲያን አስተዳደር ሲኖዶሳዊ መሆኑ ይታወቃል፡፡ ይሁን እንጂ በአንዳንድ አካባቢዎች እንደ ፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ አብያተ ክርስቲያናት ከሲኖዶሳዊ መዋቅር የወጣ ቀኖናዊ ትውፊትን ያልጠበቀና ኢክርስቲያናዊ ኢኦርቶዶክሰዊ የሆነ ገለልተኛ ቅንጅት በመፍጠር ምእመናንን በሚያደናግሩ አካለት ዙሪያ ቅዱስ ሲኖዶስ አስቸኳይ መፍትሔ እንዲያስቀምጥለት ለተግባራዊነቱም የበኩላችንን ለማድረግ ቃል እንገባለን፡፡

20. የቅዱስነታቸው ሐዋርያዊ ጉዞ የቤተ ክርስቲያን ዓለም አቀፋዊነት የሚያረጋግጥ በመሆኑ በውጭ ያሉትን አህጉረ ስብከት የሚያጠናክር በመሆኑ ቀጣይነት እንዲኖረው እየጠየቅን በዚህ ረገድ ከኦርየንታል አብያተ ክርስቲያናት በተለይም ከግብፅ ኮፕት ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ጋር ያለውን ግንኙነት በሚገባ እንዲተኮርበት በታለቅ አጽንኦት እንጠይቃለን፡፡

21. በአሁኑ ጊዜ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በመላው ዓለም እየሰፋችና ከራሷ ምእመናን አልፎ የውጭ ሀገር ተወላጅ የሆኑ ምእመናንን ያፈራች በመሆኑ የውጭ ግንኙነት ሥራዋ ዓለማቀፋዊ ይዘቱን እንደጠበቀ እንዲስፋፋ ቅዱስ ሲኖዶስ ልዩ ትኩረት እንዲሰጠው እንጠይቃለን፡፡

22. በሊቢያ በረሃ ስለ ክርስትና ሃይማኖታቸው ሰማዕትነትን የተቀበሉ ወጣቶችን አስመልክቶ የተደረገው ሲኖዶሳዊና ቀኖናዊ ውሳኔ የተቀበልን ሲሆን በፍትሕ መንፈሳዊ ሰማዕታትን የሚያስቡ፣ ከሰማዕታት ዋጋ ያገኛሉ የሚለውን በመከተል የቅዱስ ሲኖዶስን ውሳኔ ተግባራዊ ለማድረግ ቃል እንገባለን፡፡

23. የእግዚአብሔርን ሕግና ትእዛዝ የተፈጥሮ ሕግን ወሰን በማለፍ በታላላቅ ሀገሮች ተጽእኖና ድጋፍ እየተስፋፋ ያለውን የግብረ ሰዶምን እንቅስቃሴ በመቃወም ቤተ ክርስቲያን ድምጿን ለዓለም ማሰማት እንዳለባት እየጠየቅን ጥያቄውን ከዚህ በፊት ላስተጋቡ ብፁዓን አባቶች ላደረጉት ጥረት ልባዊ ድጋፋችንና አጋርነታችን በመስጠት ሃይማኖታዊና ቀኖናዊ ግዴታችን ስለሆነ ምእመናንን በትምህርት ወንጌል ለማነጽ ቃል እንገባለን፡፡

2015 ኦክቶበር 19, ሰኞ

34ኛው አጠቃላይ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ መደበኛ ስብሰባ ተጀመረ


አትም ኢሜይል
01sebeka 34
ጥቅምት 8 ቀን 2008 ዓ.ም
በእንዳለ ደምስስ
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን 34ኛው አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ መደበኛ ስብሰባ ጥቅምት 8 ቀን 2008 ዓ.ም በጠቅላይ ቤተ ክህነት ስብከተ ወንጌል አዳራሽ ቅዱስ ፓትርያርኩ፣ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ የየአህጉረ ስብከቱ ሓላፊዎችና የጠቅላይ ቤተ ክህነት ልዩ ልዩ መምሪያ ሓላፊዎች በተገኙበት ተጀምሯል፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት የመክፈቻ ቃለ በረከት በማስተላለፍ ቀጥሏል፡፡

03sebaka3402sebeka34ቅዱስነታቸው ባስተላለፉት ቃለ በረከት ትናንት ቤተ ክርስቲያን ሀብተ ወልድ እና ስመ ክርስትና ሰጥታ በአባልነት የተቀበለቻቸው ልጆቿ ዛሬ እናት ቤተ ክርስቲናቸውን እየካዱ ወደሌላ ጎራ የመቀላቀሉ ጉዳይ እጅግ እየናረና የምእመናን ፍልሰት በየጊዜው እየጨመረ መሔዱ አሳሳቢ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡

06sebeka34የምእመናን ፍልሰት በተመለከትም መንስኤው ምንድነው ሲሉ ጠይቀዋል፡፡ ምእመናን ከቤተ ክርስቲያናችን እየወጡ ወደ ሌላ ካምፕ ለመግባት ለምን መረጡ? የሚያስተምራቸው ካህን አጥተው ነው? የቤተ ክርስቲያንናችን ትምህርት ሃይማኖት ክፍተት ኖሮት ነው? የቤተ ክርስቲያናችን አስተዳደር የማያረካ ሆኖ ነው? የካህን እጥረት ስላለ ነው? ወይስ ሌሎች ከእኛ ተሽለው ስለተገኙ ነው? አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤው ትኩረት ሰጥቶ ሊነጋገርበት ይገባል ብለዋል፡፡

ቅዱስነታቸው ወደፊት ትኩረት ሊሰጣቸው የሚገቡ ናቸው ያሏቸውንም እንደመፍትሔ ጠቁመዋል፡፡ ምእመናንን የመጠበቅ ተልእኮ በሚገባ እየተወጣን አይደለምና ባዶአችንን ከመቅረታችን በፊት ለተደራጀና ለድንበር የለሽ ትምህርተ ወንጌል ብንነሣ፤ የአስተዳደር ሥራችን ለምእመናን ሕሊና እንቅፋት እየሆነ ነውና የሃይማኖቱን መርህ ጠብቀን አስተዳደራችን የሕግ የበላይነት ያረጋገጠ፣ ግልጽ፣ ተአማኒና ተጠያቂነትን ያሰፈነ፣ የምእመናን ልብ የሚያረካ ተጨባጭ ለውጥ ማስመዝገብ ያስፈልጋል ሲሉ አሳስበዋል፡፡

04sebeka34ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ የወላይታ ኮንታና ዳውሮ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ባስተላለፉት መልእክትም በዚህ ባለንበት ዘመን ሰበካ ጉባኤን የማጠናከር እንዲሁም የቤተ ክርስቲያናችንን ሁለንተናዊ ተልእኮ በመወጣት እድገቷንና ልማቷን በማፋጠን ተገቢ ሥራ በተገቢው ሥፍራ ሠርተን የጥንታዊትና የታሪካዊቷን ቤተ ክርስቲያናችን ሕልውና በመጠበቅ ዛሬም ለሀገርና ለወገን የምትሰጠውን አገልግሎት ማጠናከር ይገባል ብለዋል፡፡


በ2007 ዓ.ም የተከናወኑ ዓበይት ተግባራትንም በተመለከተ አባ ኃ/ማርያም መለሰ /ዶ/ር/ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ ቤት ምክትል ሥራ አስኪያጅ ዝርዝር ሪፖርት አቅርበዋል፡፡ ባቀረቡት ሪፖርትም በ2007 በጀት ዓመት በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ የተከናወኑ ዋና ዋና ተግባራት፣ የሊቃውንት ጉባኤን፣ የሰበካ ጉባኤ ማደራጃ መምሪያን፣ የትና ሒሳብ መምሪያን፣ የገማት መምሪያን፤ የቅርስ ጥበቃና ተ መጻሕፍት ወመዘክርን፣ የሰብከተ ወንጌልና የሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያን፣ የቤቶችና ሕንፃዎች አስተዳደርና የልማት ድርጅትን፣ የማኅበረ ቅዱሳንን፣ . . . ወዘተ ሪፖርት አቅርበዋል፡፡05sebaka34
ከሰዓት በኋላ ጠቅላላ የሰበካ ጉባኤው ከየአህጉረ ስብከት የቀረቡ ሪፖርቶችን በማድመጥ ላይ ይገኛል፡፡

የአጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤው እስከ ጥቅምት 14 ቀን 2008 ዓ.ም ይቀጥላል፡፡

2015 ኦክቶበር 16, ዓርብ

ለዘብተኛነት/ሊበራሊዝም/፡የክርስትና ዘመናዊው ጠላት - ክፍል 2

ባለፈው ጽሑፍ የሊበራል ክርስትናን ምንነት እና ጠባያት ተመልክተናል፡፡ በዚህ ቀጣይ ጽሑፍ ደግሞ ያመጣውን መዘዝ እና መፍትሔውን እናያለን፡፡ መልካም ንባብ፡፡

ሊበራል ክርስትና ምን አመጣ?

ሰዎች እግዚአብሔርን እንዳይፈሩ አደረገ

ቀዳሚሃ ለጥበብ ፈሪሃ እግዚአብሔር የተባለው ተዘንግቶ ክርስቲያን ነን የሚሉ ሰዎች በእግዚአብሔር ላይ የሚያሾፉ ፊልሞችን እንዲሠሩ፣ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ሰይጣን እንኳን የማይለውን የዳቪንቺን ኮድን የመሰሉ አስተሳሰቦችን እንዲያራምዱ፣ በስቅለት ቅርጽ የፋሲካ ካንዲ እንዲሠሩ፣ ወዘተ አደረጋቸው፡፡ በየዘፈኖቻቸው ስመ እግዚአብሔርን እያነሡ እንዲቀልዱ አበረታታቸው፡፡ የጌታችን የስቅለት ሥዕል ከየቦታው እንዲነሣ ፣ አሠርቱ ትእዛዛት ከአሜሪካ ፍርድ ቤት በር እንዲነሣ አስደረጉ፡፡

ዛሬ ዛሬ ቅዱሳንን፣ ቤተ ክርስቲያንን እና የቤተ ክርስቲያን አካላትን እያነሡ መቀለድ እና ማቃለል በሀገራችን እየተለመደ ነው፡፡ ምሁራን፣ባለ ሥልጣናት፣ጋዜጠኞች እና ሌሎችም በይፋ በቤተ ክርስቲያን ነገሮች ላይ መቀለድ ልማድ አድርገውታል፡፡ የሚገርመው ነገር እነርሱም አይሰቀቁ፣እኛም ለምደነው እንስቃለን፤ አናዝንም፡፡ ለሌሎች አርአያ ይሆናሉ ተብለው የሚጠበቁ አገልጋዮች፣የእምነት አባቶች እና ገዳማውያን ሳይቀሩ በሥነ ምግባር ብልሹነት እና በሙስና እስከ መዘፈቅ ደርሰዋል፡፡

ለአክራሪ እስልምና አጋለጠን

አክራሪ እስልምና እጅግ በጣም ወግ አጥባቂ እምነት ነው፡፡ ይህ እምነት ወደ ምዕራቡ ዓለም ሲዘምት በሊበራሊዝም የተቦረቦረ ኅብረተሰብ ነው ያገኘው፡፡ ይህ የራሱ ማንነት የሌለው እና ሁሉም ትክክል ነው ብሎ የሚያምን ኅብረተሰብ ደግሞ በፍጥነት እና በፍላጎት ለሚሠራው አክራሪ እስልምና የተመቸ ሁኔታ ፈጠረለት፡፡ ፓትሪክ ሱኬዶ የተባሉ «የእስልምና እና ክርስትና ጥናት ተቋም ዳይሬክተር» እንደ ተናገሩት 200 ከፍተኛ የአሜሪካ ኩባንያዎች የሸሪያ ሕግን አጣጥመው ይሠሩበታል፡፡ ሳዑዲ ዐረቢያም ለዋና ዋና የአሜሪካ ዩኒቨርሲቲዎች የገንዘብ ርዳታ በመስጠት የትምህርት ሥርዓቱ ከተቻለ ለእስልምና አመቺ ካልተቻለም ለዘብተኛ እንዲሆን ታደርጋለች ብለዋል፡፡

እጅግ ታዋቂ የሆኑ አሜሪካውያን ክርስትናው አላረካቸው ብሎ እስልምናን ሊቀበሉ የቻሉት፣ መጀመርያውኑ ርግጠኛውን ክርስትና ባለማግኘታቸው ነው፡፡ ሌላው ቀርቶ አንዳንድ የምዕራብ ዜጎች ከነ አልቃይዳ ጎን ተሰልፈው የገዛ ሀገራቸውን እና ወገናቸውን እስከማጥፋት የደረሱት ያሳደጋቸው ለዘብተኛ ክርስትና ሊያረካቸው ባለመቻሉ ነው፡፡

የሞራል መላሸቅን አስከተለ

ክፉ እና ደጉን ለይቶ የማያውቅ፣ ማንንም የማይፈራ፣ ለሱስ፣ ለመገዳደል፣ ለመጠጥ፣ ለሐሺሽ፣ ለዝሙት፣ ለጭፈራ፣ የተጋለጠ ለማኅበረሰባዊ እሴቶች ግድ የሌለው፣ ሀገሩን እና ወገኑን ለመርዳት የማያስብ፣ ከትምህርት ይልቅ መዝናናትን የሚመርጥ ትውልድ እንዲያፈሩ አደረገ፡፡ ዛሬ አሜሪካን ውስጥ ድራግ የማይቀምስ ወጣት የለም፡፡ በድንግልና መቆየት ነውር ሆኗል፡፡ ሌላው ቀርቶ አሜሪካውያን ለሂሳብ፣ ለፊዚክስ እና ለኢንጂነሪንግ ፍቅር የሌላቸው በሙዚቃ ግን የተለከፉ እንዲሆኑ ያደረጋቸው ይሄ ነው፡፡ ቅዱሳንን ንቀው ታላላቅ ሰዎችን የሚያመልኩ፣ የፈለግኩትን ባደርግ ምን አለበት? በሚል ስሜት ለወንጀል የሚዳረጉ እንዲሆኑ አደረጋቸው፡፡

ቅድመ ጋብቻ የግብረ ሥጋ ግንኙነት እንደ ኃጢአት ሳይሆን እንደ መብት በመታየቱ ዛሬ ወጣቶቻቸው እምብዛም አይጨነቁበትም፡፡ በአሜሪካ ውስጥ በተደረገ ጥናት ዕድሜያቸው 20 ዓመት ከሞላቸው ወጣቶች መካከል ቢያንስ 75% ቅድመ ጋብቻ የጾታ ግንኙነት ፈጽመዋል፡፡ በነገራችን ላይ የዛሬ 2 ዓመት በአዲስ አበባ ከፍተኛ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ላይ በተደረገ ጥናትም ከ50% በላይ ተማሪዎች 18 ዓመት ሳይሞላቸው ጾታዊ ግንኙነት ማድረጋቸውን አመልክቷል፡፡

ጋብቻ በተጋቢዎች መካከል የሚኖር ዘለዓለማዊ ቃል ኪዳን መሆኑ እየቀረ በተፈለገ ጊዜ ሊቀር የሚችል መሆኑ ስለተሰበከ ፍቺ በርክቷል፡፡ ጋብቻ በአንደ ወቅት የሚፈጸም ሥነ ሥርዓት እንጂ የቅድስና ምንጭ መሆኑ እየተረሳ ነው፡፡ በዚህም ምክንያት ሳይጋቡ በደባልነት መኖር እንደ ጋብቻ ኑሮ እየተቆጠረ መጥቷል፡፡

በአሜሪካ አብያተ ክርስቲያናቱ የጽንስ ማስወረድ ደጋፊዎች እና ተቃዋሚዎች ተብለው እስከ መለየት ደርሰዋል፡፡

አገልግሎትን እንደ ሞያ ማየት

በሊበራሊዝም አስተሳሰብ መንፈሳዊ አገልግሎቶች እንደ አንደ ሞያ ብቻ ይታያሉ፡፡ ጵጵስና፣ ካህንነት፣ ዘማሪነት፣ወዘተ ሞያዎች ናቸው፡፡ በመሆኑም የሃይማኖት ሥነ ምግባርን እና አርአያ ክህነትን አይጠይቁም፡፡ አገልግሎት እንደሞያ ከታየ ፈሪሃ እግዚአ ብሔር ጠፍቶ ድፍረት ቦታውን ይይዛል፡፡ የሚያስተምሩትን ራሳቸው የማይፈጽሙ፣ለክብር ፣ለዝና እና ለገንዘብ ብቻ ሲሉ የሚያገለግሉ፣ በመንፈሳዊነት ስም ኃጢአትን የሚፈጽሙ አገልጋዮች እየበዙ ይሄዳሉ፡፡ ባለፉት ዓመታት በአሜሪካ እና በአውስ ትራሊያ በካቶሊክ መነኮሳት ላይ የታየው የሞራል ዝቅጠት በሽታው የደረሰበትን ደረጃ ያመለክተናል፡፡

በሀገራችንም ቢሆን ዛሬ ዛሬ ምንኩስናን ለፍጹምነት መብቂያ መንገድ ሳይሆን የድብር አስተዳዳሪ ለመሆን፣ውጭ ሀገር ለመሄድ፣ የተሻለ ደመወዝ ለማግኘት የሚያስችል መንገድ አድርገው የሚቆጥሩት እየበዙ መጥተዋል፡፡ ሰባኪነት እና ዘማሪነትም ቢሆን ተሰጥኦ እና ትምህርት፣ሃይማኖት እና ምግባር የሚጠይቅ መሆኑ እየተዘነጋ ነው፡፡ እንዲያውም አንዳንዴ ቀላል እና ክፍት የሥራ ቦታም ይመስላል፡፡

የማይጾም፣ የማይጸልይ፣ የማያስቀድስ፣ ከምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን የራቀ፣ የሌለበትን ሕይወት የሚያስተምር እና የሚዘምር አገልጋይ እየመጣ ነው፡፡ እንደ ባለሞያ ለእንጀራው ሲል ብቻ የማያምንበትን የሚያስተምር አገልጋይ እየመጣ ነው፡፡ ሰዓታት መቆም፣መቀደስ፣መመንኮስ፣ኪዳን ማድረስ፣ ጠዋት ተገብቶ ማታ የሚወጣበት ሥራ እየሆነ መጥቷል፡፡

የቤተ ክርስቲያን መዋቅር የማያውቃቸው ምእመናንን እና ካህናትን አፈራ

ወደ ቤተ ክርስቲያን ሄደው የማያስቀድሱ፣ የንስሐ አባታቸውን አግኝተው የማያውቁ፣ በአዳራሽ እንጂ በቤተ ክርስቲያን ቅጽር ግቢ ለመሰብሰብ የማይፈልጉ፤ አንድም ቤተ ክርስቲያን የማያውቃቸው ካህናት፣ ገዳም የማያውቃቸው መነኮሳት እየበዙ መጥተዋል፡፡

ከዚህም ብሶ ከአጠቃላዩ የቤተ ክርስቲያን መዋቅር የተነጠሉ አብያተ ክርስቲያናት እና ጳጳሳት ቁጥራቸው እየጨመረ ነው፡፡ «እኔን ከመሰለኝ» የሚለውን የሊበራል አስተሳሰብ በመከተል በአንድ በኩል ከቅዱስ ሲኖዶስ ጋር እየተሰበሰቡ በሌላ በኩል ደግሞ የግላቸው ቤተ ክርስቲያን መሥርተው የሚንቀሳቀሱ ጳጳሳት ተፈጥረዋል፡፡

ትምህርት ቤቶች እና የጤና ተቋማት የግል እና የመንግሥት ተብለው እንደ ሚከፈሉት ሁሉ አገልጋዮችም የግል አገልጋዮች እና የቤተ ክህነት አገልጋዮች ተብለን እስከ መከፈል ደርሰናል፡፡

የሊበራሊዝም ግርፍ የሆኑ አንዳንዶች ኢየሱስ ክርስቶስ ዓለምን ሊያድን እንጂ ሃይማኖት ሊመሠርት አልመጣም የሚል ፍስፍና ያስፋፋሉ፡፡ ለመሆኑ ሃይማኖት ምንድን ነው? ሃይማኖት ማለትኮ በቀላሉ ሲተረጎም እግዚአብሔርን የማምለኪያ መንገድ ማለት ነው፡፡ ታድያ ኢየሱስ ክርስቶስ ይህንን መንገድ አልዘረጋም? ሐዋርያው ይሁዳስ «ለቅዱሳን አንድ ጊዜ የተሰጠች ሃይማኖት» በማለት የገለጠው ምንድን ነው?/ይሁዳ 1÷3/ ቅዱስ ጳውሎስስ በኤፌሶን መልእክቱ «አንድ ሃይማኖት አለ» ያለው/ኤፌ 4÷5¼ ተሳስቷልን? ልጁ ቲቶን «ስለዚህም ምክንያት የቀረውን እንድታደራጅ በየከተማውም እኔ አንተን እንዳዘዝሁህ» ቲቶ 1÷5 በማለት የገለጠው ክርስትና የራሱ አደረጃጀት ስላለው አይደለምን?

ምን ይደረግ ?

ሊበራል ክርስትና ዛሬ የምሥራቅ አብያተ ክርስቲያናትን እየተፈታተኑ ካሉት የዘመኑ ፈተናዎች አንዱ ነው፡፡ ይህ ፈተና በሁለት መልኩ ይገባል፡፡

የመጀመርያው አስተሳሰቡን በማራመድ ሆን ብሎ በሚደረግ ወረራ ነው፡፡ በሀገራችን ፕሮቴስታንቶች እና ተሐድሶዎች ሞክረውት የነበረው ይሄንን መንገድ ነበር፡፡ ዛሬም ቢሆን አንዳንድ ፖለቲከኞች፣ ፓስተሮች እና ተሐድሶዎች ይህንኑ አስተሳሰብ ያራምዱታል፡፡ የሁለት ሺ ዓመት መሠረትን በማጥፋት ቤተ ክርስቲያንን ያልተጣሩ አስተሳሰቦች መናኸርያ ለማድረግ ጥረት እየተደረገ ነው፡፡ ባለፉት ሁለት ሺ ዓመታት ወንጌል የገባው ሕዝብ አልተፈጠረም፣ ክርስቲያኑ ክርስቶስን አያውቅም ነበር ብሎ ማሰብ፡፡ መጽሐፍ ቅዱስን በቋንቋው ተርጉሞ እና ከዮዲት እና ግራኝ ጠብቆ ያቆየን ሕዝብ መጽሐፍ ቅዱስን አታውቅም ነበር ብሎ በድፍረት ማስተማር መሠረትን ለማናጋት እንጂ እውነቱ ጠፍቶ አይደለም፡፡ አንድ ምሁር እንዳለው ይህ «ክርስቲያንን መልሶ ክርስቲያን ማድረግ  re  christianization of the Christians » ማለት ነው፡፡

በተለይም አሜሪካ የዚህ ወረራ ዋነኛ ቦታ ሆናለች፡፡ የቤተ ክርስቲያንን ሥርዓት፣ትውፊት እና ባሕል እያቃለሉ ማስተማር፣ወይንም ደግሞ በጭራሽ ርእሰ ጉዳይ አድርጎ አለማስተማር እና ማስረሳት አንዱ መንገድ ነው፡፡ ባለፉት ዘመናት ከ30 በላይ ገድላትን እና ድርሳናትን የሚሳደቡ ጽሑፎች በተሐድሶአውያን ታትመው በነጻ እየተሠራጩ ይገኛሉ፡፡  አክራሪ እስልምናን በተመለከተ ግን ትንፍሽ ብለው አያውቁም፡፡

ሁለተኛው ደግሞ አስተሳሰቡ ሳይታወቅ ይገባና ውስጥ ለውስጥ ይሸረሽራል፡፡ ከዚያም በሃይማኖት ለዘብተኛ ያደርጋል፡፡

ቅዱሳንን እና ክብራቸውን ማቃለል፣ ከቅዱሳት መጻሕፍት ውስጥ ስሕተት ለመፈለግ መኳተን፣ የጸሎት መጻሕፍትን አለመጠቀም፣ በሰበብ በአስባቡ ከጾም መሸሽ፣ በየምክንያቱ ከቤተ ክርስቲያን መራቅ፣ ለንዋያተ ቅድሳት ያለን አክብሮት መቀነስ፣ ምን አለበት በሚል ምክንያት ነገሮችን በፈለግነው መንገድ ማድረግ፣ ጳጳሳትን፣ ካህናትን እና አገልጋዮችን መናቅ፣ እና በድፍረት መናገር፤ ቤተ ክርስቲያን ባልሄድም በልቤ መልካም ሰው ከሆንኩ ይበቃኛል እያሉ መጽናናት፣ በሃይማኖት ጉዳዮች ሳቅ እና ቀልድ ማብዛት፣ በሃይማኖት ማፈር፣ አንዲት እምነት ከሚለው የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ወጥቶ፣ ለሌሎቹ ያዘኑ በመምሰል፣ ሁሉም ልክ ነው የሚል አዝማሚያ መያዝ ከበሽታው ምልክቶች ጥቂቶቹ ናቸው፡፡

በሽታው ሌላም ምልክቶች አሉት፡፡ የሊበራል ክርስትና «እኔ እኔ» አስተሳሰብ ወደ መዝሙሩም፣ ወደ ትምህርቱም ይገባና ሁሉም በዚሁ ይቃኛል፡፡ እግዚአብሔርንም የኔ ማለት ይጀመራል፡፡ በትምህርታችን ውስጥ እኔ እንዲህ ሆኜ፣ ይህንን አድርጌ፣ እንዲህ ያለ ነገር ታይቶኝ፣ ወዘተ እያሉ ራስን ከፍ ከፍ ሊያደርጉ የሚችሉ ነገሮችን መጨማመር፣ በመዝሙሮቻችንም ራስን መስበክ ይመጣል፡፡ በምሥራቃውያን ትውፊት ሰው ስለ ራሱ ይናገር የነበረው ታናሽነቱን፣ ትኅትናውን ወይንም በደለኛነቱን ለመግለጥ ነበር፡፡ ሊበራሊዝም ዘልቆ ሲገባ ግን የራስን ታላቅነት እና ክብር መናገርም ይጀመራል፡፡

ሊበራሎች ኢየሱስ ክርስቶስን እግዚአብሔር ነው ብለው አያምኑም፡፡ ከዚያ ይልቅ ለሰዎች ሕይወት «ሞዴል ነው» ይላሉ፡፡ ስለዚህም እንደ አንድ ፍቅረኛ፣ ጓደኛ፣ አርአያ ያዩታል እንጂ በአምላክነቱ አይቀበሉትም፡፡ በመሆኑም ናፈቀኝ፣ እወደዋለሁ፣ ጓዴ ነው፣ አብሮ አደጌ ወዘተ ብሎ መጥራት ያዘወትራሉ፡፡ ይህ አስተሳሰባቸው ገብቶብን እንደሆነም አላውቅም «ስትናፍቀን እንዘምራለን» የሚል መዝሙር በሰንበት ት/ቤቶች ሲዘመር የሰማሁ ይመስለኛል፡፡

ዛሬ ቤተ ክርስቲያናችን ከሁለት አቅጣጫ በሚመጣ ፈተና ተወጥራለች፡፡ ከምሥራቅ ወግ አጥባቂው እና በከፍተኛ ሁኔታ ኃይልን፣ ገንዘብን እና ነውጥን በሚጠቀመው አክራሪ እስልምና፣ ከምዕራብ በኩል ደግሞ ለሃይማኖት ግድየለሽ፣ በፈጣሪ በሚቀልደው እና ጠንካራ እና ጽኑዕ እምነትን ለመሸርሸር በተነሳው ሊበራል ክርስትና፡፡ አንዱ በኃይል ሌላው በፍልስፍና - ኦርቶዶክሳዊነትን ለማጥፋት ዘምተዋል፡፡

ይህንን ከሁለት ወገን የመጣ እና ሳንዱዊች ሊያደርገን የተዘጋጀ ፈተና «መንፈሳውያን ሃይማኖታውያን» በመሆን ብቻ ነው ድል የምንነሣው፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን በመዋቅር የተበታተነች፤ በአሠራርዋ የተዳከመች ከሆነች፤ ልጆቿ በመንፈስ የዛሉ፣ በሃይማኖት ዕውቀት ያልበረቱ ከሆኑ ፈተናውን መቋቋም አይችሉም፡፡

«በክርስትና እና በሳይንስ መካከል ያለው ዐቢይ ልዩነት፣ በሳይንስ የቅርቡ በጣም የተሻለ ሲሆን፣በክርስትና ግን የጥንቱ በጣም የተሻለ መሆኑ ነው in science the latest is the best, but in Christianity the oldest is the best» በማለት ይስሐቅ አል ባራኪ የተባሉ ሶርያዊ ሊቅ እና ሳይንቲስት ተናግረዋል፡፡ ክርስቲያን የሆንነው እኛ አባቶቻችንን ለመምሰል እንጂ አባቶቻችን እኛን እንዲመስሉን አይደለም፡፡ ወደ ቤተ ክርስቲያንም የመጣነው እኛ በቤተ ክርስቲያንዊ ትምህርት እና ሕግ ልንመራ እንጂ ቤተ ክርስቲያን በኛ ትምህርት እና ሕግ ለመምራት አይደለም፡፡

በመሆኑም ትክክለኛውን ክርስትና ለመኖር እኛም ወደ ቤተ ክርስቲያን፣ ቤተ ክርስቲያንም ወደ እኛ መግባት አለባት፡፡ ኦርቶዶክሳዊ ክርስትና በሦስት መልኩ መገለጥ አለበት ትምህርታዊ፣ ሊተርጂያዊ፣ እና ትውፊታዊ፡፡ ትምህርታዊ ማለት መጽሐፍ ቅዱስን አባቶቻችን በተረዱበት መንገድ እና መሠረት መረዳት፣ መመስከር እና መኖር ማለት ነው፡፡  በክርስትና አዳዲስ ማብራርያዎች እንጂ አዳዲስ መሠረተ ሃሳቦች ሊኖሩ አይችሉም፡፡

ሊተርጂያዊ ማለት ደግሞ በቤተ ክርስቲያን ሕይወት የሚገኙትን ጾም ፣ጸሎት፣ ቅዳሴ፣ የምሥጢራት ተሳትፎ፣ ዝማሬ፣ ወዘተ ገንዘብ ማድረግ እና የእነዚህ ፍሬዎች የሆኑትን የምግባር ፍሬዎች ማሳየት ማለት ነው፡፡ ትውፊታዊ ማለትም በቤተ ክርስቲያን ያገኘናቸውን የቀደሙ አበው የሕይወት መንገዶች፣ትሩፋቶች፣ጸጋዎች፣ ቅርሶች በመያዝ፣በመጠበቅ እና በመጠቀም መኖር ነው፡፡

ዋናን ከውኃ ውጭ መዋኘት እንደማይቻለው ሁሉ ክርስትናንም ከቤተ ክርስቲያን ውጭ መኖር አይቻልም፡፡ በመርከቧ ሲጓዙ ማዕበል በተነሣባቸው ጊዜ በዚያው መርከብ ውስጥ ሆነው አድነን ነበር ያሉት ሐዋርያት፡፡ እኛም በየምክንያቱ ከቤተ ክርስቲያን መውጣታችንን ትተን በቤተ ክርስቲያን ውስጥ በመኖር ችግሮችን መጋደል እና መቋቋም ያስፈልጋል፡፡

በረከታቸው ይደርብንና ብጹዕ አቡነ ጎርጎርዮስ «ሸረሪት አትሁኑ» ይሉ ነበር፡፡ ሸረሪት ድር አድርታ የኖረችበት ቤት ሲቃጠል ውኃ አምጥታ ከማጥፋት ይልቅ ቤቱን ለቅቃ ሌላ ቦታ በመሄድ ድር ታደራለች፡፡ ቤተ ክርስቲያን ፈተና በገጠማት ቁጥር እየሸሹ የራስን ኅሊናዊም ቁሳዊም ጎጆ መቀለስ ሸረሪትነት ነው፡፡

ሃይማኖት የትርፍ ጊዜ ሥራ መሆን የለበትም፡፡ መንፈሳዊነትም ባሕል እና ልማድ ብቻ ሆኖ ያለ ልቡና እንዲሁ የሚኖርበት መሆን የለበትም፡፡ በመሆኑም ቀጥ ብሎ ራስን መፈተሽ ያስፈልጋል፡፡ ዛሬ እንደዋዛ የምንናገራቸው እና የምናደርጋቸው ነገሮች ቤተ ክርስቲያንን ሸርሽረው ሸርሽረው በምእመናን ላይ የማይጠገን ቁስል ከመጣላቸው በፊት በቀደሙት አበው ትምህርት እና ኑሮ መነጽርነት መንገድን እና ልብንም መመርመሩ የተሻለ ነው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር
ወለወላዲቱ ድንግል
ወለመስቀሉ ከቡር

ለዘብተኛነት/ሊበራሊዝም/፡የክርስትና ዘመናዊው ጠላት



ግን በመጨረሻው ቀን የሚያስጨንቅ ዘመን እንዲመጣ ይህን ዕወቅ፣ ከእግዚአብሔር ይልቅ ተድላን የሚወዱ ይሆናሉ፣

የአምልኮት መልክ አላቸው ኃይሉን ግን ክደዋል፡፡ 2ኛጢሞ. 3÷5

ለዘብተኛነት/ሊበራሊዝም/ በ18ኛው መክዘ መጨረሻ እና በ19ኛው መክዘ መጀመርያ ብቅ ያለ አስተሳሰብ ነው፡፡ ይህ አስተሳሰብ በፖለቲካው መስክ ግራ ዘመም አስተሳሰብ በመባል ይታወቃል፡፡ በደምሳሳው ልቅ በሆነ መብት እና ነጻነት የሚያምን፤ ነባር ባሕሎችን፣ ልምዶችን እና እምነቶችን በየጊዜው በመናድ ሰዎች ራሳቸውን አማልክት አድርገው እንዲያስቡ የሚያበረታታ አመለካከት ወይም ርእዮተ ዓለም ነው፡፡

ዛሬ በፖለቲካው መስክ ያለው ለዘብተኛነት ርእሰ ጉዳያችን አይደለም፡፡ የምንወያየው ስለ ለዘብተኛ/ሊበራል/ ክርስትና ነው፡፡

ሊበራል ክርስትና የግራ ዘመምን አስተሳሰብ በመያዝ በዚያው በ18ኛው መክዘ መጨረሻ እና በ19ኛው መክዘ መጀመርያ ብቅ ያለ አስተምህሮ ነው፡፡ ይህ አስተምሮ ፕሮቴስታንቲዝምን ሳይቀር አክራሪ /conservative/ ነው ብሎ የሚያምን እና በሃይማኖት ለሰው ልጅ ልቅ የሆነ መብት እና ነጻነት ሊሰጠው ይገባል በሚል የተነሣ ነው፡፡ በአሜሪካ እና በአውሮፓ አብዛኞቹ ፕሮቴስታንቶች እና ፓስተሮቻቸው በዚህ አመለካከት የሚመሩ ናቸው፡፡

ይህ አመለካከት የፕሮቴስታንቱን ዓለም ሃይማኖት አልባ ማድረጉ ሳያንሰው የካቶሊካውያንን እና የምሥራቅ እና የኦርየንታል አብያተ ክርስቲያናትን በር በማንኳኳት ላይ ይገኛል፡፡ በመገናኛ ብዙኃን እና በኤሌክትሮኒክስ ሚዲያው በየጊዜው ስለሚለፈፍ፣ ታላላቅ የሚባሉ ፖለቲከኞች እና የተከበሩ ሰዎች በየአጋጣሚው ስለሚያነሡት የሊበራል ክርስትና አስተሳሰብ እንደ ተስቦ በየሰው እየሠረፀ ነው ማለት ይቻላል፡፡ ሊበራል ክርስትናን እንዲህ እና እንዲያ ነው ብሎ ከመበየን መገለጫዎቹን ማቅረቡ ይበልጥ ግልጽ ያደርገዋል፡፡

የሊበራል ክርስትና አመለካከት ዋና ዋና መገለጫዎቹ የሚከተሉት ናቸው፡፡

መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር ቃል አይደለም ይላሉ

ሊበራል ክርስቲያኖች መጽሐፍ ቅዱስ በአንድ ወቅት የነበሩ ሰዎች ስለ እግዚአብሔር ምን እንደሚያምኑ የገለጡበት መጽሐፍ እንጂ የእግዚአብሔር ቃል አይደለም ብለው ያምናሉ፡፡ በመሆኑም ሊተች፣ ሊስተካከል፣ ሊታረም እና ሊቀየር የሚችል ጽሑፍ ነው ይላሉ፡፡ በዚህ አስተሳሰባቸው ምክንያትም ዛሬ ዛሬ ብዙዎቹ የፕሮቴስታንት አስተማሪዎች በትምህርታቸው ውስጥ መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ማለት አልነበረበትም እያሉ ይተቻሉ፡፡ ወይም አንድ ሰው እንዳለው they want to re-write the bible፡፡ ሃይማኖታቸውም የግድ መጽሐፋዊ መሆን እንደሌለበት እና መጽሐፍ ቅዱስ የሃሳብ መነሻ ብቻ መሆን እንደሚችል ያስተምራሉ፡፡ በመሆኑም በየጊዜው አዳዲስ እና የተሻሻሉ የመጽሐፍ ቅዱስ ቅጅዎች እንዲታተሙ ያበረታታሉ፡፡

መጽሐፍ ቅዱስ ወጥ ትርጓሜ አያስፈልገውም ይላሉ

ሊበራሎች መጽሐፍ ቅዱስን ማንም ሰው እንደተመቸው እና እንደገባው መተርጎም ይችላል፡፡ አንድ ወጥ የሆነ እና «ትክክል ነው» ተብሎ ሊመሰከርለት የሚችል ትርጓሜ የለም ይላሉ፡፡ ይህም በሃይማኖት እና በአስተሳሰብ የተለያዩ ሚሊዮን ዓይነት የክርስትና ክፍልፋዮች እንዲፈጠሩ አድርጓል፡፡ ዶግማ እና ቀኖና የሚባል ነገር ስለሌላቸው ስለሚያመልኩት አምላክ እንኳንስ ሁሉም፣ በአንድ ጉባኤ የተገኙት እንኳን ተመሳሳይ እምነት የላቸውም፡፡ በማናቸውም ትምህርታቸውም ቢሆን የቀደሙ አበውን ትምህርት፣ ትርጓሜ እና ሐተታ አያካትቱም፡፡ ምናልባት መጽሐፍ ቅዱስን ይጠቅሱ ካልሆነ በቀር፡፡ የቅዱሳንን ሕይወትም አስረጂ አድርገው አይቆጥሩትም፡፡

በሃይማኖት ጉዞ ውስጥ አንድ ሊቋረጥ የማይገባው አንድነት «አሐተኔ» አለ፡፡ ይኸውም በአንድ ዘመን በሚኖሩ ክርስቲያኖች መካከል፣በአንድ ዘመን በሚኖሩ ወይንም በነበሩ ክርስቲያኖች እና ከእነርሱ በፊት በነበሩ ክርስቲያኖች መካከል፣እንዲሁም በአንድ ዘመን በሚኖሩ ወይንም በነበሩ ክርስቲያኖች እና ከእነርሱ በኋላ በሚመጡ ክርስቲያኖች መካከል የሃይማኖት አንድነት መኖሩ ነው፡፡ እኛ ከቀደሙ ክርስቲያኖች እና ወደፊት ከሚመጡ ክርስቲያኖች ጋር የሃይማኖት አንድነት ከሌለን «አንዲት ሃይማኖት፣ አንዲት ቤተ ክርስቲያን» ብለን መጥራት አንችልም፡፡

ሊበራሊዝም መጽሐፍ ቅዱስን እያንዳንዱ ሰው በራሱ መንገድ እንደፈለገ እንዲተረጉመው በመፍቀዱ የተነሣ በአንድ ዘመን በሚኖሩ ክርስቲያኖች መካከል የሃይማኖት አንድነት የለም፡፡ በአንድ ዘመን በሚኖሩ ክርስቲያኖች እና ከእነርሱ በፊት በነበሩ፣በኋላም በሚመጡ መካከል ያለውም አንድነት ፈርሷል፡፡

ትክክለኛም ሆነ የተሳሳተ ሃይማኖት የለም ይላሉ

ሊበራሎች «አንድ ሰው ትክክል ነው ብሎ እስካመነበት ድረስ ማንኛውም እምነት ትክክል ነው» ብለው ያስተምራሉ፡፡ ከኤፌሶን ምዕራፍ ሁለት «አንዲት እምነት» ከሚለው ትምህርት በተቃራኒ «የተሳሳተ ሃይማኖት የለም፤ ሁሉም ሃይማኖት እኩል እና ትክክል ነው፡፡ ልዩነቱ የሰዎች አስተሳሰብ ነው» ብለው ያስተምራሉ፡፡ በመሆኑም ልዩ ልዩ አመለካከት ያላቸው አማኞች በአንድ ጊዜ፣ በአንድ ቦታ ፣በጋራ ማምለክ ይችላሉ ብለው ያስባሉ፡፡

ይህ አስተሳሰባቸውም ሰዎች የራሳቸውን ፍልስፍና እንደ ሃይማኖት ትምህርት እየቆጠሩ በየጊዜው እንዲበታተኑ አድርጓቸዋል፡፡ ወደ ትክክለኛዋ መንገድ ከመመለስ ይልቅ ሁላችንም ትክክል ነን በሚል ፍልስፍና በስሕተቱ ጎዳና እንዲበረቱበት ረድቷቸዋል፡፡

የሚያስፈልገው ማኅበራዊ ወንጌል ብቻ ነው ይላሉ

የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ለማኅበራዊ ኑሮ፣ ለፍትሕ፣ ለዴሞክራሲ፣ ለሰብአዊ መብት እና ለእኩልነት መዳበር ከሚሰጠው ጥቅም አንጻር እንጂ በመሠረተ እምነት/ዶግማ/ ላይ ማተኮሩን ይቃወማሉ፡፡ ለስብከቱ ማራኪነት፣ አስደሳችነት እና ሳቢነት እንጂ ለትምህርቱ ትክክለኛነት አይጨነቁም፡፡ የነገረ ሃይማኖት ጉዳዮችን ማንሣት ሊለያየን ስለሚችል «ከዚህም ከዚያም ያልሆነ አቀራረብ» /neutral approach/ መጠቀም ያስፈልጋል ባዮች ናቸው፡፡ ትምህርታቸው መንፈሳዊ ሳይሆን ሥነ ልቦናዊ፣ ለማዳን ሳይሆን ለማስደሰት፣ እውነቱን ለመመስከር ሳይሆን ሰው እውነት የመሰለውን እንዲመርጥ ለማድረግ የታሰበ ነው፡፡ የዶግማ እና የቀኖና ትምህርት አይሰጡም፡፡

ዛሬ ዛሬ ይህ በሽታ እኛም ውስጥ ገብቶ ነው መሰለኝ ሰባክያን የተባልን ሰዎች ከዶግማ ትምህርት እየወጣን በስብከት ላይ ብቻ ወደማተኮር እየቃጣን ነው፡፡ በትምህርታችን ውስጥ እንኳን መሠረታዊ የሃይማኖት ትምህርትን በተገቢው መንገድ አናቀርብም፡፡ ምእመናንም ይህንኑ ለምደው መሠረታዊ ትምህርት ሲሰጥ እንደ ባከነ ጊዜ ይቆጥሩታል፡፡ በትምህርት አሰጣጣችንም ውስጥ የአበው ትምህርት፣ ትርጓሜ እና ሐተታ እየተረሳ፣ የቅዱሳንም ሕይወት በአስረጅነት መጠቀሱ እየቀረ ነው፡፡

ቤተ ክርስቲያን አልባ ክርስትናን ያስፋፋሉ

ሊበራል ክርስቲያኖች ቤተ ክርስቲያን ለድኅነት የግድ አስፈላጊ አይደለችም፡፡ ያለ ቤተ ክርስቲያን ክርስቲያን መሆን ይቻላል፤ ብለው ያምናሉ፡፡ አንድ ሰው ካመነ ክርስቲያን ለመሆን በቂው ነው፡፡ ስለዚህም ወደ ቤተ ክርስቲያን ሄዶ መጠመቅ፣ መቁ ረብ፣ መማር፣ መዘመር ወዘተ የግድ አያስፈልገውም ብለው ያስተምራሉ፡፡ ፕሮቴስታንቲዝም ሲጀመር «ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ከተራ ቤት እኩል ነው» ብሎ ተነሣ፣ ቀጥሎ ደግሞ ሊበራሎቹ «ያም ቢሆን አያስፈልግም» ብለው ደመደሙት፡፡ ውሻ በቀደደው አይደል ድሮስ ጅብ የሚገባው፡፡

በዚህ የተነሣም ብዙ ፕሮቴስታንቶች ወደ ቤተ ክርስቲያን አይሄዱም፣ አይሳተፉምም፡፡ ለምሳሌ በእንግሊዝ ሀገር 10% የሚሆኑ ክርስቲያኖች ብቻ ናቸው ቤተ ክርስቲያን እሑድ እሑድ የሚሄዱ፡፡ በስካንዴኒቪያን ሀገሮች ደግሞ ከ2 እስከ 3% ብቻ ይሄዳል፡፡ በአሜሪካ 60% ክርስቲያኖች ቤተ ክርስቲያን አይሄዱም፡፡ ከሚሄዱት ከ40% ብዙዎቹ ማኅበራዊ ጥቅማ ጥቅም ለማግኘት የሚሄዱ ናቸው፡፡ እንዲያውም በአሁኑ ዘመን ደግሞ «የኮምፒውተር ቤተ ክርስቲያን» online church የሚባል እየተከፈተ ነው፡፡ ስለዚህም በዳታ ቤዙ ላይ የኃጢአት ዝርዝር አለ፤ የሠሩትን ኃጢአት ከዳታ ቤዙ ውስጥ ገብተው ክሊክ ሲያደርጉ ቅጣቱን ይነግርዎታል፡፡

መዋቅር አልባ እምነትን ያስፋፋሉ

ሊበራሊዝም ማንኛውም ክርስቲያን በፈቀደው መንገድ እንዲያምን ስለሚያስተምር ማናቸውንም ዓይነት የሃይማኖት መዋቅሮች አይቀበልም፡፡ ሃይማኖታዊ መዋቅሮች ይኑሩ ከተባለም በዲሞክራሲያዊ መንገድ በሚመረጡ የቦርድ አባላት የሚመሩ እና ለብዙኃኑ ድምጽ ተገዥ የሆኑ መሆን አለባቸው ይላል፡፡ በዚህም የተነሣ የክህነትንም ሆነ የአስተዳደር እርከኖችን አይቀበልም፡፡ ጳጳሳት በካህናት ላይ፣ ካህናት በምእመናን ላይ ያላቸውን ሃይማኖታዊ ሥልጣን፣ እንዲሁም የቤተ ክርስቲያንን ሃይማኖታዊ እና አስተዳደራዊ ጉዳይ በመወሰን ረገድ ቅዱስ ሲኖዶስ ያለውን ሥልጣን አይቀበልም፡፡

በአሜሪካን ሀገር በ1960 እኤአ መሥመራውያን አብያተ ክርስቲያናት /main line protestants/ ከጠቅላላ ክርስቲያኑ 40% ይሸፍኑ ነበር፡፡ በ40 ዓመታት ውስጥ ግን በሊበራሎች ተነጥቀው ዛሬ 12% ብቻ ናቸው፡፡

ኑፋቄ የሚባል ነገር የለም ይላሉ

ሊበራሎች «የሁሉም ሰው ሃይማኖታዊ አመለካከት ትክክል ነው» ብለው ስለሚያምኑ ኑፋቄ የሚባል ነገር የለም ይላሉ፡፡ እንዲያውም ጥንት የተወገዙ መናፍቃን መብታቸው ተነክቷል ብለውም ያስባሉ፡፡ በቤተ ክርስቲያን ጉባኤያት የተለዩ የግኖስቲኮች መጻሕፍትን እንደ ገና ወደ ቤተ ክርስቲያን ለማስገባትም ይጥራሉ፡፡ መናፍቃንን በተመለከተ ምናልባት በዚያ ጊዜ የነበሩ አባቶች ተሳስተው ከሆነ ነገሩን እንደ ገና ማየት አለብን የሚል አመለካከት አላቸው፡፡ የበርናባስ ወንጌል፣ የይሁዳ ወንጌል፣ የማርያም መግደላዊት ወንጌል ወዘተ የተባሉና በግኖስቲኮች የተጻፉ የክህደት መጻሕፍት ዛሬ ዛሬ እንደ አዲስ ግኝት በመቸብቸብ ላይ ናቸው፡፡

መናፍቃንን መናፍቃን ማለተ ሰውን ማራቅ ነው፡፡ ስለ መናፍቃን ማውራት መለያየትን ማባባስ ነው፡፡ ስለ ራሳችን ብቻ እንናገር እንጂ ስለሌሎች አናንሣ፡፡ የሚሉት አመለካከቶች የልዩነቱን ድንበር አፍርሰው ክርስቲያኖች ስንዴውን እና እንክርዳዱን መለየት እንዳይችሉ የሚያደርጉ ናቸው፡፡

ለአዳዲስ አስተሳሰቦች ክፍት በር ይከፍታሉ

ሊበራሎች ለአዳዲስ አስተሳሰቦች በራችን ክፍት መሆን አለበት፣ አንድ ነገር አሳማኝ እስከሆነ ድረስ ልንቀበለው ይገባል ይላሉ፡፡ ዋናው ነገራቸው በቅዱሳት መጻሕፍት ትምህርት መሠረት ሳይሆን ምን ያህል ሕዝቡ ይቀበለዋል? በሚለው መሠረት ነው፡፡ በዚህ የተነሣም የተመሳሳይ ጾታ ጋብቻን፣ የሴቶችን ክህነት፣ የእንስሳትን አባልነት ወዘተ በመቀበል ላይ ናቸው፡፡ የሊበራሎች አንዱ መሠረታዊ አስተሳሰብ ዘመኑን በቅዱሳት መጻሕፍት መዋጀት ሳይሆን ቅዱሳት መጻሕፍትን ለዘመኑ ማመቻቸት ነው፡፡ በዚህ የተነሣ ቤተ ክርስቲያን በቅዱሳት መጻሕፍት ቃል እና በአባቶች ትምህርት ሳይመረመሩ አዳዲስ አስተሳሰቦች እንዲሁ የሚገቡባት ቤት መሆን አለባት ይላሉ፡፡

ግዴለሽነትን ያስፋፋሉ

ሊበራሎች ለጾም፣ ለጸሎት፣ ለሥነ ምግባር እና ለባሕል ግዴለሾች ናቸው፡፡ ሥርዓታዊ እምነት አይመቻቸውም፡፡ አንድ ሰው ክርስቲያን ለመሆን ከማመን እና ከማወቅ በላይ አያስፈልገውም ስለሚሉ ሌላ ዓይነት ሥርዓተ አምልኮን እንዲፈጽም አይገደድም፡፡ ጋብቻን ማክበር፣ ከሱስ ነጻ መሆን፣ ንጽሕናን መጠበቅ፣ ድንግልናን ማክበር፣ ወዘተ የሰው በጎ ፈቃድ እንጂ የሃይማኖት ትምህርት ናቸው ብለው አይወስዷቸውም፡፡ ስለዚህም አማኞች ትክክለኛ ኑሮ እና የተሳሳተ ኑሮ፣ሥነ ምግባራዊ እና ኢሥነ ምግባራዊ የሚባለውን ለይተው እንዲያውቁ እና እንዲኖሩ አይነገራቸውም፡፡

ሊበራል ክርስትና ምን አመጣ?
               ይቀጥላል
                                                           

                                   በአውሮጳ   የካህናት አንድነት ማኅበር ሊቋቋም መሆኑ ታወቀ በ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከመላዋ አውሮጳ   የተውጣጡ ካህናት፡” የ...