2014 ሴፕቴምበር 8, ሰኞ

የኢትዮጵያ የዘመን አቆጣጠር ከአውሮፓውያን ጋር ያለው ልዩነት መንስኤ እና ትክክለኛ መሰረቱ

 


የዘመን መስፈሪያዎች 
እግዚአብሔር «ቀንና ሌሊትን ይለዩ ዘንድ ፣ ለዕለታት፣ ለዘመናትና ለዓመታት ምልክት ይሆኑ ዘንድ» / ዘፍ.1. 14- 15/ የፈጠራቸውን የፀሐይንና የጨረቃን እንቅስቃሴ መሠረት ያደረጉት መስፈሪያዎች ናቸው፡፡ እነዚህም፤

ሀ. ዕለት-
አንድ ዕለት አንድ ቀንን /የብርሃን ክፍለ ጊዜን / እና አንድ ሌሊትን /የጨለማ ክፍለ ጊዜን/ ያካተተ ፀሐይ አንድ ጊዜ ከወጣች በኋላ ተመልሳ እስክትወጣ ድረስ ያለውን ጊዜ የያዘ ነው፡፡ በአሁኑ ዕውቀታችን አንድ ዕለት ምድር በራሷ ዛቢያ አንድ ጊዜ የምትሸከረከርበት ጊዜ ነው፡፡

ለ. ውርኅ-
ወርኅ ማለት በግእዝ ጨረቃ ማለት ነው፡፡ አንድ ወርኅ የሚባለው ጊዜ ሙሉ ጨረቃ ከወጣች በኋላ ድጋሚ እስከምትወጣ ድረስ ያለው ጊዜ ነው፡፡ በአሁኑ ዕውቀታችን / በጥንቱም ጨምሮ/ ይህ ጨረቃ መሬትን አንድ ጊዜ ዙራ ለመጨረስ የሚፈጅባት ጊዜ ነው፡፡ አንድ ወር ሃያ   ዘጠኝ ተኩል ዕለታትን ይፈጃል፡፡
   
ሐ. ዓመት-
አንድ ዓመት ማለት መሬት አንድ ጊዜ በፀሐይ ዙሪያ ለመዞር የሚፈጅባት ጊዜ ነው፡፡ ይህም 365 ከ1/4 / ሦስት መቶ ስድሳ አምስት ቀን ከሩብ/ ዕለታት ይፈጃል፡፡ይህ ከመታወቁ በፊትም ግን የዓመት ጽንሰ ሓሳብ ነበር፡፡ ፕሮፊሰር ጌታቸው ኃይሌ የፅንሰ ሐሳቡን አመጣጥ እንዲህ ያስረዳሉ፡፡
ሰዎች ርዝመታቸው እኩል የሆኑ ሁለት  ሻማዎችን ሠሩና ልክ ፀሐይ ስትወጣ /ቀኑ ሲያልቅና ሌሊቱ ሲጀምር/  አንዱን ሻማ አበሩት፡፡ልክ ፀሐይ ስትወጣ እሱን አጠፋና ሌላውን / ሁለተኛውን/ ሻማ አበሩት፤ ጧት ፀሐይ እንደገና ስትወጣ / ሌሊቱ አልቆ ሌላ ቀን ሲጀምር/ ሻማውን አጠፉት፡፡ አሁን እንግዲህ ከየሻማዎቹ /ከሁለቱ ሻማዎች/ ምን ያህል እንደተቃጠለላቸው ሲያስተያዩት ከሁለቱ ሻማዎች የተቃጠለው እኩል አለመሆኑን ተመለከቱ በዚህም የቀኑና የሌሊቱ ርዝማኔ እኩል አለመሆኑን ተረዱ፡፡

ቀደም ብለውም የቀኑና የሌሊቱ ርዝማኔ በተለያዩ ወቅቶች የተለያየ መሆኑን ልብ ብለው ነበርና ይህንን ሙከራቸውን ሲቀጥሉ በቀኑና በሌሊቱ ርዘማኔ / በሚቃጠለው የሻማዎቹ መጠን/ መካከል ያለው ልዩነት ከወቅት ወቅት የተለያየ እንደሆነ ተመለከቱ ይህን ሙከራቸውን ሲቀጥሉ ግን በየ182 /ተኩል/ ዕለቱ ቀኑና ሌሊቱ እኩል የሚሆኑባቸው ሁለት ዕለታት በዓመት ውስጥ እንዳሉ ተገነዘቡ፡፡ እነዚህ ዕለታት አንዱ የሙቀት ወራት ከመጀመሩ በፊት የሌላው ደግሞ የቅዝቃዜው ወራት ከመጀመሩ በፊት የሚመጡ ናቸው፡፡ ስለዚህ የቀኑና የሌሊቱ ርዝመት አንድ ጊዜ እኩል ሁኖ ደግሞ በዚያው ወቅት እኩል እስከሚሆን ድረስ ያለውን ጊዜ ማለትም / 182 ተኩል + 182 = 365/ ዕለት አንድ ዓመት አሉት፡፡ አሁን ባለን ግንዛቤ ምድር በራሷ ዛቢያ እንደተሽከረከረች በፀሐይ ዙሪያ ትዞራለች፡፡ ምድር በፀሐይ ዙሪያ የምትዞረው ወደ ጎን 23 ተኩል ዲግሪ ያህል አጋድላ ነው፡፡ ይህ የቀንና የሌሊት ርዝመት መለያየትም የሚከሰተው በዚህ ማጋደል ምክንያት ነው፡፡
እንግዲህ በአጠቃላይ ዋናዎቹ የጊዜ / የዘመን/ መስፊሪያዎች ዕለት፣ ወር እና ዓመት ናቸው፡፡ ሦስትቱም ተመላላሽ ክስተቶችን / ለምሳሌ የፀሐይን መውጣት/ መሠረት ያደረጉ ናቸው፡፡ እነዚሀ ተመላላሽ ክስተቶች አንድ ጊዜ ከተከሰቱ በኋላ ደግመው እስኪከሰቱ የሚፈጁት ዘመን ወይም ጊዜ  ዓውድ ይባላል፡፡ ዓውድ ማለት ዙሪያ፣ ክብ፣ እንደ ቀለበት ዙሮ የሚገጥም ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ዓውድ ማለት ክስተቶቹ አንድ ጊዜ ከተከሰቱ በኋላ ደግመው እስኪመጡ ድረስ ያለው ጊዜ ማለት ነው፡፡
በዚህ መሠረት ከላይ ያየናቸው ሦስት መስፈሪያዎች / ዕለት፣ ወርኀ፣ ዓመት/ ዓዕዋዳት / ዓውዶች/ የሚወጡበት ጊዜ ዓውደ ዕለት፣ ዓውደ ወርኀ፣ ዓውደ ዓመት ይባላሉ፡፡
መጀመሪያ ላይ ሰዎች እነዚህን ሦስቱን መስፈሪያዎች /ዓዕዋዳት/ /በተለይም ቀንና እና ወርን/ ለየብቻቸው ይጠቀሙባቸው ነበር፡፡ ከዚህን ያህል ቀን፣ ከዚህን ያህል ወር በኋላ /በፊት/ እያሉ ጊዜን ይለኩ ነበር፡፡
እነዚህ ሦስቱን በቅንብር /በቅንጅት/ ለመጠቀም ሲፈለግ ግን የዘመን አቆጣጠር ስሌት ያስፈልጋል፡፡ ምክንያቱም አንድ ወር 29 ከግማሽ ቀን ነው፡፡
እንዲሁ እንዳለ ለመቁጠር ቢፈለግ የመጀመሪያው ወር ጠዋት ላይ ቢጀመር ሁለተኛው ወር ምሽት ላይ ይጀምራል፣ ሦስተኛው ደግሞ ድጋሚ ጠዋት ላይ ይጀምራል፤ ይህን ለመቅረፍ ወሩን ሙሉ  ሰላሳ ቀን ቢያደርጉት ከትክክለኛው ወር /የጨረቃ ዐውድ/ ግማሽ ቀን ይተርፋል፤ 29 ቀን ብቻ ቢያደርጉት ደግሞ ግማሸ ቀን ይጎድላል፡፡ አንድ ዓመት 365 ከሩብ ዕለታት አሉት፡፡
ዓመትን በወራት ለመቁጠር ቢፈለግ፤ ዓመቱን 12 ወር ቢያደርጉት የዓመቱ /የዕለታት ቁጥር /29.5X12=354/ ብቻ ይሆናል፡፡ ይህም ከትክክለኛው ዓመት /365-354=11/ ዕለታት ያህል ያንሳል፡፡ 13 ወር ቢያደርጉት ዓመቱ /365X13=385.5/ ቀናት ይሆናል ይህም ከትክክለኛው ዓመት /383.5-365=19/ ቀናት ያህል ይበልጣል፡፡
ስለዚህ እነዚህን መስፈሪያዎች በቅንጅት ለመጠቀም ይህንን አለመጣጣም የሚፈታ ቀመር /የዘመን አቆጣጠር ሥርዓት/ ያስፈልጋል፡፡ በተለያዩ አካባቢዎች የተለያዩ የዘመን አቆጣጠሮች ተዘጋጅተዋል፡፡



የአይሁድ ዘመን አቆጣጠር

የአይሁድ ዘመን አቆጣጠር እያንዳንዳቸው 29 እና 30 ዕለታት ያሏቸው 12 ወራት አሏቸው፤
ተ.ቁ
የአይሁድ ወራት
የዕለታት ብዛት
ወራቱ በእኛ
1
ኒሳን
30
መጋቢት/ ሚያዝያ
2
ኢያር
29
ሚያዝያ/ ግንቦት
3
ሲዋን
30
ግንቦት/ ሰኔ
4
ታሙዝ
29
ሰኔ/ ሐምሌ
5
አቭ
30
ሐምሌ/ ነሐሴ
6
አሉል
29
ነሐሴ/ መስከረም
7
ኤታኒም
30
መስከረም/ ጥቅምት
8
ቡል
29/30
ጥቀምት/ ኅዳር
9
ከሴሉ
30/29
ኅዳር/ ታህሳስ
10
ጤቤት
29
ታህሳስ/ ጥር
11
ሳባጥ
30
ጥር/ የካቲት
12
አዳር 1
29
የካቲት/ መጋቢት
እነዚህ የዓመቱ 12 ወራት በአጠቃላይ 354 ያህል ብቻ ዕለታት ይኖሯቸዋል፡፡ ይህም በትክክለኛው ዓመት በ11 ዕለታት ያህል ቢያንስም አዲስ ዓመት ይጀምራሉ፡፡ ልዩነቱ በሁለት ዓመታት 22 ዕለታት፣ በሦስት ዓመት ደግሞ 33 ዕለታት ያህል ይሆናል፡፡ ስለዚህ በየሦስት ዓመቱ ከአስራ ሁለተኛው ወር ጳጉሜን በፊት አንድ ሌላ ወር ይጨምሩና ጨምረው የዓመቱን የወራት ቁጥር ዐሥራ ሦስት ያደርጉና ልዩነቱን ያስተካክሉታል፡፡

የኢትዮጵያውያንና የግብጻውያን ዘመን አቆጣጠር

የሀገራችን ኢትዮጵያ እና የጥንት ግብጻውያን /ዛሬም ድረስ የግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን የምትጠቀምበት/ የዘመን አቆጣጠር ተመሳሳይ ነው፡፡ ሁለታችንም እኩል ሰላሳ ቀናት ያሏቸው 12 ወራት አሉን፡፡ እነዚህ 12 ወራት / 12X30=360/ ቀናት አሏቸው እነዚህ ቀናት በትክክለኛው ዓመት በ/365.25-360=5.25/ ቀናት ያንሳሉ፡፡ ይህንንም 5 ቀናት / በ4 ዓመት አንድ ጊዜ 6 ቀናት/ ያሏትን 13ኛ ወር በመጨመር ያስተካክሉታል፡፡ የኢትዮጵያውያን እና የግብጻውያን ወሮች ስም እንደሚከተለው ነው፡፡
ተ.ቁ
የግብጽ ወሮች
የኢትዮጵያ ወሮች
1
ቱት/ዩት
መስከረም
2
ባባ/ፓከር
ጥቅምት
3
ሀቱር
ኅዳር
4
ኪሃክ/ከያክ
ታኅሣሥ
5
ጡባ/ቶቢር
ጥር
6
አምሺር/ሜሺር
የካቲት
7
በረምሃት
መጋቢት
8
በርሙዳ
ሚያዝያ
9
በሸንስ
ግንቦት
10
ቦኩሩ
ሰኔ
11
አቢብ
ሐምሌ
12
መስሪ
ነሐሴ
13
ኒሳ/አፓጎሜኔ
ጳጉሜን
/ባሕረ ሐሳብ፣ፕ/ር ጌታቸው ኃይሌ ፣ገጽ.65/

የኢትዮጵያ ዘመን አቈጣጠር

የኢትዮጵያ እምነታዊ ባህል የሚወረሰው በሦስት ዐይነት ጠባይ ነው። አንዱ ሕገ ልቡና ይባላል። ከመጽሐፍ በፊት የነበረ ነው። ከአበው ቃል በቃል የተወረሰ ነው። ሁለተኛው በሕገ ኦሪት ከኦሪት የተቀዳ ነው። ሦስተኛው በሕገ ወንጌል ከወንጌል የተማርነው ነው። እና በሦስት ዐይነት ጠባይ የሚመራ ነው። በዚህ ዐይነት ከወረስናቸው በዓላት ማለት በሦስቱም ጠባያት ከወረስናቸው በዓላት የየራሳቸው መልክ ያላቸው አሉ። ለምሳሌ ልደት፥ ጥምቀት፥ ዕርገት፥ ደብረ ታቦር እነዚህን የመሳሰሉት ከወንጌል የተማርናቸው ናቸው፤ በብሉይ የሉም። ፋሲካ፥ በዓለ ጰራቅሊጦስ ደግሞ ከኦሪት የተማርናቸው ናቸው። የዘመን መለወጫ በዓል ግን ከሕገ ልቡና ቃል በቃል ተምረን፥ በኦሪት የመጽሐፍ መሠረት አግኝተንለት በወንጌልም አጽንተን ይዘነው የኖርነው ሦስት የሥራ ዘመን ክፍል የተላለፈና እዚህ የደረሰ ነው። እኛ የዘመን መለወጫ ብለን በሀገራችን ባህል የምናከብረው ዓለም ካለመኖር ወደ መኖር የተገኘበት፥ ብርሃን፥ ጊዜ፥ ዕለት፥ ሰዓት የተፈጠሩበት፤ ለብርሃን፥ ለጊዜ፥ ለዕለት፥ ለወር ለዓመት ጥንት መሠረት የሆነ ቀን ነው። ይህንን ሁሉ በማስገኘት እግዚአብሔር ራሱን የገለጠበት፥ ዓለምን በመፍጠር ከሃሊነቱን ያረጋገጠበት ቀን ነው ብለን ነው የምናከብረው። ስለዚህም ጥንተ ብርሃን፥ ጥንተ ዕለት፥ ጥንተ ጊዜ፥ ጥንተ ፍጥረት ርእሰ ዐውደ ዓመት ብለን ነው የምናከብረው። በዚህ ስያሜ በዓሉ ርእሰ ዐውደ ዓመት፥ ቅዱስ ዮሐንስ፥ የዘመን መለወጫ ብለን እናከብረዋለን።
ቅዱስ ዮሐንስ
የኢትዮጵያ ዘመን መለወጫ በዓል ሌላው ስሙ ቅዱስ ዮሐንስ ይባላል። ቅዱስ ዮሐንስ የሚባልበትም ሁለት ጠባይ አለው። አንዱ፤ መጥምቁ ዮሐንስ በሄሮድስ አንቲጳስ ጊዜ ከጳጉሜን ቀን ጀምሮ ታስሮ ሰንብቶ በመስከረም ቀን ዐሳብ ስለ ተቆረጠበትና በመስከረም ቀን እንዲሞት ውሳኔ ስለ ተሰጠበት አንገቱን በሰይፍ ተቆርጦ ስለ ሞተ ሊቃውንት ይህንን በዓል እሱ ራሱ ለኦሪትና ለወንጌል መገናኛ መምህር ስለ ነበረ ይህም በዓል ላለፈው ዘመን መሸኛ፥ ለሚመጣው ዘመን መቀበያ እንዲሆን ብለው በመስከረም ቀን እንዲከበር ስላደረጉ በሱ ስም ቅዱስ ዮሐንስ እየተባለ ይጠራል። በሁለተኛው ግን ከአራቱ ወንጌላውያን አንዱ ወንጌላዊ ዮሐንስ የተሰየመበት ስለ ሆነ በአቆጣጠርም ተራ ወደ ኋላ ተመልሶ ቢቈጠር ዓለም የተፈጠረበት ዘመን በዘመነ ዮሐንስ እንዳጋጣሚ ሆኖ ስለሚገኝ ቅዱስ ዮሐንስ ተብሎ ይጠራል።

ዕንቍጣጣሽ
በዚያም ጊዜ የነበሩ ኖኅና ልጆቹ ሰማዩ በደመና በመክበዱ ምክንያት ማየ አይኅ እንደገና ይመጣ ይሆን፥ የጥፋት ውሃ እንደገና ይዘንም ይሆን እያሉ ሲደነግጡ ከርመው በመስከረም ወር መጀመሪያ ላይ ሙሉ የፀሓይ ብርሃን ስላዩ፥ ምድር በአበባ አሸብርቃ ስለ ተገለጠችና በዚህም የእግዚአብሔርን ቸርነት፥ የቃል ኪዳኑን መጽናት ስለ ተረዱ ይህንን በዓል ቀድሞ ከአባቶቻቸው እንደ ወረሱት ያው ጥንተ ብርሃን፥ ጥንተ ዓመት፥ ጥንተ ዕለት አድርገው አክብረውታል። ሲያከብሩትም እንግጫ ነቅለው፥ አበባ ጐንጕነው መጀመሪያ መሥዋዕት ይሠዉነት ከነበረው ቦታ ሄደው ለእግዚአብሔር ገጸ በረከት አቅርበው ከዚያ በኋላ ግን እርስ በርሳቸው የአበባ ስጦታ በመለዋወጥ አክብረውታል። ሲያከብሩትም ዕንቍጣጣሽ በሚል ቃል እውነት የመልካም ሞኞታቸውን ይገላለጡበት ነበር። ዕንቍጣጣሽ ማለትንም ብዙ ታሪክ ጸሓፊዎች በልዩ ልዩ መልክ ተርጕመውታል። እንዲያውም ንጉሡ ሰሎሞን ለሳባ ንግሥት የዕንቍ ቀለበት ሰጥቷት ነበርና «ዕንቍ ለጣትሽ» ማለት ነው ብለው የጻፉ ብዙ ሰዎችም አሉ፤ የሚናገሩም አሉ። ነገሩ ግን እንዲህ አይደለም። ዕንቍጣጣሽ ማለት ተንቈጠቈጠ፥ አንቈጠቈጠ ከሚለው ቃል ተወስዶ ምድር በአበባ አጌጠች፥ ሰማይም በከዋክብት አሸበረቀ እንደ ማለት ሰማይን በከዋክብት ያስጌጠ አምላክ ምድርንም በአበቦች አጎናጸፋት ለማለት የተሰጠ ቃል ነው እንጂ ስለ ሳባ ንግሥት የተሰጠ አይደለም። ሁለተኛም አባቶቻችን ኢትዮጵያን በሙሉ ሀብት ተረክበዋት ነበርና፤ «ዕንቍ ዕጣ ወጣሽ፤» ሲሉ ወደ አገራቸው ሲገቡ ለአገራቸው መታሰቢያ አድርገው የተጠቀሙበት ቃል ነው ይባላል። በመሠረቱ ግን የጥፋት ውሃ ቀርቶ ምድር ጸንታ፥ አበባ ቋጥራ፥ ፍሬ ለመስጠት ተዘጋጅታ መገኘቷን የሚያበሥር ቃል ነው።
መስከረም 
መስከረም የሚባለው ወርም ኖኅ በመርከብ ውሥጥ በነበረ ጊዜ እንደ ዕብራውያን አቈጣጠር ሰባተኛ በሆነው በመስከረም ወር መጀመሪያ ላይ መርከቢቱ አራራት ከሚባለው ተራራ ላይ ዐርፋ ምድር ጨብጣለች። በግእዝ ቋንቋ መርከብ መስቀር ይባላል። ከዘመን ብዛት በኋላ «» ወደ «» ተለውጦ መስከረም ተባለ እንጂ መስቀርም ምድር አገኘች፥ መርከብም ምድር ነካች ለማለት የተሰጠ የወሩ ስያሜ ነው።

ርእሰ ዐውደ ዓመት 

የምንለው፤ ዐውድ ማለት በግእዙ ቋንቋ ዙሪያ፥ ክብ የሆነ ነገር ማለት ነው። የዓመት ጠቅላላ ቀኖች መሠረታውያን ቀኖች የሚባሉት ሦስት መቶ ስድሳ አራት ቀኖች ናቸው። እነዚህም በኀምሳ ሁለት ሱባዔ ተከፍለው ለእያንዳንዱ ቀን በዓመት ውስጥ ለሰባቱ ዕለታት ኀምሳ ሁለት ኀምሳ ሁለት ቀን ይደርሳቸዋል። ከነዚህ ቀኖች የተሳሳበ የሴኮንድ፥ የደቂቃ፥ የሰዓት ዕላፊ ተጠራቅሞ ሦስት መቶ ስድሳ ዐምስተኛዋን የዘመን ማገጣጠሚያ ቀን ያስገኛል። ይህቺ ቀን እንግዲህ ዙሪያ፥ ክብ መግጠሚያ ናት ማለት ነው። በዚህች ቀን አማካይነት ወደ ዐዲሱ ዘመን መጀመሪያ እንተላለፋለን። ይህቺ ቀን ዕለት አዕዋዲት፥ ዕለተ ምርያ የመዘዋወሪያ ቀን ወይም የመጨረሻ ቀን ተብላ ትጠራለች። በአራት ዓመት ደግሞ ከዚህች መሳሳብ የምትገኝ አንዲት ቀን ትመጣለች። ሦስት መቶ ስድሳ ስድስተኛ። ይህቺ ቀን ዕለተ ሰግር ትባላለች። መረማመጃ ማለት ነው። አንድ ቀን ታስተላልፋለች። እንግዲህ እነዚህን ሁለቱን ቀኖች ተከትሎ የሚመጣው ቀን የዘመን መጀመሪያ፥ የዘመን ክብ መነሻና መድረሻ ተብሎ ርእሰ ዐውደ ዓመት ተብሎ በግእዙ ይጠራል። እነዚህ ቀኖች በኢትዮጵያውያን አቆጣጠር ተጠቃለው አንድ ጊዜ የሚገኙ ናቸው።

የኢትዮጵያ ቍጥር መሠረቱ መጽሐፈ ሔኖክ የሚባለው ነው። መጽሐፈ ሔኖክ በ፲፱፥ ፳፥ ፳፩ እና ፳፪ ምዕራፎች የሚሰጠን የፀሐይን፥ የጨረቃን ጉዞ መነሻ አድርጎ የወሮችን፥ የዕለታትን፥ የዓመታትን መነሻ፥ መድረሻ፥ መዘዋወሪያ ብተታቸውን፥ ጥንታቸውን ነው የሚያሳየው። ስለዚህም በሔኖክ ቍጥር የወር ቀኖች ቍጥር ሠላሳ ናቸው። በሦስት በሦስት ወር ግን አንድ ቀን ትከተላቸዋለች። እና ዓመቱ ለአራት ይከፈላል። በዘጠና አንድ በዘጠና አንድ ቀን። ጠቅላላው ይሄ ድምር ሦስት መቶ ስድሳ ስድስት ቀን ይመጣል። ይህ ካለቀ በኋላ አንዲት ቀን ለዘመን ማገጣጠሚያ ዕለተ ምርያ የምትባለው ትመጣለች። እንግዲህ በኢትዮጵያውያን ቍጥር ወሩ ከሠላሳ አያንስም፤ ከሠላሳ አይተርፍም። ለዓመቱም ሦስት መቶ ስድሳ ዐምስት ቀን መደበኛው አቆጣጠር ነው ማለት ነው። ይህ ነገር በአውሮፓውያን ቍጥርም አለ። ግን እነሱ ከዓመት ወሮች ሰባቱን ሠላሳ አንድ ሠላሳ አንድ አድርገው አራቱን ደግሞ ሠላሳ ሠላሳ አድርገው አንዷን ወር ሦስቱን ዓመት ሃያ ስምንት፥ በአራተኛው ዓመት ሃያ ዘጠኝአድርገው ያጣጧታል። 
እንግዲህ የአቀማመጡ ለውጥ ካልሆነ በስተቀር በቍጥር አካሄድ ዞሮ ዞሮ የዓመት ቀኖች ሦስት መቶ ስድሳ ዐምስት ወይም ሦስት መቶ ስድሳ ስድስት በመሆን አንድ ሆነዋል ማለት ነው። ልዩነቱ ግን የአቀማመጥ ለውጥ ነው። በኢትዮጵያ አቈጣጠር ግን ጠቅላላውን ፲፪ ወሮች መደባቸው ሠላሳ ብቻ ነው። እነዚያ በሔኖክ መጽሐፍ በጣልቃ ገብነት የነበሩት አራት ቀኖች ተጠቅለው ጳጉሜን በሚባል በዓመቱ መጨረሻ ላይ ተገኝተዋል። ዐምስተኛዪቱ ቀንም ከእነሱ ጋር ተገኝታለች። ይህም ለቍጥር ተራ ቅምር መቅናት የተደረገ እንጂ ቀኑን የሚለውጥ ምንም ነገር የለበትም። እና ከእነዚህ ቀኖች በኋላ የምናገኘው ቀን ርእሰ ዐውደ ዓመት ይባላል። ይህንን በዓል ከአዳም ጀምሮ እስከ ኖኅ ድረስ የነበሩ ዐሥሩም አበው በዐሥሩ ትውልድ እስከ ማየ አይኅ ድረስ ሲያከብሩት እንደ ቆዩና ኋላም የኖኅ ልጆች ከአባታቸው ተቀብለው ሲያከብሩት እንደ ነበረ ኩፋሌ የተባለው መጽሐፍ በምዕራፍ ያስረዳናል። እንግዲህ ኢትዮጵያ ይህንን ቀን የወረሰችው ከአበው ነው የምንለው በዚህ ምክንያት ነው።
  

  የዘመን ቁጥር ልዩነት

ፕ/ር ጌታቸው ኃይሌ የዘመን አቆጣጠር መለያየትን መነሻ እንዲህ በማለት ያብራራሉ፤ «ክብ የሆነ ነገር ሲከብ ከየትኛውም ቦታ መጀመር ይቻላል፤ የዘመን አቆጣጠር /ዓውደ ዓመትም/ ይኸው ነው፡፡ ዋናው ነገር አንድ ታላቅ ታሪካዊ ድርጊት ፈልጎ እርሱን መነሻ ማድረግ አንድ ታላቅ ታሪካዊ ድርጊት ፈልጎ እርሱን መነሻ ማድረግ ነው፤ የዘመን አቆጣጠሮቹም ልዩነት መንስኤው ይኸው ነው» ይላሉ፡፡ ባሕረ ሐሳብ፣ ጌታቸው ኃይሌ፣ ገጽ.65/ ለምሳሌነትም ሮማውያን የሮም ከተማ የተቆረቆረችበትን ጊዜ መነሻ ማድረጋቸውን/ በኋላም ታላቁ እስክንድር የነገሠበት ዘመን የዘመን ቆጠራ መነሻ ሆነው እንደነበር ይጠቅሳሉ፡፡ መሐመድና ተከታዮች ከመካ ወደ መዲና ያደረጉትን ስደት መነሻ የሚያደርገው ኢስላማዊ  የዘመን አቆጣጠርም ሌላው ተጠቃሽ ነው፡፡
የአይሁድን አቆጣጠር ትተን ከላይ ያየናቸው ሁለቱ የዘመን አቆጣጠሮች /የምዕራባውያኑ የጁልየስ ጎርጎርዮሳዊ አቆጣጠርና የኢትዮጵያና የግብጽ አቆጣጠር/ ሁለቱም ዘመንን የሚቆጥሩት ከክርስቶስ ልደት መነሻ አድርገው ነው፡፡ ይሁን እንጂ እኛ ዛሬ 2006ዓ.ም ነው ስንል እነርሱ ደግሞ 2014 ዓ.ም ነው ይላሉ፡፡ በመካከሉ የ7/8 ዓመታት ልዩነት አለ፡፡ እንግዲህ ጥያቄው ትክክለኛው የትኛው ነው? የሚለው ነው፡፡
ጉዳዩ መጻሕፍትን ሊያጽፍ የሚችልና በእርግጥም የተጻፉበት ቢሆንም ለማሳያ ያክል ሁለት ነገሮች እንመልከት፤

1. አሁን ባለው የምዕራባውያን አቆጣጠር ሄሮድስ የሞተው 4 ዓመት ቅ.ል.ክ ነው፡፡ ሄሮድስ የሞተው ጌታ ተወልዶ በስደት ሦስት ዓመት ያህል በግብጽ ከቆየ በኋላ ነው፡፡ ይህ ማለት በእርሱ አቆጣጠር ጌታ የተወለደው በ7 ዓመት ቅ.ል.ክ ነው ማለት ነው፡፡ እንግዲህ ጌታ በትክክል በተወለደበት በአንድ ዓ.ም እነርሱ ጌታ ሰባት ዓመት ሆኖታል ይላሉ ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ትክክለኛውን ቁጥር ለማግኘት አሁን ካላቸው ቁጥር ላይ ሰባት ዓመት መቀነስ አለባቸው፡፡

2. ፍላቪየስ ጆሴፈስ የተባለው የአይሁድን ታሪክ የጻፈው ሊቅ እንደመሰከረው ጌታ የተወለደበት ዓመት ነው ተብሎ በወንጌል ላይ የተጻፈው የቆጠራ ዓመት /ሕዝቡ ሁሉ የተቆጠረበትን ዘመን /ሉቃ.2.1/ በጎርጎሪያን ዘመን አቆጣጠር «7 ዓመተ እግዚአ /A.D/ ላይ ነው፡፡» በማለት መረጃ ትቶልናል ይህ ማለት ደግሞ ከምዕራባውያኑ ዘመን አቆጣጠር ላይ 7 ዓመቶች የግድ መቀነስ አለበት ማለት ነው፡፡ ያ ሲደረግ ደግሞ የኛን ዘመን አቆጣጠር ያመጣል፡፡

የዘመን መለወጫ ቀን ልዩነት

ሁለተኛው ጉዳይ የዘመን መለወጫ ወርና ዕለት ልዩነት ነው፡፡ እኛ መስከረም  1 አዲስ ዓመት ስንጀምር እነርሱ በ January 1 / በእኛ ታኅሣሥ 23/ አዲስ ዓመት ይጀምራሉ፡፡ ይህ ከየት የመጣ ልዩነት ነው?
የእኛ እና የግብጻውያን አቆጣጠር እዚህ ጉዳይ ላይ ከአይሁድ አቆጣጠር ጋር ይስማማል፡፡ በአይሁድ አቆጣጠር የመጀመሪያው ወር ኒሳን የሚባለው /በእኛ መጋቢት/ ሚያዝያ/ ነው፡፡
«ይህ ወር የዓመቱ የመጀመሪያ ወር ይሁናችሁ፣ በዚህም ወር በዐሥራ አራተኛው ቀን የአንድ ዓመት ተባዕት ላይ ወስደው ይረዱ፡፡ . . .»/ዘፀ.12.1-14/ ተብሎ የተሰጣቸውን የፋሲካ በዓል የሚያከብሩት በዚህ ወር ነው፡፡
ይሁን እንጂ አዲስ የዓመት በዓል አድርገው የሚያከብሩት «የሰባተኛው ወር የመጀመሪያ ቀን ዕረፍት ይሁናችሁ፡፡ በዚሁ በመለከት ድምጽ የሚከበር የተቀደሰ ጉባኤ ይኑራችሁ መስዋዕት ለእግዚአብሔር አቅርቡ እንጂ የተለመደ ተግባራችሁን አታከናውኑበት» /ዘሌ.13.23-25/ ተብሎ የተሰጣቸው የሮሽ ሆሻና፣/የመለከት በዓል ወይም በዓለ መጥቅዕ/ ተብሎ የሚጠራው በዓል ነው፡፡ ይህም ማለት አዲስ ዓመት የሚያከብሩት በሰባተኛው ወር በኢታኒም ወር /በእኛ መስከረም ጥቅምት/ ነው፡፡
በቤተክርስቲያናችንም ትምህርት ዓለም የተፈጠረው መጋቢት 29 ቀን ነው፡፡ መስከረም ደግሞ ከመጋቢት ጀምሮ ሲቆጠር ሰባተኛው ወር ነው፡፡ ይህም ከአይሁድ ዘመን አቆጣጠር ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡
አይሁድስ ቢሆኑ የመጀመሪያው ወር እያለ አዲስ ዓመትን ለምን በሰባተኛው ወር ያከብራሉ ለሚለው ጥያቄ ሁለት ዓይነት ምላሾች /ምክንያቶች/ ይሰጣሉ፡፡ የመጀመሪያው ምክንያት «ሰባተኛው ወር ኖኅ ከመርከብ የወጣበት ወር በመሆኑ ይህ የአዲስ ዓመት መጀመሪያ ተደርጎ መከበር በመጀመሩ ነው» የሚል ነው፡፡ በዘመን መለወጫ ዕለት ልጃገረዶች አበባ እና ለምለም ሣር መያዛቸው ርግቢቱ ለኖኅ ካመጣችው ለምለም ወይራ /ቄጠማ/ ጋር ተያይዞ የተጀመረ መሆኑን ይናገራሉ፡፡
ሁለተኛው ደግሞ መስከረም የቀንና የዕለቱ ርዝመት እኩል የሚሆኑበት ወር በመሆኑ ነው የሚል ነው፡፡ የመስከረም 1 ቀን ስንክሳር «የተባረከ የመስከረም ወር የግብጽና የኢትዮጵያ ዓመታት ወሮች ርእስ ነው፤ የቀኑ ሰዓትም ከሌሊቱ ሰዓት የተስተካከለ ዐሥራ ሁለት ነው» ይላል፡፡
እዚህ ላይ ማስተዋል የሚገባው ሌላው ጉዳይ በቤተክርስቲያናችን ትምህርት እመቤታችን ጌታን የጸነሰችው መጋቢት 29 ቀን ነው፡፡ ይህም ቅዱስ ጳዉሎስ ፣የዘመኑ ፍጻሜ በደረሰ ጊዜ እግዚአብሔር ከሴት ተወለደ» /ገላ.4.4/ እንዳለው የ5500 ዘመኑ ፍጻሜ /ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ/ ነው፡፡
ጽንሰትን መጋቢት 29 ካልን በኋላ ልደትን ታህሣሥ 29 ቀን እናከብራለን፡፡ ከመጋቢት 29 እስከ ታህሣሥ 29 ድረስ 9 ወር ከ5 ቀን ነው፡፡ /ጳጉሜን ጨምሮ/፡፡ ጳጉሜ 6 በምትሆንበት ጊዜ ደግሞ ታህሣሥ 28 ቀን ልደት ስለሚከበር አሁንም በመሐሉ ያለው ጊዜ 9 ወር ከአምስት ቀን ይሆናል፡፡

ማጠቃለያ  

በመጨረሻም የኢትዮጵያ የዘመን አቆጣጠር ፍፁም መፅሐፍ ቅዱሳዊ መሰረት ያለው ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ የሚቆጥር መሆኑን እንጂ እንደ ዘመኑ ነገስታት ፍላጎት በታሪክ ክስተትን መሰረት ያደረገ አለመሆኑን ከተረዳን ይህንን ሃሳባችንን የሚያጠናክርልን የሳምንታንት እና የወራት ስያሜዎቻችንን እንዲሁም የልሎቹ የቀን አቆጣጠር ምንጭን ከ እዚህ በታች ባሉት ሰንጠረዦች እንመልከት።ለምሳሌ እነኚህ የሳምንታንት ልዩነቶች አውሮፓውያን ከጥንት ከነበረ አምልኮት ጋር የትዛመደ ሲሆን የእኛ ግን እግዚአብሔር አለምን መፍጠር ከጀመረ የመጀመርያ ቀን ስንል እሁድ ማለታችንን ሁለተኛ ቀን ስንል ሰኑይ (ሰኞ) ማለታችንን ወዘተ እንረዳለን።
ማኅበረ ቅዱሳን አውደ-ርዕይ 2000 ዓም
ማኅበረ ቅዱሳን አውደ-ርዕይ 2000 ዓም

አዲሱ ዓመት - ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዳስተማረው (የመጨረሻው ክፍል - ክፍል ፬)



(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ጳጉሜ ፪ ቀን፣ ፳፻፮ ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
የቀጠለ…
 እግዚአብሔር የሚወዳችኁ እናንተም የሚምትወዱት ልጆቼ! ይኽን ኹሉ በዝርዝር የምነግራችኁ ለምን ይመስላችኋል? ይኽን ኹሉ በዝርዝር መናገሬ በዘዴ ኹላችንም የምናደርገውን ማናቸውም እንቅስቃሴያችን ለእግዚአብሔር ክብር እናደርገው ዘንድ ስለምሻ ነው፡፡ በባሕር የሚነግዱ ነጋዴዎች ንብረታቸውን ወደ ከተማ ዳር መልሕቅ ካመጡ በኋላ መዠመሪያ የሚያደርጉት ነገር ቢኖር በቀጥታ ወደ ገበያ ሥፍራ መሔድ አይደለም፡፡ ወደ ገበያ ሥፍራ ከመሔዳቸው በፊት ስለ ትርፋቸው ያስባሉ እንጂ፡፡ እኛም በምናደርገው ኹሉ ከእግዚአብሔር ዘንድ የምናገኘውን ጥቅም ማሰብ አለብን፡፡

 ከእናንተ መካከል፡- “ኹሉንም ነገር ስለ እግዚአብሔር ክብር ብሎ ማድረግ ግን የሚቻል አይደለም” የሚል ፈጽሞ አይገኝ፡፡ ጫማችንን ብንጫማ፣ ፀጕራችንን ብናስተካክል፣ ልብሳችንን ብንለብስ፣ ከአንድ ቦታ ወደ ሌላ ቦታ ብንጓጓዝ፣ የቁመናችን አኳኋን፣ ንግግራችን፣ ስብስባችን፣ መግባታችን፣ መውጣታችን፣ መገሠፃችን፣ ማመስገናችን፣ መውቀሳችን፣ አለ መውቀሳችን፣ ሰውን ወዳጅ ወይም ጠላት ማድረጋችን ለእግዚአብሔር ክብር ማድረግ የሚቻለን ከኾነ እኛ ከፈቀድን ለእግዚአብሔር ክብር ተብሎ የማይደረግ ምን ይቀራል?
 የወኅኒ አለቃ ከመኾን ምን የከፋ አለ? የወኅኒ ጠባቂ ሕይወት እጅግ የምትከብድ አትመስልምን? ነገር ግን የልቡና ፈቃደኝነት ካለን የወኅኒ አለቃም ተኩኖ ኹሉንም ለእግዚአብሔር ክብር ማድረግ ይቻላል፡፡ እስረኞችን ማዳን ይቻላል፡፡ ያለ አግባብ የታሰሩትን መንከባከብ ይቻላል፡፡ ንጹሐን ሰዎችን አለ አግባብ ከሚያሰቃዩ ክፉዎች ጋር አለመተባበር ይቻላል፡፡ እስረኞችን እንደ አለቃ ሳይኾን እንደ ወንድምና እኅት ማገልገል ይቻላል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ወደ ሃይማኖት የመለሰውን የወኅኒ ጠባቂ ስንመለከት እንደዚኽ ዓይነት ሰው ነበር /ሐዋ.16፡25-40/፡፡ ስለዚኽ በአዲሱ ዓመት ኹሉንም ነገር ለእግዚአብሔር ክብር እናድርገው ብንል ይቻለናል ማለት ነው፡፡
 እስኪ ንገሩኝ! ከነፍሰ ግድያ በላይ ምን የከፋ ነገር አለ? ነገር ግን በዚኽ የነፍስ ግድያ እንኳን የጽድቅን ሥራ መሥራት ይቻላል፡፡ አትደንግጡ! ግድያ እንኳን ለእግዚአብሔር ክብር ተብሎ ሊደረግ ይችላል፡፡ ከእናንተ መካከል “ነፍሰ ገዳይ ሰው እንዴት አድርጐ ነው በነፍሰ ገዳይነቱ ጽድቅ ሠራ ተብሎ ሊነገርለት የሚችለው?” የሚል ሰው ሊኖር ይችላል፡፡ በመጽሐፍ ቅዱሳችን ውስጥ የተመዘገበውን አንድ ታሪክ አንሥቼ ልነግራችኁ እወዳለኹ፡፡ አንድ ጊዜ ምድያማውያን ከእስራኤል ጋር ጦርነት ይገጥሙ ዘንድ እግዚአብሔርን ለቁጣ ቀስቅሰዉት ነበር፡፡ በጦርነቱም ልዕልናቸውን በማሳየት፥ የእግዚአብሔርን መልካም ፈቃድ ለማስቀረት አስበው ሴቶቻቸውን በማሳመር በድንኳኑ ፊት ቆመው ነበር፡፡ በዚኽም እስራኤላውያንን በዝሙት እስከ መሳብና ለጣዖት እንዲሰግዱ እስከ ማታለል ደርሰው ነበር፡፡ ይኽም ብቻ ሳይኾን እስራኤላውያን ሃይማኖት የለሽ እንዲኾኑ ፈልገው ነበር፡፡ ፊንሐስ ግን ይኽን ባየ ጊዜ በእጁ ሰይፍ ይዞ ኹለት ሲያመነዝሩ የተገኙትን ሰዎች ሆዳቸውን በሰይፍ ወግቶ ገድሏቸዋል፡፡ በዚኽም የእግዚአብሔር ፈቃድ ምን እንደኾነ አረጋግጧል፡፡ ፊንሐስ ያደረገው ነገር ሰውን መግደል ነው፡፡ የዚኹ ግድያ ዓላማ ግን እስራኤልን በጠቅላላ ማዳን ነበር፡፡ በመኾኑም ከግድያ እንኳን ጽድቅን ማፍራት ይቻላል ማለት ነው /ዘኅ.25/፡፡
ፊንሐስ በፈጸመው ግድያ እጁ አልረከሰም፡፡ ይልቁንም ያ “ነፍሰ ገዳዩ” ፊንሐስ እስራኤላውያንን ከዝሙት ጠንቅ ጠብቆ ንጹሐን አደረጋቸው እንጂ፡፡ ፊንሐስ እነዚያ ኹለቱንም የገደላቸው ጠልቷቸው አልነበረም፤ የተቀሩትን የእስራኤል ሰዎች ለማዳን እንጂ፡፡ ኹለቱንም ብቻ በመግደል እልፍ እስራኤልን በነፍስ በሥጋ ከመሞት ለመታደግ እንጂ፡፡ ይኸውም ሐኪሞች እንደሚያደርጉት ነው፡፡ ሐኪሞች አንድ በቁስል መበስበስ (በጋንግሪን) የተጠቃን የሰውነት ክፍል ቈርጠው ቢያስወግዱት የተቀረውን ሰውነት ለማዳን ነው፡፡ ፊንሐስም ያደረገው እንደዚኹ ነው፡፡ መዝሙረኛው ክቡር ዳዊት ይኽንን በተመለከተ ሲናገር፡- “ፊንሐስም ተነሥቶ ፈረደባቸው፤ ቸነፈሩም ተወ፡፡ ያም እስከ ዘለዓለም ለልጅ ልጅ ጽድቅ ኾኖ ተቈጠረለት” ብሏል /መዝ.106፡30-31/፡፡ ፊንሐስ ያደረገው ነገር ትክክል ነው ተብሎ እስከ ዘለዓለም ሲነገርለት ይኖራል፡፡ (በነገራችን ላይ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን አልመለስ ያሉትን መናፍቃን ከቤተ ክርስቲያን አውግዛ የምትለያቸው ቀሪውን ምእመን እንዳይበክሉ እንጂ ጠልታቸው አይደለም፡፡ በቅርብ ጊዜ የተወገዙት የተሐድሶ አራማጆች የተወገዙትም ከዚኹ አንጻር ነው፡፡ በሌላ አገላለጽ ውግዘቱ ለእግዚአብሔር ክብር የተደረገ ነው፡፡)
  ዳግመኛም አንድ ሰው በመጸለዩ ምክንያት እግዚአብሔርን አስቈጥቷል፡፡ ምክንያቱም ጸሎቱ ለእግዚአብሔር ክብር የተደረገ አልነበረም፤ ርሱም ፈሪሳዊው ነው /ሉቃ.18/፡፡ ፊንሐስ ግድያን ስለ ፈጸመ በእግዚአብሔር ዘንድ ተቀባይነት አገኘ፤ ፈሪሳዊው ደግሞ በአንጻሩ ስለ ጸለየ እግዚአብሔርን አስቈጣ፡፡ ስለዚኽ ማናቸውም የምናደርገው ነገር ምንም መንፈሳዊ ቢኾንም ለእግዚአብሔር ክብር እስካልተደረገ ድረስ ትርፉ ጉዳት ነው፡፡ ሥጋዊ ሥራም ብንሠራ ለእግዚአብሔር ክብር ማድረግ ይቻለናል፡፡ ሰውን ከመግደል በላይ እጅግ ክፉና ዘግናኝ ነገር ምን አለ? ነገር ግን ይኽ ለእግዚአብሔር ክብር የሚደረግ ከኾነ ከዚኹ ግድያ እንኳን ጽድቅን ማግኘት ይቻላል፡፡
 እንግዲኽ ከነፍሰ ገዳይ እንኳን እንዲኽ ዓይነት ጽድቅ ከተገኘ እያንዳንዱ ግብራችን ለእግዚአብሔር ክብር ማድረግ አይቻለንም እንደምን ማለት ይቻለናል? የልቡና ፈቃደኝነት ካለን ግን ኹሉንም ነገር ለእግዚአብሔር ክብር ማድረግ ይቻለናል፡፡ ብንገዛም ብንሸጥም ለእግዚአብሔር ክብር ማድረግ ይቻለናል፡፡ ከአግባብ በላይ ዋጋን በመጨመር ሸማቹን ማኅበረ ሰብ ባለ ማስቸገር ንግዳችን ለእግዚአብሔር ክብር ማድረግ ይቻለናል፡፡ አንድን ዕቃ በመደበቅ (አኹን ባለው የአገራችን ተጨባጭ ኹኔታ ዘይትንና ስኳርን ማለት እንችላለን) አለአግባብ ለመክበር ብለን የምንደብቀው ከኾነ “እኽልን የሚያስቀር ሰው በሕዝቡ ዘንድ የተረገመ ነው” እንደተባለ /ምሳ.11፡26/ ንግዳችን እግዚአብሔር የከበረበት ንግድ አይደለም፡፡
 ከእናንተ መካከል፡- “አባታችን! አንድ ምሳሌ መስለኽ ልታስተምረን ስትችል ወደዚኽ ኹሉ ዝርዝር መግባት ለምን አስፈለገኽ?” የሚል ሰው ሊኖር ይችላል፡፡ አንድ የሕንፃ ተቋራጭ አንድን ሕንፃ ለመገንባት የሚዠምረው መሠረት በመጣል ነው፡፡ ከዚያም ደረጃ በደረጃ የተቀረውን የሕንፃን ክፍል ይገነባል፡፡ በመጨረሻም ሕንፃው እጅግ የሚያምር እንዲኾን የቅብ (finishing) ሥራን ይሠራል፡፡ እኛም ይኽን ኹሉ በዝርዝር ማየታችን በክፍል 2 ትምህርታችን፡- ወዳጄ ሆይ! ቤቱ ቆሽሾ ሳለ ውጫዊ በሩን ብቻ ለማሽቀርቀር ለምን ትጨነቃለኽ? ነፍስኅ በኀጢአት ተዳድፋ ሳለ ሥጋኽን ብቻ ለማስደሰት ለምን ትሮጣለኽ? አስቀድመኽ ቤቱን (ነፍስኽን) ለማስዋብ አትሽቀዳደምምን? አስቀድመኽ ለነፍስኽ የምታስብ ከኾነ ከሰው እጅ ሳይኾን ከክርስቶስ እጅ ሹመት ሽልማት ትቀበላለኽ፡፡ ኹል ጊዜ “የማደርገው ነገር እግዚአብሔር ይከብርበታልን?” ብለኽ አስብ እንጂ እንዲኹ ከአኹን (ከአዲሱ ዓመት) በኋላ በዘልማድ የምትመላለስ አትኹን ብዬ እመክርኻለኁ፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ሲመክረን፡- “እንግዲኽ የምትበሉ ወይም የምትጠጡ ብትኾኑ ወይም ማናቸውም ነገር ብታደርጉ ኹሉን ለእግዚአብሔር ክብር አድርጉት” ያለንም ስለዚኹ ነውና በአዲሱ ዓመት በድርጊቶቻችን ኹሉ እግዚአብሔርን ለማክበር እንዘጋጅ /1ኛ ቆሮ.10፡31/፤” የሚለውን መሠረት ይዘን ነው፡፡
  ከእንግዲኽ ወዲኽ ብንጸልይም፣ ብንጦምም፣ ብንገሥፅም፣ ይቅር ብንልም፣ ብናመሰግንም፣ ብንወቅስም፣ ብንገባም፣ ብንወጣም፣ ብንሸጥም፣ ብንገዛም፣ ብንናገርም፣ ዝም ብንልም፣ ማናቸውን ነገር ብናደርግ ለእግዚአብሔር ክብር ልናደርጋቸው ይገባናል፡፡ ይኽን ያልዠመርን ካለንም አዲሱን ዓመት ምክንያት በማድረግ እንዠምረው፡፡ ለእግዚአብሔር ክብር የማናደርገው ከኾነ ግን አንሥራው፤ በማኅበር መካከል እንድንናገር ብንገፋፋም አንናገር፡፡ የትም ብንሔድ ይኽቺውን የሐዋርያው ቃል በልቡናችን ጽላት ጽፈን ይዘናት እንሒድ፡፡ ርሷም (ኃይለ ቃልዋ) የምናደርገው ኹሉ ለእግዚአብሔር ክብር እንድናደርገው ታሳስበናለች፡፡ የምናደርገው ኹሉ ለእግዚአብሔር ክብር የምናደርገው ከኾነም “ያከበሩኝን አከብራለኹ” ብሏልና /1ኛ ሳሙ.2፡30/ ከሰው እጅ ሳይኾን ከራሱ ከክብር ባለቤት ከልዑል እግዚአብሔር ዘንድ በዚኽም ዓለም በወዲያኛውም ዓለም ክብርን እንጐናጸፋለን፡፡ እንኪያስ ከእንግዲኽ ወዲኽ ክብር የክብር ክብር፣ አምልኮና ውዳሴ ለአምላካችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ይገባዋልና በቃል ብቻ ሳይኾን በገቢር ጽድቅ በምግባር በትሩፋት ዘወትር እናክብረው፡፡ እስከ ዘለዓለሙ ድረስ አሜን!!!
መልካም አዲስ ዓመት ይኹንላችኁ፤ ይኹንልን!!!

2014 ሴፕቴምበር 6, ቅዳሜ

ጳጉሜን - አምስት፣ ስድስት፣ ሰባት

የመግቢያ ማስታወሻ
በጽሑፉ ውስጥ በግእዝ ቁጥሮች በቅንፍ ውስጥ የተጻፉት ሐሳቡን እንዲወክሉ ብቻ ነው፡፡ በኋላ (ቁጥር ፭ ተመልከት ቢል ያንን ሐሳብ መልሶ ለማየት እንዲረዳ ነው፡፡
የኢትዮጵያን የዘመን አቆጣጠር ለየት ከሚያደርጉት ነገሮች አንዱ ጳጉሜ የምትባል አሥራ ሦስተኛ ወር ስላለችን ነው፡፡ የቤት ኪራይና የወር ደመወዝ የማንከፍልባትና የማንቀበልባት፤ መብራትና ውኃ ግን ከነሐሴ ወር ጋር ጨምረው የሚያስከፍሉባት፤ ሲሻት አምስት፣ ሲያስፈልጋት ስድስት፣ ስትፈልግ ደግሞ ሰባት የምትሆን ወር ናት፡፡ እንዲያውም ከአሥራ ሁለቱ የኢትዮጵያ ወሮች ጳጉሜ በብዙ መንገድ የተለየች ናት፡፡
በአንድ በኩል በጣም ትንሿ ወር ናት፡፡ ሲቀጥልም ወርኃዊ በዓላት የማይውሉባት ወር ናት፡፡ እንዲያም ሲል ደግሞ ከሌሎች ወሮች በተለየ የቀኖቿ መጠን የሚቀያየሩ ብቸኛ ወር ናት፡፡ ከሌሎች የኢትዮጵያ ወሮች በተለየም ስሟ ኢትዮጵያዊ ያልሆነ ወር ናት፡፡ በሁለት ዘመናት መካከልም እንደ መሸጋገሪያ የምትታይ ወርም ናት፡፡  


ጳጉሜ ማለት በግሪክ ‹ጭማሪ› ማለት ሲሆን ዓመቱን በሠላሳ ቀናት ስንከፍለው የሚተርፉትን ዕለታት ሰብስበው የሰየሟት ተጨማሪ ወር ናት፡፡ ወይም በየዕለቱ በፀሐይና በጨረቃ አቆጣጠር መካከል የሚፈጠረውን ልዩነት ሰብስበው ያከማቹባት ወር ትባላለች፡፡ ዓመቱ በዐውደ ፀሐይ ሲለካ 365 ቀናት ከ15 ኬክሮስ 6 ካልዒት ሲሆን በጨረቃ ሲለካ ደግሞ 354 ቀናት ከ22 ኬክሮስ፣ 1 ካልዒት፣ 36 ሣልሲት፣ 52 ራብዒት፣ 48 ኀምሲት ነው፡፡ (60 ኬክሮስ አንድ ቀን ነው)በሁለቱ መካከል(በፀሐይና በጨረቃ) በዓመት ውስጥ ያለው ልዩነት 11 ቀናት ከ7 ኬክሮስ ይሆናል፡፡ [በነገራችን ላይ በዘመን አቆጣጠራችን ውስጥ ከዕለት በታች የምንቆጥርባቸው ስድስት መለኪያዎች አሉ፡፡ ኬክሮስ፣ ካልዒት፣ ሣልሲት፣ ራብዒት፣ ኀምሲትና ሳድሲት፡፡ 60 ሳድሲት አንድ ኀምሲት፣ 60 ኀምሲት አንድ ራብዒት፣ 60 ራብዒት አንድ ሣልሲት፣ 60 ሳልሲት አንድ ካልዒት፣ 60 ካልዒት ደግሞ 1 ኬክሮስ ይሆናል፡፡ 60 ኬክሮስ ደግሞ 1 ዕለት፡፡ 1 ኬክሮስ 24 ደቂቃ ነው]
ጳጉሜን ለማግኘት የሚጠቅመን የየዕለቱን ልዩነታቸውን መመልከቱ ነው፡፡ በየዕለቱ በጨረቃና በፀሐይ መካከል 1 ኬክሮስ 52 ካልዒት(60 ካልዒት አንድ ኬክሮስ ነው)፣ ከ 31 ሣልሲት(60 ሣልሲት አንድ ካልዒት ነው) ይሆናል፡፡[ይህም ማለት 5 ሰዓት ከ48 ደቂቃ ከ46 ካልዒት(ሴኮንድ?)] ይህ ልዩነት በአንድ ወር ምን እንደሚደርስ ለማወቅ በ30 እናባዛው፡፡ 30 ኬክሮስ፣ 1560 ካልዒት፣ ከ930 ሣልሲት ይሆናል፡፡ የዓመቱን ለማግኘት ደግሞ በ12 እናባዛው፡፡ 360 ኬክሮስ(፩)፣ 18720 ካልዒት(፪)፣ 11160 ሣልሲት(፫) ይመጣል፡፡
ቀደም ብለን 60 ኬክሮስ አንድ ዕለት ይሆናል ባልነው መሠረት 360 ኬክሮስ ለ60 ሲካፈል 6 ዕለታትን ይሰጠናል(፩)፡፡ 18720 ካልዒትን(፪) በስድሳ በማካፈል 312 ኬክሮስን እናገኛለን፡፡ ያም ማለት ትርፉን 12 ኬክሮስ ትተን 300ውን ኬክሮስ ለ60 በማካፈል 5 ዕለት እናገኛለን፡፡ ይኼም ማለት 5 ዕለት ከ12 ኬክሮስ(፬) ይሆናል፡፡ 11160 ሣልሲትን(፫)ለ60 ብናካፍለው 186 ካልዒት ወይም ደግሞ 3 ኬክሮስና 6 ካልዒት(፭) ይሆናል ማለት ነው፡፡
ከላይ ኬክሮስን በዓመቱ ቀናት አባዝተን ያገኘነው(፩) 6 ዕለት አለ፡፡ ይኼ ዕለት ሕጸጽ ይባላል፡፡ ፀሐይና ጨረቃን እኩል መስከረም አንድ ላይ ዓመቱን ብናስጀምራቸው ፀሐይ የወሯ መጠን ምንጊዜም ሠላሳ ሲሆን ጨረቃ ግን በአንደኛው ወር 29 በሌላኛው ወር ግን 30 ስለምትሆን ዓመቱ እኩል አያልቅም የጨረቃ ዓመት ነሐሴ 24 ቀን ያልቃል፡፡ ይህም ማለት ጨረቃ በሁለት ወር አንድ ጉድለት ታመጣለች፡፡ ያንን ነው ሊቃውንቱ ሕጸጽ(ጉድለት) ያሉት፡፡ በዚህም መሠረት ከላይ ኬክሮሱን(፩) በዓመቱ ቀናት አባዝተን ያገኘነውን 6 ዕለት ለጨረቃ ሕጸጽ ስንሰጠው የመስከረም/ ጥቅምት (1)፣ የጥቅምት/ ኅዳር(2)፣ የጥር/ የካቲት(3)፣ የመጋቢት/ ሚያዝያ(4)፣ የግንቦት/ ሰኔ (5)፣ የሐምሌ ነሐሴ (6) ሆነው ተካፍለው ያልቃሉ፡፡
በሌላም በኩል ደግሞ በጨረቃና በፀሐይ ዑደት መካከል በዓመት ያለው ልዩነት 11 ቀናት ከ15 ኬክሮስ ከ6 ካልዒት) ይሆናል፡፡ ስድስቱን ዕለታት ጨረቃ ለምታጎልበት (ሕጸጽ) ብንሰጠው ቀሪ 5 ዕለት ይኖረናል፡፡ ጳጉሜ ማለት እነዚህ 5 ቀናት ናቸው፡፡ አሁን የአሥራ አንዱን ዕለታት ከፈጸምን ሽርፍራፊዎቹን (15 ኬክሮስና 6 ካልዒት) እንይ፡፡
ከላይ እንዳየነው በፀሐይና ጨረቃ ዓመታት መካከል የተፈጠሩትን 11 ቀናት ስድስቱ ለሕጸጽ ማሟያ ሲገቡ የቀሩት 5 ዕለታት ናቸው ጳጉሜ የምትባለውን ወር በመሠረታዊነት የፈጠሯት፡፡ በጎርጎርዮሳውያኑ አቆጣጠር እነዚህ 5 ተጨማሪ ዕለታት በጃንዋሪ፣ ማርች፣ ሜይ፣ ጁላይና ኦገስት ላይ ስለተጨመሩ እነዚህ ወራት 31 ለመሆን ተገድደዋል፡፡ (ይህንን የከፈለው በ46 ቅልክ የነበረው ዩልየስ ቄሣር ነው፡፡ ለአራቱ ወሮች 30 ቀን፣ ለአንዱ 28/29 (በየአራት ዓመቱ)፣ ለቀሩት ሰባት ወሮች ደግሞ 31 ሰጥቷቸዋል፤ ለአምስቱ ወሮች 31 ያደረጋቸው ከጳጉሜ ወስዶ ሲሆን ለሁለቱ ወሮች አንዳንድ ቀን የጨመረላቸው ከፌቡርዋሪ 2 ቀናት ወስዶና ወሩን 28 አድርጎ ነው)፡፡
ከእንግዲህ የሚቀሩን ከላይ የየዕለቱን ልዩነት ለዓመት ስናባዛ (ቁጥር ፪ና ፫ ተመልከት) የቀሩን 15 ኬክሮስና 6 ካልዒት ናቸው፡፡ ሁለቱን  ከላይ ያየናቸውን (፬ና፭) ስንደምራቸው (12 ኬክሮስ + 3 ኬክሮስ ከ6 ካልዒት) 15 ኬክሮስ ከ 6 ካልዒት ይመጣሉ፡፡
ቀደም ብለን አንድ ዕለት 60 ኬክሮስ ነው ብለናል፡፡ ስለዚህም አንድ ዕለት (60 ኬክሮስ) ለማግኘት ከላይ ያገኘነውን 15 ኬክሮስ በ 4 ማባዛት አለብን፡፡ በአራት ዓመት አንዴ ጳጉሜ 6 የምትሆነው እነዚህ በየዓመቱ የተጠራቀሙት 15 ኬክሮሶች አንድ ላይ መጥተው በአራት ዓመት አንድ ጊዜ አንድ ዕለት ስለሚሆኑ ነው፡፡ እርሷም ሠግር(leap year) ትባላለች፡፡ ጎርጎርዮሳውያኑ ይህቺን ሠግር በፌቡርዋሪ ወር ላይ ጨምረው ወሩን በየአራት ዓመቱ አንድ ጊዜ 29 ቀን ያደርጉታል፡፡
15ቱ ኬክሮስ በአራት ዓመት ተደምረው አንድ ዕለት መጡና በአራት ዓመት አንዴ ጳጉሜን ስድስት አደረጓት፡፡ የቀረችው 6 ካልዒትስ (ቁጥር ፭) የት ትግባ?
ካልዒት አንዲት ዕለት ትሆን ዘንድ 3600 ካልዒት ያስፈልጋሉ፡፡ ይህንን ያህል ካልዒት ለማግኘት 600 ዓመታት ያስፈልጉናል፡፡ ለዚህ ነው ጳጉሜ በየስድስት መቶ ዓመታት ሰባት የምትሆነው፡፡ እስካን የጠየቅኳቸው የባሕረ ሐሳብና የታሪክ ሊቃውንት በታሪካችን ውስጥ ጳጉሜን 7 የሆነችበትን ዘመን እንደማያውቁ ነግረውኛል፡፡ ሒሳቡ ሲሰላ በየ 600 ዓመቱ ሰባት ትሆናለች ቢባልም አስቦ በስድስት መቶኛው ዓመት ሰባት የሚያደርጋት እንደሌለ ይናገራሉ፡፡ በፈረንጆቹ ብሂል ‹ፌብሩዋሪ 30› ማለት የመሆን ዕድል ያለው ነገር ግን ሆኖሞ የማያውቅ ሊሆንም የማይችል(possible but never happen)› ተደርጎ እንደተወሰደው ሁሉ ምናልባት በኛም ጳጉሜን 7 ማለት እንደዚያው ይሆን ይሆናል፡፡
በነገራችን ላይ ጳጉሜን 5 ቀን በቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ዘንድ ‹ዕለተ ምሪያ› ወይም የተመረጠች ቀን ትባላለች፡፡ የጌታችን ልደት ለመጠበቅ ሊቃውንቱ ሲያሰሉባት የቆየችው ዕለት በመሆኗ ነው ይህንን ስያሜ ያገኘችው፡፡ የጌታችንን ልደት ቀን የምትወስነው ጳጉሜ 5 ቀን ናት፡፡ ልደት የሚውለው ጳጉሜ 5 በዋለበት ቀን ነው፡፡ ለምሳሌ ዘንድሮ ጳጉሜን 5 ቀን ረቡዕ ነው የምትውለው፤ ስለዚህም በ2007 ዓም ልደት የሚውለው ረቡዕ ነው፡፡ በየአራት ዓመቱ አንድ ጊዜ ጳጉሜን 6 ስትሆን ልደት በ28 የሚከበረው ዕለተ ምሪያን ስለማይለቅ ነው፡፡ ስድስተኛዋ ቀን ልደትን በአንድ ቀን ስታዘልለው እኛ በ28 እናከብረዋለን፡፡ ልደት ጳጉሜ 5 ቀንን(ዕለተ ምሪያን) ስለማይለቅ፡፡ ታድያ ምነው እነ ጥምቀትና ግዝረት አይለወጡም? ቢሉ፡፡ ሊቃውንቱ የሚሰጡት መልስ ‹ትውልድ ሱባኤ እየቆጠረ በተስፋ የጠበቃት ዕለተ ልደትን ስለሆነ ነው፤ ሌሎቹ የመጡት በልደቱ ምክንያት ነው›› የሚል ነው፡፡
በጎርጎርዮሳውያንም ቢሆን በአራት ዓመት አንዴ ልደት ዝቅ ትላለች፡፡ የእነርሱ የማይታወቀን ጭማሪዋ ፌብርዋሪ ላይ ስለሆነች ነው፡፡ ያ ደግሞ አዲሱን ዓመት ካከበሩ በኋላ ስለሚመጣ ነው፡፡ የእኛ ግን የምትወድቀው ጳጉሜን መጨረሻ ላይ በመሆኗ ከአዲስ ዓመት በፊት ስለምትጨመር ጎልቶ ይታወቃል፡፡
እንግዲህ ጳጉሜ የምትባለው አስገራሚ ትንሷ ወራችን እንዲህ በስሌት የተሞላች፣ አምስት ሆና ቆይታ በየአራት ዓመቱ አንዴ ስድስት፣ በየስድስት መቶ ዓመቱ ደግሞ ሰባት የምትሆን ናት፡፡ ታላላቆቹ ወሮች ምንም ሳይፈጥሩ የልደትን ቀን የምትወስን፣ የዓመቱን ሠግር የምታመጣ፣ ታሪከኛ ወር ናት፡፡ ትንሽ ትልቅ ማለት እንዲህ ነው፡፡

አዲሱ ዓመት - ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዳስተማረው (ክፍል ፫)



(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ጳጉሜ ፩ ቀን፣ ፳፻፮ ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
የቀጠለ…                       
 ለእግዚአብሔር ክብር ብሎ ሰውን መውቀስም አለ፡፡ ከእናንተ መካከል፡- “እንዴት ብሎ? ርግጥ ነው ብዙውን ጊዜ ሠራተኞቻችንን እንወቅሳለን፡፡ ለእግዚአብሔር ክብር ብሎ መውቀስስ እንደምን ያለ ነው?” አዎ! የሚሰክር ወይም የሚሰርቅ ሠራተኛ ወይም ጓደኛ ብናይ ወይም ከዘመዳችን አንዱ ወደ ተውኔት ቤት፣ ወይም ለነፍሱ ምንም ረብሕ ወደማያገኝበት ሥፍራ ሲሮጥ፣ በከንቱ ሲምል፣ የሐሰት ምስክርነትን ሲሰጥ፣ ወይም ሲዋሽ፣ ወይም ሲቈጣ ብናየው ዠርባችንን ብንሰጠውና ብንገሥፀው ወቀሳችን ለእግዚአብሔር ክብር የተደረገ ነው ይባላል፡፡

 ዳግመኛም አንድ ሰው ቢበድለን፣ ርሱ ራሱ የሠራውንም ጥፋት በእኛ ቢያመካኝ ስለ እግዚአብሔር ብለን ይቅር ልንለው ይገባል፡፡ ብዙዎቻችን ግን ለጓደኞቻችን፣ ለሠራተኞቻችን የዚኽ ተቃራኒውን ነው የምናደርገው፡፡ ጓደኞቻችን ወይም ሠራተኞቻችን ቢበድሉን እናንባርቃለን፤ ይቅርታ የሌለው ፍርድም እንፈርድባቸዋለን፡፡ እኛው ራሳችን እግዚአብሔርን በገቢር ስንሰድብ አንድም ስናሰድብ ወይም ነፍሳችንን ስንጐዳ ግን እንደበደልን አይሰማንም፡፡ ይኽ ግን በአዲሱ ዓመት ልናስተካክለው የሚገባ ነገር ነው፡፡ ዕለት ዕለትም ልንለማመደው ይገባል፡፡  
 የበደሉንን ሰዎችስ ወዳጅ ማድረግ ይገባልን? አዎ! ለእግዚአብሔር ክብር ሲባል የበደሉንን ሰዎች ወዳጅ ማድረግ ይገባናል፡፡ ለእግዚአብሔር ክብር ሲባል ሰውን ጠላት ማድረግስ? አዎ! ይቻላል፡፡ ለመኾኑ ስለ እግዚአብሔር ክብር ብሎ ሰውን ወዳጅና ጠላት ማድረግ ሲባል ምን ማለት ነው? ሰውን ወዳጅ ማድረግ ሲባል ያንን ሰው ከገንዘባችን፣ ከማዕዳችን እንዲካፈል በእኛም እንዲደገፍ ማድረግ ማለት አይደለም፡፡ አንድን ሰው እውነተኛ ወዳጅ ኾንነው አንድም አደረግነው የሚባለው ነፍሱን እንዳይጐዳ ብንገሥፀውና ብንመክረው፣ ቢበድል (በበደሉ የሚጐዳው ርሱ ራሱ ነውና) እንደ ጠላት ሳይኾን እንደ ወዳጅ ቀረብ ብለን የሚረባውን ብንነግረው፣ ከወደቀበት የኀጢአት አረንቋ እንዲነሣ ብናደርግ ለዚኽም ዘወትር በጸሎት ብንረዳውና ወደ እግዚአብሔር እንዲቀርብ ብናደርግ ነው፡፡ ስለ እግዚአብሔር ክብር ብሎ ሰውን ጠላት ማድረግም ይፈቀዳል፡፡ ይኽን ከዚኽ በፊት ያላከናወንነው ከኾነም ከአኹኑ አዲሱ ዓመት መዠመር እንችላለን፤ ለእግዚአብሔር ክብር ብለን ሰውን ጠላት ማድረግ፡፡ ለምሳሌ አንድ ጋጠ ወጥ፣ ክፋትን የተመላ፣ ንግግሩ (ትምህርቱ) ኹሉ በምንፍቅና መርዝ የተለወሰ፣ ዘወትር ነፍሳችንን የሚያውካትና የሚጐዳት ሰው ካለ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “ቀኝ ዓይንኅም ብታሰናክልኽ አውጥተኽ ከአንተ ጣላት” እንዳለ /ማቴ.5፡29/ እነዚኽን ሰዎች መራቅ ጠላትም ማድረግ ይፈቀዳል፡፡ እነዚኽ ሰዎች ቀኝ ዓይን ተብለው መጠቀሳቸውም ምንም እንኳን እንደ ዓይናችን የምናያቸው ወዳጆቻችን ቢኾኑም ነፍሳችንን የሚጐዷት ከኾነ ከእኛ ዘንድ ልናርቃቸው ይገባል፡፡
 ንግግራችንም ዝምታችንም ለእግዚአብሔር ክብር ልናደርገው ይገባል፡፡ ስለ እግዚአብሔር ብሎ መናገር ሲባል ምን ማለት ነው? ለምሳሌ ከአንድ ጓደኛችን ጋር ቁጭ ብለን ስንጨዋወት “ማን ሥልጣን ላይ ወጣ፣ ማን ወረደ፣ ማን አለፈ፣ ማን ምን ክብር አገኘ” እያልን ከምንጨዋወት ይልቅ ስለ ነገረ ሃይማኖት፣ ስለ ገሃነመ እሳት፣ ስለ መንግሥተ ሰማያት ብንጨዋወት መናገሩ ጥቅምን ይሰጣል፡፡ ነፍሳችንን በማይጠቅማት ነገር አላስጨነቅናትምና፡፡ ይኽን ዓይነት ኅብረት ባንተወዉም አንጐዳንም፡፡ በኋለኛው ቀን ላይ ይኽ ኹሉ ማድረጋችን አንዳች ጥቅም ይሰጠናልና፡፡ ስለዚኽ ለነፍሳችን አንዳች የሚጠቅም ነገር በሌለው ስብስብ መካከል መቀመጡና ማውራቱ ለእኛ ጉዳት እንጂ ረብሕ የለውም፡፡ የዚኽ ስብስብ መንፈስ ለውጦ ስለ ነገረ እግዚአብሔር ማውራቱም ስለ እግዚአብሔር ክብር አደረግነው ይባላል፡፡ ዝምታችንም ለእግዚአብሔር ክብር መኾን ይገቧል፡፡ ምንም ሳንበድለው ክፉ ለሚያደርግብን ሰው፣ ሳንወቅሰውና ሳናንጐራጉርበት በትዕግሥት ዝም ብንል ዝምታችን ለእግዚአብሔር ክብር የተደረገ ነው ይባላል፡፡
ማመስገንና መገሠፅ፣ ወይም ከቤት ውስጥ መኾንና አለመኾን ወይም መናገርና አርምሞ ብቻ አይደለም፤ ኀዘናችንም ደስታችንም ስለ እግዚአብሔር ክብር ሊኾን ይገባል፡፡ አንድ ወንድማችን ኀጢአት እየሠራ ብናየው ወይም እኛው ራሳችን በበደል ስንወድቅ ብናለቅስና ብናዝን ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እንዳለ “እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ የኾነ ኀዘን ጸጸት የሌለበትን፣ ወደ መዳንም የሚያደርሰውን ንስሐ ያደርጋልና” /2ኛ ቆሮ.7፡10/ ኀዘናችን ለእግዚአብሔር ክብር የተደረገ ነው ይባላል፡፡ አንድ ወንድማችን መልካም ነገርን ስላገኘ ልክ ለእኛ እንደተደረገ አድርገን እግዚአብሔርን ብናመሰግንም ደስታችን ለእግዚአብሔር ክብር የተደረገ ነው ይባላል፡፡ ከዚኽ ደስታም እጅግ ብዙ ጥቅምን እናገኝበታለን፤ እንኪያስ ይኽን በአዲሱ ዓመት እንለማመደዋ!!!
 በወንድሙ ደስታ መደሰት ሲገባው ወንድሙ ስለ ተጠቀመ ብቻ በቅናት ከሚቃጠል ሰው በላይ አሳዛኝ ሰው ማን አለ? እስኪ ንገሩኝ! በወንድሙ ደስታ በማዘኑ የእግዚአብሔርን ፍርድ በራሱ ላይ በመጨመር በነፍስ በሥጋ ከሚጐዳ ቅናተኛ ሰው በላይ የሚያሳዝን ፍጥረት ማን አለ? ወንድማችን ስለ ተጠቀመ ብናመሰግን ወይም ብንደሰት፣ ወንድማችን ስለ ተጐዳም ብናዝን እና ብናለቅስ ይኽንንም ለእግዚአብሔር ክብር ብለን ብናደርገው አንጠቀምምን?
  ፀጉርን ከማሳጠር በላይ ምን ትንሽ ነገር አለ? ነገር ግን ይኽም ለእግዚአብሔር ክብር ማድረግ ይቻላል፡፡ ለምሳሌ ሴቶች በፀጉራቸው ምክንያት ወንዶች የሚሰነካከሉ ከኾነና ይኽንን ዐውቀው ባይቈርጡትም ወንዶቹ በማይሰናከሉበት መንገድ ቢሸላለሙት፣ ደካማ ወንድሞቻቸው በማይሰናከሉበት መንገድ ራሳቸውን ቢያጌጡ ይኽን ለእግዚአብሔር ክብር አድርገዉታልና ሹመት ሽልማታቸው የበዛ ነው፡፡ የክፉ ምኞት ፍላጻን ለእግዚአብሔር ክብር ሲባል አስቀርተዉታልና ዋጋቸው በሰማያት ዘንድ ታላቅ ነው፡፡ ስለ እግዚአብሔር ክብር ብሎ አንዲት ኩባያ ውኃን የሰጠ ሰው ርስት መንግሥተ ሰማያትን የሚያገኝ ከኾነ፥ የምናደረግው ኹሉ ለእግዚአብሔር ክብር ብለን የምናከናውነው ከኾነማ ሹመት ሽልማታችን እንደምን አይበዛ?
  ስለ እግዚአብሔር ክብር ብሎ መሔድም አለመሔድም አለ፡፡ ምን ማለት ነው? ወደ ክፋት የማንሔድ ከኾነ፣ የቆነጃጅትን ውበት በማድነቅ ስም ልቡናችን በምኞት መንፈስ የማንጠመድ ከኾነ፣ አንዲት ቆንጆ ልጅ በፊታችን ብናይና እንደምታሰናክለን ተረድተን ዓይናችንን ከርሷ ዞር የምናደርግ ከኾነ ውበትን ለእግዚአብሔር ክብር አዋልነው ይባላል፡፡
 አለባበሳችንም ቢኾን ለእግዚአብሔር ክብር ልናደርገው ይገባናል፡፡ እጂግ ውድ የኾኑ አልባሳትን ባንለብስ፣ ሰውነታችንን እጂግ ሳናራቁት፣ በአጭሩ ሰውን የማያሰናክል አለባበስን ብንከተል አለባበሳችን ስለ እግዚአብሔር ክብር አደረግነው ይባላል (በነገራችን ላይ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በአጸደ ሥጋ በዚኽ ዘመን ቢኖርና ከቅርብ ጊዜ ወዲኽ የምናየውን የእኅቶቻችንን አለባበስ ቢያይ ምን ብሎ ሊገሥፅ እንደሚችል አስቡት፡፡ ምክንያቱም እኅቶቻችን በስመ ዘመናዊነት የሚለብሱት እጅግ በጣም አጭር ቀሚስ ወይም ሱሪ የብዙ ደካማ ወንዶችን ልብ በዝሙት ይፈታተናልና)፡፡
 የምጫማው ጫማ እንኳን ለእግዚአብሔር ክብር ልናደርገው ይገባል፡፡ አንዳንድ ሰዎች ለሚያደርጉት ጫማ ከዓቅም በላይ ሲጨናነቁ አያለኹ፡፡ ፊታቸውን በተለያየ መንገድ ለማሸብረቅ የሚወዱትን ያኽል ስለ ጫማቸው ውበት እጂግ የሚጨነቁ ሰዎችን አያለኹ፡፡ ምንም እንኳን ይኽ እንደ ትንሽ ነገር አድርገን ብናስበውም ዘወትር በወንዶችም በሴቶችም የምናየው ነገር ነው፡፡ ስለዚኽ ጫማችን እንኳን ሳይቀር ለእግዚአብሔር ክብር ልናደርገው ይገባናል ማለት ነው፡፡ በአካሔዳችንም፣ በአለባበሳችንም፣ እግዚአብሔርን ደስ ማሰኘት እንደሚቻል ሲናገር ጠቢቡ ምን እንደሚለን እስኪ እናድምጠው፡- “ከአለባበሱና ከአካሔዱ ከአሳሳቁም የተነሣ የሰው ጠባዩ ይታወቃል” /ሲራክ 19፡27/፡፡ ስለዚኽ በአዲሱ ዓመት ብቻ ሳይኾን በየዕለቱ የምናደርገው ኹሉ ለእግዚአብሔር ክብር የምናደርገው ከኾነ አሕዛቡም፣ መናፍቁም፣ ፈላስፋውም አስቦበት ሳይኾን እንዲኹ በእኛ ይደነቃል፡፡
 ትዳራችን እንኳን ለእግዚአብሔር ክብር ልናደርገው ይገባናል፡፡ መኝታችን (በትዳር ውስጥ የሚደረገው ሩካቤ) ንጹሕ ማድረግ፣ ትዳርን ለብር ወይም ሌላ ምድራዊ ነገርን ለማግኘት ሳይኾን ነፍሳችንን ለማዳን፣ እግዚአብሔርን ለማግኘት የሚደረግ ከኾነ ለእግዚአብሔር ክብር አደረግነው ይባላል፡፡ የትዳር አጋራችንን ከዘለዓለማዊ ሕይወት አንጻር እንጂ ከውበት፣ ከሃብት፣ ወይም ከሌላ ጊዜአዊ ጥቅም አንጻር የማንመለከት ከኾነ ትዳራችን ለእግዚአብሔር ክብር የተደረገ ነው ይባላል፡፡ በአዲሱ ዓመት ይኽን ልንለማመድ ይገባናል፡፡
 ይቀጥላል…

አዲሱ ዓመት - ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዳስተማረው (ክፍል ፪

)




(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ነሐሴ ፳፯ ቀን፣ ፳፻፮ ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
የቀጠለ…

 ከገቢረ ኀጢአት ሳይወጡ አዲስ ዓመት ሲመጣ መደሰት፣ ብዙ መብልና መጠጥ ማዘጋጀት፣ አዲስ ልብስም መልበስ ጥቅም የለውም፡፡ ነፍሳችን በኀጢአት እየተጨነቀች፣ ነፍሳችን ተርባና ተጠምታ ሳለ፣ የተዳደፈ የኀጢአት ልብስም ተጆቡና ሳለ አዲስ ዓመት ማክበር ለእኛ ምን ጥቅም ይሰጠናል? እንዲኽ ከገቢረ ኀጢአት ሳይወጡ አዲስ ዓመትን ማክበር ማለት ለእኔ እንደ ልጆች የዕቃ ዕቃ ጨዋታ ነው፡፡

 ክርስቶስ ከዚኹ ሥራ አውጥቶናል፡፡ ከሕፃንነት አዕምሮ ወደ ማወቅ አሸጋግሮናል፡፡ ከምድራውያን ለይቶ ከሰማያውያን ጋር ደባልቆናል፡፡ ስለዚኽ “መልካሙን ሥራችኁን ዐይተው በሰማያት ያለውን አባታችኁን እንዲያከብሩ ብርሃናችኁ እንዲኹ በሰው ፊት ይብራ” እንደተባለ አፍአዊ ሳይኾን መንፈሳዊውን ብርሃን ልናበራ ይገባናል /ማቴ.5፡16/፤ በአዲሱ ዓመት፡፡ ይኽም ብርሃን ተስፋ መንግሥተ ሰማያትን የሚያስገኝ ነው፡፡
 ወዳጄ ሆይ! ቤቱ ቆሽሾ ሳለ ውጫዊ በሩን ብቻ ለማሽቀርቀር ለምን ትጨነቃለኽ? ነፍስኅ በኀጢአት ተዳድፋ ሳለ ሥጋኽን ብቻ ለማስደሰት ለምን ትሮጣለኽ? አስቀድመኽ ቤቱን (ነፍስኽን) ለማስዋብ አትሽቀዳደምምን? አስቀድመኽ ለነፍስኽ የምታስብ ከኾነ ከሰው እጅ ሳይኾን ከክርስቶስ እጅ ሹመት ሽልማት ትቀበላለኽ፡፡ ኹል ጊዜ “የማደርገው ነገር እግዚአብሔር ይከብርበታልን?” ብለኽ አስብ እንጂ እንዲኹ በዘልማድ የምትመላለስ አትኹን ብዬ እመክርኻለኁ፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ሲመክረን፡- “እንግዲኽ የምትበሉ ወይም የምትጠጡ ብትኾኑ ወይም ማናቸውም ነገር ብታደርጉ ኹሉን ለእግዚአብሔር ክብር አድርጉት” ያለንም ስለዚኹ ነውና በአዲሱ ዓመት በድርጊቶቻችን ኹሉ እግዚአብሔርን ለማክበር እንዘጋጅ /1ኛ ቆሮ.10፡31/፤ አዲስ ዓመት ማክበር ማለት ይኼ ነውና፡፡
 ለመኾኑ ለእግዚአብሔር ክብር ሲባል መብላት ወይም መጠጣት ማለት ምንድነው? ድኻውን ወደ ቤታችን ስንጠራው፤ በማዕዳችንም ክርስቶስ አብሮ ሲኖር ለእግዚአብሔር ክብር በላን ወይም ጠጣን ይባላል፡፡
 ሐዋርያው የመከረን ግን በመብላችን ወይም በመጠጣችን ብቻ እግዚአብሔርን እንድናከብረው አይደለም፡፡ ጨምሮም “ማናቸውም ነገር ብታደርጉ ለእግዚአብሔር ክብር አድርጉት” አለን እንጂ፡፡ ስለዚኽ ወደ ሸንጐም ብንሔድ፤ ወደ ቤተ ክርስቲያንም ብንሔድ ለእግዚአብሔር ክብር ልናደርገው ይገባናል፡፡ እነዚኽን ለእግዚአብሔር ክብር ማድረግ የምንችለውስ እንዴት አድርገን ነው? ወደ ቤተ ክርስቲያን፣ ወደ ሥርዓተ ቅዳሴው፣ ወደ ጉባኤው፣ ወደ ሌላውም አግልግሎት ስንሔድ አካሔዳችን እግዚአብሔር የሚከብርበት መኾን አለበት፡፡ እግዚአብሔር የማይከብርባቸው ብዙ ምልልሶች አሉና በአዲሱ ዓመት ወደ ቤተ ክርስቲያን መመላለሳችን ለእግዚአብሔር ክብር መኾን አለበት፡፡
 ከቤት ቁጭ ማለትን የምንመርጥ ከኾነም ለእግዚአብሔር ክብር ልናደርገው ይገባናል፡፡ “ምን ማለት ነው?” ልትል ትችላለኅ፡፡ ከቤት ወጥተን ክፋት ወደ መላበት ሥፍራ፣ ክርክርና ክስ ወደ ሰፈነበት ሸንጐ፣ ዘፈን ስካርና ገቢረ ኀጢአት ወደሚደገስበት ነፍስንም ወደሚያውክ ስፍራ ከመሔድ ተቈጥበን ከቤት ቁጭ ብንል ለእግዚአብሔር ክብር አደረግነው ይባላል፡፡ ስለዚኽ ከቤት ውስጥ ቁጭ ማለትም ወደ ቤተ እግዚአብሔር መሔድም እኩል ለእግዚአብሔር ክብር ማድረግ ይቻለናል ማለት ነው፡፡
 በአዲሱ ዓመት ብናመሰግንም ብንገሥፅም ለእግዚአብሔር ክብር መኾን አለበት፡፡ “ለእግዚአብሔር ክብር ሲባል ማመስገንና መገሠፅ ሲባልስ ምን ማለት ነው?” ብሎ የሚጠይቅ ሰው ሊኖር ይችላል፡፡ እንበልና በመሥሪያ ቤታችን ቁጭ ብለናል፡፡ እጂግ ክፋትን የተመሉ ሰዎችም በፊታችን ይመላለሳሉ፡፡ እነዚኽ ሰዎች በውስጣቸው በትዕቢት፣ በቁጣ፣ እንዲኹም ይኽን በመሳሰሉ ጥገኛ ተሐዋስያን የተመሉ ናቸው፡፡ ነገር ግን እጂግ ውድ የኾኑ አልባሳትን ለብሰዋል፡፡ አከባቢውን የሚለውጡ ውድ የኾኑ ሽቶዎችን ተቀብተዋል፡፡ ይኽን እያየን ሳለ አንድ ሰው መጥቶ፡- “እንዴት የታደለ ሰው እንደኾነ ዐየኸውን? ደስ አይልም?” ሊለን ይችላል፡፡ እንዲኽ የሚላችኁን ሰው ገሥፁት፤ ምክሩት፤ ወይም ዝም በሉት፡፡ ቢቻላችኁ እዘኑለት (አልቁስለት)፡፡ ተግሣፅን ለእግዚአብሔር ክብር ማድረግ ማለትም ይኼ ነው፡፡
 ተግሣፅ ሲባል ሰዎች ከነበሩበት የተሳሳተ አመለካከት ወጥተው ወደ ቀና አስተሳሰብ እንዲመጡ ማድረግ ነው፡፡ ከእንግዲኽ ወዲኽ ክፋትን ሳይኾን ምግባር ትሩፋትን እንዲያደንቁና እነርሱም ራሳቸው ለዚያ የተዘጋጁ እንዲኾኑ ማድረግ ነው፤ ተግሣፅ፡፡
 ከላይ እንደነገርኳችኁ “እንዴት የታደለ ሰው እንደኾነ ዐየኸውን? ደስ አይልም?” ለሚላችኁ ሰው እንዲኽ በሉት፡- “ወዳጄ! ይኽ ሰው ንዑድ ክቡር ነው የምትለኝ ስለምንድነው? እጂግ ግሩምና ድንቅ የኾነች ሠረገላ (በዚኹ በ21ኛው መ/ክ/ዘ. የግል አውሮፕላን ወይም ሃመር መኪና ልንለው እንችላለን!) ስላለው ወይም ብዙ ሠራተኞችን (ብዙ ኩባንያዎችን ልንለው እንችላለን!) ስለሚያስተዳድር፣ እጂግ ውድ ውድ የኾኑ ፋሽን ልብሶችን ስለሚለብስ፣ በየዕለቱም የተለያዩ የመጠጥ ዓይነቶችን ስለሚጠጣና ቅንጡ የኾነ ሕይወትን ስለሚመራ ነውን? እውነት እውነት እልኻለኁ! ለዚኽ ሰውዬስ የዕድሜ ዘመን ዕንባ ያስፈልገዋል ብዬ እነግርኻለኁ፡፡ አንተ ርሱን የምታደንቀው አፍአዊ ነገሩን ብቻ በማየት ነው፡፡ አንተ ርሱን የምታደንቀው ግሩምና ድንቅ የኾነችውን ሠረገላው፣ ወይም ወርቃማው መጋለቢያውን፣ ወይም ልብሱን ዐይተኽ ነው፡፡ ይኽ ግን ለእኔ ምንም ነው፡፡ እስኪ ንገረኝ! ከዚኽ ሰው በላይ ጐስቋላ ሰው ማን አለ? ሠለገላው፣ መጋለቢያው፣ ልብሱ፣ እና ሌላው ሃብቱ እየተደነቀለት ሳለ ርሱ ግን ምንም ሳይመሰገን ቢሞት ከርሱ የባሰ ጐስቋላ ሰው ማን አለ ትለኛለኽ? ከዚኽ ዓለም ወደዚያኛው ዓለም ይዞት የሚሔድ ብዕል (ሃብት) ከሌለው ከዚኽ ሰው በላይ ድኻ ማን አለ? ከአፍአ ሲታይ እጂግ የሚያምርበት ከውስጡ ግን የተለሰነ መቃብር ከኾነው ከዚኽ ሰውዬ በላይ ጐስቋላ ሰው ማን አለ? የእኛ የክርስቲያኖች ትክክለኛ ሃብት ጌጣ ጌጥ፣ ወይም ሠራተኞቻችን ወይም ልብሳችን ወይም ሠረገላዎቻችን አይደሉም፡፡ የእኛ ትክክለኛ ሃብት ምግባር ትሩፋታችን ነው፡፡ የእኛ ሃብት በእግዚአብሔር ማመናችንና መታመናችን ነው፡፡”
 ዳግመኛም እጅግ ድኻ፣ በጓደኞቹ ዘንድ ዕድሜውን በሙሉ እንደ ፋራና ያልዘመነ ሰው የሚቈጠር፥ ግን ደግሞ በምግባር በትሩፋት ያጌጠ ሰውን ብታዩ ይኽ ሰው ንዑድ ክቡር ሰው ነው ብዬ እነግራችኋለኹ፡፡ ምንም በዚኽ ምድር ላይ ያፈራውና ያጠራቀመው ሃብት ባይኖሮውም በሰማያት ዘንድ ድልብ ሃብት አለውና ይኽ ሰው በእውነት ንዑድ ክቡር ነው ብዬ እነግራችኋለኹ፡፡
 ይኽን አመለካከት ስለያዛችኁ ብቻ ጓደኞቻችኁ፡- “ኧረ በሥሉስ ቅዱስ! ይኽ ሰውማ እጅግ የተረገመ ሰው ነው!” ቢልዋችኁ፥ “እንደዉም እንደዚኽ ሰው ንዑድ ክቡር የለም፡፡ ወዳጅነቱ ከኃላፊውና ጠፊው ሃብትና ንብረት ሳይኾን ከእግዚአብሔር ጋር ነውና ንዑድ ክቡር ነው፡፡ ዕድሜውን በሙሉ ሲያከማች የነበረው እንደ እኛ አፍአዊውን ሳይኾን ብልና ዝገት የማያገኘውን ብዕል ነበርና ንዑድ ክቡር ነው፡፡ የዚኹ ሰው ሀብቱ በትዕቢት፣ በቁጣ፣ በዘፈን፣ በስካርና በገቢረ ኀጢአት ያልቆሸሸ ንጽሐ ልቡናው ነውና ንዑድ ክቡር ነው፡፡ እስኪ ንገረኝ! ይኽ ሰው ግሩምና ድንቅ የኾነች ሠረገላ፣ በወርቅ የተሽቆጠቆጠ መጋለቢያ፣ ውድ ውድ የኾኑ አልባሳት ስለሌለው የተጐዳ ይመስልኻልን? ርስት መንግሥተ ሰማያትን ከማግኘት በላይ ሌላ ምን ሃብት አለ ብለኽ ልትነግረኝ ትችላለኽ?” ብላችኁ መልሱላቸው፡፡
 እግዚአብሔር የሚወዳችኁ እናንተም የምትወዱት ሆይ! በአዲሱ ዓመት ብቻ ሳይኾን ዘወትር እንዲኽ እግዚአብሔርን በሚያስከብር መንገድ የምንገሥፅ፣ ወይም የምናመሰግን ከኾነ ሹመት ሽልማታችን ብዙ ነው፡፡
 ልጆቼ! ይኽን ኹሉ የምነግራችኁ እንዲኹ ስሜታችኁን ለማርካት አይደለም፡፡ ይልቁንም በአዲሱ ዓመት ብቻ ሳይኾን በየዕለቱ አስተሳሰባችንን እንዲኽ የምናስተካልለው ከኾነና እኛም እንደዚኹ በምግባር በትሩፋት ለማጌጥ የምንሽቀዳደም ከኾነ ሹመት ሽልማታችን ብዙ የብዙም ብዙ መኾኑን ለማስረዳት ነው፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ክቡር ዳዊት ስለዚኹ ጕዳይ ምን እንደሚል እስኪ አብረን እናድምጠው፡- “በአንደበቱ የማይሸነግል፣ በባልንጀራው ላይ ክፋትን የማያደርግ፣ ሰርቆ ቀምቶ እናት አባቱን የማያሰድብ፣ እኩይ ምግባር በፊቱ የተናቀለት፣ እግዚአብሔርንም የሚፈሩትን የሚያከብር፣ ለባልንጀራው ምሎ የማይከዳ፣ ገንዘቡን በአራጣ የማያበድር፣ ከድኻው መማለጃን የማይቀበል፣ እንዲኽ የሚያደርግ ሰው በመከራ ሥጋ መከራ ነፍስ ለዘለዓለም አይታወክም” /መዝ.15፡3-5/፡፡ ይኽም ማለት ክፋትን በመጸየፍ በጐውንም በማመስገን እግዚአብሔርን የሚያከብር ሰው ነፍሱ ለዘለዓለም አትታወክም ማለት ነው፡፡ ዳግመኛም ይኼ ክቡር ዳዊት በሌላ ሥፍራ እንዲኽ አለ፡- “አቤቱ ባለሟሎችኅ በእኔ ዘንድ እንደምን እጅግ ንዑዳን ክቡራን ናቸው! አስቀድመው ከነበሩት ባለሟሎችኅ ይልቅም እኒኽ ፈጽመው ጸኑ!” /መዝ.139፡17/፡፡
 እግዚአብሔር ያከበረውን ግን አትገሥፁ፡፡ ምክንያቱም እግዚአብሔር በጽድቅ በቅድስና ሕያዋን የኾኑትን ያከብራልና፡፡ በሰው ዓይን እዚኽ ግቡ የማይባሉ ድኾች ቢኾኑም በእግዚአብሔር ዘንድ ንዑዳን ክቡራን ናቸውን እነዚኽን አትገሥፁ፡፡ እግዚአብሔር ያላከበረውን ግን ገሥፁት፡፡ ምንም ያኽል በወርቅ ላይ ቆሞ በወርቅ ላይ ቢተኛም ምግባር ትሩፋትን ሳይይዝ በገቢረ ኀጢአት የፀናውን፣ በሚቀጥለው ዓመትም ይኽን ለማድረግ የሚያቅደውን ሰው ገሥፁት፡፡ በአጭር ቃል ስታመሰግኑም ስትገሥፁም ለእግዚአብሔር ክብር አድርጉት፡፡ አዲስ ዓመትን ማክበር ማለት እንደዚኽ በኹለንተናችን አዲስ ሰው ኾኖ በመዘጋጀት ነውና፡፡
ይቀጥላል…

አዲሱ ዓመት - ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዳስተማረው (ክፍል ፩)



(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ነሐሴ ፳፬ ቀን፣ ፳፻፮ ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
 የምወዳችኁ ልጆቼ! አዲሱ ዓመት የደስታ የሰላምና የጤና እንዲኾንላችኁ ትሻላችሁን? እንኪያስ ገና ከዥመሩ በስካር፣ በዘፈን፣ በገቢረ ኀጢአት ለማሳለፍ አታቅዱ፡፡ የአዲሱ ዓመት የመዠመሪያውን ዕለት ብቻ ሳይኾን እያንዳንዱን ቀን በገቢረ ኀጢአት አትዠምሩት፡፡ እግዚአብሔርን ደስ የሚያሰኝ ሥራ፣ ምግባር ትሩፋት በመሥራት አሐዱ በሉ እንጂ፡፡ ዕለታት ክፉዎች ወይም ጥሩዎች የሚኾኑት በተፈጥሮአቸው እንደዚያ ኾነው አይደለም፡፡ ዕለቱን ክፉ ወይም ደግ እንዲኾን የምናደርገው እኛው ነን፡፡ የአምናው ማግሰኞ ከዘንድሮ ማግሰኞ የተለየ አይደለም፡፡ የተለየ የሚያደርገው የእኛ ብርታት ወይም ስንፍና ብቻ ነው፡፡
የጽድቅን ሥራ የምንሠራበት ከኾነ አዲሱ ቀን ብቻ ሳይኾን አዲሱ ዓመት ለእኛ መልካም ነው፡፡ ኀጢአት የምንሠራበት ከኾነ ግን ቀኑ ብቻ ሳይኾን አዲሱ ዓመትም ክፉና መከራ የመላበት ይኾንብናል፡፡ አዲሱን ዓመት በበጐ ሥራ የምንዠምረው ከኾነ በዓመቱ በምናደርገው ማንኛውም ክንውን ላይ በጐ ተጽዕኖ ያሳድርብናል፡፡ በትግሃ ሌሊት፣ በቀዊም፣ በጾም በጸሎት እንድንበረታ ስንቅ ይኾነናል፡፡ በስካር፣ በዘፈን፣ በኀዘን የምንዠምረው ከኾነ ግን ዓመቱ ሙሉ እንዲኽ የተጐሳቈለ ዓመትን እናሳልፋለን፡፡ ሕይወታችንን በከንቱ እንገፋለን፡፡ ዲያብሎስም ይኽን ጥንቅቅ አድረጐ ስለሚያውቅ ዓመቱን በገቢረ ኀጢአት እንድንዠምረው እየቀሰቀሰ ነው፡፡ ፈቃዳችንን አጥፍቶ፣ ዓይነ ልቡናችንን አሳውሮ በዘፈን፣ በስካር፣ በዋይታ እንድንዠምረው በተለያየ መንገድ እየለፈፈ ነው፡፡
 ሰነፍ ሰው “ቀኑ ክፉ ወይም መልካም የሚኾነው በእኔ ምክንያት አይደለም” ብሎ ያምናል፡፡ እንዲኽ በማመኑም ክፉ ነው ብሎ በሚያስበው ቀን ገቢረ ጽድቅ መሥራት እንደሚቻል አያስብም፡፡ ቢያደርግም ትርጕም እንደሌለው አድርጐ ይቈጥሯል፡፡ የጽድቅ ሥራ ለመሥራት በተመቻቸለት ቀንም ልል ዘሊል ከመኾኑ የተነሣ ምግባር ትሩፋት ለመሥራት አይሽቀዳደምም፡፡ ስንፍናው ምን ዓይነት ጉዳት እንደሚያመጣበት አይረዳም፡፡ ድኅነቱን ሳይፈጽም ዕድሜውን ኹሉ በከንቱ ይገፋል፡፡ እንዲኽ ያለ የሥጋም የነፍስም ጕዳት እንደሚያገኘው ዲያብሎስ ዓይነ ልቡናውን ስለሚያሳውርበት ከአጋንንት ወጥመድ ለመሸሽ ዓቅምን ያጣል፡፡
 ዲያብሎስም ዕለት ዕለት ይኽን እንዳንገነዘብ በተለያየ ማጥመጃ መንገዶች እኛን ለመጣል ይሯሯጣል፡፡ አንዱ መንገድም ስለ ክርስትና ሕይወታችን ግድ እንዳይኖረን ማድረግ ነው፡፡ በዚኽም ክርስቲያናዊ ተፈጥሮአችንን ያሳጣናል፡፡ የእግዚአብሔርን ሥራ በገቢር እንድንሰድብ ያደርገናል፡፡ ነፍሳችንን በቆሸሸ ስፍራ ተወሽቃ እንድትቀር ያደርጋታል፡፡
 የምወዳችኁ ልጆቼ! እኛ ግን ይኽን ልናውቅ ልንረዳ ይገባናል፡፡ በዓለም ላይ ከኀጢአት በቀር ክፉ ነገር እንደሌለ ልናውቅ ልንረዳ ይገባናል፡፡ ከምግባር ከትሩፋት በቀርም መልካም ነገር እንደሌለ ልናውቅ ልንረዳ ይገባናል፡፡ በዚኽም ዘወትር እግዚአብሔርን ደስ አሰኝተን ልንኖር እንዲገባን ማወቅ መረዳት ይገባናል፡፡ መጠጥ ደስታን አያመጣም፤ ደስታን የሚያመጣው ጸሎት ነው፡፡ ደስታን የምናገነኘው ቃለ እግዚአብሔርን ከመስማት እንጂ ከስካር አይደለም፡፡ ስካር የነፍስ መታወክን ያመጣል፤ ቃሉን መስማት ግን ተመስጦን ያመጣል፡፡ ስካር ሁካታን ያመጣል፤ ቃሉን መስማት ግን ሁካታን ያርቃል፡፡ ስካር ዓይነ ልቡና እንዲጨልም ያደርጋል፤ ቃለ እግዚአብሔር ግን የጨለመው ዓይነ ልቡናችን ብሩህ እንዲኾን ያደርጋል፡፡ ስካር የኀጢአት ጓዝ ይዞ ይመጣል፤ ቃለ እግዚአብሔር ግን አዲስ የሚመጡትን ብቻ ሳይኾን የነበሩትንም ያስወግዳል፡፡
 ልጆቼ! የዚኽን ዓለም ደስታ ንቆ ሰማያዊ ደስታን እንደመሻት ያለ ጥበብ ምንም የለም ብዬ እነግራችኋለኹ፡፡ ይኽን ገንዘብ የምናደርግ ከኾነ፣ ለሰማያዊ ሕይታችን ቅድሚያን የምንሰጥ ከኾነ የዚኽ ዓለም ዝባዝንኬ ቢቀርም አይከፋንም፡፡ አንድ ሰው ባለጸጋ ስለኾነ ቅናት አይይዘንም፡፡ ምንም ምድራዊ ሀብት ባይኖረንም ድኾች እንደኾንን አናስብም፡፡ ባለ ጸጋውን ክርስቶስ የያዘ ሰውስ እንዴት ድኻ ይባላል? በዓመት አንድ ጊዜ ብቻ ሳይኾን በየዕለቱ በዓል ማድረግ ማለትም ይኸው ነው፡፡
 እግዚአብሔር የሚወዳችኁ አንድም እግዚአብሔርን የምትወዱት ሆይ! አንድ ክርስቲያን በዓልን ሲያከብር ሳምንትን ወይም ወርን ወይም ዓመትን ጠብቆ መኾን የለበትም፡፡ ከክርስቲያናዊ ተፈጥሮው ጋር እንደሚስማማ አድርጐ ዕለት ዕለት በዓል ሊያደርግ ይገቧል እንጂ፡፡ ከክርስቲያናዊ ተፈጥሮው ጋር የሚስማማ በዓል ማለትስ ምን ማለት ነው? ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ምን እንደሚለን አብረን እናድምጠው፡- “በቅንነትና በእውነት ቂጣ በዓልን እናድርግ እንጂ በአሮጌ እርሾ በክፋትና በግፍ እርሾም አይደለም” /1ኛ ቆሮ.5፡8/፡፡ ንጽሐ ልቡናን ገንዘብ ያደረገ ሰው ዕለት ዕለት በዓልን ያከብራል፡፡ ተስፋ መንግሥተ ሰማያት የተጠበቀለት ነው፡፡ ከሰማያዊው ማዕድና መጠጥ ተካፍሎ ሐሴት ያደርጋል፡፡ በዚኽ ምድር ላይ የሚደረጉ ጊዜያዊ ክንውኖች ስለቀረበት የኾነ ነገር እንደቀረበት አያስብም፤ ርሱ ያገኘው ከዚኽ በእጅጉ የሚልቅ ነውና፡፡ ነፍሱን ከሚያቆሽሹ ገቢረ ኀጢአቶች ራሱን ይጠብቃል፡፡
  በገቢረ ኀጢአት ተሰማርተን ሳለ ሺሕ ጊዜ በዓላትን ብናከብር ግን እንዳከበርን ልንቈጥረው አይገባንም፡፡ ያከበርነው የበዓል ቀን (በዓል ማለት ደስታ ማለት ነው) ሳይኾን የኀዘን ቀን ነውና፡፡ ነፍሴ በኀጢአት ቀንበር ተይዛ በድቅድቅ ጨለማ ውስጥ ሳለች የደስታን ቀን ባከብር ለእኔ ምን ጥቅም ያመጣልኛል?
 እግዚአብሔር የሚወዳችኁ እናንተም የምትወዱት ልጆቼ! አዲሱ ዓመት የእውነት አዲስ ዓመት እንዲኾንላችኁ ካሻችኁ ነፍሳችኁን ከኀጢአት ቀንበር አላቋት እንጂ ድጋሜ በኀጢአት ሸክም አትጫኗት፡፡ አሮጌው ዓመት እንዳለቀ ስታዩ እግዚአብሔርን አመስግኑት፡፡ ወደሌላ ዘመን አሸጋግሯቸዋልና እግዚአብሔርን አመስግኑት፡፡ ልቡናችኁንም ውቀሱት፡፡ በዕሜአችኁ ስንት ጊዜ እያለፈ እንደኾነ እያሰባችኁም ራሳችኁን እንዲኽ ብላችኁ ጠይቁት፡- “ቀናት እየሮጡ ነው፡፡ ዓመታቱም እየነጐዱ ነው፡፡ የዕድሜዬ መንገድም እየተጋመሰ ነው፡፡ ታድያ ምን በጐ ምግባር ያዝኩ? ከዚኽ ምድር የማልፍበት ቀን እየቀረበ ነው፡፡ ታድያ ምን የጽድቅ ሥራ ሠራኹ? በዚኽ ዕድሜዬ መሥራት የነበረብኝ ምግባር ትሩፋት ዕድሜዬ ሲገፋ ማድረግ አልችልም፡፡ ታድያ ዕድሜዬ ሲገፋ ማድረግ የማልችላቸውም የጽድቅ ሥራዎች (ፆም፣ ጸሎት፣ ስግደት፣ አገልግሎት፣… ዕድሜ ሲገፋ ይከብዳሉና) እንዳቅሜ እያደረግኩ ነውን?”
ተወዳጆች ሆይ! አዲስ ዓመት ሲመጣ እነዚኽን ነገሮች በጥንቃቄ ልናስብባቸው ይገባናል፡፡ ይኽን እያደረግንም ስለቀጣዩ ዓመት እናስብ፡፡ ይኽን የምናደርግ ከኾነ “ቀኖቻቸውም በከንቱ አለቁ፤ ዓመቶቻቸውም በችኰላ” አይባልብንም /መዝ.78፡3/፡፡ ዕለት ዕለት በዓልን እናድርግ ብዬ የገለጥኩላችኹም ይኸው ነው፡፡ የእኛ በዓል ዘወትር መኾን ይገባዋል፡፡ የክርስቲያኖች በዓል በዓመታትና በቀናት ብቻ መወሰን የለበትም፡፡ ቤተ ክርስቲያንም በሳምንት፣ በወር፣ በዓመት የሚከበሩ በዓላት እንዲኖሩ ማድረጓ ዘወትር ከዚኹ ልንርቅ እንደማይገባ ማሳሰቧ እንጂ ሌላ አይደለምና፡፡ ይኽን በዓል በየዕለቱ ማድረግም ለኹሉም ይቻላል፤ ለድኻውም ለባለጸጋውም ይቻላል፡፡ በዓልን ለማድረግ (የጽድቅ ሥራን ሠርቶ ሐሴት ለማድረግ) የሚያስፈልገው ቅን ልቡና እንጂ ገንዘብ አይደለምና፡፡ ወዳጄ ሆይ! ገንዘብ የለኽምን? ፈሪሐ እግዚአብሔርን ገንዘብ አድርግ፡፡ ፈሪሐ እግዚአብሔርን ገንዘብ የምታደርግ ከኾነ ገንዘብ ካላቸው በላይ ባለጠጋ ነኽ፡፡ “እንዴት?” ትለኝ ይኾናል፡፡ እኔም እንዲኽ ብዬ እመልስልሃለኹ፡- የእነዚያ (የባለጠጐቹ) ገንዘብ ያልቃል፡፡ ያንተ ግን ብል አይበላውም፡፡ ጊዜ አይለውጠዉም፡፡ አያልቅም፡፡ ወደ ሰማያት፣ ወደ ሰማየ ሰማያት፣ ወደ ምድር፣ ወደ አየራት፣ ወደ እንስሳቱ ዓይነት፣ ብዙ የብዙ ብዙ ወደሚኾኑት ዕፅዋት፣ ወደ ደቂቀ አዳም በጠቅላላው፣ ወደ መላዕክት፣ ወደ መላዕክት አለቆች፣ ወደ ኀይላት ተመልከት፡፡ እነዚኽ ኹሉ የአምላክኽ ፍጥረቶች ናቸው፡፡ የእነዚኽን አምላክና መጋቢ ባርያ መኾን ድኻ መኾን አይደለምና ድኻ አይደለኽም ብዬ እነግርኻለኹ፡፡
 ተወዳጆች ሆይ! ቀናትን ቈጥሮ በዓል ማድረግ የክርስቲያን ግብር አይደለም፤ የአሕዛብ ግብር እንጂ፡፡ እንዴት? የክርስቲያኖች ተፈጥሮ በቀንና በወር የተገደበ አይደለምና፡፡ አገራችን ሰማይ ነው፡፡ ግብራችን ሰማያዊ ነው፡፡ ኅብረታችንም ከሰማያውያን መላዕክት ጋር ነው፡፡ በዚያ መዓልት ለሌሊት ስፍራውን አይለቅም፡፡ ሌሊትም በተራው ለመዓልት አይለቅም፡፡ እዚያ ኹሌ መዓልት ነው፡፡ እዚያ ኹል ጊዜ ብርሃን ነው፡፡ ስለዚኽ “ከክርስቶስ ጋር ከተነሣችኁ ክርስቶስ በእግዚአብሔር ቀኝ ተቀምጦ ባለበት በላይ ያለውን እሹ” እንደተባልን ኹል ጊዜ ማሰብ ያለብን ይኽንን ነው /ቈላስ.3፡1/፡፡ ክርስቲያናዊ ተፈጥሮአችን ከዚኽ ምድራዊ አቈጣጠር በላይ ነው፡፡ በንጽሕና በቅድስና እየኖርን ዘወትር በዓልን የምናከብር ከኾነም የዚኹ ዓለም ሌሊት ለእኛ ሌሊት አይደለም፤ መዓልት ነው እንጂ፡፡ ዘመናችንን በሙሉ በገቢረ ኀጢአት፣ በስካር፣ በዘፈን የምናሳልፈው ከኾነ ግን መዓልቱ ለእኛ መዓልት አይደለም፤ ሌሊት ነው እንጂ፡፡ ፀሐይዋ ብትወጣም ልቡናችን ገና በድቅድቅ ጨለማ ውስጥ ይኖራልና ቀን እንደወጣ አይቈጠርም፡፡
ይቀጥላል…

                                   በአውሮጳ   የካህናት አንድነት ማኅበር ሊቋቋም መሆኑ ታወቀ በ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከመላዋ አውሮጳ   የተውጣጡ ካህናት፡” የ...