2014 ፌብሩዋሪ 4, ማክሰኞ

በቅዱስ ላልይበላ ደብር የተፈጠረው አለመግባባት በሰላም ተፈታ






በሀገራችን ታሪክ መቀዳሚነት ዓለምን በማስደነቅ የሚታወቀውና በዩኔስኮ ተመዝግቦ ሀገሪቱን በከፍተና ደረጃ የሚያስተዋውቀው የቅዱስ ላልይበላ ደብር በቀድሞው አሰተዳዳሪ አበ ገብረ ኢየሱስ አስተዳደር ፤ የከተማው ባለሃብት እና በከተማው የቱሪስት አስጎብኚ ማህበራት መካከል አለመግባባት ተፈጥሮ ረጅም ጊዜ የፈጀ መሆኑን የተለያዩ የዜና ምንጮች  ሲዘግቡት መቆታቸው ይታወቃል  ይሁን እንጂ በሶስት ተከፍለው ማለትም በደብሩ አስተዳደር፤ በከተማው ባለሀብት እና በከተማው ያሉ አስጎብኚ ማህበራት መካከል የአሰራር ክፍተቶች  እንደ ነበረና በተለይ በደብሩ የቀድሞ አስተዳደር አማካይነት የተፈጠሩ የአሰሠራር ችግሮች ስለነበሩ የደብሩ አስተዳዳሪ አባ ገብረ ኢየሱስ  ከስተዳዳሪነት ንዲነሱ ተደርጓል፡፡ ነገር ግን በወቅቱ የተከሰተውን አለመግባባትን ለመፍታት የከተማው አስተዳደር እና የሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት የሰላም ኮሚቴ አዋቅሮ ስለነበር ኮሚቴው የሶስቱንም አካላት ችግሮች ካጠና በኋላ ለሶስቱም የሚስማማ የእርቀ ሰላም ሰነድ አዘጋጅቶ ጥር 25/2006ዓ.ም በዚያው በላልይበላ ጽርሐ ቤተ አብርሃም አዳራሽ የደብሩ ሊቃውንት፤ ሰበካ ጉባዔ፤ የከተማው ባለሃብት፤ አስጎብኚ ማህበራት በተገኙበት ለደብሩ አዲስ በተመደቡት አስተዳዳሪ መ/ር አባ ወልደ ትንሣኤ አስተባባሪነት በከተማው ከንቲባና እና በሰላም ኮሚቴው ከፍተኛ ጥረት ሁሉም አካላት እንዲታረቁ ሆኖአል፡፡ በእርቀ ሰነዱ ላይም የሚከተሉት ስምምነቶች ተካተዋል፡፡

                                                                 
                                                                   

                                                                   እርቀ  ሰላሙ ሲፈጸም

በደብሩ አስተዳደር
1 . በቀድሞው አስተዳዳሪ የተባረሩት ሊቃውንት ካህናትና ልዩልዩ ሠራተኞች እንዲመለሱ
2. በደብሩ ግልጽና ተጠያቂነት ያለው አሠራር እንዲኖር
3. የአብነት መምህራን  ሊቃውንቱ ከፍተኛ ትኩረት እንዲሰጣቸው
4.ደብሩ ልዩ ልዩ እቅዶችን እያቀደ ከህዝቡ ጋር እተመካከረ እንዲሠራ
5. የደብሩ ትኩረት ከቱሪስቱ ባለፈ ለአካባቢው ሕዝብ የሚሆን የልማት አውታር ቢቀርጽ እና ተግባራዊ  ቢያደርግ የሚሉት እና ሌሎችም ይገኙበታል፡፡
                          በከተማው ባለሀብት
1.    በደብሩ የሚፈጠረውን ማንኛውንም ችግሮችን ዝም ማለቱ ቀርቶ ችግሩን በጋራ መፍታት
2.   በልማት ሆነ በመሳሰሉት አገልግሎት ተሳታፊ እንዲሆኑ
3.   በከተማው የሚስተናገዱትን ቱሪስቶች በትብብር ማስተናገድና የመሳሰሉትን አካቶአል
                 የከተማው አስጎብኚ ማኅበራት

1.    የደብሩን ታሪክ በሚገባ አጥንተው ሳይጨመርና ሳይቀነስ ቱሪስቱን እንዲያስረዱ
2.   ሃይማኖታዊ ሥነ ምግባርን በተላበሰ መልኩ የማስጎብኘት ተግባራትን እንዲያከናውኑ
3.   የከተማውን ሰላም በማስፈን ረገድ ከፍተኛ ድርሻ ስላላቸው የበኩላቸውን ድርሻ እንዲወጡ
4.   በገንዘባቸውም ሆነ በመሳሰሉት ደብሩን የመደገፍ ሥራ እንዲሰሩ እና የመሳሰሉትን እንዲተገብሩ በእርቀ ሰላሙ  ሰነድ ላይ ከተካተተው ውስጥ ጥቂቶቹ ናቸው፡፡ በአጠቃላይ ወደፊት ችግሮች ቢኖሩም በውይይት እንዲፈታ እና ሁሉም የቤተ ክርስቲያን ልጆች እንደ መሆናችን መጠን ለቤተ ክርስቲያናችን የሚገባንን ሁሉ ለመወጣት ዝግጁ ነን በማለት እርቀ ሰላሙ ተፈጽሟል፡፡

                                        
                                                    

                                                    የጉባኤው ተሳታፊዎች በከፊል

2014 ጃንዋሪ 27, ሰኞ

በዐረብ ፔኒዙኤላ የመጀመሪያዋ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ልትታነጽ ነው


 click here for pdf

በመካከለኛው ምሥራቅ ከእሥራኤልና ቤይሩት ቀጥሎ ሦስተኛዋ፣ በዐረቢያ ፔኑዙኤላ ደግሞ የመጀመሪያዋ የምትሆነው ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን በኳታር ምድር ልትታነጽ ነው፡፡ 
በኳታር ምድር የዛሬ አሥር ዓመት ለጸሎትና ለትምህርት መሰባሰብ በጀመሩ ወንድሞችና እኅቶች የተጀመረችው የኳታር ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ወደ አካባቢው ለሥራ የሚጓዙ ምእመናንን በማሰባሰብና በማገናኘት፣ ስብከተ ወንጌልን በማስፋፋትና ክርስቲያናዊ ማኅበራዊ ኑሮን በማጠናከር የምትታወቅ ናት፡፡ ቤተ ክርስቲያንዋ አገልግሎቷን የምትፈጽመው በግብጽ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሲሆን በዓረቡ ዓለም እንደተለመደውም ዘወትር ዓርብ ከሰዓት በኋላ የቅዳሴና የትምህርት አገልግሎት ይሰጣል፡፡ የኳታር ቅድስት ሥላሴ ምእመናን የሥራ ጫናውን ሁሉ ተቋቁመው ተግተው በማገልገል ብቻ ሳይሆን ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን ጠብቀው በማስጠበቅም የሚታወቁ ናቸው፡፡
በአብዛኞቹ የዓረበ ሀገሮች እንዳሉት አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ሁሉ በኳታር ለነበረችው ቤተ ክርስቲያንም ዋና ፈተና የነበረው የራስዋ ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን አለመኖር ነው፡፡ ይህም አገልግሎቷን በሳምንት ወደ ተወሰኑ ቀናትና ሰዓታት ከማሳነሡም በላይ፣ ምእመናን የሚፈልጓቸውን ሁሉን አገልግሎቶች ለመስጠት እንዳትችል አድርጓት ነበር፡፡ ለቤተ ክርስቲያንዋ የራስዋ ሕንጻ መሥሪያ ቦታ በመፈለግ ችግሩን ለመፍታት ጥረት ሲያደርግ የነበረው የሰበካ ጉባኤ ባሳለፍነው ሳምንት በዐረቡ ዓለም የመጀመሪያ የምትሆነውን ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን ለመሥራት የሚያስችል መሬት ተረክቧል፡፡ 
እስካሁን ድረስ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን በየመን፣ በዓረብ ኤምሬትስ፣ በባሕሬን፣ በኩዌት፣ በሊባኖስና በግብጽ የራስዋ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ቢኖሯትም በራስዋ ገንዘብ የተሠራና ንብረትነቷ የቤተ ክርስቲያኒቱ የሆነ ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን ግን ከእሥራኤልና ቤይሩት በቀር አልነበራትም፡፡ የኳታር ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ከተሠራ በመካከለኛው ምሥራቅ ሦስተኛው የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ‹ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን› ይሆናል፡፡
በኳታር ሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑ መሠራት ዘርፈ ብዙ ጥቅም ይኖረዋል፡፡ በአንድ በኩል የአጥቢያ ቤተ ክርስቲያኑን አገልግሎት ከሳምንት እስከ ሳምንት የማያቋርጥ እንዲሆን ሲያደርገው በሌላ በኩል ደግሞ በአካባቢው ላሉት ሌሎች አጥቢያዎችም አርአያነት ይኖረዋል፡፡ ከኳታር በፊት እንቅስቃሴ የጀመሩት እንደ አቡዳቢ መድኃኔዓለም ያሉትን አጥቢያዎች የጀመሩትን በርትተው እንዲፈጽሙ ያነሣሣቸዋል፡፡
በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን የሐዋርያነት ታሪክ በዐረቢያ ፔኒዙኤላ የነበረው ቤተ ክርስቲያን ከ1400 ዓመታት በፊት በየመን ናግራን ታንጾ የነበረው የቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ነበር፡፡ እርሱ ከጠፋ ከ1600 ዓመታት በኋላ በዓረቢያ ፔኑዚኤላ ሁለተኛው ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን በቅድስት ሥላሴ ስም እንደገና በኳታር መታነጹ የታሪኩ ተገጣጣሚነት የሚያስደንቅ ነው፡፡
ይህ ቤተ ክርስቲያን በአንድ በኩል ታሪካዊ፣ በሌላ በኩል የቤተ ክርስቲያኒቱን ሐዋርያዊ ተልዕኮ ወደ አንድ ምዕራፍ የሚያሸጋግር፣ ሲሠልስም ለሌሎች አርአያነት ያለው በመሆኑ ሥራ በኳታር ለሚገኙ ብቻ የሚተው አይደለም፡፡ ግብጻውያን እንደዚህ ባሉ አካባቢዎች የሚታነጹ የተለየ ታሪክና ጠቀሜታ ያላቸውን አብያተ ክርስቲያናት በመተጋገዝ እንደሚገነቧቸው ሁሉ በመላው ዓለም የሚገኙ ኢትዮጵያውያንም እያንዳንዷን የሕንጻዋን ብሎኬት ተካፍለው በመገንባት በታሪክ ምዕራፍ ላይ አሻራቸውን ማስቀመጥና በረከት ማግኘት ይጠበቅባቸዋል፡፡
 በሀገር ቤት፣ በአውሮፓ፣ በአሜሪካና በአውስትራልያ የሚገኙ ምእመናን በአካባቢያቸው ቤተ ክርስቲያን ባይኖር ነድተውም ሆነ ተሳፍረው ወደ ሌላ አካባቢ በመሄድ ቤተ ክርስቲያን መገልገል ይችላሉ፡፤ በዐረቡ ዓለም ግን በአንድ አካባቢ አንድ አጥቢያ ብቻ ስለሚገኝ ወጣ ብሎ በሌላ አጥቢያ መገልገል አይቻልም፡፡ በተለይ ደግሞ እንደ ኳታር ባሉ ሀገሮች ያለው ቤተ ክርስቲያን አንድ ነው፡፡ ይህን ቤተ ክርስቲያን ማነጽና አገልግሎቱን ማጠናከር፣ በዐረቡ ዓለም የሚገኙ ወገኖቻችን በመንፈሳ ሕይወታቸው በርትተው፣ ከመንፈስ ጭንቀት ተላቅቀው፣ የሚደርስባቸውን ፈተናም አሸንፈው ለሀገራቸውና ለወገኖቻቸው የሚጠበቅባቸውን እንዲያደርጉ የሚያስችል ነው፡፡ በመሆኑም በመላው ዓለም የተሠማሩ ኢትዮጵያውያን ሁሉ የሚታነጸው የራሳቸው አጥቢያ መሆኑን አስታውሰው ልባቸው ኳታር ሊሆን ይገባል፡፡ 
 
የገባው ክርስቲያን እግዚአብሔር ሲሠራ አብሮ ይሠራል፡፡ 
         ዶሃ፣ ኳታር

2014 ጃንዋሪ 24, ዓርብ

ፓትርያርኩ የሰንበት ት/ቤት ወጣቶች በሙስና ላይ እንዲዘምቱ አዘዙ


  • በቤተ ክርስቲያናችን ሸፍጥና ጉቦ ተንሰራፍቷል›› /ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ/
  • ሰንበት ት/ቤቶቹ የአማሳኝ አስተዳዳሪዎችን ዶሴ ለፓትርያርኩ ለማቅረብ ተዘጋጅተዋል
(አዲስ አድማስ፤ ቅጽ ፲፫ ቁጥር ፯፻፴፩፤ ቅዳሜ ጥር ፲ ቀን ፳፻፮ ዓ.ም.)
His Holiness Patriartch Abune Mathias
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ፣ የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ሰንበት ት/ቤት ወጣቶች በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ በተንሰራፋውና ለዕድገቷ መሰናክል ኾኖ በተደነቀረው ሙስናና ሸፍጥ ላይ በተጠናከረ ኃይል በመዝመት የተጀመረውን የአደረጃጀትና የአሠራር ለውጥ ከዳር እንዲያደርሱ አዘዙ፡፡
Dn Yonas Isayas of A.A.D SSD Unity reading the position paper
የአ/አበባ ሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ሥራ አመራር ተወካይ ዲያቆን ዮናስ ኢሳይያስ ለፓትርያርኩ የፁረ ሙስና እንቅስቃሴ፣ ለአ/አ ሀ/ስብከት የአደረጃጀትና አሠራር ለውጥ ተግባራዊነት የሰንበት ት/ቤቶቹን የድጋፍ መግለጫ ሲያሰማ
ብፁዕ ወቅዱስ አባታችን፣ ቅዱስነትዎ በይፋ የገለጹትንና እንዲስተካከል አበክረው ማሳሰቢያ የሰጡበትን የቤተ ክርስቲያን ዘርፈ ብዙ ችግር ለማረም በሚደረገው ጥረት ኹሉ በግንባር ቀደምነት መሰለፍ የእኛም የወላጆቻችንም ጽኑ አቋም እንደኾነና በታዘዝንበት መሥመር ኹሉ ለመሰለፍ ዝግጁዎች መኾናችንን ለቅዱስነትዎ በላቀ አክብሮትና ትሕትና ለመግለጽ እንወዳለን፡፡

አቡነ ማትያስ ትእዛዙን የሰጡት ሙስናና ብልሹ አስተዳደርን በሥር ነቀል እርማት ለማስተካከል ያስተላለፉትን መግለጫ ለመደገፍና የፓትርያርኩ ልዩ ሀ/ስብከት የኾነው የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ያዘጋጀው የአደረጃጀትና የአሠራር ለውጥ ጥናት ተግባራዊ እንዲኾን ለመጠየቅ ከትላንት በስቲያ ኀሙስ፣ ጥር 8 ቀን 2006 ዓ.ም. በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት አዳራሽ ለተሰበሰቡት በሺሕ ለሚቆጠሩ የሰንበት ት/ቤት ወጣቶች በሰጡት መመሪያ፣ ቃለ ምዕዳንና የበዓለ ጥምቀት ቡራኬ ነው፡፡
ከአዲስ አበባ ሀ/ስብከት 160 ገዳማትና አድባራት የተሰበሰቡት የሰንበት ት/ቤት ወጣቶች በሀ/ስብከቱ የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ሥራ አመራር አማካይነት ባወጡት መግለጫ፣ ፓትርያርኩ ሙስናና ብልሹ አስተዳደርን በማውገዝ ለማስተካከል አበክረው ሥራ በመጀመራቸው ምስጋናቸው አቅርበዋል፡፡ ብዙኃን የሰንበት ት/ቤት አባላት አይነኬ ኾኖ ቤተ ክርስቲያኒቱን ሲያስተቻት የቆየውን ሙስናና ብልሹ አስተዳደር እስከ እስር ደርሰው ሲታገሉት እንደቆዩም ተናግረዋል፡፡
የሙስናና ብልሹ አስተዳደር ተጠቂ እየኾኑ በማደጋቸው አስከፊነቱን በሚገባ እንደሚያውቁ በመግለጫቸው ያተቱት የሰንበት ት/ቤት ወጣቶቹ፣ ፓትርያርኩ በየጊዜው ያስተላለፏቸውን መመሪያዎች በመከታተልና የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ለአደረጃጀትና አሠራር ለውጥ ስለሚያደርገው እንቅስቃሴ በሀ/ስብከቱ ጽ/ቤትና በየክፍለ ከተማቸው በመወያየት ችግሩ ከመሠረቱ እንደሚወገድና በዘመናቸው የቤተ ክርስቲያኒቱ አስተዳደር ትንሣኤ እንደቀረበ መገንዘባቸውን ገልጸዋል፡፡
ሙስናንና ብልሹ አስተዳደርን ለማረም የሚካሔደው እንቅስቃሴ በእነርሱም በወላጆቻቸውም ጽኑ እምነት እንደተያዘበት የጠቀሱት ወጣቶቹ፣ ጥረቱን ከግቡ ለማድረስ ከፓትርያርኩ ጎን ቆመው በታዘዙበት መሥመር ለመሰለፍ ዝግጁዎች መኾናቸውን አስታውቀዋል፡፡
Sunday School Students of Holy Trinity Cathedral headind to Jan Meda,2004E.CTimket
የመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ሰንበት ት/ቤት መዘምራን ወደ ጃንሜዳ ባሕረ ጥምቀት ሲያመሩ
‹‹የፀረ ሙስና እንቅስቃሴውን እንደግፋለን ብላችኁኛል፤ እኔም እንደምትደግፉኝ አምናለኹ፤›› በማለት ተስፋቸውን የገለጹት ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ በበኩላቸው÷ ‹‹ዘመኑ የእምነት ጉድለትና የኑፋቄ ነው፤ ሐቅ፣ መልካም አስተዳደር፣ እውነተኝነትና ሓላፊነት ጠፍቷል፤ በቤተ ክርስቲያናችን ሸፍጥና ጉቦ ተንሰራፍቷል፤›› ሲሉ አምርረው ተናግረዋል፡፡ ስለ ሙስናና ብክነት ከሚሰጧቸው ተደጋጋሚ መግለጫዎች ጋራ ተያይዞ ‹‹ኹላችንም ሌቦች ተብለናል›› የሚል ቅሬታ ያቀረቡላቸው ወገኖች መኖራቸውን ያልሸሸጉት አቡነ ማትያስ፣ ‹‹የሚያመው ያመው ይኾናል፤ ኹላችኁም አማሳኞች ናችኹ የሚል አልወጣኝም፤ የሚያማስኑ እንዳሉ ግን ሐቅ ነው፤›› ሲሉ የችግሩ አስከፊነት ሊካድ እንደማይገባው አረጋግጠዋል፡፡
ሙስና ማለት ጥፋት ነው ሲሉ የቃሉን ትክክለኛ ንባብና ገላጭነት ያብራሩት ፓትርያርኩ፣ ‹‹በቤተ ክርስቲያን ያለው የሙስና ሙስና›› መኾኑን በመግለጽ በፀረ ሙስና ቅስቀሳው የሰንበት ት/ቤት ወጣቶቹ በይበልጥ እንዲዘምቱበት አሳስበዋቸዋል፡- ‹‹ተይዞ ባለው የፀረ ሙስና ቅስቀሳ እናንት የሰንበት ት/ቤት አባላት በይበልጥ ብትዘምቱበት፤ በተጠናከረ ኃይል ይህን ብትረዱኝና ከዳር ብናደርሰው አመሰግናችኋለኹ፡፡››
በተያያዘ ዜና÷ የአዲስ አበባ ሀ/ስብከትን የአደረጃጀትና አሠራር ለውጥ እንቅስቃሴ የሚበዙት የገዳማትና አድባራት አስተዳዳሪዎች፣ የጽ/ቤት ሠራተኞች፣ ማኅበረ ካህናት፣ ማኅበረ ምእመናንና የሰንበት ት/ቤት ወጣቶች እንደሚደግፉት እየተገለጸ ቢሰነብትም ‹‹ምእመናን በእኛ ሕግ ምን ያገባቸዋል፤›› የሚሉ አንዳንድ አስተዳዳሪዎች ቅሬታቸውን ለፓትርያርኩ ማቅረባቸውን የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ምንጮች ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡
እንደምንጮቹ መረጃ፣ ቅሬታ አቅራቢ አስተዳዳሪዎቹ የመዋቅር ለውጡን የሚቃወሙ ሲኾኑ ከእነርሱም መካከል ለአደረጃጀትና አሠራር ለውጡ በተከታታይ የተካሔዱት የድጋፍ መግለጫ ስብሰባዎች ምእመናኑን በእነርሱ ላይ ኾነ ተብሎ ለማነሣሣት የታለሙ ናቸው ብለው ያምናሉ፡፡ ሰንበት ት/ቤቶቹ ከፓትርያርኩ ጋራ ባካሔዱት ውይይት ሙስናና ብልሹ አስተዳደርን በግልጽ በመቃወማቸውና በማጋለጣቸው ያሳሰሯቸውና ያስደበደቧቸው አስተዳዳሪዎች እንዳሉ ተገልጧል፡፡
የሰንበት ት/ቤት ወጣቶቹ የቤተ ክርስቲያንን ሀብትና ንብረት ለግል ጥቅም በማዋልና ለባዕድ አሳልፎ በመስጠት አላግባብ በልጽገዋል የሚሏቸውን አማሳኝ አስተዳዳሪዎች ዶሴ ለፓትርያርኩ ለማቅረብ፣ እንደ ሕጉ አግባብም ለፀረ ሙስና ኮሚሽን ለማመልከትም ዝግጅታቸውን ማጠናቀቃቸውን ከአዲስ አበባ ሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ሥራ አመራር አባላት ተጠቁሟል፡፡
YeTimket Lijoch
ዉሉደ ጥምቀት
የቤተ ክርስቲያኒቱ የጥቅምት ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ÷ ቤተ ክርስቲያኒቱ የሃይማኖት ዕንከን ሳይኖርባት፣ ሞያ ሳያንሳትና ተቆርቋሪ ምእመናን እያሏት በመልካም አስተዳደርና በፋይናንስ አያያዝ ምክንያት የምትወቀስበትና ልጆቿን የምታጣበት ታሪክ መገታት እንዳለበት የገለጸ ሲኾን የቤተ ክርስቲያኒቱን የአገልግሎት አፈጻጸም እሴቶችና መርሖዎች የሚገልጸው መሪ ዕቅድ ከገመገመ በኋላ ሙስናና የመልካም አስተዳደር ዕጦትን ከሥሩ ለመቅረፍ በሚያስችል አኳኋን ተዘጋጅቶ እንዲቀርብለት መመሪያ መስጠቱ ይታወሳል፡፡

                                   በአውሮጳ   የካህናት አንድነት ማኅበር ሊቋቋም መሆኑ ታወቀ በ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከመላዋ አውሮጳ   የተውጣጡ ካህናት፡” የ...