2013 ኖቬምበር 14, ሐሙስ

Help us by sharing this pic for the world to see!
oneTellSaudiArabia

 

ለዚህማ አልተፈጠርንም!

ከዲያቆን ዓባይነህ ካሤ

                                                             

ኢትዮጵያውያን ደማቸው የዐረብን አስፋልት አቀለመው፡፡ ባንዲራውን በራሱ ላይ ሸብ ያደረገው የእማማዬ ልጅ የእኔ ጀግና ማንነቱን እየተናገረ በአናቱ ላይ የወረደውን የድንጋዩን ናዳ በሀገሩ ፍቅር ተቋቁሞ በክብር አሸለበ፡፡ ለእርሱ ከዚህ በላይ ሌላ ድል አልነበረምና፡፡ ድንጋዩስ እርሱን አሳርፎታል፡፡ ነፍሱን ይማርልን እንጂ! ባንዲራችን ግን እንደተመታች እንደታመመች ናት፡፡ እውን ይኽ የሆነው በእኛ ላይ ነው? 


ይህቺ ባንዲራ እኮ ጨርቅ አይደለችም፡፡ ያ በሳኡዲ መሬት ተወግሮ የሞተው ወንድሜ የኮራባት በሞቱ ጊዜ የለበሳት የክብሩ፣ የማንነቱ መገለጫ እንጂ፡፡ ማንም ባይደርስለት ባንዲራው ነበረችለት፡፡ በእርሷ ተጽናና፡፡ ሞተ አልለውም መሰከረ እንጂ፡፡ ባንዲራ ለብሶ መከራን መጋፈጥ የሰማእታት ወግ ነው፡፡ 

ዳግማዊ ሆሎኮስት በኢትዮጵያውያን ላይ? እንዴት እንዴት? ደግሞ በ ፳፩ኛው ክፍለ ዘመን፡፡ የሰውን ሕይወት የሚያስገብር ምን ጥፋት ተገኝቶ ነው ወይስ የሟርት መስዋእታቸው እኛ ነን፡፡ "ከሕግ አስከባሪው ፖሊስ" እስከ ዱርየው የእኅቶቻችን ክቡር ሰውነት እንደ ውሻ ሲጎተት ከማየት የሚዘገንን አረመኔነት ምን አለ? ይህ እኮ ንቀት ነው፡፡ ይህ እኮ ድፍረት ነው፡፡ ይህ እኮ የሀገርን ሉዐላዊነት መድፈር ነው፡፡ 

2013 ኖቬምበር 10, እሑድ


ኢሕአዴግ እና የሃይማኖት ነጻነት

FACT Magazine Cover 02(ፋክት መጽሔት፤ ቅጽ ፪ ቁጥር ፲፱ ጥቅምት ፳፻፮ ዓ.ም.)
ተመስገን ደሳለኝ
… ኢሠፓ መራሹ መንግሥት በኢሕአዴግ ከተተካ ጥቂት ወራት ቢያልፈውም፣ የተራዘመው የእርስ በርስ ጦርነት ያልደረሰባቸው በደቡብ ኢትዮጵያ የሚገኙ አንዳንድ ከተሞችን ገና በቅጡ አልተቆጣጠራቸውም፤ በአናቱም በኢሠፓ መንግሥት ሽንፈት ሳቢያ እንዲበተን ከተገደደው የአገሪቱ መደበኛ ወታደር አብዛኛው ከእነትጥቁ የትውልድ መንደሩንና ቤተሰቡን መቀላቀሉ በአገሪቱ ላይ ከባድ ፍርሃት አንብሯል፡፡ በሰላም ወጥቶ ለመመለስ ርግጠኛ መኾን የማይቻልበት ከባቢያዊ አየርም አስፍኗል፡፡ በበርካታ ቦታዎች ተጠንተውና ታቅደው የሚፈጸሙ ወንጀሎችም ከአምስት እስከ ዐሥራ አምስት በሚደርሱ ወታደሮች የተደራጁ ልዩ ልዩ ሕገ ወጥ ቡድኖች በየማዕዘኑ እያቆጠቆጡ መኾኑን አመላክትዋል፡፡
በሌላ በኩል ደግሞ የዐዲስ አበባ ቆዳ ስፋትና የነዋሮዎቿ የአኗኗር ዘይቤን በቀላሉ ለመልመድ የተቸገሩ ተጋዳላዮች ለትንሽ ለትልቁ ግርግር ጠመንጃን እንደ መፍትሔ መምረጣቸው ችግሩን አባብሶታል፡፡ ጉዳዩ እያሳሰባቸው የሄደው የኢሕአዴግ ዋነኛ መሪዎችም እንዲህ ዐይነቱን አለመረጋጋትና ሥርዐተ አልበኝነት ለመቆጣጠር የመንፈሳዊ መሪዎች አስተዋፅኦ ወሳኝ ስለ መኾኑ ከስምምነት ላይ ደርሰዋል(እንደ ቀደሙት ሥርዐቶች ኹሉ ለቅቡልነት ከሚጠቀሙበት በተጨማሪ ማለት ነው)፡፡ ይኹንና በመንበሩ ላይ የነበሩት ፓትርያርኩ አቡነ መርቆሬዎስ አገር ለቀው እንዲወጡ በመደረጉ ክፍተት ተፈጥሯል፡፡
ይህ ጊዜ ነው ከ፲፱፻፸፬ ዓ.ም. ጀምሮ [ከኢየሩሳሌም ተሰደው] መኖርያቸውን አሜሪካን አገር ያደረጉ አንድ መንፈሳዊ አባት ወደ ኢትዮጵያ እንዲመጡ የተወሰነው፤ በጥሪው መሠረትም ወደ አገራቸው ሲገቡ መንግሥት የክብር አቀባበል አደረገላቸው፡፡ እኚኽ አባት ዛሬ በመንበረ ፕትርክናው የተሠየሙት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ነበሩ፡፡ ኾኖም ከሳምንት ሽር ጉድ በኋላ አቡነ ‹‹የኢዲዩ አባል ነበሩ›› የሚል ወሬ በአመራሩ አካባቢ በስፋት መሰራጨቱ ያልተጠበቀ ዱብ ዕዳ አስከተለ፡፡
ምክንያቱ ደግሞ ኢሕአዴግ እና ኢዲዩ በ፲፱፻፸ዎቹ መጀመርያ ትግራይ እና ጎንደር ውስጥ በርካታ መሥዋዕትነት ያስከፈለ ውጊያ ማድረጋቸው ብቻ አልነበረም፡፡ የመጀመርያዎቹ ሊቀ መንበሮች ስሁል ገሰሰ እና መሐሪ ተኽሌ(ሙሴ) ‹‹የተገደሉት በኢዲዩ ነው›› የሚለው ወሬ በድርጅቱ ውስጥ ከጫፍ ጫፍ የተናኘና የታመነበት ጉዳይ መኾኑ ነበር፡፡ በዚህም ላይ የህ.ወ.ሓ.ት መሪዎች ግራ ዘመምነት ተደማምሮ አቡነ ማትያስ በወቅቱ ወደ ታሪክነት ከተቀየረ ዓመታትን ባስቆጠረው ኢዲዩ ተፈርጀው ከታጩበት የፕትርክና መንበር ተገፈተሩ፡፡
ከዚህ በኋላ ነበር አብላጫውን የትጥቅ ትግል ዘመን በአሜሪካ ያሳለፉት አሰፋ ማሞ እና ብርሃነ ገብረ ክርስቶስ ‹‹ዉድብ›› የሰጠቻቸውን ተልእኮ ተቀብለው ወደ ዋሽንግተን ዲሲ ያመሩት፤ እናም ቀድሞም ትውውቅ ወደነበራቸው ብፁዕ አቡነ ጳውሎስ ዘንድ ሄደው ለፕትርክና ወንበር መታጨታቸውን አበሠሯቸው፡፡ በእንዲህ ያለ መንገድ መንግሥት የቀባቸው አቡነ ጳውሎስም እስከ ኅልፈታቸው ድረስ አወዛጋቢ መሪ ኾነው ዘልቀዋል፡፡
(በነገራችን ላይ በአሜሪካ ለመጀመርያ ጊዜ ከሲኖዶሱ ተነጥሎ የቆመ ቤተ ክርስቲያን የመሠረቱት አቡነ ጳውሎስ እንደነበሩ ይነገራል፡፡ አቡኑ ደርግ ለጥቂት ዓመታት አስሮ ከለቀቃቸው በኋላ ወደ አሜሪካ ሄደው የፈጣሪያቸውን ሰማያዊ መንግሥት ሲሰብኩ ቆይተው የህወሓት ሠራዊት ክንዱ እየበረታ በቁጥጥሩ ሥር ያዋላቸው ከተሞችም እየበዙ ሲሄዱ እርሳቸውም ስብከታቸውን ወደ ትግርኛ ቋንቋ ከመቀየራቸውም በላይ ለ‹ነጻ አውጭ›ው ድርጅት የገንዘብ ድጋፍ ያሰባስቡ ጀመር፡፡ የሥርዐት ለውጥ መደረጉን ተከትሎም በፖሊቲከኞች በተቀነባበረ ሤራ ከአቡነ ጳውሎስ ጋራ ቦታ የተለዋወጡት አቡነ መርቆሬዎስም፣ እዚያው አሜሪካ ‹ተተኪ›ያቸው የጀመሩትን ብሔር ተኮርና ከሲኖዶሱ የተገነጠለ ቤተ ክርስቲያን አስፋፍተው ዛሬ ለደረሰበት ‹የጎንደሬ ማርያም›፣ ‹የትግሬ ገብርኤል›. . .ለተሰኘ አሳፋሪ ክፍፍል ዳርገውታል፡፡ በርግጥ ለአቡኑ[አቡነ መርቆሬዎስ] ከአገር መውጣት የኢሕአዴግ እጅ እንዳለበት እንድናምን የሚያስገድደን በቅርቡ ታምራት ላይኔ ‹‹በእኔ ፊርማ ነው ያባረርናቸው›› ማለቱን ዊኪሊክስ ካደረሰን መረጃ በተጨማሪ በትጥቅ ትግሉ ዘመን ህወሓት በተቆጣጠራቸው በትግራይና ወሎ ነጻ መሬቶች በሚገኙ ከተሞች ያሉ ነዋሪዎችን ቀስቅሶና አደራጅቶ ፓትርያርኩ ላይ ‹‹ሽጉጥ ታጣቂ ጳጳስ››፣ ‹‹ቀይ ደብተር ያለው/ለኢሠፓ አባላት የሚሰጥ/ የሸንጎ ተወካይ››. . .የመሳሰሉትን መፈክሮች እያሰሙ በተቃውሞ ሰልፍ እንዲያወግዟቸው ማስተባበሩን ስናስታውስ ነው)፡፡
ዛሬስ የሃይማኖት ነጻነት የት ድረስ ነው?
ከላይ ታሪክን ወደ ኋላ መለስ ብዬ በደምሳሳው ለመጠቃቀስ እንደሞከርኹት፣ ኢሕአዴግ በሃይማኖት ጉዳይ እጁን ጣልቃ ማስገባት የጀመረው ክንዱ ሳይፈረጥም ገና በረሓ ላይ ሳለ ነበር፡፡ በዚህ ኹኔታ የተጀመረው ጣልቃ ገብነት ዛሬም ድረስ ተባብሶ ቀጥሏል፤ ምንም እንኳ በሃይማኖት ጉዳዮች ጣልቃ እንደማይገባ በደፈናው ከሕገ መንግሥቱ አንቀጽ ፲፩ን በመጥቀስ በተደጋጋሚ ለማስተባበል ቢሞክርም ያለፉት ዓመታት ተጨባጭ ተግባሮቹ የሚመሰክሩት ግልባጩን ነው፡፡ ድርጅቱ ራሱም ቢኾን ጥያቄው በተነሣ ቁጥር ከሕገ መንግሥቱ አንቀጽ ፲፩ን የሚጠቅሰው ለስሙ እንጂ ሕጉ ተግባራዊ አለመኾኑን ሳይረዳ ቀርቶ አይደለም፤ አቶ ተፈራ ዋልዋም በ፲፱፻፺፰ ዓ.ም. ኅዳር/ታኅሣሥ ወር ከታተመችው ሐመር መጽሔት ጋራ ባደረጉት ቃለ መጠይቅ ጉዳዩን አስመልክቶ የሰጡት አስተያየት የኢሕአዴግን አጭበርባሪነት ፍንትው አድርጎ የሚያሳይ ነው፡-
‹‹ኢሕአዴግ እኮ የሚመራው መንግሥት በደርግም ጊዜ፣ በኃይለ ሥላሴም ጊዜ እንደሚታወቀው ‹የቤተ ክርስቲያን ሥራ አስኪያጅ ሹምልን› ተብሎ ተጠይቆ ‹የለም ራስዋ ቤተ ክርስቲያኒቱ ትሾማለች እንጂ እንደ ቀድሞው መንግሥት አይሾምላችኁም› የሚል መልስ የሰጠ መንግሥት ነው፡፡››
በሕዝበ ሙስሊሙ ተመርጦ ለእስር የተዳረጉት የኮሚቴ አባላትም በአንድ ወቅት ለሚመለከተው የመንግሥት ባለሥልጣን የጻፉት ደብዳቤ ጣልቃ ገብነቱን በግልጽ ያሳያል፡-
‹‹መንግሥት እንደ መንግሥት ሕዝቡ ተበድዬአለኹ፤ ምርጫ ይካሔድ፤ የመጅሊሱን አመራር አላመንኹበትም፤ ውክልና የለውምና ሕገ ወጥ ነው ያለውን አካል ሕገ ወጥነቱ እንዲረዝም ምርጫውን እርሱው እንዲያካሒድ መወሰን ሕዝብን ግራ አጋቢ ነው፡፡››
ሥርዐቱ በሃይማኖት ጉዳዮች ላይ ጣልቃ እንደማይገባ ለማሳመን ይህን ያህል ቢዳክርም በቅርቡ ‹‹የፀረ አክራሪነት ትግል የወቅቱ ኹኔታና ቀጣይ አቅጣጫዎች›› በሚል ርእስ የተዘጋጀው ባለ 44 ገጽ ሰነድ፣ መንግሥት በዘወርዋራ በሃይማኖት ጉዳይ ጣልቃ መግባቱን ሙሉ በሙሉ የሚያምን ኾኖ አግኝቸዋለኹ፤
‹‹የመንግሥት መዋቅራትን ሴኩላር መንግሥት መኾናችንን ዐውቆ የመንግሥትን መዋቅር ተጠቅሞ የራሱን ሃይማኖት መሠረት ያደረገ አገልግሎት ከመስጠት ሙሉ በሙሉ ያልጸዳ መኾኑን የተለያዩ ጥቂት የማይባሉ ገሃድ የወጡ መገለጫዎች አሉ፡፡ እንዲያውም የትኛውም አክራሪ ኃይል ከመዋቅር(ከመንግሥት) አካል በርታ ሳይባልና ሽፋን ሳይሰጠው የሚንቀሳቀስ እንደሌለ አማኞቹ በገሃድ ይገልጻሉ፡፡››
መቼም ይህን ያነበበ ዜጋ መረጃው የተገኘው በመንግሥት ከተዘጋጀ ሰነድ ሳይኾን በኒዮሊበራሊስት›ነት ከተፈረጁት እነ‹‹ሂዩማን ራይትስዎች›› እና ‹‹አምንስቲ ኢንተርናሽናል›› ቢመስለው አይደንቅም፡፡ ሐቁ ግን ይኸው ነው፡፡ አገዛዙ ላለፉት ኻያ ሁለት ዓመታት መንግሥት እና ሃይማኖት እንዲለያዩ ማድረጉን ሲለፍፍ ከመቆየቱም በላይ በሃይማኖት ጉዳይ ጣልቃ መግባቱን የዘገቡ ጋዜጠኞችን ከሥሦ ዛሬም ድረስ ፍርድ ቤት እያመላለሳቸው እንደኾነ ይታወቃል፡፡ ከዚህ አንጻር ይመስለኛል ዓለም አቀፍ ማኅበረሰቡን ጨምሮ በርካታ ኢትዮጵያውያን በእስር ላይ የሚገኙት የእነ አቡበበከር መሐመድ ክሥ፣ የሼኽ ኑር ሑሴን ግድያ፣ በማኅበረ ቅዱሳን ላይ እየተሰነዘሩ ያሉ ውንጀላዎችንና መሰል ፍረጃዎችን አምኖ ለመቀበል የተቸገሩት፡፡
ያም ኾነ ይህ ሃይማኖትን ብቻ ሳይኾን ዕድርና ዕቁብንም ሳይቀር ‹ካልተቆጣጠርኹ ሞቼ እገኛለኹ› በሚል የቁጥጥር ልክፍት የተያዘው ኢሕአዴግ፣ በተለይም 99.6 ድምፅ አግኝቼ አሸንፌአለኹ ብሎ ካወጀበት ከምርጫ ፳፻፪ ማግሥት ጀምሮ ‹‹አናት ላይ ከተቀመጡ መሪዎቻቸው በቀር ሙሉ በሙሉ አልተቆጣጠርናቸውም›› የሚላቸውን የኦርቶዶክስ ክርስትና እና የእስልምና እምነቶችን ዋነኛ አጀንዳ አድርጎ እየሠራ ለመኾኑ በርካታ መረጃዎች አሉ፡፡
በ፳፻፫ ዓ.ም. ኅዳር ወር ‹‹የአምስት ዓመት የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድና የኢትዮጵያ ሕዳሴ›› በሚል ርእስ በአቶ መለስ ዜናዊ ተሰናድቶ የተሰራጨው ጥራዝ፣ የሥርዐቱን ቀጣይ አካሔድና ይህን ኹናቴ የሚያሳይ ከመኾኑም በተጨማሪ ዛሬም ድረስ በሃይማኖት ጉዳዮች ላይ መንግሥት የሚያዘጋጃቸው ሥልጠናዎችም ኾኑ ጥናታዊ ጽሑፎች መነሻ ሐሳባቸው ይኸው ዳጎስ ያለ ጥራዝ እንደኾነ ይነገራል፡፡
ጥራዙ የእምነት ተቋማትን በተመለከተ ከገጽ 128 – 132 ያካተተው ሐሳብ፣ ለኪራይ ሰብሳቢነት ዋነኛው ምክንያት ‹‹የሃይማኖት አክራሪነት›› መኾኑን ከጠቃቀሰ በኋላ ችግሩን ‹‹ተኪ የኾነ ልማታዊ አስተሳሰብ›› በማምጣት ማስወገድ እንደሚቻል ይመክራል፡፡ ይህን ከግብ ለማድረስ ደግሞ ሚዲያዎችንና ተያያዥነት ያላቸውን ማኅበራት መጠቀሙ አዋጭ እንደኾነ ይተነትናል፡፡ የኢሕአዴግ አባላት በየእምነት ተቋሞቻቸው ያሉ ማኅበራትን በዐይነ ቁራኛ መከታተል እንዳለባቸውም ያሳስባል፡- ‹‹[የግንባሩ አባላት] ከእምነት ተቋማት ውጭ ባላቸው አደረጃጀት አማካይነት በሰፊው መሥራት አለብን››፡፡ በርግጥም የእስልምና እምነት ተከታዮች ‹‹የሃይማኖት ነጻነት ይከበር›› የሚል ተቃውሟቸውን ባጠናከሩበት ሰሞን፣ አዲስ አበባን ጨምሮ በተለያዩ ክልሎች የሚገኙ ሙስሊም አባላቱን ለብቻ እየሰበሰበ እንቅስቃሴውን የማክሸፍ ሥራ መሥራት ግዴታቸው መኾኑን የሰበከው ከዚኹ አቶ መለስ ዜናዊ አዘጋጅተውት ከነበረው ጥራዝ ነው ብሎ መከራከር ይቻላል፡፡
ከጣልቃ ገብነት ወደ ጠቅላይ ተቆጣጣሪነት
በዘወርዋራም ቢኾን በሃይማኖት ጉዳይ ጣልቃ መግባቱን ሙሉ በሙሉ የሚያምነው ከላይ የተጠቀሰው ሰነድ በአገሪቱ ‹‹የሃይማኖት አክራሪነት›› መከሠቱን ካተተ በኋላ ዋነኛ ተጠያቂዎች አድርጎ ያቀረበው እንደወትሮው ኹሉ ለተደጋጋሚ መሸማቀቅ የተዳረጉትን መንፈሳዊ መሪዎችንና ማኅበራትን ሳይኾን የመንግሥት መዋቅርን ነው፡-
‹‹የመንግሥት መዋቅራችን አካል ኾነው አክራሪነቱን በድብቅም በገሃድም የሚደግፍ አካል በፌዴራልም በክልልም ከሞላ ጎደል የሚታወቁ ናቸው፡፡ እነዚኹ አካላት በተቻላቸው ኹሉ በመድረክ ጤናማ እየመሰሉ የሚኖሩ ናቸው፡፡ የፀረ አክራሪነቱን ትግል ማጧጧፍ የሚፈልገውን መዋቅር አካልም ይኹን የሕዝብ አካል በተደራጀና በመረባቸው አማካይነት ከፍተኛ ጫና የሚያሳድሩ፣ የተቋማቸውን ምቹ ኹኔታ ተጠቅመው በፀረ አክራሪነት የሚንቀሳቀሱትን አካል የሚቀጡ፣ አሉባልታ እየፈጠሩ የሚያሸማቅቁ፣ ኾን ብለው ድጋፍ የሚነፍጉና በሐሰት ምስክርም ጭምር ዜጎችን የሚያሳስሩ ናቸው፡፡ የመንግሥትን አቅሞች ተጠቅመው አክራሪነትን የሚያስፋፉና ከአክራሪነት እንቅስቃሴ ጋራ በተለያዩ ጥቅሞች የተሳሰሩ ናቸው፡፡››
እነኾም በእንዲህ ዐይነቱ የውንብድና ተግባር የተሠማሩ ባለሥልጣናት የተሰባሰቡበት፣ ውንብድናው መኖሩንም የሚያምን መንግሥት አንድም ተጠያቂዎቹን ለሕግ አሳልፎ አለመስጠቱ፣ አልያም ሥልጣኑን በፈቃዱ አለመልቀቁ በአገር ላይ ሊያስከትል የሚችለውን አደጋ ለመረዳት ነቢይነትን አይጠይቅም፡፡ በአናቱም ሥርዐቱ ለሕግ የበላይነት ተገዥ አለመኾኑን የሚያሳየው በዚህ ደረጃ ‹‹ችግሩን ተረድቸዋለኹ›› እያለም እንኳ፣ ዛሬም የቅጣት ብትሩን ያሳረፈው ከመዋቅሩ ጋራ አንዳችም ንክኪ በሌላቸው መንፈሳዊ መሪዎች ላይ መኾኑ ነው፡፡ በርግጥም ይህ ዐይነቱ አሠራር ከዐምባገነን አስተዳደር መገለጫዎች አንዱ ነው፡፡ ኢሕአዴግም ያለፉትን አራት ምርጫዎች ጨምሮ በተለያየ ጊዜ የዴሞክራሲም ኾነ የሰብአዊ መብትን በዐደባባይ መጣስ፣ የሐሰት ክሦችንና ፍረጃዎችን እንደ ምክንያት መጠቀም ነባር ስልቱ እንደኾነ ይታወቃል፡፡ በማኅበረ ቅዱሳን ላይ እየዘረዘረ ያለው የፈጠራ ውንጀላ እና ለሙስሊሙ ‹‹መፍትሔ አፈላላጊ›› ተብለው በተመረጡት የኮሚቴ አባላት ላይ የወሰደው ዕመቃ መግፍኤ ይኸው ነው፡፡
ሌላው ቀርቶ ከዚህ ቀደም በተቃዋሚ ፓርቲ አባላት ላይ ስለሚፈጸመው የግፍ ግድያዎች ይሰጥ የነበረውን ምክንያት በመንፈሳዊ ሰዎችም ላይ ያለአንዳች የይዘት ለውጥ ለመጠቀም አላመነታም፡፡ እንደሚታወሰው በድኅረ ምርጫ – ፺፯ በአምቦና በኢተያ በታጣቂዎች የተገደሉትን የኦሕኮ አባላት ከተፈጥሮ ሕመም ጋራ አያይዞት ነበር፡፡ በያዝነው ዓመት ጥቅምት ወር መጀመርያ ላይ በተካሔደው የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ዓመታዊ ስብሰባ ላይ ደግሞ የምዕራብ ወለጋና አሶሳ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ አቡነ ኄኖክ ‹‹ቤጊ›› ወረዳ በመንግሥት ባለሥልጣናት ተፈጸመ ያሉትን ግድያ ለፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስትር ተወካይ፡-
‹‹በቤተ ክርስቲያን 70 ሜትር ርቀት ላይ የሌላ እምነት ተከታዮች የራሳቸውን ቤተ ክርስቲያን እንዲሠሩ መፈቀዱን ከተቃወሙት መካከል አንድ ዲያቆን ተደብድቦ በሦስተኛው ቀን ሕይወቱ ሲያልፍ ‹በወባ በሽታ ነው የሞተው› ተብሎ ለፍርድ ቤቱ የሐሰት ማስረጃ ከዶክተሩ እንዲቀርብ ታዘዘ›› ማለታቸውን መጥቀሱ ለጉዳዩ አስረጅነት በቂ ይመስለኛል፡፡
የኾነው ኾኖ አገዛዙ በዘረጋው ግዙፍ መዋቅሩ ውስጥ ያልታቀፉ ማኅበራትንም ኾነ የሃይማኖት ተቋማትን የስጋት ምንጭ አድርጎ ማየቱ፣ በእምነት ነጻነት ላይ ጣልቃ ለመግባትም ኾነ ምንም ዐይነት ገለልተኛ ተቋማት እንዳይኖሩ ዕንቅልፍ ዐጥቶ መሥራቱን ያሳያል ብዬ አስባለኹ፤ በሚቆጣጠራቸው የኤሌክትሮኒክስና የኅትመት ሚዲያዎች ቀን ከሌት የፕሮፓጋንዳ ከበሮ የሚመታበት የ‹አክራሪነት› ፍረጃም መነሾው ይኸው ይመስለኛል፡፡ ሰነዱን ከዚህ ቀደም ካየናቸው ለየት የሚያደርገው፣ በመንግሥት መዋቅር ውስጥ አሉ ከሚላቸው ወንበዴዎች በተጨማሪ የሚከሥሣቸውን መንፈሳውያን ማኅበራት በደፈናው ‹‹በክርስትና እምነት ውስጥ ያሉ›› ብሎ አለማለፉ ነው፤ ቃል በቃል እንዲህ ይላልና፡-
‹‹በማኅበረ ቅዱሳን ውስጥ የመሸጉ የትምክህት ኃይሎች ጽንፈኛ የፖሊቲካ ኃይሎች አካል በመኾን በጋዜጣና በመጽሔት ሕዝባችንን ለዐመፅና ለሁከት ለማነሣሣት ከፍተኛ ጥረት አድርገዋል፡፡. . .በራሳችንም ኃይል እንደሌላው ሰልፍ ልንወጣ ይገባል በሚል የዐመፅና የሁከት ቅስቀሳ ለማድረግ ይፈልጋሉ፡፡››
ይህ ኹኔታ መንግሥት መንፈሳውያን ማኅበራትን ጠቅልሎ ለመቆጣጠር በመፈለጉ ለተቃዋሚዎች ያሠመረውን ‹ቀይ መሥመር› መጣሱን ያሳያል፡፡ አስገራሚው ጉዳይ ደግሞ የሃይማኖት ተቋማትን የፖሊቲካ መሣርያ አድርጎ መጠቀሙ አልበቃ ብሎት ወደ መንፈሳውያን ማኅበራቱ መዞሩ ነው፡፡
በገሃድ እንደሚታወቀው የክርስትና ይኹን የእስልምና እምነት መሪዎች በተለያየ ጊዜ ከሥርዐቱ ጎን ተሰልፈው ‹ናዳን ለመግታት› ያደረጉት አበርክቶ በቀላሉ የሚገመት አለመኾኑ ነው፡፡ በርግጥም ‹‹የቄሣርን ለቄሣር›› በሚል አስተምህሮ የሚያድሩ፣ ደመወዛቸው በምድር ያልኾኑት መንፈሳውያን አባቶች በድኅረ ምርጫ – ፺፯ ሕፃናትን ሳይቀር በጥይት የፈጀውን ሥርዐት ማውገዝ ቀርቶ መምከር ያለመፈለጋቸው ምክንያት ፍርሃት ብቻ ሳይኾን የግል ጥቅምን ታሳቢ ያደረገው ግንኙነታቸው ያሳደረው ተጽዕኖ ይመስለኛል፡፡ ከቅዱሳን መጻሕፍት ይልቅ አብዮታዊ ዴሞክራሲን ‹አዳኝ› አድርገው የመቀበላቸው መግፍኤ ይኸው ነው፡፡ ኢሕአዴግም ‹ነገረ መለኰት›ን ለሲኖዶሱና ለመጅሊሱ እስከ ማስተማር ድረስ የደፈረው የእነርሱ ለሁለት ጌታ መገዛት ነው – ለገንዘብ እና ለጌታ፡፡
የሲኖዶሱ እና የመንግሥት ፍጥጫ
በኦርቶዶክስ ክርስትና እምነት ሕገ ቤተ ክርስቲያን ሲኖዶስ ከፍተኛውን ሥልጣን የሚይዝ ሲኾን ፓትርያርክንም የመሾምና የመሻር ሥልጣን አለው፡፡ ኾኖም ይህ የላዕላይ መዋቅር እስከ አቡነ ጳውሎስ ኅልፈት ድረስ ለእርሳቸውም ኾነ ለሥርዐቱ ሰጥ ለጥ ብሎ የሚገዛ ጥርስ የሌለው አንበሳ በመኾኑ ለትችት ከመዳረጉም በላይ በምእመናን ዘንድ ለመንፈሳውያን አባቶች የሚሰጠው ክብርም ተነስቶት ቆይቷል፡፡
ይኹንና በያዝነው ዓመት ጥቅምት ወር መጀመርያ በተካሄደው የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ፴፪ ዓመታዊ ስብሰባ ላይ ከመንግሥት የተወከሉ ሓላፊዎች÷ ‹‹የብዝኃነት አያያዝ አክራሪነት/ጽንፈኝነት ዝንባሌዎቹና መፍትሔዎቹ›› በሚል ርእስ ያቀረቡትን ጥናት ተከትሎ ስድስት ጳጳሳት ቀድሞ ባልታየ መልኩ ጠንካራ ተቃውሞ ማቅረባቸው፣ በብዙዎች ዘንድ የሃይማኖት መሪዎች ለመንፈስ ልዕልና ሊገዙ ይኾን? ከምድራዊው ይልቅ ሰማያዊውን ሊመርጡ ይኾን? ‹‹እመን እንጂ አትፍራ›› የሚለውን አስተምህሮአቸውን ሊተገብሩ ይኾን? የሚል ጥያቄ አጭሯል፡፡
በዕለቱ የመጀመርያው ተናጋሪ የነበሩት የሰሜን ወሎና ዋግ ኽምራ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ አቡነ ቄርሎስ በጥናቱ ላይ መቻቻል አስመልክቶ የቀረበውን ድምዳሜ እንዲህ ሲሉ ነበር ያጣጣሉት፡-
‹‹ይኼ አክራሪነት፣ ጽንፈኝነት የሚለውን ቋንቋ እናንተው ናችኹ ያሰማችኹን፤ ከዚህ በፊትም አይታወቅም፣ በደርግም ይኹን በሌላ፡፡ እንደገና ደግሞ ብዙ ጊዜ ጽንፈኝነት፣ አክራሪነት እያላችኹ ዕድሜ ሰጥታችኹ ያበለጸጋችኋቸው እናንተው ናችኹ፡፡››
በርግጥም አቡኑ የተቹት ሥርዐቱ የፕሮፓጋንዳው ፋሽን ያደረገውን ‹‹መቻቻል››ን ብቻ አይደለም፤ ‹‹በመቃብሬ ላይ ነው የሚሻሻለው›› የሚለውን የመሬት ፖሊሲንም ነው፡፡. . . ‹‹በፊት መሬትም ሕዝብም የነገሥታቱ ነበር፤ አሁንስ የማን ነው? ይልቁንም ከአንድ ቤት ‹ግድግዳው የቤቱ ባለቤት ነው፤ ሳሎኑ የመንግሥት ነው› የሚለው ዐዋጅ የአሁን አይደለም እንዴ? ለኢትዮጵያዊነቱ ዋስትና የለውም፤ ይኼ የእኔ ነው የሚለው ከሌለ ምንድን ነው? ይህች የእኔ የኢትዮጵያዊነቴ መገለጫ ናት ካላለ ምንድን ነው ኢትዮጵያዊነት? አሁንም መሬቱም ሕዝቡም የእናንተው ኹኖ ሳለ ለፊቱ፣ ለነገሥታቱ መስጠታችኹ በምን ተመልክተውት ነው?››
የደቡብ ጎንደር ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ አቡነ እንድርያስም በሚያስተዳድሩት አካባቢ ያለውን የመንግሥት ጣልቃ ገብነትና ተጽዕኖን ከዘረዘሩ በኋላ ለተሰነዘረው ፍረጃና ማሸማቀቂያ እንዲህ የሚል አስተያየት ሰጥተዋል፡-
‹‹የተበደለ ሰው ሲናገር ‹ፖሊቲካ ተናገረ› እየተባለ የውሸት ውሸት ሲያተራምሱን የሚኖሩ ብዙዎች ናቸው፡፡. . .እንዴ! የመንግሥት ሥልጣን የተረከቡ ወንድሞች የእኛን አፍ፣ የእኛን አንደበት ብቻ ነው እንዴ የሚጠብቁት፤ ለሌሎች ሞራል ይሰጣሉ ማለት ነው?. . .ለምንድን ነው ግን በሽፋንነት የምትጠቀሙብን? መንግሥት እኛን ሽፋን አድርጎ ነው ሲበዘብዘን የምንኖረው፡፡ ሌባውም ቀጣፊውም ሰርጎ ገቡም ሲያጭበረብረን ሲያታኩሰን መንግሥትን ሽፋን አድርጎ ነው፡፡››
የወላይታ ሀ/ስብከት ሥራ አስኪያጅም በተመሳሳይ መልኩ መንግሥት በሃይማኖት ጉዳይ ጣልቃ መግባቱን ቤተ ክርስቲያኗ ስትቃወም ጉዳዩን ወደ ፖሊቲካ እየቀየሩ ማስፈራራቱ እንደተለመደና ለቀብር ማስፈጸሚያ የሚኾን መሬት ከመስተዳድሩ በሚጠየቅበት ጊዜ የሚሰጠው መልስ በሐሰት መወንጀል እንደኾነ ከገለጹ በኋላ ጉዳዩ መፍትሔ ካላገኘ ሊከተል ስለሚችለው ስጋታቸውን ተናግረዋል፡-
‹‹ ‹የፖሊቲካ ጉዳይ ነው፤ ሕዝብን በሃይማኖት ሽፋን ታንቀሳቅሳላችኹ› እየተባልን እየተሸማቀቅን ያለንበት ኹኔታ ነው ያለው፡፡ ይህን እንዴት ታዩታላችኹ? መቻቻልስ የሚመጣው ከምን አኳያ ነው? ዝም ብለን የምንቀመጥ ከኾነ ምናልባት ሓላፊነት ለመውሰድ ስለሚከብደን ይህን ወርዳችኹ እንድትፈትሹ ለማለት ነው፡፡››
(በነገራችን ላይ የአጠቃላይ ጉባኤው ዓመታዊ ስብሰባ በተጠናቀቀ ማግሥት ከማኅበረ ቅዱሳን አመራር ሦስት አባላት ወደ ፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር ተጠርተው ዶ/ር ሽፈራውን ጨምሮ ከሚመለከታቸው ሓላፊዎች ጋራ ውይይት ማድረጋቸውን ከመሥሪያ ቤቱ ምንጮቼ ሰምቻለኹ፡፡ ሚኒስትሩ ከማኅበሩ አመራሮች ጋራ ለመወያየት የተገደዱት ካልተጠበቀው የሲኖዶሱ አባላት ድፍረት ጀርባ ‹የማኅበረ ቅዱሳን እጅ አለበት› የሚል ጥርጣሬ በመያዙ ነው፡፡ በውይይቱም ላይ የተንጸባረቀው የአባላቱ መለሳለስ፣ ማኅበሩን አክራሪ ብለው እንደማያምኑና ከዚህ ቀደም የተሰራጩት ወንጃይ ሰነዶችን ሳይቀር ‹አናውቃቸውም› እስከማለት የደረሰ እንደነበር አረጋግጫለኹ፡፡ ይኹንና ይህ እሳት ማጥፊያ ስልት ከሥርዐቱ ጋራ የቆየ መኾኑ ይታወቃል፤ የማኅበሩ አመራርም ይህ ይጠፋዋል ብዬ ባላስብም፤. . .)
የኾነው ኾኖ [በአጠቃላይ ጉባኤው ዓመታዊ ስብሰባ] ከፌዴራል ጉዳዮች ከመጡት ሦስት ተወካዮች መካከል አቶ ገዛኽኝ ጥላሁን አብዛኛውን ጥያቄ በተመለከተ የሰጡት ምላሽ የወከሉት መንግሥት ዛሬም በተሳሳተ ታሪክ ንባብ እያሸማቀቀ፣ እያስፈራራ፣ ሕግን እየጠመዘዘ፣ እስር ቤት እየከተተ. . . የፖሊቲካ ጥቅሙን ማስከበር ላይ ያተኮረ መኾኑን ያሳያል፡፡ ሓላፊው ማስጠንቀቂያውን ያስተላለፉት እንዲህ በማለት ነው፡-
‹‹መጀመርያ ግንዛቤ ላይ እንሥራ በሚል ርምጃ አልወሰድንም፡፡ ኮሽ ባለ ቁጥር ወደ ቃሊቲ መፍትሔ አይኾንም፡፡››
. . .‹ቃሊቲ›ን ምን አመጣው? መቼም ለጣልቃ ገብነቱ ከዚህ የበለጠ ማሳያ መፈለግ ‹ዐውቆ የተኛን. . .› እንደመኾን ነው፡፡ ‹‹መንግሥት እና ሃይማኖት የተለያዩ ናቸው›› ብሎ መከራከሩም ጊዜ ያለፈበት ፕሮፓጋንዳ ይመስለኛል፡፡ እናም የተሻለው መንገድ ከላይ በጠቀስኹት ሰነድ ‹‹በየማእከላዊ ኮሚቴው በሚካሄደው የስምሪት ተግባር በፀረ አክራሪነት ትግል ላይ ያለው የእያንዳንዱ ግለሰብ ቁመና መፈተሽ አለበት›› ተብሎ የተገለጸውን ማሳሰቢያ በፍጥነት በመተግበር፣ በቅድሚያ ራስን ከአክራሪነትና አሸባሪነት ማራቅ ነው፡፡ ማረጋገጫ የማይቀርብበትን አፈ ታሪክንም እየለቃቀሙ በአንድ ሃይማኖት ላይ መለጠፉ አስተማሪ አይመስለኝም፡፡
ከዚህ ባለፈ ‹‹የሃይማኖት ኮማንድ ፖስት አቋቁመን ለችግሩ እልባት እንሰጣለን›› የምትሉት ጉዳይ በቀጥታ መንግሥት በሃይማኖት ጉዳይ እጁን ማስገባቱን በዐደባባይ ከማመን ያለፈ የፖሊቲካ ጠቀሜታ አይኖረውም፡፡ ጳጳሳቱም ኾኑ ሼኾቹ ሓላፊነትና ግዴታቸው ሰማያዊውን መንግሥት መስበክ እንጂ ከሰላይ አለቆችና ከፖሊስ አዛዦች ጋራ ቢሮ ዘግተው የመንፈስ ልጆቻቸውን ‹‹ትምክህተኛ››፣ ‹‹አሸባሪ››፣ ‹‹አክራሪ››. . .እያሉ እንዲፈርጁ መፈታተኑ ያልታሰበ ሕዝባዊ ቁጣ መቀስቀሱ አይቀርም፡፡

2013 ኖቬምበር 9, ቅዳሜ

በገለልተኛ አስተዳደር ስር የሚኖሩትን አጥቢያዎች ቁጥር በአንድ እንደሚቀንስ ይጠበቃል

  • ‹‹እግዚአብሔር ቅዱስ ፍቃዱ  ሆኖ ወደ ህብረትና አንድነታችን አንደምንመለስ ትልቅ ተስፋ ነው ያለኝ፡፡›› ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ ከ12 ዓመት በፊት ካደረጉት ቃለ መጠይቅ የተወሰደ

(አንድ አድርገን ጥቅምት 29 2006 ዓ.ም)፡- ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማቲያስ ለሁለት አስርተ ዓመታት ወደኖሩበት አሜሪካ ጥቅምት 27 2006 ዓ.ም ለመጀመሪያ ጊዜ በዘመነ ፕትርክናቸው እንደሚሄዱ ሰሞኑን ከተለያዩ ዜና ማሰራጫዎች ለመረዳት ችለናል። በመረጃው መሰረት ብፁዕነታቸው 6ተኛ ፓትርያርክ ተብለው ከተሸሙ በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ ጥቅምት 27 ወደ አሜሪካ አቅንተዋል ፡፡ ከብፁዕነታቸው ጋር ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ኄኖክ እና ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ አብረዋቸው እንደተጓዙ ታውቋል ፡፡አካሄዳቸው በዋሽንግተን ዲሲ የሚገኘውን የመድኅኒዓለም ቤተክርስቲያን የቅዳሴ ቤት ለማክበር እንደሆነ ለመረዳት ተችሏል።


እንደሚታወቀው ይህ አጥቢያ በብፁዕነታቸው ከተመሰረተ ጀምሮ እስከ አሁን ድረስገለልተኛበሚባል አስተዳደር መቆየቱም ይታወሳል። በዚህ ታሪካዊ የብፁዕነታቸው ጉዞም ይህንን አጥቢያ ወደ እናት ቤተክርስቲያን አስተዳደር እንደሚመልሱት እና በቀጥታ በቅዱስ ሲኖዶስ በሚሾመው ሊቀ ጳጳስ እንደሚተዳደር ይጠበቃል። በዚህም በዋሺንግተን ዲሲ አካባቢ በገለልተኛ አስተዳደር ስር የሚኖሩትን አጥቢያዎች ቁጥር በአንድ እንደሚቀንስ እና መልካም እርምጃ እንደሚሆን ይጠበቃል። ሌሎችስ በአሜሪካ እና በተለያዩ የአውሮፓ ምድር ራሳቸውን ገለልተኛ ብለው የሚገኙ የአብያ ክርስቲያናት አስተዳዳሪዎች ምን ይማሩ ይሆን? ከዚች ከአንዲት ቤተክርስቲያን ተገሎ እስከመቼ ይኖራል? እንደ ብዙዎች ምዕመናን አስተያየት ወደፊት እግዚአብሔር በፈቀደው ቀን በውጭ ሀገር የተመሰረተው ሲኖዶስ ከአዲስ አበባው ቅዱስ ሲኖዶስ ጋር እንደሚቀላቀል እና አንድ እንደሚሆን እምነታው ነው ፤ የዛኔ ደግሞ አሁን ላይ ራሳቸውን ገለልተኛ ብለው የተቀመጡት ሌላ ፈተና ይሆናሉ ብለው ሃሳባቸውን ይገልጻሉ ፡፡ ዛሬም በነ አቶ ወይም ዶክተር እከሌ መመራት ወይስ ቀደምት አባቶቻችን በሰሩልን ሥርዓት መቀጠል? እኛ እኮ አባቶቻችን የሰሩልን የእምነት ስርዓት አስቀጣይ እንጂ እንደ አዲስ ጀማሪ መሆን መቻል የለብንም………ይህ መልካም ጅምር ነው ! ቸር ያሰማን

2013 ኖቬምበር 5, ማክሰኞ


ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ በአሜሪካ ሐዋርያዊ ጉብኝት ያደርጋሉ

His Holiness Abune Mathias
ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት (ፎቶ: ማኅበረ ቅዱሳን)
  • ለ10 ዓመታት (ከ፲፱፻፸፬ – ፲፱፹፬ ዓ.ም.) በስደት፣ ለ15 ዓመታት (፲፱፹፬- ፲፱፻፺፱ ዓ.ም.)  በሐዋርያዊ አገልግሎት ቆይተውበታል፡፡
  • በግርማዊ ቀዳማዊ ንጉሠ ነገሥት ዐፄ ኃይለ ሥላሴ ድጋፍ በኒውዮርክ ከተመሠረተውና የጃማይካ ተወላጆች ከሚገኙበት የኒውዮርክ ቅድስ ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ቀጥሎ የመጀመሪያውን የመድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን በዋሽንግተን ዲሲ (መካነ ሕይወት መድኃኔዓለም) አቋቁመዋል፡፡
  • ገለልተኛ አብያተ ክርስቲያን መዋቅርንና የሁለተኛ ሲኖዶስ  ምሥረታን በመቃወም የእናት ቤተ ክርስቲያን እንቅሰቃሴመርተዋል፡፡
  • የትኛውም አካል ባላሰበበት ዘመን ስለ ዕርቀ ሰላም አሳስበዋል፡፡ ለመጀመሪያ ጊዜ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስንና ሌሎች በስደት የሚገኙ አባቶችን በአትላንታ ጆርጅያ በአካል አግኝተው ከተወያዩ በኋላ ለኢትዮጵያው ቅ/ሲኖዶስ መልእክት በመላክ ዕርቀ ሰላም እንዲጀመር መሠረት ጥለዋል፡፡
  • ቃለ ዐዋዲው ለሰሜን አሜሪካ ሀ/ስብከት እንዲስማማ ኾኖ ወደ እንግሊዝኛ የተተረጎመው በቅዱስነታቸው የሰሜን አሜሪካ ቆይታ ዘመን ነው፡፡
  • ‹‹ተዐቀቡኬ እምሐሳውያን ነብያት›› በሚል ርእስ በዋሽንግተን ዲሲ በተዘጋጀው ከፍተኛ ጉባኤ የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ኑፋቄ ሤራ ቤተ ክርስቲያንን እያወካት መኾኑን በመግለጽ ካህናትና ምእመናን በብርቱ እንዲቋቋሙት አጠንክረው አስተምረዋል፤ በእመቤታችን ቅድስና ላይ የስሕተት ትምህርት ለማስተማር የሞከሩ ካህናትን በመምከር ከስሕተታቸው አልመለስ ያሉትን አውግዘው በመለየት ሃይማኖታዊ ቅንዐታቸውን በተግባር ገልጸዋል፡፡
  • ‹‹የተከፋፈለች ቤተ ክርስቲያን መረከብ አንፈልግም፤ ታሪካዊ አንድነታችንና ቀኖና ቤተ ክርስቲያናችን መጠበቅ አለበት›› በሚል የተነሣሣውን የኦርቶዶክሳውያን ወጣቶች እንቅሰቃሴ በማጠናከር የሰንበት ት/ቤቶች እንዲስፋፉ አድርገዋል፡፡ በሀ/ስብከቱ ማኅበረ ቅዱሳን በእናት ቤተ ክርስቲያን መዋቅር ሥር የሚያበረክተው አገልግሎት እንዲጠናከር የማይቋርጥ ምክርና አባታዊ መመሪያ ሰጥተዋል፡፡
  • ቅዱስነታቸው በአሜሪካ የሚያደርጉት ሐዋርያዊ ጉብኝት ከሢመተ ፕትርክናቸው ወዲህ ለመጀመሪያ ጊዜ ከኢትዮጵያ ውጭ የሚያካሂዱት ነው፡፡
  • ‹‹የቅዱስነታቸው ሐዋርያዊ ጉብኝት የቤተ ክርስቲያናችንን ልዕልና የሚያሳይ ለካህናትና ለምእመናን መንፈሳዊ ኩራት ስለኾነ በቂ የቅድሚያ ዝግጅት እየተደረገ በውጭ ሀገርም ሳይቀር ተጠናክሮ ይቀጥል፡፡›› /ከመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ፴፪ው ዓመታዊ ስብሰባ የአቋም መግለጫ/
ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት ከነገ ጥቅምት ፳፯ ቀን ፳፻፮ ዓ.ም. ጀምሮ ለዐሥር ቀናት የሚቆይ ሐዋርያዊ ጉብኝት በአሜሪካ ለማድረግ ዛሬ ማምሻውን ይጓዛሉ፡፡
ቅዱስነታቸው ሢመተ ፕትርክናቸው ከተፈጸመበት የካቲት ፳፬ ቀን ፳፻፭ ዓ.ም. ወዲህ የመጀመሪያቸው በኾነው በዚህ ሐዋርያዊ ጉብኝታቸው የዋሽንግተን ዲሲ ሜሪላንድ መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያንን የምረቃ ሥነ ሥርዐት እንደሚያከናውኑ ከልዩ ጽ/ቤታቸው የተገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡
ከብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ ጋራ የቋሚ ቅ/ሲኖዶስ አባላት የኾኑት÷ የምዕራብ ወለጋና አሶሳ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ኄኖክ እንዲሁም የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ የወላይታ ኮንታና ዳውሮ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ አብረዋቸው እንደሚጓዙ ተገልጧል፡፡
በቅርቡ ፴፪ውን ዓመታዊ ስብሰባውን ያካሄደውና በብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ ሪፖርት የተካተተውን የውጭ ግንኙነት መምሪያ ዘገባ ያዳመጠው የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ በአቋም መግለጫው ተ.ቁ(3)÷ ቅዱስነታቸው በአገር ውስጥ ይኹን በውጭ የሚያደርጓቸው ሐዋርያዊ ጉብኝቶች፣ ‹‹የቤተ ክርስቲያናችንን ልዕልና የሚያሳዩ፣ ለካህናትና ለምእመናን መንፈሳዊ ኩራት›› ናቸው፡፡ በመኾኑም ‹‹የቅድሚያ ዝግጅት እየተደረገ በውጭ ሀገርም ሳይቀር ተጠናክሮ እንዲቀጥል›› አጠቃላይ ጉባኤው ድጋፉን ሰጥቷል፡፡
በሢመተ ፕትርክናቸው ወቅት የወጡ ኅትመቶች እንደሚያስረዱት፣ ቅዱስነታቸው በአሜሪካ በስደት በቆዩባቸው ዐሥር ዓመታትና የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ በመኾን ባገለገሉባቸው ዐሥራ አምስት ዓመታት በኻያ ያህል ግዛቶች በአጠቃላይ ኻያ አምስት አብያተ ክርስቲያንን አቋቁመዋል፡፡ እኒህም ዛሬ በሦስት አህጉረ ስብከት ተከፍሎ በሁለት ሊቃነ ጳጳሳት ለሚመራው የአህጉረ ስብከቱ ሐዋርያዊ አገልግሎት ‹‹እንደ ቅዱስ ዮሐንስ መንገድ ጠራጊ ፋና ወጊ ኾነውለታል፡፡›› – ‹‹ዛሬ በሦስት አህጉረ ስብከት ተከፋፍሎ የሚታየው የሰሜን አሜሪካ አገልግሎት ብቻቸውን በመኾን ምግብ አብስሎ የሚያቀርብላቸው በሌለበት ራሳቸው ቄስ፣ ራሳቸው ዲያቆን አንዳንዴም ሹፌር በመኾን ከዳር እስከ ዳር አገልግለውበታል፡፡››
በሰሜን አሜሪካ ጎልቶ የሚታየውን የገለልተኝነት መዋቅርና አስተዳደር የሚቃወሙትና በክፍለ አህጉሩ የእናት ቤተ ክርስቲያን እንቀስቃሴ መሪ ናቸው የሚባሉት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ፣ የጥቅምት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በመግለጫው ባስተላለፈው ይፋዊ ጥሪ መሠረት፣ በገለልተኛ አስተዳደራዊ መዋቅር ከሚመሩ አብያተ ክርስቲያን ወገኖች ጋራ ወደ እናት ቤተ ክርስቲያን የሚመለሱበትንና የቤተ ክርስቲያን አንድነት የሚጠናከርበትን መልእክት በሐዋርያዊ ጉብኝታቸው እንዲያስተላልፉ ይጠበቃል፡፡
ሐዋርያዊ ጉብኝታቸው ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ፣ ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስና በስደት ከሚገኙ ሌሎች አባቶች ጋራ በፊታውራሪነት የጀመሩት የዕርቀ ሰላም ውይይት ወደፊት እንዲቀጥልና የቤተ ክርስቲያን አንድነት እንዲጠናከር በምልአተ ጉባኤው የሰፈረውን መግለጫ ተፈጻሚነት ለመርዳት ምቹ አጋጣሚ እንደሚፈጥርም የብዙዎች እምነትና ተስፋ ነው፡፡

2013 ኦክቶበር 31, ሐሙስ

                                                                          
Participants of the 32nd SGGA03
 

የምእመናን ቆጠራና ምዝገባ በአህጉረ ስብከት ሓላፊነት ይካሄዳል: የቅ/ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ስብሰባ መግለጫ

  • ቅ/ሲኖዶስ ስለ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታሪካዊነትና ቀዳሚነት እውነታውንና ትክክለኛውን የሚገልጽ ጽሑፍ እንዲዘጋጅ ለሊቃውንት ጉባኤው ትእዛዝ ሰጠ
  • የኢትዮጵያ ቴሌቪዥንና ሬዲዮ ድርጅት ለምልአተ ጉባኤው ስብሰባ የሰጠው ሽፋን ‹‹የጉርሻ ያህል ነው›› በሚል ተነቀፈ
  • ‹‹ጉባኤው አገር አቀፍ ብቻ ሳይኾን ዓለም አቀፍም ነው፤ የምንሰጠው ትምህርት ነው፤ የምንወድቀው የምንነሣው ስለ ሀገር ጉዳይ ነው፤ ቤተ ክርስቲያን በዐይን የሚታይ በእጅ የሚጨበጥ ታሪክ ነው ያስረከበችው፤ በምን ምክንያት ነው [የአየር ሽፋኑ]ቀለል የሚለው›› /ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ/
  • ‹‹ከባለሥልጣናት[ከመንግሥት] የምናገኛቸውን መልእክቶች እናስተላልፋለን፤ ከጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ሚኒስትሩ እናቶች በሆስፒታል እንዲወልዱ ደጋግማችኹ አስተላልፉን ብለው ነግረውን በቤተ ክርስቲያናችን ብዙ ሺሕ ሕዝብ በተሰበሰበበትና በየአጋጣሚው እናስተላልፋለን፤ እኛም እዚህ ስለ አገር ጉዳይ እንነጋገራለን፤ የምንነጋገረው ግን የሚተላለፈው የጉርሻ ያህል ነው፤ ለሕዝቡ እንዲተላለፍ እንጂ የሚዲያ ሱሰኛ ኾነን አይደለም፤ የሚነገረው ነገር ለሕዝቡ በአግባቡ ቢተላለፍ መልካም ነው›› /ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ/
Holy SynodTikmit Meeting
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምእመናን ቆጠራና ምዝገባ በእያንዳንዱ አህጉረ ስብከት ሓላፊነት እንደሚካሄድ ቅዱስ ሲኖዶስ አስታወቀ፡፡
‹‹ቤተ ክርስቲያን በሥሯ ያሉ ምእመኖቿን ቆጥራ መመዝገብ እንድትችል›› የሚካሄደው ይኸው ታላቅ አገራዊ ክንዋኔ የሰበካ ጉባኤ ማደራጃ መምሪያ በሚያዘጋጀው ቅጽ አማካይነት እንደሚከናወን ነው ቅዱስ ሲኖዶሱ የገለጸው፡፡
የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ሰበካ ጉባኤ ማደራጃ መምሪያ በ፳፻፮ ዓ.ም. በጀት ዓመት የምእመናን ቆጠራ ለማካሄድ ከብር 29 ሚልዮን በላይ የበጀት ጥያቄ ለቅ/ሲኖዶስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት ማቅረቡን መዘገባችን የሚታወስ ሲኾን ዛሬ በቅ/ሲኖዶሱ መግለጫ እንደተጠቀሰው፣ በአህጉረ ስብከት ሓላፊነት የሚካሄደውን ቆጠራ ክንውን በቀጣይ የምንመለከተው ይኾናል፡፡
በተያያዘ ዜና፣ ስለ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታሪካዊነትና ቀዳሚነት ሁሉም ሰው መጻፍ ሲገባው እውነት ያልኾነውን፣ በማስመሰል የሚነገረውንና የሚጻፈውን ማስተካከል እንደሚያስፈልግ ቅዱስ ሲኖዶሱ አሳስቧል፡፡
በመኾኑም እውነተኛውንና ትክክለኛውን አስተካክሎ ለሕዝብ፣ ለትውልደ ትውልድ ማስተላለፍ እንዲቻል መነሻ ይኾን ዘንድ በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የኮሚቴ አባልነት ተጠንቶ የቀረበውን ጽሑፍ ምልአተ ጉባኤው በንባብ ሰምቶ ጉዳዩ ወደ ሊቃውንት ጉባኤ እንዲቀርብ ትእዛዝ መስጠቱን ቅ/ሲኖዶሱ አስታውቋል፡፡
የቅዱስ ሲኖዶሱ መግለጫ እንደሚያመለክተው፣ ሊቃውንት ጉባኤው ስለ ኢትዮጵያ ታሪካዊነትና ጥንታዊነት በምልአተ ጉባኤው ላይ የተነበበውንና በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የተዘጋጀውን የመነሻ ጽሑፍ አብራርቶ፣ አስፍቶና አምልቶ ለግንቦት፣ ፳፻፮ ዓ.ም. የርክበ ካህናት ምልአተ ጉባኤ እንዲያቀርብ ተወስኗል፡፡
የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት የኾኑ ሦስት ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፡- ብፁዕ አቡነ ማርቆስ፣ ብፁዕ አቡነ ኄኖክ እና ብፁዕ አቡነ እንድርያስ በቅርቡ በተካሄደው ፴፪ው የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ዓመታዊ ስብሰባ ላይ፥ ኢትዮጵያ ከአይሁድ በፊት ጀምሮ በአምልኮተ እግዚአብሔር ጸንታ መኖሯን፣ ክርስትናም ወደ ኢትዮጵያ የገባው ክርስቶስ ባረገበት ዓመትና ቅዱሳን ሐዋርያት ገና ከኢየሩሳሌም ባልወጡበት በ፴፬ ዓ.ም. መኾኑን ጠቅሰው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ታሪካዊነትና ቀዳሚነት በማስረዳት ከፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር ሓላፊዎች ጋራ መጠያየቃቸው ይታወሳል፡፡
የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤው ጥቅምት ፲፩ ቀን ፳፻፮ ዓ.ም. በመክፈቻ ሥርዐተ ጸሎት የጀመረውንና ለዐሥር ቀናት ያህል ሲያካሂድ የቆየውን የመጀመሪያ ዓመታዊ የምልአተ ጉባኤ መደበኛ ስብስባ ዛሬ፣ ጥቅምት ፳፩ ቀን ፳፻፮ ዓ.ም. በጸሎት አጠናቋል፡፡
ምልአተ ጉባኤው መደበኛ ስብሰባውን ሲያጠናቅቅ ያወጣው ባለ28 ነጥብ መግለጫ የሚከተሉትን ዋና ዋና ነጥቦች አካትቷል፡-
  • ከአጥቢያ ቤተ ክርስቲያን እስከ አዲስ አበባ ሀ/ስብከት ጽ/ቤት ድረስ በባለሞያዎች ተጠንቶ የቀረበውና በስላይድ የታየው የሥራ መዋቅር ወደ ታች ወርዶ በካህናት፣ በምእመናንና በሰንበት ት/ቤት ወጣቶች ውይይት ዳብሮ በሚገባ ተጠንቶና ተስተካክሎ ለቋሚ ሲኖዶስ እንዲቀርብና ቋሚ ሲኖዶሱም አይቶና ተመልክቶ በሥራ ላይ እንዲያውል ምልአተ ጉባኤው ወስኗል፡፡
  • ቤተ ክርስቲያናችን ወደፊት የምታከናውነው ማኅበራዊና መንፈሳዊ አገልግሎት በዕቅድ የሚመራ እንዲኾን ለማስቻል በግንቦቱ ርክበ ካህናት ጉባኤ ፳፻፭ ዓ.ም. ተቋቁሞ የነበረው ኮሚቴ ያዘጋጀውን ጥናት ለጉባኤው አቅርቦ ጉባኤው ማብራሪያውን ካዳመጠ በኋላ ኮሚቴው ያላለቁ ሥራዎችን እንዲቀጥል በማለት መመሪያ ሰጥቷል፡፡
  • የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ጥንታዊትና ታሪካዊ እንደመኾኗ ኹሉ በቀጣይም አጠቃላይ ማኅበራዊም ኾነ መንፈሳዊ ሥራዎቿን በመሪ ዕቅድ በመምራት ሙስናና የመልካም አስተዳደር ዕጦትን ከሥሩ መቅረፍ እንዲቻል በባለሞያዎች የተጠናውን የመሪ ዕቅድ ዘገባ በመገምገም በቀጣይ ዕቅዱ ዳብሮ በሥራ መተርጎም በሚቻልበት ኹኔታ ተዘጋጅቶ እንዲቀርብ ጉባኤው መመሪያ ሰጥቷል፡፡
  • አሁን ያለው ሕገ ቤተ ክርስቲያን ተሻሽሎ እንዲቀርብ በተወሰነው መሠረት የተሻሻለው የሕገ ቤተ ክርስቲያን ረቂቅ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት እንዲመለከቱት የታደለ ሲኾን እንዲሁም በሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ታይቶና ሐሳብ ተሰጥቶበት በ፳፻፮ ዓ.ም. ግንቦት ርክበ ካህናት ውይይት እንዲካሄድበት ምልአተ ጉባኤው ወስኗል፡፡
  • በውጭው ዓለም ገለልተኛ አብያተ ክርስቲያናት ነን በሚል የሚገኙ ወገኖች ወደ እናት ቤተ ክርስቲያናቸው እንዲመለሱ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ጥሪውን ያስተላልፋል፡፡
  • በውጭ አገር ከሚገኙ የቤተ ክርስቲያን አባቶች ጋራ ተጀምሮ የነበረው ዕርቀ ሰላም ወደፊት እንዲቀጥልና የቤተ ክርስቲያኒቱ አንድነት እንዲጠናከር ጉባኤው ተስማምቷል፡፡
  • ገዳማቱን መልሶ ማቋቋምና ማጠናከር ብሎም በነበሩበት ኹኔታ አደራጅቶ ሥራቸውን መቀጠል ይችሉ ዘንድ የሚያመለክት በመምሪያው በኩል ሰፊ ጥናት የተደረገ በመኾኑ ገዳማቱ የሚገኙትም በየአህጉረ ስብከቱ ስለኾነና ብፁዓን አበው የሌሉበት ጥናትም አጥጋቢ ውጤት ስለማይኖረው የተወሰኑ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ከመምሪያው ተጠሪ ጋራ ተገናኝተው ገዳማቱ እንዴት መቋቋምና መልማት እንዳለባቸው ጥናት ይደረግበት በሚለው ጉባኤው ተስማምቶ ጠለቅ ያለ ሐሳብ ከነመፍትሔው አጥንተው ለግንቦት ፳፻፮ ዓ.ም. ርክበ ካህናት ምልአተ ጉባኤ እንዲያቀርቡ፡-
1.  ብፁዕ አቡነ ኤጲፋንዮስ – የምዕራብ ሸዋ ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣
2.  ብፁዕ አቡነ ሳሙኤል – የልማትና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን ሊቀ ጳጳስ፣ የሕንፃዎችና ቤቶች አስተዳደር ድርጅት የበላይ ሓላፊ
3.  ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ – የከምባታ ሐዲያና ጉራጌ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በመምረጥ ምልአተ ጉባኤው በሙሉ ድምፅ ተስማምቶ ወስኗል፡፡
  • የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅን በተመለከተ ኮሌጁን ማጠናከር አስፈላጊ ኾኖ በመገኘቱ ለኮሌጁ ዋና ዲን እንዲሾም ጉባኤ ውሳኔ አሳልፏል፡፡

የቤተ ክርስቲያን ተቋማዊ ለውጥ ጥናቶች የቅ/ሲኖዶሱን ሙሉ ድጋፍና ባለቤትነት አገኙ፤ በጥናቶቹ ቀጣይ አካሄድ ላይ ምልአተ ጉባኤው የአፈጻጸም አቅጣጫ ሰጥቷል፤ የምልአተ ጉባኤው ስብሰባ ዛሬ ያበቃል፤ መግለጫም ይኖራል

Holy SynodTikmit Meeting
  • በአገልግሎት ጥራት /በሰው ተኮር ነፍስ የማዳን አገልግሎት/ ምእመናንን ማብዛትና ማጽናት፣ ቤተ ክርስቲያንን ከባይተዋርነትና ጠባቂነት ወደነበራት ሚና መመለስ፣ አስተምህሮዋን ከማይቃረኑ ጋራ ዓለም አቀፍ አጋርነትን በማጠናከር የሰላምና አንድነት ተምሳሌት ማድረግ፣ ለሙስና ችግሮች በንስሐ መንገድ መፍትሔ ማበጀት የቤተ ክርስቲያናችን ስትራቴጂያዊ ዕቅድ ማሕቀፍና ቊልፍ ጉዳዮች ኾነዋል፡፡
  • በቡድን እየተደራጁ የመንግሥትን ወቅታዊ አጀንዳዎች በአሉታዊ መንገድ የሚጠቀሙ አሉባልተኞችና ሙሰኞች እንዲሁም በቤተ ክህነቱ ቢሮክራሲ ውስጥ የተሰገሰጉ የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ አቀንቃኞች ዋነኛ የለውጡ ተግዳሮቶች እንደኾኑና እንደሚኾኑ ተጠቁሟል፡፡
  • የለውጥ አመራር መዋቅሩ፣ አደረጃጀቱና ዝርዝር አሠራሩ ሕገ ወጥ ጥቅምን የሚያስቀር ተገቢ ጥቅምን የሚያጎለብት፣ ማንኛውንም ሠራተኛና አገልጋይ ለለውጡ የሚያበቃ እንጂ የማያፈናቅል መኾኑ በቅ/ሲኖዶሱ ምልአተ ጉባኤ ታምኖበታል፡፡ ካህናት፣ ባለሞያ ሠራተኞች፣ የሰንበት ት/ቤት ወጣቶችና ምእመናን የለውጡ ግንባር ቀደም አራማጆች ይኾናሉ፡፡
  • ተቋማዊ ለውጡን ለመተግበር÷ ነባሩ የሰው ኃይል የሚበቃበት አዲስ የሰው ኃይል የሚወጣበት የሥራ አመራር ማሠልጠኛ አካዳሚ/የሥልጠና ማእከል/ለመገንባት ጥናቱ ተጠናቆ ዝግጅቱ ተጀምሯል፤ ማእከሉ የድኩማን/አረጋውያን መጦርያና የነዳያን መልሶ ማቋቋሚያም ያካተተ ነው፡፡
  • በአ/አበባ ሀ/ስብከት ለተቋማዊ ለውጥ አመራር ጥናቱ ምቹ ኹኔታ የፈጠሩትና ያስቻሉት የፓትርያርኩ ረዳት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ አለጊዜውና አላግባብ በተደረጉ የአድባራት አስተዳዳሪዎች፣ ጸሐፊዎችና ሌሎች ሠራተኞች ዝውውሮች ቢገመገሙም ከምደባቸው የመነሣታቸው ዜና ከእውነት የራቀ ነው፡፡
  • በሀ/ስብከቱ ጽ/ቤት አዲስ የሙስና ኔትወርክ ዘርግተው ሕገ ወጥ ሲያጋብሱ በቆዩ ሦስት ሓላፊዎች ላይ ርምጃ ይወሰዳል፤ ሓላፊነታቸው ለቀው ወደ አሜሪካ በሄዱት የሀ/ስብከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ መጋቤ ሐዲስ ይልማ ቸርነት ምትክ አዲስ ዋና ሥራ አስኪያጅ ይሾማል፤ ገለልተኝነታቸው፣ የትምህርት ዝግጅታቸውና አገልግሎታቸው የሚጠቀስላቸው የአራዳና ጉለሌ ክፍለ ከተማ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ሥራ አስኪያጅ ቀሲስ ታጋይ ታደለ ቀጣዩ ዋና ሥራ አስኪያጅ እንደሚኾኑ በስፋት እየተነገረ ነው፡፡
  • የገዳማት አጠቃላይ ወቅታዊ ይዞታና ሥርዐተ ምንኵስናው የሚገኝበትን ኹኔታ ተከታትሎ ለቋሚ ሲኖዶስ ሪፖርት የሚያቀርብ የሊቃነ ጳጳሳት ኮሚቴ በምልአተ ጉባኤው ተደራጀ፤ የዴር ሡልጣን ገዳምን ውዝግብ ለመፍታት ከኮፕት ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ጋራ የሚደራደር በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ገዳማት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ዳንኤል የሚመራ ኮሚቴ እንዲቋቋም ምልአተ ጉባኤው መመሪያ ሰጥቷል፡፡
  • የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት መተዳደርያ ደንብ በቅዱስ ሲኖዶሱ ጸድቋል፡፡ ደንቡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሕፃናትና ወጣቶች ጥራትና ወጥነት ባለው ሥርዐተ ትምህርት ተኮትኩተውና በሥነ ምግባር ታንጸው ተተኪዎች ለማድረግ የሚያስችል፣ ሁለገብ አገልግሎታቸውን ለማጠናከር የሚያግዝ እንደኾነ ተገልጧል፡፡ ሕገ ወጥ ሰባክያንን በመከላከል ስብከተ ወንጌልን በተለያዩ መንገዶች ለማስፋፋት ሰንበት ት/ቤቶችን በይበልጥ የማደራጀት ሥራ ትኩረት ይሰጠዋል
  • ብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ በቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ ከነበራቸው የበላይ ሓላፊነት ተነሥተው በበላይ ጠባቂነት ተወስነው ይሠራሉ፤ በኮሌጁ አስተዳደራዊና የፋይናንስ እንቅስቀሴ ጉዳዮች ላይ የመወሰን ሥልጣን አይኖራቸውም፤ የኮሌጁ ዋና ዲን በግልጽ ማስታወቂያ በውድድር በሚካሄድ የቅጥር ሥርዐት ይመደባል፡፡
  • የካህናትና ምእመናን ምዝገባ/ቆጠራ/ ለማካሄድ የተያዘው ዕቅድ ተጨማሪ ዝርዝር ጥናት ያስፈልገዋል በሚል እንዲዘገይ ተደረገ፤ የመንግሥት ፈቃደኝነትና የበጀት አቅም እንደ ስጋት ቢጠቀስም የሊቃነ ጳጳሳት ደመወዝ በመቶ ፐርሰንት እንዲጨምር መወሰኑ አነጋጋሪ ኾኗል፡፡
About these ads

2013 ኦክቶበር 30, ረቡዕ


                                         

Ethiopian_Orhodox church bilden addis_Abeba_2

                                   የኤጲስ ቆጶሳት አስመራጭ ኮሚቴ ተቋቋመ፤ የዕጩዎችን ዝርዝር ለርክበ ካህናት ምልአተ ጉባኤ ያቀርባል

የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በዛሬው፣ ጥቅምት ፳ ቀን ፳፻፮ ዓ.ም ዘጠነኛ ቀን የቀትር በፊት ውሎው የኤጲስ ቆጶሳትን ምርጫ የሚያስፈጽም አስመራጭ ኮሚቴ ሠየመ፡፡
አስመራጭ ኮሚቴው ስድስት ሊቃነ ጳጳሳት በአባልነት የሚገኙበት ሲኾን የትግራይ፣ ወሎ፣ ጎንደር፣ ጎጃም፣ ሸዋና ኦሮሚያ አህጉረ ስብከትን በመወከል የተመረጡ ናቸው፡፡ በዚህም መሠረት÷ ከትግራይ የልማትና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ሳሙኤል፣ ከወሎ የደቡብ ወሎ ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ አትናቴዎስ፣ ከጎንደር የሰሜን ጎንደር ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ፣ ከጎጃም የምሥራቅ ጎጃም ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ማርቆስ፣ ከሸዋ የከምባታ ሐዲያ ጉራጌና ስልጢ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ እና ከኦሮሚያ የደቡብ ምዕራብ ሸዋ – ወሊሶ ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ በአስመራጭ ኮሚቴ አባልነት ተሠይመዋል፡፡
ዕጩዎችን በሕገ ቤተ ክርስቲያን ለኤጲስ ቆጶሳት ምርጫ በወጣው መስፈርት ብቻና ብቻ ለይቶ እንዲያቀርብ በምልአተ ጉባኤው ከባድ አደራ የተጣለበት አስመራጭ ኮሚቴው÷ ከመስፈርቱ ውጭ ጎጠኝነትን ጨምሮ በተለያዩ መደለያዎች ሢመተ ኤጲስ ቆጶስነትን ለማግኘት ካሰፈሰፉ ቆሞሳት እንዲጠበቅ ከፍተኛ ማስጠንቀቂያ ተሰጥቶታል ተብሏል፡፡
አስመራጭ ኮሚቴው በመምረጫ መስፈርቱ መሠረት የዕጩዎችን ማንነት ከመለየት ባሻገር ከበጀት፣ ከመንበረ ጵጵስና እና ከጽ/ቤቶች መሟላት አኳያ ኤጲስ ቆጶሳቱ ሊመደቡባቸው የሚገቡ አህጉረ ስብከትን በቅደም ተከተል በመለየት ብዛታቸውን የመወሰን ሥራም እንደሚሠራ ተገልጧል፡፡
በጽርሐ መንበረ ፓትርያርክ በሚሰጠው ቢሮ ሥራውን የሚያከናውነው አስመራጭ ኮሚቴው፣ በሥራው ወራት የፍትሕ መንፈሳዊ ድንጋጌ እንደሚያዝዘውና በተሻሻለው የኤጲስ ቆጶሳት ምርጫ ሕግ እንደተመለከተው ተቀባይነት ያለው የግልጽነት መርሕ በመከተልና የልዩ ልዩ ውጫዊ አካላት ጣልቃ ገብነቶችንና ተጽዕኖዎችን በመከላከል አደራውን መወጣት ይኖርበታል፡፡
አስመራጭ ኮሚቴው ሥራውን ጨርሶ ሪፖርቱን የሚያቀርበው ለመጪው የርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ሲኾን ሥርዐተ ሢመቱም የምልአተ ጉባኤውን መጠናቀቅ ተከትሎ እንደሚፈጸም ተመልክቷል፡፡
የኤጲስ ቆጶሳትን ምርጫና ተያያዥ ጉዳዮችን የተመለከቱ ሌሎች መረጃዎችን ወደፊት እንደምናቀርብ ከወዲሁ እንገልጻለን፡፡

                                   በአውሮጳ   የካህናት አንድነት ማኅበር ሊቋቋም መሆኑ ታወቀ በ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከመላዋ አውሮጳ   የተውጣጡ ካህናት፡” የ...