2014 ሴፕቴምበር 3, ረቡዕ

የ2006 ዓ.ም. የግቢ ጉባኤያት ፍሬዎች ዋንጫና ሜዳልያቸውን ለማኅበረ ቅዱሳን አስረከቡ


አትም ኢሜይል
ነሐሴ 28 ቀን 2006 ዓ.ም
እንዳለ ደምስስ
  • ለኔ ይህ ዋንጫ ትልቁ ሀብቴ ነው፤ ሰው ሀብቱ ባለበት ልቡ ይኖራልና ዋንጫውን ሳስብ ማኅበሬን አስባለሁ፤ ተግቼም እንዳገለግል ያደርገኛል፡፡ የማልተካውን ሀብቴ ለማይተካው የማኅበሬ አገልግሎት መሥጠት ለኔ ታላቅ ደስታ ነው፡፡ /ዲያቆን ቶሎሳ ታዬ/

dn tolosa 2ማኅበረ ቅዱሳን በ2006 ዓ.ም. ከዩኒቨርስቲዎችና ኮሌጆች ግቢ ጉባኤያት በርካታ ተማሪዎችን አስመርቋል፡፡ በዩኒቨርስቲዎችና ኮሌጆች ቆይታቸው ያስመዘገቡት ውጤት ከፍተኛ በመሆኑም በርካቶች የተሸለሙትን ዋንጫና ሜዳልያ በሥጦታ ለማኅበሩ በማበርከት ላይ ይገኛሉ፡፡

ከእነዚህ ተመራቂዎች መካከል በወሎ ዩኒቨርስቲ ደሴ ካምፓስ በእንስሳት ሳይንስ ትምህርት የተመረቀው ዲያቆን ቶሎሳ ታዬ አንዱ ነው፡፡ በዩኒቨርስቲ ቆይታው የግቢ ጉባኤው ሰብሳቢ የነበረ ሲሆን፤ በርካታ ውጣ ውረዶችን ተቋቁሞ 4 ነጥብ 18A+ በማምጣት የዩኒቨርስቲው አጠቃላይ አሸናፊ በመሆን ዋንጫና ሜዳልያ ለመሸለም በቅቷል፡፡

የተሸለመውን ዋንጫ በማኅበረ ቅዱሳን ጠቅላላ ጉባኤ ላይ በመገኘት ለማኅበሩ ሲያስረክብ፤ ሜዳልያውን ደግሞ ከሕፃንነት ጀምሮ ሲያገለግልበት ለነበረው ለምእራብ ወለጋ ሀገረ ስብከት በለስ ወረዳ ዳቡስ መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን እንዲሰጥለት በጉባኤው ላይ ለተገኘው የወረዳ ማእከሉ ተወካይ እንዲያደርስለት አስረክቧል፡፡dn tolosa 3

ዲያቆን ቶሎሳ ዋንጫና ሜዳልያውን ካበረከተ በኋላ ባስተላለፈው መልእክት “ወሎ ዩኒቨርስቲ ስገባ ማኅበሩ ባዘጋጀው የእንኳን ደህና መጣችሁ አቀባበል መርሐ ግብር ላይ ተገኝቼ የጉባኤ ቃና ጋዜጣን ገዝቼ ዶክተር እንግዳ በጅማ ዩኒቨርስቲ ሲመረቁ ያገኙትን ሜዳልያ ለማኅበሩ እንደሰጡ አነበብኩ፡፡ ወዲያውኑ እኔም ለዚህ ክብር እግዚአብሔር ቢያበቃኝ ያገኘሁትን ሽልማት ለማኅበሩ ለመሥጠት ቃል ገባሁ፡፡ እግዚአብሔርም ምኞቴን አሳካልኝ፡፡ ለኔ ይህ ዋንጫ ትልቁ ሀብቴ ነው፤ ሰው ሀብቱ ባለበት ልቡ ይኖራልና ዋንጫውን ሳስብ ማኅበሬን አስባለሁ፤ ተግቼም እንዳገለግል ያደርገኛል፡፡ የማልተካውንና በሕይወቴ አንድ ጊዜ ብቻ የማገኘውን ሀብቴ ለማይተካው የማኅበሬ አገልግሎት መሥጠት ለኔ ታላቅ ደስታ ነው” ብሏል፡፡

በጠቅላላ ጉባኤው ላይ የተገኙት ፕሮፌሰር ጥላሁን ተሾመ ዋንጫውንና ሜዳልያውን ከዲያቆን ቶሎሳ በመረከብ ለማኅበሩ ሰብሳቢና ለወረዳ ማእከሉ ከሠጡ በኋላ የተሰማቸውንdn tolosa 4 ደስታ ሲገልጹ “ይህ ውጤት በሀገራችን በሚገኙ ዩኒቨርስቲዎች ታሪክ በጥቂቶች ብቻ ሊመዘገብ የሚችል ከፍተኛ ውጤት ነው፡፡ ካስመዘገበው ውጤት ይልቅ ደግሞ ታማኝ አገልጋይ ሆኖ በሕይወቱ አንድ ጊዜ ብቻ ሊገጥመው የሚችለውን እድል ውድ ሥጦታ ለማኅበሩ መሥጠቱ አስደንቆኛል፡፡ ብዙዎቻችንንም ያስተማረ ነው፡፡ ወደፊትም በሕይወቱ የተሳካ ጊዜ አሳልፎ ለሌሎች አርአያ እንዲሆን እመኛለሁ” ብለዋል፡፡

የማኅበሩ ሰብሳቢ ቀሲስ ሰሙ ሥጦታውን ከተቀበሉ በኋላ የተሰማቸውን ሲገልጹም “ይህ ሥጦታ ጠቅላላ ጉባኤውንና ማኅበራችንን ወክዬ ነው የተቀበልኩት፡፡ እኛም ይህንን ታሪክና ሀብት ለመጠበቅ፤ አገልግሎቱንም ለማገዝ አብሮንም በአገልግሎት እንዲዘልቅ የምንችለውን ሁሉ እናደርጋለን፤ አደራውንም ተቀብለናል” ብለዋል፡፡

የደሴ ማእከል የማኅበረ ቅዱሳን ጸሐፊ ዲያቆን ሰሎሞን ወልዴ በሠጠው ምሥክርነትም ዲያቆን ቶሎሳ የግቢ ጉባኤው ሰብሳቢ ሆኖ የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች መሠብሠቢያ አዳራሽ በማሠራት፤ በአቅራቢያው ቤተ ክርስቲያን በማሳነጽና በመምራት፤ የሥራ አስፈጻሚና በዩኒቨርስቲው የሚካሔዱ አገልግሎቶችን በማስተባበር ተጠምዶ ስለሚውል ለዚህ ክብር ይበቃል የሚል ግምት አልነበረንም፡፡ ሆኖም ለግቢ ጉባኤውና ማኅበሩ ለሚያከናወነው አገልግሎት አርአያ እንዲሆን ስናበረታታው ቆይተናል፡፡ እግዚአብሔር መልካም ነገር አደረገልን፡፡ በወረዳ ማእከላችን ከሚገኙ 8 ዩኒቨርስቲዎችና ኮሌጆች ውሰጥ ከተዘጋጁት ሜዳልያዎች ሰባቱን የወሰዱት የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች ናቸው ብሏል፡፡

ከዚሁ ጋር በተያያዘ በወልዲያ ዩኒቨርስቲ በደሴ ካምፓስ በትምህርትና እቅድ አስተዳደር ከፍተኛ ውጤት በማምጣት ሜዳልያ ተሸላሚ የሆነው አሰፋ አደፍርስ፤ በደብረ ታቦርdn tolosa 5 ማእከል የፈቃደ እግዚእ ኮሌጅ ተመራቂዎቹ ዘውዴ ደሴና ከፍያለው ስመኝ ለማኅበሩ ማእከላት ሜዳልያቸውን አስረክበዋል፡፡ እንዲሁም ከሐረር የሜንሽን አግሮ ቴክኒካል ኮሌጅ ግቢ ጉባኤ ሰብሳቢ የሆነው ቃል ኪዳን ዓለሙ ሜዳልያውን በማእከሉ በኩል ለኪዳነ ምሕረት ቤተ ክርስቲያን እንዲሰጥለት አበርክቷል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን 11ኛ መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤውን አካሔደ


አትም ኢሜይል
ነሐሴ 27 ቀን 2006 ዓ.ም.
እንዳለ ደምስስ
guba 2006 24  1የማኅበረ ቅዱሳን 11ኛ መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤ ነሐሴ 24 እና 25 ቀን 2006 ዓ.ም. በማኅበሩ ሕንፃ መሰብሰቢያ አዳራሽ የሀገር ውስጥና የውጭ ማእከላት፤ የወረዳ ማእከላትና ግንኙነት ጣቢያዎች፤ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ግቢ ጉባኤያት ተወካዮች፤ የማኅበሩ ሥራ አመራርና ሥራ አሥፈፃሚ አባላት፤ የማኅበሩ ልዩ ልዩ ክፍል ተጠሪዎች፤ ጥሪ የተደረገላቸው ተጋባዥ እንግዶች በተገኙበት አካሄደ፡፡

guba 2006 24  2የጠቅላላ ጉባኤው ተሳታፈዎች ከነሐሴ 23 ቀን 2006 ዓ.ም. ጀምሮ የእንኳን ደህና መጣችሁ አቀባበል የተደረገላቸው ሲሆን፤ የጸሎት፤ የመርሐ ግብር ትውውቅና ማስገንዘቢያ በጠቅላላ ጉባኤው አዘጋጅ አብይ ኮሚቴ ሰብሳቢ በዶክተር ዳኝነት ይመኑ ቀርቧል፡፡ የእጽበተ እግር መርሐ ግብርም ተከናውኗል፡፡

ነሐሴ 24 ቀን 2006 ዓ.ም. ጠዋት ጉባኤው በጸሎተ ወንጌል ተጀምሮ የእንኳን ደህና መጣችሁ መልእክትና የማኅበሩ የሁለት ዓመታት የዕቅድ ክንውን ዘገባ በማኅበሩ ሰብሳቢ ቀሲስ ዶክተር ሰሙ ምትኩ ቀርቧል፡፡ በቀረበው ዘገባም የስብከተ ወንጌል guba 2006 24  3አገልግሎት ፤ የአብነት ትምህርት ቤቶችና ገዳማትን በማጠናከር ረገድ፤ የቤተ ክርስቲያንን መንፈሳዊ አገልግሎት ለማጠናከር ከአህጉረ ስብከቶች ጋር እየተሠሩ ስለሚገኙ በርካታ ተግባራት ፤ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ግቢ ጉባኤያትን በማጠናከር ረገድ፤ የማኅበሩን ተቋማዊ አቅም ለማሳደግ እየተሠሩና በመሠራት ላይ የሚገኙ ሥራዎች፤ ያጋጠሙ ችግሮችና የተወሰዱ መፍትሔዎችን በዝርዝር አቅርበዋል፡፡

የ2005 ዓ.ም. የማኅበሩ የሒሳብ ሪፖርት በማኅበሩ ዋና ጸሐፊ አቶ ተስፋዬ ቢሆነኝ፤ እንዲሁም የኦዲትና ኢንስፔክሽን ሪፖርት በአቶ የሺዋስ ማሞ የቀረቡ ሲሆን፤ የ2004 ዓ.ም. እና የ2005 ዓ.ም. የሁለቱን ዓመታት የኦዲት ሪፖርት ዓለም አቀፍ እውቅና ባለው የውጭ ኦዲተር በማስመርመር በድርጅቱ ሓላፊ የኦዲት ሪፖርቱ ለጠቅላላ ጉባኤው ቀርቧል፡፡ ጠቅላላ ጉባኤውም በቀረቡት ሪፖርቶች ላይ ውይይት በማካሔድ አጽድቋቸዋል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን ከ1996 ዓ.ም. በማኅበሩ ሥራ አመራር ጉባኤ ጸድቆ ሲሠራበት የቆየው የማኅበረ ቅዱሳን ጠቅላላ ጉባኤ ዝግጅትና የምርጫ ሥነ ሥርዓት መመሪያ በአሁኑ ወቅት ማኅበሩ ከደረሰበት የእድገት ደረጃና የአገልግሎት ስፋት አንጻር ሊጣጣም ባለመቻሉ መመሪያውን ማሻሻል በማስፈለጉ በሥራ አመራር ጉባኤው የተሰየመው ኮሚቴ የጥናቱን ረቂቅ ለጠቅላላ ጉባኤው አቅርቧል፡፡ በቀረበው የጠቅላላ ጉባኤ ዝግጅትና የምርጫ ሥነ ሥርዓት መመሪያ ማሻሻያ ረቂቅ ላይ በተሳታፊዎች ውይይት ተካሒዶበት ለማሻሻያ የሚጠቅሙ በርካታ ሃሳቦች ተነስተዋል፡፡ አጥኚ ኮሚቴውም የቀረቡለትን ገንቢ ሃሳቦች በማካተት ለመደበኛ ሥራ አመራር ጉባኤ እንዲያቀርብ፤ ሥራ አመራር ጉባኤውም የቀረበለትን ማሻሻያውን መርምሮ ውሳኔ እንዲያሳልፍ ጠቅላላ ጉባኤው መመሪያ ሰጥቷል፡፡

guba 2006 24  5ጠቅላላ ጉባኤው በሁለተኛ ቀን ውሎው ብፁዕ አቡነ ሰላማ የምሥራቅ ሐረርጌ ሊቀ ጳጳስ የተገኙ ሲሆን፤ በሰጡት ቃለ ምእዳን “ያሰባሰባችሁ እግዚአብሔር ነው፤ በእናንተ ኃይል አልተሰባሰባችሁም፡፡ ፈቃደ እግዚአብሔር አስነስቷችኋልና በጉዟችሁ ፈተና ሊገጥማችሁ ይችላል፡፡ ፈተና ደግሞ ያለ ነው፤ ይጠቅማል እንጂ አይጎዳም፡፡ ከሚወድህ ይልቅ የሚጠላህ ይጠቅምሃል እንዲሉ አባቶቻችን ካልተፈተኑ ክብር አይገኝም፡፡ በአገልግሎታችሁ እንደጸናችሁ ሳትበሳጩ ልትጓዙ ያስፈልጋል፡፡ እግዚአብሔር ማኅበሩን ይባርክ” ብለዋል፡፡

በቀጣይነትም ጠቅላላ ጉባኤው የግቢ ጉባኤያት የእድገትና ውጤታማነት መርሐ ግብር ስልታዊ አቅጣጫና እቅድ በሚቀጥሉት ዐሥር ዓመታት /ከ2007 - 2017/፤ እንዲሁም የማኅበረ ቅዱሳን ስልታዊ እቅድ አጋማሽ ዘመን ግምገማ በሚሉ ሁለት ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ተወያይቷል፡፡

የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት እድገትና ውጤታማነት ስልታዊ አቅጣጫና እቅድ ለሚቀጥሉት ዐሥር ዓመታት ተግባራዊ ለማድረግ በቀረበው ጥናት ላይ ተሳታፊዎችን በ23 ቡድን በመከፋፈል ውይይት ተደርጓል፡፡ በቡድን ውይይቱ የተነሱ በርካታ ነጥቦችን በግብአትነት በመያዝ በዋናነት በተያዙ የጥናቱ ክፍሎች ተከፋፍለዋል፡፡ በዚህም መሠረት የተነደፉት ግቦች፤ ዓላማዎች፤ ስልቶችና ተግባራት ስልታዊ እቅዱን ከማሳካት አንጻር፤ የግቢ ጉባኤያትን ስልታዊ እቅድ ከማስፈጸም አንጻር መዋቅራዊ አደረጃጀቱ ምን መምሠል እንዳለበት፤ በቀረበው ሰነድ ላይ የተጠቀሰው ገንዘብ ማግኛ ስልትና ምንጭ ተገቢ መሆኑን መመልከት፤ የግቢ ጉባኤያት ሁኔታ በአገልግሎት ክፍሎች በዋና ጉዳይነት አካቶ መሥራት በሚሉት ነጥቦች ሥር ለይቶ በመያዝ ለመደበኛ ሥራ አመራር ጉባኤ ለውሳኔ በማቅረብ፤ ሥራ አመራር ጉባኤው የቀረበለትን ሠነድ መርምሮ በማጽደቅ ተግባራዊ እንዲሆን ጠቅላላ ጉባኤው ወስኗል፡፡

guba 2006 24  4የማኅበረ ቅዱሳን ስልታዊ እቅድ አጋማሽ ዘመን ግምገማ በማስመልከት ከጥር 2005 ዓ.ም. እስከ ግንቦት 2006 ዓ.ም. የተከናወኑትን ሥራዎች ተገምግመው ሓላፊነት በወሰደው አጥኒ ቡድን ለጠቅላላ ጉባኤው ቀርበዋል፡፡ ጠቅላላ ጉባኤውም ውይይት በማድረግ አቅጣጫ ሰጥቷል፡፡ በዚህም መሠረት ቀጣይ አፈጻጸማችን ምን መምሰል እንደሚገባው ለማሳየት ቢሞከር፤ የስብከተ ወንጌል አገልግሎት ከስትራቴጂክ እቅዱ አንጻር አስታርቆ ማስኬድ፤ የክብደት አሥራር ሥርዓቱን ግልጽ ማድረግ፤ ግምገማው ከስልታዊ እቅዱ ጋር በደንብ ቢታይ የሚሉና ሌሎችም ጠቃሚ ነጥቦች ከተካተቱት ውስጥ ይገኙበታል፡፡ የጥናት ቡድኑ ከጠቅላላ ጉባኤው በተሰጡት ሃሳቦች መሠረት የግምገማውን ውጤት በአጭር ጊዜ ውስጥ ለመደበኛ ሥራ አመራር ጉባኤ እንዲያቀርብ፤ ሥራ አመራር ጉባኤውም አጽድቆ በሚመለከታቸው አካላት ተግባራዊ እንዲደረግ እንዲያስተላልፍ ውሳኔ ላይ ተደርሷል፡፡

በጠቅላላ ጉባኤው ማጠቃለያ ላይም የዝግጅቱ አብይ ኮሚቴ ሰብሳቢ ዶክተር ዳኝነት ይመኑ ለጉባኤው መሳካት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያደረጉ ድርጅቶችንና በጎ አድራጊ ምእመናንን በዝርዝር በመጥቀስ በጠቅላላ ጉባኤው ስም ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡ እንዲሁም የጠቅላላ ጉባኤው ተሳታፊዎች ጉባኤው እሰኪጠናቀቅ ድረስ ላሳዩት አርአያነት ላለው ሥነ ምግባር የተላበሰ ታዛዥነትና ተሳትፎ አመስግነዋል፡፡

በጉባኤው ማጠቃለያም ቀሲስ ዶክተር ሰሙ ምትኩ የጠቅላላ ጉባኤው ተሳታፊዎች ለሦስት ቀናት በትዕግስት፤ በታዛዥነትና በንቁ ተሳታፊነት ለአገልግሎት ጠቃሚ የሆኑ ሃሳቦችን በማምንጨት ላበረከቱት አስተዋጽኦ ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡

በጠቅላላ ጉባኤው ከ650 በላይ ተወካዮች ተሳትፈዋል፡፡

2014 ኦገስት 16, ቅዳሜ

ጾመ ፍልሰታ የእመቤታችን ዕረፍት

ጾመ ፍልሰታ የእመቤታችን ዕረፍት

Written By Hulubante Abebe on Tuesday, August 5, 2014 | 1:02 PM

  መ/ር ሳሙኤል ተስፋዬ                                                                                           
 
ጾመ ፍልሰታ የእመቤታችን ዕረፍት፣ ትንሣኤና ዕርገቷ የሚታሰብበት ወቅት ነው፡፡ እመቤታችን በተለያዩ ጊዜያት ሞትና ትንሣኤዋን ለሐዋርያት የገለጸችበትን ምስጢር ከነሐሴ 1-16 ድረስ ምእመናን በጾም በጸሎት ተወስነው የልጇን ቸርነት የእርሷን አማላጅነት በሱባኤ ይማጸናሉ፡፡ የሱባኤው ወቅት ሲፈጸም “እመቤታችን በእውነት ተነሥታለች” ብለው በደስታ የጾሙን ወቅት ይፈጽማሉ፡፡ ሞቷ የሚያስደንቅ መሆኑን ቅዱስ ያሬድ “ሞትሰ ለመዋቲ ይደሉ ሞታ ለማርያም የሐጽብ ለኲሉ፤ ሞት ለማናቸውም ሰው ሁሉ የተገባ ነው፡፡ የማርያም ሞት ግን ሁሉን ያስደንቃል” በማለት ገልጾታል፡፡
በኢትዮጰያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ትውፊት መሠረት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በዚህ ዓለም በሕይወተ ሥጋ 64 ዓመታት ያህል ቆይታ አርፋ ተነሥታ በክብር አርጋለች፡፡ ይህንን የትንሣኤና ዕርገት ዐቢይ ምሥጢር ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት “ተንሥአ እግዚኦ” ውስተ ዕረፍትከ፡፡ አንተ ወታቦተ መቅደስከ፤ አቤቱ ወደ ዕረፍትህ ተነሥ፡፡ አንተና የመቅደስህ ታቦት” /መዝ.131፡8/፤ እንዲሁም “ወትቀውም ንግሥት በየማንከ በአልባሰ ወርቅ ዑጽፍት ወኁብርት፤ በወርቅ ልብስ ተጎናጽፋና ተሸፋፍና ንግሥቲቱ በቀኝህ ትቆማለች” /መዝ.44፡9/ ሲል የተናገረው ቃለ ትንቢት በንጽሐ ሥጋ፣ በንጽሐ ነፍስ፣ በንጽሐ ልቡና የጸናች የቅድስት ድንግል እመቤታችንን ዕረፍት፣ ትንሣኤ፣ ፍለሰት /ዕርገት/ ያስገነዝባል፡፡ /ራእ.11፡19/

እመቤታችን ታቦተ እግዚአብሔር መሆኗን አባ ጽጌ ድንግል በማኅሌተ ጽጌ ሲገልጽ “ከመ ታቦት ሥርጉት በወርቀ ዓረብ ወተርሴስ በድንግልና ማርያም ሥርጉተ ሥጋ ወነፍስ” ሲል አመስግኗታል፡፡ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን በትርጓሜያቸው ይህንን ቃለ ትንቢት ቅዱስ ዮሐንስ በራእዩ ከገለጣት “ንግሥተ ሰማይ፤ የሰማይ ንግሥት” /ራእ.12፡1/ ጋር በማገናዘብ የእመቤታችንን ሁለንተናዊ ክብርና ልዕልና አምልተውና አስፍተው ገልጸውታል፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ በራእዩ “… በጌታ የሚሞቱ ሙታን ብፁዓን ናቸው፡፡….. ከድካማቸው ያርፉ ዘንድ ሥራቸውም ይከተላቸዋል” /ራእ.14፡13/ ብሎ እንደመሰከረው እመቤታችን ከዕረፍቷና ዕርገቷ በኋላ የመጨረሻ ወደ ሆነው ክብር መሸጋገሯ ያስረዳል፡፡
ይህንን ክብርዋን በመረዳት ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ዘወትር “ወበእንተዝ ናዐብየኪ ኩልነ ኦ እግዝእትነ ወላዲተ አምላክ ንጽሕት ኩሎ ጊዜ፡፡ ንስአል ወናንቀዐዱ ኀቤኪ ከመ ንርከብ ሣህለ በኀበ መፍቀሬ ሰብእ፤ ሁልጊዜ ንጽሕት የምትሆኚ አምላክን የወለድሽ እመቤታችን ሆይ ስለዚህ ነገር እናከብርሻለን፣ እናገንሻለን፡፡ ሰውን ከሚወድ ልጅሽ ዘንድ የቅርታንና ምሕረትን እናገኝ ዘንድ ሁል ጊዜ ዓይነ ልቡናችንን ወደ አንቺ እናነሣለን፡፡ በማለት ቤዛዊተ ዓለም ድንግል ማርያም ከልዑል እግዚአብሔር ዘንድ ሁል ጊዜ ዓይነ ልቡናችንን ወደ አንቺ እናነሣለን፡፡ በማለት ቤዛዊተ ዓለም ድንግል ማርያም ከልዑል እግዚአብሔር ዘንድ የተሰጣትን ልዩ የቃል ኪዳን ጸጋና አምላካዊ ክብር እያመሰጠሩ ያመሰግኗታል፡፡ ሊቁ “ቀስተ ደመና ማርያም ትእምርተ ኪዳኑ ለኖኅ፣ ዘእግዚአብሔር ሤመኪ ለተዝካረ ምሕረት ወፍትሕ፣ ህየንተ ቀስፍ ለምድር ወአማሰና አይኅ፡፡ ብሎ እንዳመሰገናት፡፡

እመቤታችን በአጸደ ሥጋ ሳለች ከሦስቱ አካላት አንዱ አካል እግዚአብሔር ወልድ በተለየ አካሉ በተዋሕዶ ሰው ሆኖ በመዋዕለ ሥጋዌ ላደረገው የድኅነት ዓለም ጉዞ ምክንያት ነበረች፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ የሰው ልጆችን ባርነትና ስደት ለማጥፋት ወደዚህ ዓለም በመጣ ጊዜ የሰው ልጆችን ያሳደደ ሠይጣን በሄሮድስ አድሮ ሲያሳድደው ልጇን ይዛ በመሰደድ ለድኅነታችን ምክንያት ነበረች፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ በራእዩ እንዳየው፤ “ታላቅ ምልክትም በሰማይ ታየ ፀሐይን ተጐናጽፋ ጨረቃ ከእግሮችዋ በታች ያላት በራስዋም ላይ የአሥራ ሁለት ከዋክብት አክሊል የሆነላት አንዲት ሴት ነበረች፡፡ እርስዋም ፀንሳ ነበር፡፡ ምጥም ተይዛ ልትወልድ ተጨንቃ ጮኸች፡፡ ዘንዶውም ሴቲቱ በወለደች ጊዜ ሕፃንዋን እንዲበላ ልትወልድ ባላት ሴት ፊት ቆመ፡፡ አሕዛብንም ሁሉ በብረት በትር ይገዛቸው ዘንድ ያለውን ወንድ ልጅ ወለደች፤ ልጅዋም ወደ እግዚአብሔር ወደ ዙፋኑ ተነጠቀ፡፡ ሴቲቱም ሺህ ከሁለት መቶ ስልሳ ቀን በዚያ እንዲመግቡአት በእግዚአብሔር ተዘጋጅቶላት ወደ ነበረው ስፍራ ወደ በረሀ ሸሸች ”/ራእ.12፡1-6/

“ዘንዶውም ወደ ምድር እንደተጣለ ባየ ጊዜ ወንድ ልጅ የወለደችውን ሴት አሳደዳት፡፡ ከእባቡም ፊት ርቃ አንድ ዘመን፣ ዘመሃትም፣ የዘመን እኩሌታ ወደምትመገብበት ወደ ሥፍራዋ፣ ወደ በረሀ እንድትበር ለሴቲቱ ሁለት የትላቁ ንሥር ክንፎች ተሰጣት፡፡ እባቡም ሲቲቱ በወንዝ እንድትወሰድ ሊያደርግ ወንዝ የሚያህልን ውኃ ከአፉ በስተኋላዋ አፈሰሰ፡፡ ምድሪቱም ሴቱቱን ረዳቻት፡- ምድሪቱም አፍዋን ከፍታ ዘንዶው ከአፉ ያፈሰሰውን ወንዝ ዋጠችው፡፡ ዘንዶውም በሴቲቱ ላይ ተቈጥቶ የእግዚአብሔርን ትእዛዛት የሚጠብቁትን የኢየሱስም ምስክር ያላቸውን ከዘርዋ የቀሩትን ሊዋጋ ሄደ፤ በባሕርም አሸዋ ላይ ቆመ፡፡” /ራእ.12፡13-17/ ሲል መስክሮአል፡፡

ኢየሱስ ክርስቶስ የመጀመሪያውን አምላካዊ ድንቅ ተአምር ባደረገበት በቃና ዘገሊላ ሠርግ ቤት እመቤታችን ከልጇ ከወዳጇ ጋር እንደነበረችና ለተአምሩም ምክንያት ነበረች፡፡ በገሊላ ቃና የተፈጸመው ታላቅና ድንቅ አምላካዊ የቸርነት ሥራ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዕለተ ዓርብ የፈጸመውን የቤዛነት ሥራ ሲያደርግ ምክንያት የነበረችው እመቤታችን ነች፡፡ ይኸውም በቀራንዮ አደባባይ በተሰቀለባትና ማየ ሕይወት የሆነውን አማናዊ ወይን ደሙን ባፈሰሰባት ዕለት ቤዛዊተ ዓለም ድንግል ማርያም ከእግረ መስቀሉ አጠገብ ነበረች፡፡ በዚህም አዲሲቷ ሔዋን እመቤታችን በክርስቶስ ቤዛነት ለዳነውና በወርቀ ደሙም ለተዋጀው አዲሱ የሰው ዘር ማለትም የክርስቶስ ምሥጢራዊ አካል /ቤተ ክርስቲያን/ መንፈሳዊት እናት ሆና በጸጋ ተሰጥታናለች /ዮሐ.19፡26-27/

የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ሞትና ትንሣኤ ነገረ ማርያም፣ ስንክሳርና ተአምረ ማርያም እንደሚያስረዱት፤ ጥር 21 ቀን ዐርፋለች፡፡ እረፍቷን ቅዱስ ዳዊት ሲናገር “አቤቱ ወደ እረፍትህ ተነሥ አንተና የመቅደስህ ታቦት” መዝ.136፡8 ፈጣሪዬ ሆይ ምእመናንን ወደምታሳርፍበት ወደ መንግሥተ ሰማያት የመቅደስህን ታቦት ድንግል ማርያምን ይዘህ ተነሥ ሲል ቅዱስ ዳዊት ተናግሯል፡፡ ይህም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም 64 ዓመት በዚህ ዓለም ከኖረች በኋላ ነብሷ ከሥጋዋ ተለይቶ እንደ ልጅዋ ትንሣኤ መነሣቷን የሚያመለክት ነው፡፡ ታቦት ያላትም ማደሪያው ስለሆነች ነው፡፡

ጠቢቡ ሰሎሞን “ወዳጄ ሆይ ተነሺ ውበቴ ሆይ ነይ እነሆ ክረምት አለፈ ዝናቡም አልፎ ሄደ አበቦች በምድር ላይ ተገለጡ፡፡ የዜማም ጊዜ ደረሰ የቀረ… ቃል በምድራችን ተሰማ፡፡ በለሱ ጐመራ ወይኖችም አበቡ መዓዛቸውንም ሰጡ፡፡ ወዳጄ ሆይ ተነሺ ውበቴ ሆይ ነይ” ሲል ስለ እመቤታችን በምሳሌ ተናግሮአል፡፡ መኃ 2፡1አ-13

ወዳጁን ውበቱን ተነሺ ነይ እያለ የተጣራው ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ተጠሪዋም እመቤታችን ናት፡፡ እነሆ ክረምት አለፈ ማለት በስደት በአይሁድ የዘወትር ጠላትነት በልጅዋ መከራና ስቅላት ስምዖን በቤተ መቅደስ እንደተናገረ ልቧ በሀዘን ሠይፍ የተከፈለበት በሀዘን ፍላጻ የተወጋበት የመከራ ክረምት /ወቅት/ አልፎ የክርስቶስ ሕማሙ ፣ ሞቱ፣ ቤዛነቱ ተፈጽሟል፡፡ ትንሣኤው በምድር ላይ ተገልጧል፣ ተሰብኳል ማለት ነው፡፡ በምድራችን አበባ ታይቷል ማለት የሐዋርያት ድምፅ በምድር ሁሉ ደርሷል ማለት ነው፡፡

ነቢዩ ዳዊት ድምፃቸው ወደ ምድር ሁሉ ቃላቸውም እስከ ዓለም ዳርቻ ወጣ ብሎ ስለ ሐዋርያት የተናገረው በዓለም ያለውን መከራ ስድት ሲገልጽ ነው፡፡ /መዝ 18¸4/ የዜማም ጊዜ ደረሰ ያለው የመከራን ጊዜ ነው፡፡ ሸለቆችም በእህል ተሸፈኑ በደስታ ይጮሃሉ፣ ይዘምራሉም ተብሏል፡፡ መዝ 14፡13 የመከር ጊዜ ደረሰ የተባለው መከር የፍሬ ጊዜ በመሆኑ ክርስትና አፍርቷል ማለት ነው፡፡ በለሱ ጐመራ ማለት ደግሞ በጐ ምግባረ ፍሬ ሳያፈሩ የነበሩ ሰዎች በጐ ምግባር መሥራት መጀመራቸውን የሚያሳይ ነው፡፡ በመጨረሻም ወይኖች አብበዋል፣ መዓዛቸውንም ሰጥተዋል እንደተባለ በመላው ዓለም አብያተ ክርስቲያናት በሃይማኖት ማበብ መዓዛ ምግባራቸውን ማቅረብ ከጀመሩ በኋላ እመቤታችን አረፈች፡፡

እመቤታችን ጥር 21 ቀን እረፍት በሆነበት እለት ሐዋርያት የእመቤታችንን ሥጋ ለማሳረፍ ወደ ጌቴሰማኒ መካነ እረፍት ይዘው ሲሄዱ አይሁድ በቅንዓት መንፈስ ተነሣሥተው “ቀድሞ ልጅዋን በሦስተኛው ቀን ከሙታን ተነሳ፡፡ በአርባኛው ቀን ወደ ሰማይ አረገ፡፡ እንደገናም ተመልሶ ይህን ዓለም ለማሳለፍ ይመጣል" እያሉ በማስተማር ሕዝቡን ፈጽመው ወስደውታል፡፡ አሁን ደግሞ ዝም ብለን ብንተዋት እርሷንም እንደ ልጅዋ ተነሣች አረገች እያሉ በማስተማር ሲያውኩን ሊኖሩ አይደለምን; ኑ ተሰብሰቡና በእሳት እናቃጥላት ብለው ተማክረው መጥተው ከመካከላቸው ታውፋኒያ የተባለው ጐበዝ አይሁዳዊ ተመርጦ ሄዶ የእመቤታችንን ሥጋ የተሸከሙትን አልጋ ሽንኮር ያዘ፡፡ የአልጋውን ሽንኮር በያዘ ጊዜ የእግዚአብሔር መልአክ በእሳት ሠይፍ ሁለት እጁን ስለ ቆረጣቸው ከአልጋው ሽንኮር ላይ ተንጠልጥለው ቀሩ፡፡ ታውፋንያ በፈጸመው ድርጊት ተጸጽቶ ወደ እመቤታችን ስለተማጸነ በተአምር የተቆረጡ እጆቹን እንደ ቀድሞ አድርጋ ፈውሳዋለች (ስንክሳር ዘጥር፡፡)

የእግዚአብሔር መልአክ የእመቤታችን ሥጋ ከሐዋርያው ዮሐንስ ጋር ተድላ ደስታ ወደ አለባት ገነት በመንፈስ ቅዱስ ተነጠቁ፡፡ ጌታም የእመቤታችንን ሥጋ ታወጣ ዘንድ ምድርን እንዲጠሩዋት ሰባቱን የመላእክት አለቆች አዘዛቸው፡፡ እነርሱም ትወጪ ዘንድ እግዚአብሔር አዞሻል አሏት፡፡ ያን ጊዜም ከእፅ ሕይወት በታች ካለ መቃብር የእመቤታችን የማርያም ሥጋዋ ወጣ፡፡ ጌታችንም ዘላለማዊ ወደሆነ መንግሥተ ሰማያት መላእክት እና ሰማእታት እየሰገዱላት አሳረጓት፡፡ ንጉሥ ዳዊት “በወርቅ ልብስ ተጐናጽፋ ተሸፋፍና ንግሥቲቱ በቀኝህ ትቆማለች” እንዳለ፡፡ መዝ 44፡9

ወንጌላዊ ዮሐንስም ከእርሷ በረከትን ተቀብሎ ተመልሶ ከሰማይ ወረደ፡፡ ሐዋርያት ተሰብስበው ስለ እመቤታችን ሥጋ ፈጽሞ ሲያዝኑና ሲተክዙ አገኛቸው፡፡ እርሱም እንዳየ እንደሰማ ሥጋዋም በታላቅ ክብር ማረጉን ነገራቸው፡፡ ሐዋርያትም ዓመት ሙሉ ቆዩ፡፡ የነሐሴም ወር በባተ /በገባ/ ቀን ዮሐንስ እንዲህ አላቸው፡፡ የእመቤታችንን ሥጋዋን ለማየት ኑ፤ ሁለት ሱባኤ በመጾም እንለምን አለ፡፡ በጾም በጸሎት ሱባኤ ያዙ፤ ጌታም የእመቤታችንን ሥጋ አምጥቶ ስለሰጣቸው በታላቅ ዝማሬ፣ በውዳሴና በምሕላ ወስደው ቀድሞ በተዘጋጀው መካነ እረፍት በጌቴሴማኒ ቀበሯት፡፡

የእመቤታችን የቀብር ሥነ ሥርዓት በተፈጸመ ጊዜ ከአሥራ ሁለቱ አንዱ ቶማስ አልነበረምና ከሀገረ ስብከቱ በደመና ተጭኖ ወደ ኢየሩሳሌም ሲመጣ እመቤታችን በተቀበረች በሦስተኛው ቀን እንደ ልጅዋ ትንሣኤ ተነሥታ ስታርግ ያገኛታል፡፡ ትንሣኤዋን ሌሎቹ ሐዋርያት አይተው ለእርሱ የቀረበት መስሎት ተበሳጭቶ “በመጀመሪያ የልጅሽን ትንሣኤ አሁን ደግሞ የአንቺን ትንሳኤ ሳላይ ቀረሁ” ብሎ ከማዘኑ የተነሣ ከደመናው ተወርውሮ ሊወድቅ ቃጣው፡፡ እመቤታችንም ከእርሱ በቀር ሌሎቹ ሐዋርያት ትንሳኤዋን እንዳላዩ ነግራው አጽናንታው ሄዶም ለሐዋርያት የሆነውን ሁሉ እንዲነግራቸው አዝዛው ምልክት ይሆነው ዘንድ ሰበኗን - መግነዟን ሰጥታው አረገች፡፡

ሐዋርያው ቶማስም ኢየሩሳሌም በደረሰ ጊዜ እመቤታችንን እኮ ቀበርናት ብለው ነገሩት እርሱም “ሞት በጥር በነሐሴ መቃብር እንዴት ይሆናል?” አላቸው፡፡ “አንተ እንጂ የጌታን ትንሣኤ ተጠራጠርክ አሁንም አታምንምን;” ብለው በቅዱስ ጴጥሮስ መሪነት ወደ እመቤታችን መካነ መቃብር ይዘውት ሄደው መቃብሩን ቢከፍቱ ሥጋዋን አጡት፡፡ ደነገጡም፡፡ ቶማስም “አታምኑኝም ብዬ እንጂ እመቤታችን ተነሥታ አርጋለች” ብሎ የሆነውን ሁሉ ነገራቸው፡፡ ለማረጋገጫ ምልክት እንዲሆን የሰጠችውን ሰበኗን አሳያቸው፡፡ ሰበኗን - መግነዟን ለበረከት ቆራርጠው ከተከፋፈሉ በኋላ ወደየአህጉረ ስብከታቸው ሄደዋል፡፡

ሐዋርያትም ትንሣኤሽን ቶማስ አይቶ እኛ እንዴት ይቀርብናል ብለው በቀጣዩ ዓመት ከነሐሴ አንድ ቀን ጀምረው ሱባኤ ገቡ፡፡ በሱባኤው መጨረሻ በነሐሴ አሥራ ስድስት ቀን ጌታችን ጸሎታቸውን ተቀብሎ እመቤታችንን መንበር፣ ቅዱስ ጴጥሮስን ንፍቅ ረዳት ቄስ፣ ቅዱስ እስጢፋኖስን ገባሬ ሰናይ ዋና ዲያቆን አድርጐ ቀድሶ ሁሉንም ከአቆረባቸው በኋላ የእመቤታችንን እርገቷን ለማየት አብቅቷቸዋል፡፡

ቤተክርስቲያናችንም ሥርዓት ሠርታ ከሰባቱ ዓበይት አጽዋማት ተርታ አስገብታ ይህን ታላቅ የበረከትና የምሥጢር መግለጫ ጾም እንድንጾም አድርጋናለች፡፡ ሐዋርያት ያዩትን ድንቅ ምሥጢር የእመቤታችንን ትንሣኤና ዕርገት ለማየትና ከሐዋርያት አበው በረከት ለመሳተፍ ጌታችን “ልጆቼ” ይላቸው ለነበሩ ሐዋርያት አምሳል ሕፃናትና ወጣቶች፣ ሴቶችና ወንዶች፣ አረጋውያንም የጾመ ፍልሰታን መድረስ በናፍቆት እየጠበቁ በየዓመቱ በጾም በጸሎት ያሳልፉታል፡፡

ጾመ ፍልሰታ በሕፃናት፣ በምእመናንና በካህናት ዘንድ በተለየ ፍቅር የምትታይና ታላቅ መንፈሳዊ አገልግሎት የሚከናወንባት ወቅት ናት፡፡ ካህናት ሌሊት በሰዓታት ቀን በቅዳሴ፣ መዘምራን በስብሐተ ነግህ /የጠዋት ምስጋና/ ሕፃናት በመዝሙር ያሳልፏታል፡፡ እናቶች ደግሞ ጠዋት ውዳሴ ማርያምና ቅዳሴ ማርያም ትርጓሜ ሲያዳምጡ፣ ቀን ቅዳሴ ሲያስቀድሱ ውለው ማታ መብራት አብርተው መዝሙረ ፍልሰታን ይዘምራሉ፡፡ በመዝሙሩ የቅድስት ድንግል ማርያምን ስደት፣ የደረሰባትን መንገላታትና አማላጅነት በማንሳት የተማኅጽኖ ጸሎት ያቀርባሉ፡፡ በምግባር በሃይማኖት መጽናት የሚሰጠውን ጸጋ ይናገራሉ፡፡ እናቶች ከመዘምሩት መዝሙር መካከል፤-

ወፌ ሰንበታ ሰንበታ
መጣች ለፍልሰታ
አገርሽ የት ነው ኤፍራታ
አሳድሪኝ ማታ፡፡

ይናፍቀኛል ሌሊት
የሰማይ እልፍኝ መብራት
ወፌ የኔ እመቤት /2/

ከሁሉ ከሁሉ ጤፍ ታንሳለች
ከጭቃ ወድቃ ታነሣለች

ከዚያች ጤፍ ከዚያች ጤፍ
የአዳም ልጅ ሁሉ አትስንፍ

የአዳም ልጅ ሁሉ ሰነፈና
የኑሮ ቤቱን ረሳና

ተው አትርሳ
ተው አትርሳ

ተሠርቶለሃል የእሳት አልጋ
ያን የእሳት አልጋ

የእሳት ባሕር
እንደምን ብለህ ትሻገር
ተሻገሩት አሉ በሠሩት ምግባር
እኔ ባሪያሽ ወዴት ልደር
/እንደምን ብዬ ልሻገር/
ሰላም ሰጊድ እያሉ ሌሊቱን በሙሉ እሳት አንድደው ያመሰግኗታል፡፡ ይማጸኗታል፡፡

የእመቤታችን ትንሣኤና እርገት መታሰቢያ - ጾመ ፍልሰታ ብዙዎች ከቤታቸው ተለይተው በመቃብር ቤት ዘግተው፣ አልጋና ምንጣፍ ትተው፣ በመሬት ላይ ተኝተው ዝግን ጥሬ እፍኝ ውኃ እየቀመሱ በጾምና በጸሎት በመትጋት በታላቅ ተጋድሎ ይሰነብታሉ፡፡ በሰሙነ ፍልሰታ ምእመናን ለእመቤታችን ያላቸውን ጽኑና ጥልቅ ፍቅር የሚያሳዩበት ነው፡፡


ጌታችን ሦስት መዓልት ሦስት ሌሊት በከርሰ መቃብር ቆይቶ ሙስና መቃብር ሳያገኘው፣ መግነዝ ፍቱልኝ መቃብር ክፈቱልኝ ሳይል በሥልጣኑ እንደተነሣ እርሷም በተቀበረች በሦስተኛው ቀን ማኅደረ መለኮት ናትና ሙስና መቃብር ሳያገኛት መግነዝ ፍቱልኝ፣ መቃብር ክፈቱልኝ ሳትል የልጅዋ ሥልጣን ኃይል ሆኗት መነሣቷን ትንሣኤዋ “ከመ ትንሣኤ ወልዳ፤ እንደ ልጅዋ ትንሣኤ” ነው ተብሎ ሲከበርላት ይኖራል፡፡

2014 ኦገስት 15, ዓርብ

ደብረ ታቦርና ቡሄ



አትም ኢሜይል
 ነሐሴ 5 ቀን 2006 ዓ.ም.
መ/ር ሳሙኤል ተስፋዬ
የኢትየጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከምታከብራቸው ዘጠኝ ዓበይት በዓላት አንዱ የደብረ ታቦር በዓል ነው። በየዓመቱ ነሐሴ ፲፫ ቀን የሚከበረው ይህ በዓል መሠረቱ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ደብረ ታቦር ኢየሱስ ክርስቶስ ሦስት ደቀመዛሙርቱን ይዞ ወደ ተራራው የወጣበትና ፊቱ እንደ ፀሐይ የበራበት፣ ልብሱም እንደብርሃን ነጭ የሆነበት፣ ብርሃነ መለኮቱን የገለጠበት ተራራ ነው።
ከስድስት ቀንም በኋላ ኢየሱስ ጴጥሮስንና ያዕቆብን ወንድሙንም ዮሐንስን ይዞ ወደ ረጅም ተራራ ብቻቸውን አወጣቸው። በፊታቸውም ተለወጠ፥ ፊቱም እንደ ፀሐይ በራ፥ ልብሱም እንደ ብርሃን ነጭ ሆነ። እነሆም፥ ሙሴና ኤልያስ ከእርሱ ጋር ሲነጋገሩ ታዩአቸው። ጴጥሮስም መልሶ ኢየሱስን ጌታ ሆይ፥ በዚህ መሆን ለእኛ መልካም ነው፤ ብትወድስ፥ በዚህ ሦስት ዳስ አንዱን ለአንተ አንዱንም ለሙሴ አንዱንም ለኤልያስ እንሥራ አለ። እርሱም ገና ሲናገር፥ እነሆ፥ ብሩህ ደመና ጋረዳቸው፥ እነሆም፥ ከደመናው። በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ ይህ ነው፤ እርሱን ስሙት የሚል ድምፅ መጣ። ደቀ መዛሙርቱም ሰምተው በፊታቸው ወደቁ እጅግም ፈርተው ነበር።

ኢየሱስም ቀርቦ ዳሰሳቸውና፡ ተነሡ አትፍሩም አላቸው። ማቴ. ፲፯፡፩-፭ በቤተ ክርስቲያን ደብረታቦር ከቤተክርስቲያን ውጭ አከባበሩ ቡሄ እየተባለ የሚከበረው በዓል በሀገራችን በየዓመቱ ነሐሴ ፲፫ ቀን በታላቅ ድምቀት ይከበራል፡፡ ቡሄ ማለት ብራ፣ ብርሃን፣ ደማቅ ገላጣ፣ የተገለጠ ማለት ነው፡፡ ቡሄ ሲመጣ የክረምቱ ጨለማነት አልፎ ወደ ብርሃን፣ ወደ ጥቢ የሚያመራበት፣ ወደ መፀው የሚዘለቅበት ወገግታ ፣ ሰማይ ከጭጋጋማነት ወደ ብሩህነት የሚለወጥበት፣ የሚሸጋገርበት ወቅት በመሆኑ ከቡሄ በኋላ የጠነከረ ክረምት አይኖርም፡፡ በዚህ መሰረት የክረምቱ አፈና ተወግዶ የብርሃን ወገግታ የሚታየውም በዚህ በዓል አካባቢ ስለሆነ ይቺ ዕለት 'ቡሄ' የሚለውን ስያሜ አገኘ። ቡሄ ማለት ገላጣ፣ የተገለጠ ማለት ነው፡፡ ጌታችን ብርሃነ መለኮቱን የገለጠበት፣ ብረሃን የታየበት ድምጸ መለኮት የተሰማበት ስለሆነ፤ ችቦ ስለሚበራ የብርሃን በዓል በማለት የቡሄ በዓልም ይባላል፡፡

በገጠርም ሆነ በየከተማው ልጆች ጅራፋቸውን ገምደው ሲያጮሁ ይሰነብታሉ። እናቶችም ለበዓሉ ዝግጅት ስንዴ ሲለቅሙ፣ ሲፈትጉ፣ ሲፈጩ ይሰነብታሉ። መነሻ የሆናቸው ትውፊት ጌታችን ብርሃነ መለኮቱን የገለጠበት ዕለት ጊዜው ምሽት ነበር፡፡ እረኞችም ከብርሃኑ የተነሣ እየተገረሙና እየተደነቁ ወደ ቤት አልተመለሱም ነበር፡፡ የልጆቹን መዘግየት ያዩ ወላጆች ችቦ አብርተውና ዳቦ ይዘው ፍለጋ ወጥተዋል ፡፡ያንን ለማስታወስ «ቡሄ» ለሚሉ ልጆች ሙልሙል ዳቦ የሚሰጠውና ችቦ በማብራት በዓሉን የሚከበረው ከዚህ በመነሣት ነው፡፡ የንጋት ወጋገን ሲፈናጠቅ ልጆች በከባድ ድምጽና በጅራፍ ጩኸት የሚታጀብ፣ በገደላገደል ስር እንዲያስተጋባ ተደርጎ ብዛት ባላቸው ህጻናት በከፍተኛ ድምጽ የሚዘመር ነው ቡሄ ። የጅራፉ ጩኸትም እግዚአብሔር አብ “የምወደው ልጄ ይህ ነው እርሱን ስሙት” ሲል ሐዋርያት ራሳቸውን ስተው የወደቁበትን የመለኮት ድምፅ ለማስታወስ ነው፡፡

ደብረታቦር ወይም ቡሄ በአብነት ተማሪዎች “ስለ ደብረ ታቦር" እያሉ እህል፣ ፣ ጌሾ ለምነው ጠላውን ጠምቀው፣ ዳቦውን ጋግረው፣ ቆሎውን ቆልተው ለደብረ ታቦር ዕለት ሊያስቀድሱ የመጡትን ምዕመናን በመጋበዝ በታላቅ ድምቀት ያከብራሉ፡፡ ይህ ትውፊት መምህረ ሐዋርያት የነበረው ኢየሱስ ክርስቶስ ሦስቱን ተማሪዎቹን ጴጥሮስን፣ ያዕቆብንና ወንድሙንም ዮሐንስን ይዞ ወደ ደብረ ታቦር ይዞ ሄዶ የተገለጠ ምስጢር ስለሆነ ከመምህራቸው ጋር በመሆን በዓለ ደብረ ታቦርን /ቡሄን ያከብራሉ፡፡ ስሙን ይጠራሉ፡፡
የደብረ ታቦር ወይም የቡሄ ግጥሞች
ድምጽህን ሰማና በብሩህ ደመና
የቡሄው ብርሃን ለኛ መጣና
ያዕቆብ ዮሃንስ ሆ! እንዲሁም ጴጥሮስ
አምላክን አዩት ሆ! ሙሴ ኤልያስ
አባቱም አለ ሆ! ልጄን ስሙት
ቃሌ ነውና ሆ! የወለለድኩት
ድምጽህን ሰማና በብሩህ ደመና
የቡሄው ብርሃን ለኛ መጣና።
መጣና መጣና ደጅ ልንጥና
መጣና ባመቱ እንዴት ሰነበቱ፣
ክፈት በለዉ በሩን የጌታዪን
ክፈት በለዉ ተነሳ ያንን አንበሳ፣
የመሳሰሉት

2014 ኦገስት 12, ማክሰኞ

ፍልሰታና ሻደይ

አትም ኢሜይል
ነሐሴ 4 ቀን 2006 ዓ.ም.
ከጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ በኋላ በመላው ዓለም የክርስትና እምነት በሐዋርያቱ መሰበክ ከጀመረበት ጊዜ ጀምሮ በኢትዮጵያ ሀገራችን የክርስትና እምነት የተሰበከ ሲሆን በተለይም ሀገራችን የሰሜኑ ክፍል በወቅቱ ቀድሞ ክርስትና የተሰበከበትና የሀገሪቱ ዋና ማእከል የነበረ ነው። ይህን ደግሞ ህዝበ ክርስቲያኑ ለረጅም ዘመናት ሥርዓተ አምልኮ ሲፈጽምባቸው ነበሩ በአካባቢው የሚገኙ በርካታ ጥንታዊ አብያተ ክርስቲያናትና መንፈሳዊ ቁሶች ያስረዳሉ። እነዚህም የሚዳሰሱና የማይዳሰሱ መንፈሳዊ ቅርሶች ናቸው። ከማይዳሰሱ መንፈሳዊ ቅርሶች መካከል የተለያዩ መንፈሳዊ በዓላት የሚከበሩበት ሥርዓት አንዱ ነው።

asendya 01በዋግ ኽምራ ሀገረ ስብከት ከሚከበሩ በዓላት መካከል የሻደይ ምስጋና / ጨዋታ አንዱ ሲሆን ልጃገረዶች በአማረ ልብስ ደምቀው አሸንድዬ በሚባል ቄጠማ ጉንጉን ወገባቸውን አስረው የሚያከብሩት ነው። በዓሉ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃማኖታዊ ይዘት አለው። በዓሉ ከነሐሴ 16 ጀምሮ እስከ ነሐሴ 21 ቀን ድረስ ይከበራል። ይህ በዓል በዋግ ኽምራ ሻደይ፣ በላስታ አሸንድዬ፣ በትግራይ አሸንዳ፣ በቆቦ አካባቢ ሶለል፣ በአክሱም አካባቢ ደግሞ ዓይነ ዋሪ እየተባለ ይጠራል።

የሻደይ በዓል ከኦርቶዶክስ ተዋሐዶ እምነት ጋር እየተያያዘ የመጣ ሲሆን አጀማመሩ መጽሐፍ ቅዱሳዊ መነሻ አለው፡፡ ከነዚህም መካከል የአዳም ከገነት መባረር፣ የኖኅ ዘመን የጥፋት ውኃ፣ ከዘመን መለወጫ፣ ከመጥመቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ አንገት መቆረጥ፣ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ትንሣኤ (ፍልስታ) እና ከመስፍኑ ዮፍታሔ ልጅ ታሪክ ጋር በማስተሳሰር የሚያስቀምጡት ሲሆን በማኅበረስቡ አባቶችና ሊቃውንቱ ዘንድ ጎልቶ የሚነገረውና የሚተረከው ግን የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ትንሣኤ (ፍልስታ) በዓልን መሠረት ያደረገ ነው።

አባታችን አዳም በገነት ሳለ ሕግ በመተላለፉ ጸጋ እግዚአብሔር ርቆት እርቃኑን በሆነ ጊዜ አካሉን ለመሸፈን ቅጠል መጠቀሙን ለማሰብ ያች አዳምና ሔዋን ክብራቸውን ተገፈው ከገነት የተባረሩባትን ዕለት በማሰብ በወቅቱ ያገለደሙትን ቅጠል በምልክትነት በመውሰድ የሻደይ ቅጠልን በገመድ ላይ ጎንጉነው በወገባቸው አገልድመው/አስረው/ አዳምና ሔዋን ከገነት ከመውጣታቸው በፊት ግብረ ሥጋ ግንኙነት ያልጀመሩ ደናግላን ስለነበሩ ያንን በመከተልና በምሳሌነት በመውሰድ ያላገቡ የአገው ልጃገረዶች ተሰባስበው ያችን ዕለት ወይም ቀን በመታሰቢያነት ለመቁጠር ወይም ለመዘከር የሻደይ ጨዋታን መጫወት ወይም ማክበር እንደጀመሩ ይናገራሉ።

ከኖኅ ዘመን ታሪክ ጋር ያለው ግንኙነት ደግሞ ከጥፋት ውኃ በኋላ ውኃው የመጉደሉን ምልክት ርግብ ለኖኅ የለመለመ የወይራ ቅጠል ይዛ በመምጣት በምድር ሰላም እነደሆነ የምሥራች አብሥራለች። ከዚሁ ጋር በተገናኘ በዓሉን ያንን ለምለም ቅጠል ወገባቸው ላይ በማሰር ከጨለማ ወደ ብርሃን ተሸጋገርን ሲሉ ማክበር እንደጀመሩ ከታሪኩ ጋር አያይዘው ያስቀምጡታል።

ከመስፍኑ ዮፍታሔ ታሪክ ጋርም ቢሆን የሻደይ በዓል እንዴት ግንኙነት እንዳለው ሲያስቀምጡ ዮፍታሔ ወደ ጦርነት በሔደ ጊዜ በድል ከተመለስ ለአምላኩ መሥዋዕትን ለማቅረብ ስዕለት ገበቶ ነበር። ይህም ከቤቱ ሲመለስ መጀመሪያ የሚቀበለውን እንደሚሠዋ ሲሆን በዚህ ጊዜ ያለ ወትሮዋ ልጁ እየዘፈነች ልትቀበለው ወጣች በዚህም በጣም አዘነ። ልጁም ለአምላኩ የገባውን ስዕለት እንዳያስቀር ሁለት ወር ስለ ድንግልናዋ አልቅሳ ስዕለቱን እንዲፈጽም ጠይቃው ከሁለት ወር በኋላ ስዕለቱን የፈጸመ ሲሆን አባቷ የገባውን ቃል ኪዳን እንዳያጥፍ ያበረታታችውንና መሥዋዕትነትን ለሀገር፣ ለህዝብ፣ ለአባትና ለፈጣሪዋ የከፈለችውን የዮፍታሔን ልጅ በየዓመቱ ለአራት ቀናት ሙሾ በማውጣት አስበው ይውላሉ፡፡ በዚህ መሠረት በበዓሉ ላይ ከሚፈጸሙ ተግበራት ጋር አዛምደው መነሻው ከዚህ የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ እንደሆነ ይናገራሉ። “ጽዮንን ክበቡዋት በዙሪያዋም ተመላለሱ…በብርታትዋ ልባችሁን አኑሩ፣ ለሚመጣው ትውልድ ትነግሩ ዘንድ” መዝ 48፥12

የሻደይ በዓል አጀማመርን በተመለክተ ከላይ ከተቀመጡት ታሪኮች በተጨማሪ በአካባቢው ሕዝብና በቤተ ክርስቲያን ሊቃውንቶች ዘንድ ተደጋግሞ የሚነሣው ታሪክ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ትንሣኤ በዓል ሲሆን ይኸውም እግዚአብሔር አምላክ ለአዳምና ሔዋን ከ5500 ዘመን በኋላ ወደዚህ ዓለም አንድያ ልጁን ልኮ ከኃጢያት እሥራት ነጻ እንደሚያወጣቸው በገበላቸው ቃልኪዳን መሠረት አምላክ የተወለደባት እና ትንቢቱ የተፈጸመባት፣ በሔዋን ስህተት ከገነት የተባረረው የሰው ልጅ በእርሷ ምክንያት ከኃጢያት ባርነት ነጻ የወጣባትና ወደ ቀድሞ ቤቱ ገነት እንዲመለስ ምክንያት የሆነችው የሰው ልጅ መመኪያ የተባለች እመቤት፣ እንደማንኛውም ሰው የተፈቀደላትን እድሜ በምድር ከኖረች በኋላ ሞተ ሥጋን እንደ ሞተች ከመጽሐፍት እንረዳለን፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከዚህ በኋላ ሞትን ድል አድርጋ ከመቃብር ተነሥታ ወደ ሰማይ አረገች፡፡

በፍልሰታ ወቅት በዓሉ መከበሩም ለሻደይ ተጨዋቾች ተምሳሌትና የድንግልናቸው አርዓያ የሚያደርጓት ድንግል ማርያም አካላዊ ሥጋዋ ከጌቴሰማኔ ወደ ገነት መፍለሱን እንዲሁም በገነት በዕፀ ሕይወት ሥር ከነበረበት መነሣቱን ምክንያት በማድረግ እንደሆነ የዋግ ኽምራ ሀገረ ስብከት ስብከተ ወንጌል መምሪያ ሓላፊ የሆኑት መጋቢ ምስጢር ገብረ ሕይወት ኪዳነ ማርያም “በዓሉ በልጃገረዶች ዘንድ ተወዳጅ የሆነው በሄዋን ምክንያት የተዘጋው ገነት በእመቤታችን አማካኝነት በመከፈቱ ነው። መመኪያቸው ስለሆነች ልጃገረዶች በዓሉን ያከብሩታል ድንግልናቸውንም አደራ የሚሉት በእርሷ ነው” ሲሉ ይናገራሉ።

ዕርገቷን መላዕክት በእልልታ፣ በሽብሸባና በዝማሬ ነጫጭ ልብስ ለብሰው አጅበዋት ነበር፡፡ ዕለቱን ፍስለታ ብለን የምንጠራውም ማርያም ከሞት ተነሥታ ማረጓን፣ ሙስና መቃብር አፍልሳ መነሣትዋን ወይም ዕርገቷን በማሰብ ነው፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያት እመቤታችን በነሐሴ 16 ቀን እንደ አዲስ በመላዕክት ሽብሸባ፣ እልልታ፣ ዝማሬና ዝማሜ ታጅባ ከምድር ወደ ሰማይ ስታርግ እንዳዩ፡፡ በታላቅ ፍስሃ ይመለከቱና በታዓምራቱ ይደነቁም ነበር፡፡ ከዛን ዕለት ጀምሮ ደናግል ቅዱሳን ከመላእክቱ በተመለከቱት ሥርዓት መነሻነት ባህላዊ ነጫጭ ልብሶችን ለብሰው፣ አምረውና አጊጠው፣ የወቅቱ መታሰቢየ የሆነውን ለምለሟን ከምድር ሳሮች ሁሉ ረዘም ያለችውን የሻደይ ቅጠል በወገባቸው አስረው እንደ መላአክቱ አክናፍ ወገባቸውን ከግራ ወደ ቀኝ እያመላለሱ በማሽከርከር እያሸበሸቡ፣ በአንደበታቸው እየዘመሩና በእጆቻቸው እያጨበጨቡ በአንድነት ተሰባሰባስበው በፍቅርና በሐሴት ከነሐሴ 1 ቀን ጀምሮ በመጾም ጾሙ ከሚፈታበት ከዳግም ዕርገቷ ነሐሴ 16 ጸሎታቸው ተሰምቶላቸው የፈለጉትን ማየታቸውን ምክንያት በማድረግ እስከ ነሐሴ 21 ቀን ድረስ በየዓመቱ ማክበር እንደተጀመረ ይነገራል፡፡

እናቶችና እኅቶች በአደባባይ ወጥተው የድንግል ማርያምን ሞትን ድል አርጎ መነሣት ትንሣኤዋንና ዕርገቷን እንደ ነጻነታቸው ቀን ቆጥረው የተለያዩ አልባሳትን በማድረግና ለበዓሉ ክብር በመስጠት ከበሮ አዘጋጅተው አሸነድዬ የተባለውን ቄጠማ በወገባቸው ታጥቀው ምስጋና በማቅረብ በዓሉን ይዘክራሉ፡፡ በዚህም መሠረት የሻደይ ጨዋታ የፍስልታ በዓል መከበር ከጀመረበት ጊዜ አንሥቶ እንደተጀመረና በምእመኑ ለረጅም ጊዜ እየተከበረ የኖረ ሃይማኖታዊ በዓል እንደሆነ ይታመናል፡፡

የሻደይ ልጃገረዶች የቡድን አመሠራረት ደብርን መሠረት ያደረገ ነው፡፡ የሻደይ ጨዋታ በዓል በሚያከብሩበት ጊዜ ልጃገረዶች የተለያዩ ባህላዊ አልባሳትን ለብሰው ከበሮ እና ለምስጋናው የሚያስፈልጉ ነገሮችን በማሟላት ተጠራርተው በመጀመሪያ ወደ አጥቢያቸው በመሄድ የቤተ ክርስቲያኑን ደጁን አልፈው ይዘልቃሉ፡፡ የቤተ ክርስቲያኑን ደጅ ከተሳለሙ በኋላ የተለያዩ ጣዕመ ዝማሬ እያሰሙ ሦስት ጊዜ ይዞሩና ደጃፉን ተሳልመው በቅጥር ግቢው አመቺ ቦታ ፈልገው ምስጋናቸውን ይጀምራሉ፡፡ ከበሮአቸውን እየመቱ፣ የታቦቱን ስም እየጠሩ በሚያምር ድምፃቸው፣ ሽብሻቦ፣ ውዝዋዜ፣ ጥልቅ መልእክትን በያዙ ግጥሞች፣ ለዚህ ያደረሳቸውን አምላክና ታቦት ያወድሳሉ፣ ያሞግሳሉ፣ ያከብራሉ፣ ይለማመናሉ፡፡ ምስጋናው ለዚህ ዓመት ያደረሳቸውን አምላክ የሚያመስግኑበት እና ቀጣዩ ዓመትም እንደዚሁ የሰላም፣ የጤና የተድላ እንዲሆን የሚማጸኑበት፣ ተስፋቸውን የሚገልጹበትና ስለት የሚሳሉበት በመሆኑ ምስጋናውን ሞቅ፣ ደመቅ አድርገው ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይሉ በፍቅር፣ በደስታ፣ በመተሳሰብና በሰላም ይጫወታሉ፡፡ እያንዳንዱ አባል ለእግዚአብሔርና ለደብራቸን ታቦት ያልሆነ እያሉ ጉልበታቸውን፣ ችሎታውንና ልምዳቸውን ሳይቆጥቡ በምስጋናው ይሳተፋሉ።

ከቤተ ክርስቲያን መልስ በአካባቢው ወዳሉት ትልልቅ አባቶች ዘንድ ሄደው በመዘመር ምርቃን ይቀበላሉ። ከዚያ መልስ ወደ ተራራማ ስፍራ በመውጣት ክብ ሠርተው ይዘምራሉ፡፡ ከዝማሬያቸው ውስጥ ግጥሞቹ መንፈሳዊ ይዘት ያላቸው ግጥሞች ከግለሰባዊ ስሜት ወይም ከግለሰብ ውዳሴ የራቁ ናቸው፡፡ የቡድን አመሠራረታቸው ደብርን መሠረት ያደረገ በመሆኑ አንዱ ቡድን ከሌላው ቡድን የተሻለ መሆኑን ለማሳየት ፣ የደብሩን ኃያልነት፣ ደብራቸውን እንደማያስደፍሩና እንደሚጠብቁ በምስጋናቸው ይገልጻሉ፡፡

የወከሉትን ደብር ታቦት ስም እየጠሩ ለአባት እናት፣ ለቤተሰብ ጤና፣ ጸጋ፣ ሀብት፣ ሰላም በአጠቃላይ መልካሙን ሁሉ እንዲያድላቸው ይማጸናሉ፡፡ አደራውን ለታቦቱ ይሰጣሉ፡፡ ለዚህም ዜማውና ግጥሙ ተመሳሳይ ቢሆንም የወከሉትን ደብር ስም ብቻ በማቀያየር በተመሳሳይ ዜማና መወደስ እና መማጸን በሁሉም የሻደይ ተጨዋች ቡድኖች ይታይል፡፡ ልጃገረዶቹ በዚህ የምስጋና ጊዜ የሚሰበሰቡትን ሥጦታዎች ሁሉ ለቤተ ክርስቲያን ይሰጣሉ።

የሻደይ ምስጋና/ጨዋታ በዚህ መልኩ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን በማመስገን ከፍከፍ በማድረግ ዕርገቷን በማሰብ የአምላክ እናት አማልጅን እያሉ ስሟን በመጥራትና በማክበር የሚከናወን በመሆኑ ይህንን ሃይማኖታዊ መሠረትነት ያለውን ትውፊት የመጠበቅና የማስጠበቅ ሓላፊነት ከሁላችን ይጠበቃል። የእመቤታችን አማላጅነት አይለየን፡፡
  • ምንጭ፡-ሰቆጣ ማእከል ሚዲያ ክፍል

ዘመኑን የዋጁ በሥልጠና የታገዙ ካህናት እንደሚያስፈልጉ ሊቀጳጳሱ ገለጡ

 የደቡብ ትግራይ ማይጨው እና የደቡብ ምሥራቅ ትግራይ አህጉረ ስብከት ሊቀጳጳስ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ ሐምሌ 29 2006 ዓ.ም ከማይጨው ከተማ እና ዙሪያው  አድባራትና ገዳማት ለተውጣጡ ከ70 በላይ የሚሆኑ  ካህናትን ለ15 ቀናት ያህል ሰልጥነው በተመረቁ  ዕለት ሊቀጳጳሱ እንደተናገሩት ዘመኑ የተወሳሰበ ከመሆኑ የተነሳ  ዘመኑን የዋጁ በተለያዩ ጊዜያት በሥልጠና  የታገዙ ካህናት  ያስፈልጋሉ ሲሉ በምርቃቱ ላይ ተናገሩ፡፡ ስልጠናው የተዘጋጀው በነገረ መለኮት ምሩቃን መንፈሳዊ ማኅበር እና በደቡብ ትግራይ ማይጨው ሀገረ ስብከት ጋር በጋራ በመሆን ነው፡፡ ሥልጠናው ትምህርተ ኖሎት፤ ሥርዓተ ቤተክርስቲያን፤ የስብከት ዘዴ እና ሌሎችንም  ያካተተ መሆኑ ታውቆአል ፡፡ደፊትም በዚሁ ምልኩ ሥልጠናዎች ለካህናቱ እንደሚሰጥ ሊቀጳጳሱ አስታውሰዋል፡፡




2014 ኦገስት 11, ሰኞ

ኦ ፍና/ቆፍና ቅዱስ አማኑኤል ቤተክርስቲያን


ከአዲስ አበባ 185 ኪ.ሜ ርቀት ላይ በመርሐቤቴ ወረዳ በዓላም ከተማ  የሚገኝ  በ4ኛው ክፍለ ዘመን በአባ ሰላማ ካሣቴ ብርሃን አማካይነት በአብርሃ ውአጽብሃ ነገሥታት  እንደታነጸ ይነገራል፡፡
ነገሩ እንዲህ ነው በ4ኛው ክ/ዘ ነገስታቱ አብርሃ ወአጽብሃ ከጳጳሱ አባ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን ጋር በመሆን አብያተ ክርስቲናትን በማሳነጽ  በማስፋፋት ላይ በነበሩበት  ጊዜ በመርሐቤቴ ሲያልፉ አሁን ቤተክርስቲያኑ የታነጸበት ቦታ  ጳጳሱ አባ ሰላማ አረፍ አሉ፡ እዚያው እያሉ ጌታችን የተወለደባትን  ቤተልሔምን በራእይ  አሳያቸው ከቦታውም ጋር አመሳስሎ ካሳያቸው በኋዋላ  ቤተ ክርስቲን መስራት እንዳለባቸው ተገነዘቡ፡፡ ይህ መንገድ በጣም ድንቅ ነው ሲሉ ኦ ፍና ብለው ጠሩት /ቆፍና ማለት፡  ቆፍ  ብሂል ቅሩበ እግዚአብሔር ማለት ነውና  እገዚአብሔር የቀረበው ቦታ ነው ሲሉ እንዲህ ሰይመውታል፡፡ከዚያ ተነሳ  በእውነት እግዚአብሔር ከኛ ጋር ነው  በማለት የቅዱስ አማኑኤል ቤተክርስቲያን እንዲታነጽ ወሰኑ፡፡አማኑኤል ማለት እገዚአብሔር ከኛ ጋር ነው ማለት ነውና፡፡ይህ ጥንታዊ ቤተ ክርስቲያን እጅግ በጣም የቆዩ ቅርሳቅርስ የሚገኙበት ታርካዊ  ጥንታዊ ነው ፡፡ ባሁኑ ሰዓት በቦታው የሚገኙትን ቅርሶች ለጎብኚዎች በሚመች መልኩ ላስቀመጥና ለጉብኝት ዝግጁ ላማድረግ የደብሩ ሰበካ ጉባዔ ከሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች ጋር በጋራ በመስራት ላይ መሆናቸውን የደብሩ አስተዳዳሪ ሊቀ ትጉሃን ጳውሎስ ገልጸዋል፡፡ ኦ ፍና ቅዱስ አማኑኤል በአሁኑ ሰዓት ኦ ፍና አምሳለ ቤተልሔም ቅዱስ አማኑኤል ቤተ ክርስቲያን በሚል በብፁዕ አቡነ ኤፍሬም የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ተሰይሞአል፡፡ ይህ ጥንታዊ ደብር ከርእሰ አድባራት ተድባበ ማርያም  ቤተ ክርስቲያን  ቀጥሎ መሠራቱ  ይታውቃል፡፡ቦታውን ከፍ አድርጎ ትራራ ላይ ለመሥራት ታስቦ በውቅቱ የነበሩት  ምእመናን  ከተለያ ቦታዎች አፈር አምጥተው ስለደለደሉት አራት አይነት አፈር በቦታው ይገኛል፡፡ ደብሩም በግራኝ አህመድ ጊዜ በመቃጠሉ ብዙ ቅርሶች የወደሙ ሲሆን በየጊዜው የተነሱ ነገሥታት መልሰው  አሳንጸውታል፡፡ ምእመናን!  ወደ ቦታው በመሄደ እንድትጎበኙ የደብሩ ሰበካ ጉባኤ ጥሪውን ያስተላልፋል፡፡


                                   በአውሮጳ   የካህናት አንድነት ማኅበር ሊቋቋም መሆኑ ታወቀ በ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከመላዋ አውሮጳ   የተውጣጡ ካህናት፡” የ...