2014 ኦክቶበር 1, ረቡዕ

ማዕተብ: የክርስትናችን ዓርማ የነፍሳችን ሰንደቅ ዓላማ



  • ሦስት ቀለማት ያላቸው ክሮች የአብ የወልድ የመንፈስ ቅዱስ ምሳሌ ሲኾኑ አንድ ላይ መፈተላቸው ወይም አንድ መኾናቸው ቅድስት ሥላሴ ማለት አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ በመለኰት በህልውና አንድ አምላክ መኾናቸውን ያመለክታል፡፡ ጥቁሩ፡- ክርስቲያን ስለ ሃይማኖት የሚቀበለው መከራ የሚሸከመው መስቀል፣ ቀዩ፡- በሰማዕትነት ደም የማፍሰስ ሲኾን ቢጫው ደግሞ የክርስቲያን ተስፋ የሃይማኖት ምልክት ነው፡፡
  • ክርስቲያን ለክርስቶስ ታማኝ በመኾኑ በነፍሱ ሞግዚት በቄሱ እጅ ከሕፃንነቱ ጀምሮ የድኅነቱ ምልክት በሚኾን አንገቱ በማዕተበ ክርስትና ይታሰራል፡፡ ማዕተብ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዕለተ ዓርብ ስለ እኛ ቤዛ ለመኾን የብረት ሀብል /የብረት ገመድ/ በአንገቱ ታስሮ በአይሁድ መጎተቱን ስለሚያስታውሰን ለታማኝነታችንና ለክርስቲያንነታችን ምልክትነቱ ማረጋገጫ ስለኾነ አናፍርበትም፡፡
  • አንዲት ሀገር ነፃና ሉዓላዊ መኾኗ የሚታወቀው ወይም ራሷን የቻለች መንግሥት ያላት ከባዕድ ቀንበር ቅኝ ግዛት ነፃ የወጣች መኾኗ በቀዳሚነት የሚለየው በባንዴራዋ ምልክትነት እንደኾነ እንደዚኹም አንድ ክርስቲያን በክርስቶስ አምኖ በጥምቀት ከዲያብሎስ ቁራኝነት ነፃ መውጣቱ፣ ነፃነት ያለው አማኝ መኾኑ የሚታወቀው በማተቡ ምልክት ነው፡፡
  • አንዳንድ ሰዎች የማዕተብ ሥርዐትን ለመቃወምና ዘመናውያን መስለው ለመታየት ‹‹እምነት በልብ ነው›› ይላሉ፤ ተሳስተዋል! ሃይማኖት የልብ ብቻ አይደለም፤ የጠቅላላው ሕዋሳት ኹሉ ናት፡፡
  • አጋንንት የለከፏቸው ሰዎች ማተብና መስቀል አይወዱም፡፡ የሰፈረባቸው ርኩስ መንፈስ ማተብ እንዲበጥሱ መስቀል እንዲጥሉ ያደርጋቸዋል፡፡ ማተብ በሰይጣን ዘንድ ከተጠላ በአጋንንት ላለመለከፍ የማዕተቡ መኖር ይጠቅማል ማለት ነው፡፡
* * *
Ethiopian girl wearing a cross shaped tattoo on her foreheadየኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ክርስቲያኖች በአንገታቸው ላይ ክር ያስራሉ፤ ለሕፃኖቻቸውም ክርስትና ሲነሡ ክር ያስሩላቸዋል፡፡ በሕፃናቱም ኾነ በዐዋቂዎቹ ክርስቲያኖች አንገት ላይ የሚታሰረው ክር በግዕዝ ማዕተብ በአማርኛ ማተብ ይባላል፡፡ ቃሉ ወጣው ዐተበ ካለው ግዕዛዊ ግስ ነው፡፡ ዐተበ ፍቺው አመለከተ፣ ባረከ ማለት ነው፤ ማዕተብ ፍቺው ከዚኽ ይወጣል፡፡ ምልክት ማለት ነው፡፡
ለተጠመቁ ክርስቲያኖች የክር ማተብ ለሃይማኖት ምልክትነት ወይም መታወቂያ ከመኾኑ በፊት፣ በብሉይ ኪዳን ዘመን የሃይማኖት አባቶች ከጣዖት አምላኪዎች ተለይተው የሚታወቁበት ምልክት ነበራቸው፡፡ ስለ ታላቁ የሃይማኖት አባት ስለ ጻድቁ አብርሃም የሃይማኖት ማኅተም(ምልክት) ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ይላል፡- ‹‹ሳይገረዝም በነበረው እምነት ያገኘው የጽድቅ ማኅተም የኾነ የመገረዝን ምልክት ተቀበለ፡፡›› (ሮሜ ፪÷፲፩፤ ዘፍጥ.፲፯÷፱ – ፲፬)
በሥርዐተ ኦሪት ብኵርና ከጥንት ጀምሮ ለእግዚአብሔር የተለየ ገንዘብ ኾኖ ስለሚቆጠር ብኵርና ላለው ኹሉ የአባት በረከት ከሌሎች ይልቅ በይበልጥ ምርቃት ዕጥፍ ድርብ ኾኖ ስለሚሰጠው ብኵርና ይወደዳል፤ ይፈቀራል፡፡ ብኵርና ማቃለል ዋጋ የሌለው ጸጸትን ያስከትል ነበር፡፡ ብኵርና ለዘመነ ሐዲስ ክርስትና ምሳሌ እንደኾነ ይታመናል፡፡ ክርስትናውን ንቆ አቃሎ ዓለምን መስሎ የሚኖር ሰው፣ ለጊዜያዊ መብል ፍለጋ ብኵርናውን በሸጠው በያዕቆብ ወንድም ዔሳው ተመስሏል፤ ‹‹. . .ስለ አንድ መብል በኵርነቱን እንደ ሸጠ እንደ ዔሳው ለዚኽ ዓለም የሚመች ሰው እንዳይኾን ተጠንቀቁ፡፡ ከዚያ በኋላ እንኳ በረከቱን ሊወርስ በወደደ ጊዜ እንደተጣለ ታውቃላችኹና በእንባ ተግቶ ምንም ቢፈልገው ለንስሐ ስፍራ አላገኘምና፡፡›› (ዕብ.፲፪÷፲፮፤ ዘፍጥ. ፳፭÷፳፱ – ፴፬፤ ፳፯÷፴ – ፵)
ብኵርና ለክርስትና ምሳሌ መኾኑ ከላይ ተገልጧል፡፡ ትዕማር ከይሁዳ መንትያ ልጆችን ፀንሳ በምትወልድበት ጊዜ በኵሩ እጆቹን ሲያወጣ አዋላጅቱ ቀይ ፈትል ለምልክት አስራበታለች፡፡ ይህ ምሳሌያዊ ድርጊት በሐዲስ ኪዳን ሲተረጎም ከትዕማር የተወለደው በኵሩ ዛራ ለክርስቲያን ምሳሌ ሲኾን ቀዩ ፈትል ለክርስትናው ምልክት፤ ለማዕተብ ምሳሌ ኾኗል፡፡
አዋላጅቱ ለአጥማቂው ቄስ ምሳሌ ናት፡፡ ትዕማር የቤተ ክርስቲያን ምሳሌ ስትኾን በኋላ የመጣው ፋሬስ በኵሩን ጥሶ ቀድሞ መወለዱና ከቀይ ፈትል አልባ መኾኑ በምሳሌያዊ ትንቢትነት፣ ከቤተ ክርስቲያን በጥምቀት ከተወለዱ በኋላ ክርስትናቸውንና ጥምቀታቸውን ክደው የእውነተኞቹ ክርስቲያኖች ተቃዋሚዎች በመኾን ፊት ከተፈጠረ ጆሮ እንደ ቀንድ ብቅ ያሉ የመናፍቃንና የኢጥሙቃን (ኢአማንያን) ምሳሌ እንደኾኑ ያስረዳል፡፡ (ማቴ.፩÷፫፤ ዘፍጥ.፴፰÷ ፳፮ – ፴)
በዛራ ልማድ ጌታችን ከድንግል ማርያም በተወለደ ጊዜ እመቤታችን አውራ ጣቱን በክር አስራዋለች፡፡ ቅዱስ ገብርኤል ለኖሎት ተገልጦ ምልክቱን እንዲህ ሲል ነግሯቸዋል፡- ‹‹ወከመዝ ትእምርቱ ለክሙ ትረክቡ ሕፃነ እሱረ መንኮብያቲኹ፤ ምልክቱ ይህ ነው፡፡ ሕፃኑ አውራ ጣቱን ታስሮ ታገኙታላችኹ፡፡›› (ሉቃ.፪÷፲፪) እመቤታችን አውራ ጣቱን በክር እንዳሰረችው ‹‹ወወለደት ወልደ ዘበኵራ ወአሰርቶ መንኮብያቲኹ፤ የበኵር ልጅዋን ወለደች፤ አውራ ጣቱን አሰረችው፡፡›› ( ሉቃ.፪÷፯፤ የግእዝና አማርኛ ነጠላ ትርጉም አማርኛ ሒዲስ ኪዳን ይመልከቱ)
ድንግል እመቤታችን አውራ ጣት ማሰሯ ለክርስቲያኖች ማዕተብ ማሰር አብነት ኾኗል፡፡ ጣቱን ማሰሯ ያለምክንያት አልነበረም፡፡ ይኸውም፡- ፩ኛ/ሕፃን ስለኾነ እንዲያጸናው፤ ፪ኛ/ጣቱን ባይታሰር ምትሀት ነው፤ ሰው አልኾነም ለሚሉ መናፍቃን ለክሕደታቸው ምክንያት ባገኙ ነበርና ምክንያት ለማሳጣት፤ ፫ኛ/ቀደም ብለን እንደገለጽነው ልማዳችንን አስቀረብን እንዳይሉ በዛራ ልማድ፤ ፬ኛ/ዮሴፍና ኒቆዲሞስ በዕለተ ዓርብ ከመስቀል አውርደው እንዲኽ አድርገው ይገንዙሃል ለሰው ቤዛ ለመኾን ልትታሰር መጣኽን፣ ስትል ነው በማለት መምህራነ ቤተ ክርስቲያን በአንድምታ ትርጓሜያቸው ያትታሉ፡፡
* * *
በኦርቶዶክሳውያን ክርስቲያኖች ዘንድ ክርስቲያን የኾነ ኹሉ ማተብ የማሰር ልምድ የጀመረው በሃይማኖተ አበው በድርሳነ ያዕቆብ እንደተገለጸው፣ ከልደተ ክርስቶስ በኋላ በእስክንድርያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በአምስተኛው ምእት ዓመት ያስተምር በነበረው በሊቀ ጳጳሱ በያዕቆብ ዘእልበረዳኢ ዘመነ ስብከት ነበር፡፡
ያዕቆብ ዘእልበረዳኢ የሶርያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አባት ነው፡፡ መምህሩ ቅዱስ ዲዮስቆሮስ የእስክንድርያው ሊቀ ጳጳሳት ስለ ተዋሕዶ ሃይማኖት ሲመሰክር በመለካውያን (ልዮናውያንና ንስጥሮሳውያን) ግፊትና ተቃውሞ መከራ ሲቀበል ጽሕሙ ተነጭቶ ጥርሶቹ ረግፈው ስለነበር የተነጨ ጽሕሙን የረገፉ ጥርሶቹን በመሐረም ቋጥሮ ‹‹ዝንቱ ፍሬ ሃይማኖቱ ለእግዚአብሔር፤ ለእግዚአብሔር የምናቀርብለት የሃይማኖት ፍሬ ይህ ነው›› በማለት ለእስክንድርያ በያዕቆብ ዘእልበረዳኢ እጅ ልኮላታል፡፡ እርሱም ስለ ሃይማኖት በደሴተ ጋግራ ታስሮ ሰማዕት ኾኗል፡፡
ደቀ መዝሙሩ ቅዱስ ያዕቆብ አልባሌ መስሎ በሶርያ ብቻ ሳይኾን በእስክንድርያ የሴት ቀሚስ ሳይቀር ለብሶ ሲያስተምር ንስጥሮሳውያን ከጉባኤው እየገቡ ስላስቸገሩት ኦርቶዶክሳውያንን ከመናፍቃን ለመለየት ከእግዚአብሔር ባገኘው ምልክት ጥቁር ቀይ ቢጫ ክሮች አንድ ላይ ፈትሎ በአንገታቸው ላይ ያስርላቸው ጀመር፡፡ ሌሊት ሌሊት ሲያስተምርና ሲጸልይ የቅዱስ ዲዮስቆሮስ ጥርሶቹ እንደ ፋና ያበሩለት ነበር፡፡ ይህም በተኣምራት የተፈጸመ ነው፡፡
tattoos on neck , forehead and gums , wearing a silver cross and a white garment decorated with crosses , Lalibelaሦስት ቀለማት ያላቸው ክሮች የአብ የወልድ የመንፈስ ቅዱስ ምሳሌ ሲኾኑ አንድ ላይ መፈተላቸው ወይም አንድ መኾናቸው ቅድስት ሥላሴ ማለት አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ በመለኰት በህልውና አንድ አምላክ መኾናቸውን ያመለክታል፡፡ ጥቁሩ፡- ክርስቲያን ስለ ሃይማኖት የሚቀበለው መከራ የሚሸከመው መስቀል፣ ቀዩ፡- በሰማዕትነት ደም የማፍሰስ ሲኾን ቢጫው ደግሞ የክርስቲያን ተስፋ የሃይማኖት ምልክት ነው፡፡
ቆይቶ ግን በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ሕፃናት ክርስትና ሲነሡ፣ ኢአማንያን አምነው ሲጠመቁ ቀይ፣ ነጭና ሰማያዊ ፈትሎች በአንድ ላይ ተገምደው መታሰር ጀመረ፤ ትርጓሜውም የሦስቱ አንድ ላይ መገመድ የሥላሴን አንድነት ሦስትነት የሚያመለክት ምሳሌ ነው፡፡ ይኽንንም ኢትዮጵያዊው ሊቅ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ ጠቅለል ባለ መልኩ ሲያስረዱ፡- ሥላሴ ማዕተበ ብርሃን ኃይለ ሃይማኖቶሙ ለክርስቲያን፤ ሥላሴ ለክርስቲያን ኹሉ የሃይማኖታቸው ጉልበት መታወቂያ የብርሃን ማዕተብ (ምልክት) ናቸው፤ ብለዋል፡፡
ቀለሞቹ ደግሞ ቀይ፡- ክርስቶስ ደሙን አፍስሶ አድኖናል፤ ስለ ስሙም በሰማዕትነት ደማችንን ማፍሰስ ይገባናል የማለት፤ ነጩ፡- የጥምቀት በጥምቀትም የሚገኝ ስርየተ ኃጢአት፤ ሰማያዊ፡- በጸጋ ልጅነት አግኝቻለኹ፤ ሰማያዊ አባት አለኝ፤ ሰማያዊ ርስት መንግሥተ ሰማይ ይቆየኛል፤ ስለዚኽም በሰማያዊ ግብር ጸንቼ መኖር በሰማያዊት ሕግ ሕገ ክርስቶስ ወንጌል ተመርቼ መኖር ይገባኛል እንደማለት ነው፡፡
Ethiopia, with a cross branded on her foreheadበኢትዮጵያ ክርስትና የገባው በዘመነ ሐዋርያት በመጀመርያው መቶ ክፍለ ዘመን ነው፡፡ ይኹንና የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን በመንበረ ጵጵስና ከሌሎች ጥንታውያን አብያተ ክርስቲያን ጋራ የዕኩልነት ማዕርግ ያገኘችው በአራተኛው ምእት ዓመት በቅዱስ ፍሬምናጦስ አባ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን እንደኾነ ተረጋግጧል፡፡ በዚኽ ዘመን አቡነ ሰላማ ሕዝቡን አጥምቀው ወደ ክርስትና ሲመልሱ ለክርስትናቸው ምልክት ከግንባራቸው ላይ እየበጡ መስቀለኛ ምልክት ያደርጉላቸው እንደነበር ይተረካል፡፡
ከአቡነ ሰላማ የጀመረው ማዕተብ የማሰር ትውፊት በዘጠኙ ቅዱሳን ዘመንም እየተስፋፋ ሔዶ በቤተ ክርስቲያን ክርስትና ለሚነሡ ኹሉ ሥርዐተ እምነታችን ኾኖ ቆይቷል፡፡ እስከ አኹንም በተለይ በሰሜናውያን ዘንድ በመበጣትም ኾነ በንቅሳት ለክርስትናቸው ምልክት መስቀል ከግንባራቸው ማድረግ የጸና ልምድ ኾኖ ይታያል፡፡
* * *
ማዕተብ ያላሰረ ኦርቶዶክሳዊ የአባቶቹን የተቀደሰ ክርስቲያናዊ ትውፊት እንዳልተቀበለ ያስቆጥረዋል፡፡ በምሳሌያዊ አነጋገርም ሃይማኖት አልባውን ማለትም ክርስቲያን ያልኾነውን ማተብ የለሽ፣ ያልተጠመቀ፣ አረሚ ይሉታል፡፡ ክርስቲያን በማተቡ መነኵሴ በቆቡ እንዲታወቅ ማተብ አልባ መኾን ደግሞ ክርስቲያን ይኹን ያልተጠመቀ ለመለየት ያስቸግራል፡፡ በመለዮዋቸው ሌሎች እንዲታወቁ ክርስቲያን በማተቡ ክርስትናውን ሲያሳውቅ ኖሯል፡፡
በተለመደው አነጋገር÷ እገሌ ማተብ አለው፤ ባለማተብ ነው ሲባል እገሌ ታማኝ ክርስቲያን ነው፤ እውነተኛ ሐቀኛnigel-pavitt--ethiopia ነው የማለትን ትርጉም ይሰጣል፡፡ ባለማተቢቱ ሲባል ከአሚን ባሏ የረጋች ከባሏ ሌላ የማታውቅ እውነተኛ ታማኝ ክርስቲያን የማለት ፍች አለው፡፡ በዚኽ ምክንያት በሕዝበ ክርስቲያኑ ዘንድ የማተብ ትርጉም ከፍተኛ ቁምነገርን አዝሎ ይገኛል፡፡
አንዲት ሀገር ነፃና ሉዓላዊ መኾኗ የሚታወቀው ወይም ራሷን የቻለች መንግሥት ያላት ከባዕድ ቀንበር ቅኝ ግዛት ነፃ የወጣች መኾኗ በቀዳሚነት የሚለየው በባንዴራዋ ምልክትነት እንደኾነ እንደዚኹም አንድ ክርስቲያን በክርስቶስ አምኖ በጥምቀት ከዲያብሎስ ቁራኝነት ነፃ መውጣቱ፣ ነፃነት ያለው አማኝ መኾኑ የሚታወቀው በማተቡ ምልክት ነው፡፡ ለደብዳቤ፣ ለጽሑፍ ዓርማ ማኅተም ፊርማ እንደሚያስፈልገው ያም ለመተማመኛ እንደሚያገለግል ጥቅሙ ታውቆ ይሠራበታል፡፡
በዚኹ አንፃር የክርስቲያን ማዕተቡም ሃይማኖታዊ ጠቀሜታ ይኖረዋል፡፡ በቅድሚያ፣ በልቡ የሚያምነው ሃይማኖት ክርስትናን ሳያፍርበት በአንገቱ ባለው ማተብ መግለጹ በክርስትናው አለማፈሩን፣ ክርስትናኽን ካድ ማተብኽን በጥስ የሚል ዐላዊ ቢመጣና ያን ምልክት አይቶ ቢሠዋው የሰማዕትነት ክብር ያገኘበታል፡፡ ያም ባይኾን በማተቡ ምልክትነት በመናፍቃንና በኢአማንያን የሚቀበለው ዘለፋ ስለ ክርስቶስ መስቀል እንደተሸከመ ያስቆጥረዋል፡፡
ኹለተኛው፣ ያለጥርጥር ክርስቲያን መኾኑ ታውቆለት ከክርስቲያን ወገኖች ጋራ ተሳትፎውን ማከናወን ይችላል፡፡ ማተብ ከሌለው ግን ክርስቲያን ይኹን ያልተጠመቀ ስለማይታወቅ በሃይማኖት ዜጎች ዘንድ በቀላሉ ተቀባይነት ማግኘት አይችልም፡፡ ሦስተኛ፣ ከማይታወቅበት አገር እንደወጣ በበሽታም ይኹን በአደጋ ሕይወቱ ቢያልፍ በማተቡ መታወቂያነት የክርስቲያን ሥርዐት ተፈጽሞለት በቤተ ክርስቲያን ሊቀበር ይችላል፡፡
አራተኛ፣ ማተብና መስቀል ያለው ክርስቲያን በውኃ ዋና ወይም በበረሓ ጎዳና በውኃ የሚኖሩ ወይም በበረሓ ያሉ አጋንንት በቀላሉ ሊለክፉት አይችሉም፡፡ ይህም በየጠበሉ ስፍራ በተኣምራት ተረጋግጧል፡፡ አጋንንት የለከፏቸው ሰዎች ማተብና መስቀል አይወዱም፡፡ የሰፈረባቸው ርኩስ መንፈስ ማተብ እንዲበጥሱ መስቀል እንዲጥሉ ያደርጋቸዋል፡፡ ማተብ በሰይጣን ዘንድ ከተጠላ በአጋንንት ላለመለከፍ የማዕተቡ መኖር ይጠቅማል ማለት ነው፡፡
አንዳንድ ሰዎች የማዕተብ ሥርዐትን ለመቃወምና ዘመናውያን መስለው ለመታየት ‹‹እምነት በልብ ነው›› ይላሉ፤ ተሳስተዋል! ሃይማኖት የልብ ብቻ አይደለም፤ የጠቅላላው ሕዋሳት ኹሉ ናት፡፡ እግዚአብሔርን ስንወደውና ስናመልከው በልባችን ብቻ ሳይኾን በአፋችንም በአንገታችንም በጠቅላላው ሰብአዊ ተፈጥሯችን ኹሉ መኾን ይገባዋል፤ ምክንያቱም እግዚአብሔር የጠቅላላው ሰውነታችን አምላክና ፈጣሪ ስለኾነ ነው፡፡ ‹‹ስለዚኽ በሰው ፊት የሚመሰክርልኝ ኹሉ እኔ ደግሞ በሰማያት ባለው በአባቴ ፊት እመሰክርለታለኹ፤ በሰው ፊትም የሚክደኝን ኹሉ እኔ ደግሞ በሰማያት ባለው በአባቴ ፊት እክደዋለኹ፡፡›› (ማቴ.፲÷፴፪÷፴፫)
በዚኽ ቃለ ወንጌል መሠረት በኢአማንያን ዘንድ ክርስቲያን መኾናችንን የምንገልጸው በልባችን ብቻ ሳይኾን በቃላችንና በሥራችንም ጭምር ነው፡፡ በአንገታችንስ እንዳንመሰክርለት ማን ያግደናል? በአንገታችን ባለው ማዕተብም ለእግዚአብሔር እንመሰክራለን፡፡ የስሙን ምልክት በአንገታችን እናኖራለን፤ አናፍርበትም!! የክርስቶስን ሞትና ትንሣኤ በጥምቀታችን እንደምንመሰክር የጥምቀታችንንም ዓርማ በማተባችን እናረጋግጣለን፡፡ (ሮሜ ፲፮÷፲፫፤ ኢዩኤ. ፪÷፴፪፤ ሮሜ ፮÷፩-፭፤ ማቴ.፭÷፲፩-፲፪፤ ፩ኛጴጥ.፫÷፳፩-፳፪፤ ፬÷፲፪-፲፮)
ከወንጌል የተለየች ትምህርት እንዳንቀበል ሐዋርያት አስጠንቅቀውናል፡፡ መላእክት በራእይ ገልጸውልናል፤ ከእግዚአብሔር አግኝቻለኹ ብለው የሚመጡትን መናፍስት እንድንመረምራቸው በቅዱሳት መጻሕፍት ታዝዘናል፡፡ ማተብ የማሰር የተቀደሰ ክርስቲያናዊ ትውፊታችንን የሚቃወሙ በክርስቶስና ሞትና ትንሣኤ የማያምኑ ተረፈ አይሁድ ስለኾኑ ተቃውሞውን ዋጋ ሳንሰጠው ማተባችንን እናጠብቃለን፡፡ ‹እንደ ውሻ በአንገታችኹ ገመድ አስራችኹ› ተብለን በመነቀፋችንም እንደሰትበታለን እንጂ አንሠቀቅም፡፡ ውሻ ለጌታው ታማኝ ነው፡፡ ሌሎች የተለከፉ ያበዱ ዘላን ውሾች እንዳይለክፉትና ከሞት እንዳያደርሱት ወይም ወንበዴዎች በሥጋ መርዝ ቀብተው ለሥጋው ሲሣሣ እንዳይገድሉት ትንሽ ጎጆ ሠርቶለት ቢያስረው ለውሻው ሕይወት አስፈላጊ እንደኾነ በኹሉም የታወቀ ነው፡፡
an Ethiopian diptych icon, illustrating scenes from the life of Christ, mostly his Passion በዚኹ አንፃር ክርስቲያን ለክርስቶስ ታማኝ በመኾኑ በነፍሱ ሞግዚት በቄሱ እጅ ከሕፃንነቱ ጀምሮ የድኅነቱ ምልክት በሚኾን አንገቱ በማዕተበ ክርስትና ይታሰራል፡፡ ማዕተብ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዕለተ ዓርብ ስለ እኛ ቤዛ ለመኾን የብረት ሀብል /የብረት ገመድ/ በአንገቱ ታስሮ በአይሁድ መጎተቱን ስለሚያስታውሰን ለታማኝነታችንና ለክርስቲያንነታችን ምልክትነቱ ማረጋገጫ ስለኾነ አናፍርበትም፡፡ በድርሳነ ሰንበት ቅዱስ ያዕቆብ ዘሥሩግ የውሻን ታማኝነት ለክርስቲያን ታማኝነት ምሳሌ አድርጎ ገልጾታል – ‹‹ከልብሰ የአምር እግዚኡ፤ ውሻ ጌታውን ያውቃል››፡፡ ጌታችንም በቅዱስ ወንጌል በውሻ የተመሰለችውን ከነናዊቷን ሴት ስለ ታማኝነቷ አድንቋታል፤ ልጅዋንም ፈውሶላታል፡፡(ማቴ.፲፭÷፳፩-፳፰)
ማዕተብን ከሚቃወሙ አንዳንዶች ‹‹ጽዳት ያጎድላል›› በማለት ያመካኛሉ፡፡ በርግጥ የጠንቋይ ክታብ የቃልቻ ግሣንግሥ መሰብሰቢያ ካደረጉት የሥጋ ንጽሕናን ብቻ ሳይኾን የሚያጎድለው የነፍስንም ጽዳት የሚያጎድል መኾኑ ዕውቅ ነው፡፡ ማተብ እና መስቀሉ ግን ጽዳት ያጎደለበት ጊዜ ስለሌለ ሰበብ አያዋጣም፡፡ ስለዚኽ የክርስትናችንን ዓርማ የነፍሳችንን ሰንደቅ ዓላማ በነፃነት ስናውለበልብ ለመኖር ያብቃን፡፡ አሜን፡፡
ምንጭ፡- መለከት መጽሔት፤ ፩ኛ ዓመት ቁጥር ፮፤ ሚያዝያ ፲፱፻፹፭ ዓ.ም.
About these ads

2014 ሴፕቴምበር 23, ማክሰኞ

ነገረ መስቀል

  መስከረም ፲፮ ቀን፥ ፳፻፮ ዓ.ም.)፡-                                                                         በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሓዱ አምላክ አሜን!!!
በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ. ሥርዓት መሠረት ከመስከረም ፲ እስከ መስከረም ፳፭ ያለው ሳምንት “ዘመነ መስቀል” ይባላል፡፡ በዚህ ሳምንት ስለ መስቀል ክብር ይነገራል፤ መዝሙረ መስቀልም ይዘመራል፡፡ መስቀል ማለት “ሰቀለ” ከሚል የግእዝ ግሥ የተገኘ ሲኾን ትርጓሜውም “የተመሳቀለ፣ መስቀለኛ” ማለት ነው፡፡
 መቅድመ ወንጌል እንደሚነግረን፥ አዳም የማይበላውን በልቶ ከእግዚአብሔር አንድነት ከተለየ በኋላ አብዝቶ ያለቅስ ነበር፡፡ በኀጢአቱ ከማዘንና ከማልቀስ በቀርም ሌላ ግዳጅ አልነበረውም፡፡ በልብ መታሰቡ በቃል መነገሩ ከፍ ከፍ ይበልና ብዙ መጨነቁን፥ ጸዋትወ መከራዉን ያየው ቸሩ እግዚአብሔር ግን አዘነለት፡፡ “እቤዝወከ በመስቀልየ ወበሞትየ - በመስቀሌና በሞቴ አድንኀለኹ” ብሎም ቃል ኪዳን ገባለት /ኪዳነ አዳም ፫፡፫-፮፣ ዘፍ.፫፡፲፭/፡፡ መጽሐፈ ቀሌሜንጦስ እንደሚነግረንም ከ፭ ቀን ተኵል በኋላ እንደሚያድነው ተስፋ ሰጠው፤ ከ፭ ሺሕ ፭ መቶ ዓመታት በኋላ ሲል ነው፡፡ “ነገረ መስቀል” የምንለውም ይኸው ለአዳም የተሰጠው ተስፋ ነው፡፡

 የታሪክ ድርሳናት እንደሚያስረዱት የተለያዩ ሀገራት ወንጀለኞችን በመስቀል ይቀጡ ነበር፡፡ ሰውን በመስቀል ሰቅሎ መቅጣት የተዠመረውም በፋርሳውያን ዘንድ ነው፡፡ ፋርሳውያን አንድ ወንጀለኛ ነው ያሉትን ሰው ስለምን በመስቀል እንደሚቀጡት ሲገልፁ “ኦዝሙድ” ከተባለው “የምድር አምላክ” ጋር ያያዙታል፡፡ እንደነርሱ አባባል ወንጀለኛው ሰው ቅጣቱን በምድር የተቀበለ እንደኾነ አምላካቸው ይረክሳል፡፡ በመኾኑም አምላካቸው እንዳይረክስ ወንጀለኛው ከመሬት ከፍ ብሎ በመስቀል ይሰቀል ነበር፡፡
 ከፋርሳውያን በተጨማሪ በግብጽ፣ በፊንቄ፣ በግሪክ፣ በሮም፣ በአሶር፣ በካርቴጅና በሕንድ ወንጀለኛ ነው ያሉትን ሰው በመስቀል ሰቅለው ይቀጡ ነበር፡፡ በተለይ ሮማውያን የራሳቸው ዜጋ ያልኾነ “ወንጀለኛን” ይቀጡ የነበረው በመስቀል ነበር፡፡ የራሳቸውን ዜጋ ግን ቶሎ እንዲሞት ከማሰብ አንጻር አንቀው ይገድሉት ነበር፡፡ ለዚህም ጥሩ ማስረጃ የሚኾኑን ቅዱስ ጴጥሮስና ቅዱስ ጳውሎስ ናቸው፡፡
የመስቀል ዓይነቶች
 እነዚህ ከላይ የጠቀስናቸው ማኅበረ ሰቦች “ወንጀለኛ ነው” የሚሉትን ሰው የሚቀጡበት የተለያዩ ዓይነት መስቀሎች ነበርዋቸው፡፡ የታወቁትን ለመጥቀስ ያህልም፡-
v ያልተመሳቀለ መስቀል ( I )
v የእንግሊዘኛው ኤክስ ፊደል ዓይነት መስቀል ( X )፡፡ ይኸውም በተለምዶ የሐዋርያው የቅዱስ እንድርያስ መስቀል ተብሎ ይታወቃል፡፡
v የእንግሊዘኛው ቲ ፊደል ዓይነት መስቀል ( T )፡፡ ይኸውም በተለምዶ የቅዱስ እንጦንስ መስቀል ይባላል፡፡
v የግእዝ ተ ፊደል ዓይነት መስቀል ( † )፡፡ ይኸውም የጌታችን መስቀል የሚባለው ነው፡፡
የመስቀል አተካከል
 እነዚህ ከላይ የጠቀስናቸው ማኅበረ ሰቦች ወንጀለኛ ነው ያሉትን ሰው ለመስቀል መስቀሉን በሦስት መንገድ ይተክሉት እንደነበር የታሪክ ድርሳናት ይናገራሉ፡፡ እነርሱም፡-
  ፩ኛ) መዠመርያ መስቀል ይተከላል፡፡ ቀጥሎም የተፈረደበት ሰው በመሰላል ያወጡትና በሚስማር ከግንዱ ጋር ይመቱታል፡፡
  ፪ኛ) ኹለት ግንድ በአንጻር ይተክላሉ፡፡ በግንዶቹም ሠረገላ ይጋደማል፡፡ በሠረገላው ላይም ባለ ሸምቀቆ ገመድ ይቋጠራል፡፡ በመጨረሻም ወንጀለኛው በዚያ ገመድ ታንቆ ይሞታል፡፡
  ፫ኛ) መዠመሪያ መስቀሉ መሬት ላይ ይጋደማል፡፡ በመቀጠል ወንጀለኛው ተጋድሞ በመስቀሉ ላይ ይቸነከራል፡፡ በመጨረሻም መስቀሉ ከወንጀለኛው ጋር ይቆማል፡፡ ጌታችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለዓለም ኹሉ ቤዛ በመኾን የተሰቀለው በዚሁ መንገድ ነበር፡፡
መስቀል በብሉይ ኪዳን
 ከአዳም ዠምሮ እስከ ፸ ዓ.ም. ያለውን ዜና አይሁድ የጻፈው ዮሴፍ ወልደ ኮርዮን እንደሚነግረን በአይሁድ ማኅበረ ሰብ ዘንድም የተለመደ ነበር፤ መስቀል /ዮሴፍ ወ.ኮ. ፲፯፡፲/፡፡ አይሁዳውያን ርጉም፤ ውጉዝ ነው ያሉትን ሰው በመስቀል ይቀጡ ነበር፡፡ መጽሐፍ ቅዱሳችንን ስንመለከት አይሁድ አንድ ጥፋተኛ ነው ያሉትን ሰው በተለያየ መንገድ ይቀጡት እንደነበር እንረዳለን፡፡ ለምሳሌ በሰይፍ /ዘጸ.፳፩፡፲፬/፣ በእሳት /ዘሌ.፳፡፲፬/፣ በውግረተ እብን /ዘሌ.፳፡፳፯/፣ በማነቅ /ዘኅ.፳፭፡፬/ መጥቀስ ይቻላል፡፡ ከዚህ በኋላ ይህ ርጉም፤ ውጉዝ ነው በማለት፥ ከላይ በጠቀስነው መንገድ የገደሉትን ሰው ለመቀጣጫ ሬሳዉን በግንድ ይሰቅሉት ነበር /ዘዳ.፳፩፡፳፪-፳፫/፡፡
 ወንጀለኛውን በመስቀል መቅጣት የፈለጉ እንደኾነ ግን ከመስቀላቸው በፊት ይገርፉታል፡፡ መስቀያውን ተሸክሞ እየተንገላታ ከከተማ ውጪ ወዳለ መስቀያ ቦታ ይወሰዳል፡፡ ሕማሙንም ይረሣ ዘንድ የኢየሩሳሌም ሴቶች ሥቃዩን ለማደንዘዝ መጠጥ ያጠጡታል፡፡ ከዚያም በመስቀሉ ላይ እጆቹንና እግሮቹን ይቸነከራል ወይም በገመድ ይታሠራል፡፡ ከራሱ በላይም ወንጀሉ ይጻፋል፡፡ የተሰቀለው ሰው የሚሞተው ደሙን በማፍሰስ ሳይኾን በልቡ ድካም በመኾኑ ብዙ ጊዜ ነፍሱ ከሥጋው የምትለየው በኹለተኛው ወይም በሦስተኛው ቀን ነው፡፡ ቶሎ መግደል የፈለጉ እንደኾነ ግን እግሮቹን ይሰብሩታል፡፡
  ክብር ምስጋና ለስም አጠራሩ ይኹንና ምንም በደል ያልተገኘበት ጌታችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ለመግደል የተጠቀሙበት መንገድ መስቀል ነበር፡፡ በመኾኑም አስቀድመው ገርፈዉታል፤ መስቀሉን አሸክመው አንገላተዉታል፤ በሰፍነግ ሆምጣጣ ነገር አጠጥተዉታል፡፡ እጆቹንና እግሮቹን ቸንክረዉታል፡፡ ጐኑን በጦር ወግተዉታል፡፡ “ወንጀለኛ ነው” ሲሉም “ኢየሱስ ናዝራዊ ንጉሠ አይሁድ” የሚል ጽሑፍ ከራሱ በላይ ጽፈው ለጥፈዉበታል፡፡ ነገር ግን ትንቢቱ ይፈጸም ዘንድ አንድም በፈቃዱ ቶሎ ስለሞተ እግሩን አልሰበሩትም፡፡

 በዘመነ ብሉይ ስለ ነገረ መስቀል ብዙ ትንቢት ተነግሯል፤ ብዙ ኅብረ አምሳልም ተመስጥሯል፡፡ ከትንቢቶቹ ጥቂቶቹን ለመጥቀስ ያህል፡-
Ø “ከቀስት ፊት ያመልጡ ዘንድ፥ ለሚፈሩህ ምልክትን ሰጠሃቸው” /መዝ.፶፱፡፬/። ይኸውም ምእመናን በክርስቶስ አምነው ከማየ ሥራዌ ከማየ ድምሳሴ፣ ከኀጢአት፣ ከአምልኮ ጣዖት አምልጠው (ድነው) አጋንንትን፣ መናፍቃንን፣ ፍትወታት እኩያትን በትእምርተ መስቀል ድል እንደሚያደርጉ ሲናገር ነው፡፡
Ø “ከኃሢሦን ተቈርጦ በጐልጐታ የሚተከለው የወይን ሐረግ መድኀኒቴ ነው” /የመኃ.፭፡፩ አንድምታውን ይመልከቱ/፡፡
 ስለ ነገረ መስቀል በኅበረ አምሳል ከተመሰጠሩ ጥቂቶቹን ለመጥቀስ ያህልም፡-
v አዳም ለጊዜው ከእርሷ እንዳይበላ የተከለከላት ዕፀ ሕይወት /ዘፍ.፫፡፳፪/፣
v ኖኅ ከነቤተ ሰቡ ከማየ ድምሳሴ የዳነባት የመርከብ ዕንጨት /ዘፍ.፮፡፲፬-፳፪/፣
v በይሥሐቅ ፈንታ የሚሠዋውን በግ ታስሮ የተገኘባት ዕፀ ሳቤቅ /ዘፍ.፳፪፡፲፫-፲፱/፣
v ሰዋስወ ያዕቆብ /ዘፍ.፴፡፴፯/፣
v የይሁዳ በትረ መንግሥት /ዘፍ.፵፱፡፲/፣
v በትረ ፋሲካ /ዘጸ.፲፪፡፲፩/፣
v ባሕረ ኤርትራን የከፈለች በትረ ሙሴ /ዘጸ.፲፬፡፲፮/፣
v የማራ ውኃ የጣፈጠበት ዕንጨት /ዘጸ.፲፭፡፳፪-፳፯/፣
v የሙሴ አቋቋም /ዘጸ.፲፯፡፲፩-፲፯/፣
v የእሥራኤላውያን መስቀለኛ የጉዞ ሰልፍ /ዘኅ.፪፡፫-፳፮/፣
v ሙሴ በበረሃ የሰቀለው የአርዌ ብርት /ዘኅ.፳፩፡፰-፱/፣
v የኤልሣዕ ዕንጨት /፪ኛ ነገ.፮፡፩-፯/፣
v የሰሎሞን ዕፀ ሕይወት /ምሳ.፫፡፲፰/፣
v የሕዝቅኤል ትእምርተ ድኅነት /ሕዝ.፱፡፬-፮/፣
v ወቦ ዘተርፈ፡፡
መስቀል በሐዲስ ኪዳን
 ክብር ምስጋና ለስም አጠራሩ ይኹንና ከጌታችንና ከመድኀኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ሞት በኋላ ግን ቅዱስ ሥጋው የተቈረሰበት ክቡር ደሙም የፈሰሰበት ስለኾነ፥ መስቀል ትእምርተ መርገም መኾኑ ቀርቶ የክብርና የበረከት መገለጫ ኾነ፤ ትእምርተ ኀፍረት መኾኑ ቀርቶ የነጻነት ምልክት ኾነ፤ የድኅነትና የሕይወት አርማ ኾነ፡፡ ለዚህም ነው በዘወትር ጸሎታችን “ዓለምን ኹሉ ለማዳን ሲል ኢየሱስ ክርስቶስ ለተሰቀለበት መስቀል እንሰግዳለን፡፡ መስቀል ኃይላችን ነው፡፡ መስቀል ቤዛችን ነው፡፡ መስቀል የነፍሳችን መድኀኒት ነው፡፡ አይሁድ ይክዱታል፤ እኛ ግን እናምነዋለን፡፡ ያመንንበት እኛም በመስቀሉ እንድናለን፤ ድነናልም” እያልን የምናከብረው፡፡ በዕፅ ምክንያት ሞት ወደ ዓለም ገባ፤ በዕፀ መስቀል ምክንያትም ሕይወት ወደ ዓለም ገባ፡፡ በዕፅ ምክንያት የሞት ቀንበር በላያችን ላይ ተጫነ፤ በዕፀ መስቀል ምክንያትም ይኸው ቀንበር ተሰበረ፡፡ ዲያብሎስ በዕፅ ምክንያት አዳምን ከነልጆቹ ድል አደረጋቸው፤ ጌታችንም ዲያብሎስን በዕፀ መስቀል ራስ ራሱን ቀጠቀጠው፡፡ ዲያብሎስ እኛን ሲቀጣበት በነበረው ዕፅ፥ ዛሬ ግን እኛ ድል የምናደርገው ኾነናል፡፡ ስለዚህ መስቀል ኃይላችን ነው፤ መስቀል ቤዛችን ነው፡፡ ከጥንት የነበሩ አባቶችም ይህን የመሰለ ነገር በድርሳናቶቻቸው ጽፈውልናል፡፡ ለምሳሌ ያህልም፡
·        “በተግባራችን ኹሉ፣ በምንገባበትና በምንወጣበት ጊዜ፣ ልብሳችንን ከመልበሳችን በፊት፣ ከመታጠባችን በፊት፣ በቀንና በማታ ወደ ምግብ በምንቀርብበት ጊዜ፣ መብራት በምናበራበት ጊዜ፣ መጽሐፍ ቅዱስን ለማንበብ በምንዠምርበትና በምንፈጽምበት ጊዜ፣ በዕለታዊ ሕይወታችን መደበኛ ሥራችንን በምንዠምርበት ጊዜ በትእምርተ መስቀል ግንባራችንን እናማትባለን፡፡”  /ከ፩፻፰-፪፻፳፭ ዓ.ም. የነበረው ጠርጡለስ/፡፡
·        “ይህን መስቀል በልቡናችሁ ቅረጹት፤ የነፍሳችን መዳኛ የኾነው ይህንን መስቀል በአንገታችሁ እሰሩት፡፡ ዓለምን ኹሉ የፈወሰ እና ያጣፈጠ፤ ስሕተትን ኹሉ ያስወገደ፤ እውነትን የመለሰ፤ ምድርን ገነት ያደረገ፤ ሰዎችን መላእክት ያደረገ ይህ መስቀል ነው፡፡ በዚሁ መስቀል ምክንያት ዲያብሎስ አስፈሪነቱ ቀርቷል፤ ሞት ወደ እንቅልፍ ተቀይሯል፤ በእኛ ላይ ነግሦ የነበረው የሞት ፍርድ ተወግዶ ከእግራችን በታች ተጥሏል፡፡” /ከ፫፻፵-፯፬፻፯ ዓ.ም. የነበረው ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ/፡፡
ስለማይነገር ስጦታው እግዚአብሔር ይመስገን!!!
የመስቀል በዓል ጥንተ ነገር
  የመስቀል በዓል በየዓመቱ መስከረም ፲፯ በታላቅ ሥነ ሥርዓት ይከበራል፡፡ ይኸው በዓል የቤተ ክርስቲያኒቱ ብቻ ሳይኾኑ ብሔራዊ በዓልም ኾኖ ይከበራል፡፡ የመስቀል በዓል የሚከበርበት ምክንያት ምን እንደኾነ የታሪክ ድርሳናትን ስንመረምር እንደሚከተለው ነው፡፡ አይሁድ ከጌታችን ስቅለት በኋላ በዕፀ መስቀሉ ይደረግ የነበረውን የተለያየ ተአምራት ሲያዩ ዓይናቸው ቀላ፤ ቅንአት ያዛቸው፡፡ ሰዎች በተአምራቱ ተስበው ወደ አሚን እንዳይመጡም አንድ ተንኰል አሰቡ፡፡ በመኾኑም በኢየሩሳሌም አቅራቢያ ቀበሩት፡፡ በቦታዉም በአዋጅ የከተማው ኹሉ ጥራጊና ቆሻሻ እንዲደፋበት በማድረግ ተራራ እስኪያክል ድረስ ከመሩበት፡፡ በቀደመው በደላቸው ንስሐ መግባት ሲገባቸው በበደል ላይ በደል ይጨምሩ ነበር፡፡ ኾኖም የሰው ሐሳብ ጊዜአዊ ነውና ጊዜው ሲደርስ መስቀሉ የሚወጣበት ቀን ደረሰ፡፡ በመኾኑም ጊዜ ገቢር ለእግዚአብሔር እንዲል ፫፻ ዓመታት አለፈና መፍቀሬ ሃይማኖት ቈስጦንጢኖስ ነገሠ፡፡ እግዚአብሔርም በቈስጠንጢኖስ ልብ ፍቅረ መስቀልን አሳደረ፡፡ በእናቱ በንግሥት ዕሌኒ አማካኝነትም በ፫፻፳፯ ዓ.ም. ገደማ ተገኘ፡፡
 ንግሥት ዕሌኒ መስቀሉን ለማግኘት አባ መቃርስና አረጋዊው ኪራኮስ እንዲሁም ቅዱስ ሚካኤል ባመላካቷት መሠረት ጸሎትና ምህላ አድርሳ ዕጣን የተጨመረበት ደመራን ያስደመረችው መስከረም ፲፮ ነበር፡፡ የዕጣኑ ጢስ ወደላይ ወጥቶ ተመልሶ መስቀሉ የተቀበረበትን ቦታ ስላመለከታትም ቁፋሮ የዠመረችው መስከረም ፲፯ ነበር፡፡ በመጨረሻም መጋቢት ፲ መስቀሉ ተገኘ፡፡ ዛሬ ደመራን ደምረን መስከረም ፲፮ን የምናከብረው ቅድስት ዕሌኒ በኢየሩሳሌም ያሳነጸቻቸውን አብያተ ክርስቲያናት የተባረኩበት ቀን ስለኾ ነው፡፡ መስከረም ፲፯ ደግሞ መስቀሉ ገብቶ ቅዳሴ ቤቱን ያከበረችበት ዕለት ነው፡፡
ምንም እንኳን መስቀሉ የተገኘው መጋቢት ዐሥር ቢኾንም ወርኃቱ ወርኃ ፆም ስለኾነና በዐቢይ ፆም ደግሞ ተድላና ደስታ ማድረግ በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን የተከለከለ ስለኾነ የመስቀሉ በዓል በአበው ውሳኔ ቁፋሮው በተዠመረበትና ቅዳሴ ቤቱ በተከበረበት መስከረም ፲፯ እንዲኾን ተደርጓል፡፡

 የመስቀሉ መገኘት ለዓለም ሕዝብ ኹሉ ደስታ ቢኾንም በሌላው ዓለም ደብዛው ጠፍቶ በሃገራችን ግን ሃይማኖታዊና ባህላዊ ሥርዓቱን እንደጠበቀ አሁንም ይገኛል፡፡ ይህም ብቻ አይደለም፤ በአጼ ዳዊት ዘመነ መንግሥት ወደ ኢትዮጵያ የመጣው ግማደ መስቀል እስከ አሁን አለ፤ የመስቀል ቅርጽ ባላት በግሸን ደብረ ከርቤ ቅድስት ማርያም ገዳም፡፡
መስቀል በኢትዮጵያ
v መስቀልና ኢትዮጵያ የማይነጣጠሉ ወዳጆች ናቸው፡፡
v  ሀገሪቱ ምዕራፈ መስቀል ልጆቿም የመስቀል ፍሬዎች ናቸው፡፡ በመኾኑም መስቀል በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን እጅግ ታላቅ ክብር አለው፡፡
v ከእመቤታችን ቀጥሎ በቤተ ክርስቲያን ስሙ የሚነሣው ቅዱስ መስቀሉ ነው፡፡ የመዠመሪያው የሥላሴ ስም ነው፡፡
v ቤተ ክርስቲያን ያለመስቀል አይተከልም፡፡
v ቅዱስ ዳዊት “ወደ ማደሪያዎቹ እንገባለን፤ እግሮቹ በሚቆሙበት ስፍራ እንሰግዳለን” ለቅዱስ መስቀል የጸጋ ስግደት ይቀርብለታል /መዝ.፻፴፩፡፯/፡፡
v ካህናቶቿ ኹሉ መስቀል ይይዛሉ፤ በቅዱስ መስቀሉ ይባረካሉ፤ ይባርካሉም፡፡
v የቤተ ክርስቲያኒቱ ልጆች በሙሉ መስቀል ይሳለማሉ፤ በትእምርተ መስቀል ያማትባሉ፤ በመስቀል ይባረካሉ፡፡
v ሰው ያልበላውን አያገሳም፡፡ በመኾኑም ምእመናን በመስቀሉ ላይ በተከፈለው ዋጋ ተገዝተዋልና በአንገታቸው ያስሩታል፡፡ በግንባራቸው፣ በደረታቸው፣ በክንዳቸው ይነቀሱታል፡፡ በአልባሳታቸው ይሥሉታል፤ ይሸለሙታል፡፡
v እንደ ዛሬው አያድርገውና ነገሥታቱ በገንዘባቸው፣ በበትረ መንግሥታቸው፣ በፈረስ ልጓማቸው ትእምርተ መስቀል ነበረ፡፡ ጌጥ አይደለም፤ ሃይማኖታዊ አርማ እንጂ፡፡ የአጼ ይሥሓቅ የደብዳቤያቸው ርእስ መስቀል ነበር፡፡ በላዩ ላይም ኢየሱስ የሚል ጽሑፍ ነበረበት፡፡
v የቤተ ክርስቲያኒቱ ንዋያተ ቅዱሳት አብዛኛዎቹ ባለመስቀል ናቸው፡፡
v መጋቢት ፲ና መስከረም ፲፯ ቀን የሚጠመቁ ልጆቿ (ቤተ ክርስቲያን) ገብረ መስቀል፣ ወልደ መስቀል፣ ብርሃነ መስቀል፣ ኃይለ መስቀል፣ ዐምደ መስቀል፣ ወለተ መስቀል፣ መስቀል ክብራ፣ መስቀል ኃይላ፣ መስቀል ሞገሳ፣ ወቦ ዘተርፈ እያለች ስመ ክርስትና ትሰጣቸዋለች፡፡
v ወሩ በገባ በ፲ የመስቀል በዓል ይታሰባል፡፡
v ከመስከረም ፲፮ እስከ መስከረም ፳፭ ዘመነ መስቀል ተብሎ ስለ ነገረ መስቀል ይነገራል፤ መዝሙረ መስቀልም ይዘመራል፡፡
  አንዳንድ ሰዎች ቤተ ክርስቲያኒቱ ለዕንጨት አምልኮትን የምታቀርብ የሚመስላቸው አሉ፤ ድሮም ነበሩ፡፡ “ለዕንጨት ትሰግዳላችሁን? በዓልስ ታደርጋላችሁን? ለሚሉን ኹሉ እኛም “አዎ! ዕፀ መስቀሉ የክርስቶስ ደም አልቀደሰውምን? ስለዚህ እኛ ለመስቀል የጸጋ ስግደት እንሰግድለታለን” ብለን ከቅዱስ ያሬድ ጋር እንመልስላቸዋለን /ድጓ ዘመስቀል/፡፡
በአጠቃላይ መስቀል በትንቢት የተነገረ፣ በኅብረ አምሳል የተመሰጠረ፣ በክርስቶስ ደም የከበረ፣ ቤዛነትንና ድኅነትን ስለተፈጸመበት እናከብረዋለን፡፡ “መስቀል ኃይላችን፣ መጠጊያችን፣ ሞገሳችን ነው” እያልን እንዘምረለታለን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር!!!

መጽሐፈ ጤፉት ለኅትመት በቃች


አትም ኢሜይል
መስከረም 12 ቀን 2007 ዓ.ም.
መምህር ሳሙኤል ተስፋዬ
a tefut 2007 1የጌታችን የመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል ወደ ኢትዮጵያ መጥቶ ግሸን ደብረ ከርቤ መቀመጡንና ሌሎችንም ታሪኮች ያያዘው መጽሐፈ ጤፉት በግሸን ደብረ ከርቤ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ሰበካ ጉባኤ ጽ/ቤት አማካይነት ከግእዝ ወደ አማርኛ ተተረጉማ ለኅትመት በቃች፡፡

መጸሐፉ በሰባት ምዕራፎች ተከፍሎ የቀረበ ሲሆን፤ የመጀመሪያው ምዕራፍ በዐፄ አምደ ጽዮን ዘመነ መንግሥት የነበረውን የግብጻውያንና የኢትዮጵያውያንን ግንኙነት የሚገልጽ ነው፡፡ ሁለተኛው ምዕራፍ በዐፄ ዳዊት አማካይነት ቅዱስ መስቀሉ ከግብጽ ወደ ኢትዮጵያ መጥቶ በዐፄ ዳዊት ግዛት ስለመቀመጡ ይናገራል፡፡

ሦስተኛው ምዕራፍ ስለ ዐፄ ዘርዓ ያዕቆብና ቅዱስ መስቀሉን ወደ መስቀለኛው የአምባሰል ተራራ በግሸን ደብረ ከርቤ ስለማስቀመጣቸው በስፋት ይገልጻል፡፡ ዐራተኛው ምዕራፍ ከቅዱስ መስቀሉና መስቀሉ ስለተቀመጠባት የግሸን ደብረ ከርቤ ቅድስት ማርያም ደብር ክብር ጋር ተያይዞ በንጉሥ ዘርዓ ያዕቆብ የተጻፉት ደብዳቤዎችን አካትቷል፡፡

አምስተኛውና ስድስተኛው ምዕራፎች ግሸን ደብረ ከርቤ ጌታችን በተሰቀለበት በቅዱስ መስቀሉ መክበሩንና ለቦታው ስለተሰጠው ቃል ኪዳን ይዳስሳል፡፡ ሰባተኛውና የመጨረሻው ምዕራፍ መስቀሉ በክብር የተቀመጠበትን የግሸን ደብረ ከርቤ አምባና የአካባቢው ሹማምንት ስለተሰጣቸው ትእዛዛትና ሌሎችንም መረጃዎች ያብራራል፡፡

ሊቀ ሊቃውንት ተክለ ማርቆስ ብርሃኑ የግሸን ደብረ ከርቤ ቅድስት ማርያም ደብር አስተዳዳሪ ስለ መጽሐፉ መታተም ሲገልጹ “መጽሐፈ ጤፉት ለበርካታ ዓመታት የቤተክርስቲያናችንን የታሪክ፣የቀኖና፣ የሥርዐትና ሌሎችም ሰነድ ይዛ በክብር ተጠብቃ የቆየችና በየዓመቱ በውስጧ የዘችው ቃልኪዳን እየተነበበ የኖረ ሲሆን አሁን ታትሞ ለምዕመናን እንዲደርስ መደረጉ የሀገርንና የቤተክርስቲያን ታሪክ አውቀን ሥርዐቱንና ቃል ኪዳኑን ጠብቀን ለቦታው የሚገባውን ክብር እንድንሰጥ ያስችላል፡፡” ብለዋል፡፡

a tefut 2007 2መጽሐፈ ጤፉት በ15ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በዐፄ ዘርዓ ያዕቆብ አማካይነት እንደተጻፈና በየዓመቱ፤ በተለይም በመስከረም 21 እና መጋቢት 10 ቀን የመስቀሉ አመጣጥና በግሸን ደብረ ከርቤ ስለተሰጠው ቃል ኪዳን በመተርጎም ለምእመናን ይሰማል፡፡

መጽሐፈ ጤፉትን ማግኘት የሚፈልጉ በግሸን ደብረ ከርቤና በአዲስ አበባ በ0911238610፣ 0911616880 በመደወል ማግኘት እንደሚቻል ከመጽሐፉ የኅትመት አስተባባሪዎች ለመረዳት ተችሏል፡፡

2014 ሴፕቴምበር 8, ሰኞ

የኢትዮጵያ የዘመን አቆጣጠር ከአውሮፓውያን ጋር ያለው ልዩነት መንስኤ እና ትክክለኛ መሰረቱ

 


የዘመን መስፈሪያዎች 
እግዚአብሔር «ቀንና ሌሊትን ይለዩ ዘንድ ፣ ለዕለታት፣ ለዘመናትና ለዓመታት ምልክት ይሆኑ ዘንድ» / ዘፍ.1. 14- 15/ የፈጠራቸውን የፀሐይንና የጨረቃን እንቅስቃሴ መሠረት ያደረጉት መስፈሪያዎች ናቸው፡፡ እነዚህም፤

ሀ. ዕለት-
አንድ ዕለት አንድ ቀንን /የብርሃን ክፍለ ጊዜን / እና አንድ ሌሊትን /የጨለማ ክፍለ ጊዜን/ ያካተተ ፀሐይ አንድ ጊዜ ከወጣች በኋላ ተመልሳ እስክትወጣ ድረስ ያለውን ጊዜ የያዘ ነው፡፡ በአሁኑ ዕውቀታችን አንድ ዕለት ምድር በራሷ ዛቢያ አንድ ጊዜ የምትሸከረከርበት ጊዜ ነው፡፡

ለ. ውርኅ-
ወርኅ ማለት በግእዝ ጨረቃ ማለት ነው፡፡ አንድ ወርኅ የሚባለው ጊዜ ሙሉ ጨረቃ ከወጣች በኋላ ድጋሚ እስከምትወጣ ድረስ ያለው ጊዜ ነው፡፡ በአሁኑ ዕውቀታችን / በጥንቱም ጨምሮ/ ይህ ጨረቃ መሬትን አንድ ጊዜ ዙራ ለመጨረስ የሚፈጅባት ጊዜ ነው፡፡ አንድ ወር ሃያ   ዘጠኝ ተኩል ዕለታትን ይፈጃል፡፡
   
ሐ. ዓመት-
አንድ ዓመት ማለት መሬት አንድ ጊዜ በፀሐይ ዙሪያ ለመዞር የሚፈጅባት ጊዜ ነው፡፡ ይህም 365 ከ1/4 / ሦስት መቶ ስድሳ አምስት ቀን ከሩብ/ ዕለታት ይፈጃል፡፡ይህ ከመታወቁ በፊትም ግን የዓመት ጽንሰ ሓሳብ ነበር፡፡ ፕሮፊሰር ጌታቸው ኃይሌ የፅንሰ ሐሳቡን አመጣጥ እንዲህ ያስረዳሉ፡፡
ሰዎች ርዝመታቸው እኩል የሆኑ ሁለት  ሻማዎችን ሠሩና ልክ ፀሐይ ስትወጣ /ቀኑ ሲያልቅና ሌሊቱ ሲጀምር/  አንዱን ሻማ አበሩት፡፡ልክ ፀሐይ ስትወጣ እሱን አጠፋና ሌላውን / ሁለተኛውን/ ሻማ አበሩት፤ ጧት ፀሐይ እንደገና ስትወጣ / ሌሊቱ አልቆ ሌላ ቀን ሲጀምር/ ሻማውን አጠፉት፡፡ አሁን እንግዲህ ከየሻማዎቹ /ከሁለቱ ሻማዎች/ ምን ያህል እንደተቃጠለላቸው ሲያስተያዩት ከሁለቱ ሻማዎች የተቃጠለው እኩል አለመሆኑን ተመለከቱ በዚህም የቀኑና የሌሊቱ ርዝማኔ እኩል አለመሆኑን ተረዱ፡፡

ቀደም ብለውም የቀኑና የሌሊቱ ርዝማኔ በተለያዩ ወቅቶች የተለያየ መሆኑን ልብ ብለው ነበርና ይህንን ሙከራቸውን ሲቀጥሉ በቀኑና በሌሊቱ ርዘማኔ / በሚቃጠለው የሻማዎቹ መጠን/ መካከል ያለው ልዩነት ከወቅት ወቅት የተለያየ እንደሆነ ተመለከቱ ይህን ሙከራቸውን ሲቀጥሉ ግን በየ182 /ተኩል/ ዕለቱ ቀኑና ሌሊቱ እኩል የሚሆኑባቸው ሁለት ዕለታት በዓመት ውስጥ እንዳሉ ተገነዘቡ፡፡ እነዚህ ዕለታት አንዱ የሙቀት ወራት ከመጀመሩ በፊት የሌላው ደግሞ የቅዝቃዜው ወራት ከመጀመሩ በፊት የሚመጡ ናቸው፡፡ ስለዚህ የቀኑና የሌሊቱ ርዝመት አንድ ጊዜ እኩል ሁኖ ደግሞ በዚያው ወቅት እኩል እስከሚሆን ድረስ ያለውን ጊዜ ማለትም / 182 ተኩል + 182 = 365/ ዕለት አንድ ዓመት አሉት፡፡ አሁን ባለን ግንዛቤ ምድር በራሷ ዛቢያ እንደተሽከረከረች በፀሐይ ዙሪያ ትዞራለች፡፡ ምድር በፀሐይ ዙሪያ የምትዞረው ወደ ጎን 23 ተኩል ዲግሪ ያህል አጋድላ ነው፡፡ ይህ የቀንና የሌሊት ርዝመት መለያየትም የሚከሰተው በዚህ ማጋደል ምክንያት ነው፡፡
እንግዲህ በአጠቃላይ ዋናዎቹ የጊዜ / የዘመን/ መስፊሪያዎች ዕለት፣ ወር እና ዓመት ናቸው፡፡ ሦስትቱም ተመላላሽ ክስተቶችን / ለምሳሌ የፀሐይን መውጣት/ መሠረት ያደረጉ ናቸው፡፡ እነዚሀ ተመላላሽ ክስተቶች አንድ ጊዜ ከተከሰቱ በኋላ ደግመው እስኪከሰቱ የሚፈጁት ዘመን ወይም ጊዜ  ዓውድ ይባላል፡፡ ዓውድ ማለት ዙሪያ፣ ክብ፣ እንደ ቀለበት ዙሮ የሚገጥም ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ዓውድ ማለት ክስተቶቹ አንድ ጊዜ ከተከሰቱ በኋላ ደግመው እስኪመጡ ድረስ ያለው ጊዜ ማለት ነው፡፡
በዚህ መሠረት ከላይ ያየናቸው ሦስት መስፈሪያዎች / ዕለት፣ ወርኀ፣ ዓመት/ ዓዕዋዳት / ዓውዶች/ የሚወጡበት ጊዜ ዓውደ ዕለት፣ ዓውደ ወርኀ፣ ዓውደ ዓመት ይባላሉ፡፡
መጀመሪያ ላይ ሰዎች እነዚህን ሦስቱን መስፈሪያዎች /ዓዕዋዳት/ /በተለይም ቀንና እና ወርን/ ለየብቻቸው ይጠቀሙባቸው ነበር፡፡ ከዚህን ያህል ቀን፣ ከዚህን ያህል ወር በኋላ /በፊት/ እያሉ ጊዜን ይለኩ ነበር፡፡
እነዚህ ሦስቱን በቅንብር /በቅንጅት/ ለመጠቀም ሲፈለግ ግን የዘመን አቆጣጠር ስሌት ያስፈልጋል፡፡ ምክንያቱም አንድ ወር 29 ከግማሽ ቀን ነው፡፡
እንዲሁ እንዳለ ለመቁጠር ቢፈለግ የመጀመሪያው ወር ጠዋት ላይ ቢጀመር ሁለተኛው ወር ምሽት ላይ ይጀምራል፣ ሦስተኛው ደግሞ ድጋሚ ጠዋት ላይ ይጀምራል፤ ይህን ለመቅረፍ ወሩን ሙሉ  ሰላሳ ቀን ቢያደርጉት ከትክክለኛው ወር /የጨረቃ ዐውድ/ ግማሽ ቀን ይተርፋል፤ 29 ቀን ብቻ ቢያደርጉት ደግሞ ግማሸ ቀን ይጎድላል፡፡ አንድ ዓመት 365 ከሩብ ዕለታት አሉት፡፡
ዓመትን በወራት ለመቁጠር ቢፈለግ፤ ዓመቱን 12 ወር ቢያደርጉት የዓመቱ /የዕለታት ቁጥር /29.5X12=354/ ብቻ ይሆናል፡፡ ይህም ከትክክለኛው ዓመት /365-354=11/ ዕለታት ያህል ያንሳል፡፡ 13 ወር ቢያደርጉት ዓመቱ /365X13=385.5/ ቀናት ይሆናል ይህም ከትክክለኛው ዓመት /383.5-365=19/ ቀናት ያህል ይበልጣል፡፡
ስለዚህ እነዚህን መስፈሪያዎች በቅንጅት ለመጠቀም ይህንን አለመጣጣም የሚፈታ ቀመር /የዘመን አቆጣጠር ሥርዓት/ ያስፈልጋል፡፡ በተለያዩ አካባቢዎች የተለያዩ የዘመን አቆጣጠሮች ተዘጋጅተዋል፡፡



የአይሁድ ዘመን አቆጣጠር

የአይሁድ ዘመን አቆጣጠር እያንዳንዳቸው 29 እና 30 ዕለታት ያሏቸው 12 ወራት አሏቸው፤
ተ.ቁ
የአይሁድ ወራት
የዕለታት ብዛት
ወራቱ በእኛ
1
ኒሳን
30
መጋቢት/ ሚያዝያ
2
ኢያር
29
ሚያዝያ/ ግንቦት
3
ሲዋን
30
ግንቦት/ ሰኔ
4
ታሙዝ
29
ሰኔ/ ሐምሌ
5
አቭ
30
ሐምሌ/ ነሐሴ
6
አሉል
29
ነሐሴ/ መስከረም
7
ኤታኒም
30
መስከረም/ ጥቅምት
8
ቡል
29/30
ጥቀምት/ ኅዳር
9
ከሴሉ
30/29
ኅዳር/ ታህሳስ
10
ጤቤት
29
ታህሳስ/ ጥር
11
ሳባጥ
30
ጥር/ የካቲት
12
አዳር 1
29
የካቲት/ መጋቢት
እነዚህ የዓመቱ 12 ወራት በአጠቃላይ 354 ያህል ብቻ ዕለታት ይኖሯቸዋል፡፡ ይህም በትክክለኛው ዓመት በ11 ዕለታት ያህል ቢያንስም አዲስ ዓመት ይጀምራሉ፡፡ ልዩነቱ በሁለት ዓመታት 22 ዕለታት፣ በሦስት ዓመት ደግሞ 33 ዕለታት ያህል ይሆናል፡፡ ስለዚህ በየሦስት ዓመቱ ከአስራ ሁለተኛው ወር ጳጉሜን በፊት አንድ ሌላ ወር ይጨምሩና ጨምረው የዓመቱን የወራት ቁጥር ዐሥራ ሦስት ያደርጉና ልዩነቱን ያስተካክሉታል፡፡

የኢትዮጵያውያንና የግብጻውያን ዘመን አቆጣጠር

የሀገራችን ኢትዮጵያ እና የጥንት ግብጻውያን /ዛሬም ድረስ የግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን የምትጠቀምበት/ የዘመን አቆጣጠር ተመሳሳይ ነው፡፡ ሁለታችንም እኩል ሰላሳ ቀናት ያሏቸው 12 ወራት አሉን፡፡ እነዚህ 12 ወራት / 12X30=360/ ቀናት አሏቸው እነዚህ ቀናት በትክክለኛው ዓመት በ/365.25-360=5.25/ ቀናት ያንሳሉ፡፡ ይህንንም 5 ቀናት / በ4 ዓመት አንድ ጊዜ 6 ቀናት/ ያሏትን 13ኛ ወር በመጨመር ያስተካክሉታል፡፡ የኢትዮጵያውያን እና የግብጻውያን ወሮች ስም እንደሚከተለው ነው፡፡
ተ.ቁ
የግብጽ ወሮች
የኢትዮጵያ ወሮች
1
ቱት/ዩት
መስከረም
2
ባባ/ፓከር
ጥቅምት
3
ሀቱር
ኅዳር
4
ኪሃክ/ከያክ
ታኅሣሥ
5
ጡባ/ቶቢር
ጥር
6
አምሺር/ሜሺር
የካቲት
7
በረምሃት
መጋቢት
8
በርሙዳ
ሚያዝያ
9
በሸንስ
ግንቦት
10
ቦኩሩ
ሰኔ
11
አቢብ
ሐምሌ
12
መስሪ
ነሐሴ
13
ኒሳ/አፓጎሜኔ
ጳጉሜን
/ባሕረ ሐሳብ፣ፕ/ር ጌታቸው ኃይሌ ፣ገጽ.65/

የኢትዮጵያ ዘመን አቈጣጠር

የኢትዮጵያ እምነታዊ ባህል የሚወረሰው በሦስት ዐይነት ጠባይ ነው። አንዱ ሕገ ልቡና ይባላል። ከመጽሐፍ በፊት የነበረ ነው። ከአበው ቃል በቃል የተወረሰ ነው። ሁለተኛው በሕገ ኦሪት ከኦሪት የተቀዳ ነው። ሦስተኛው በሕገ ወንጌል ከወንጌል የተማርነው ነው። እና በሦስት ዐይነት ጠባይ የሚመራ ነው። በዚህ ዐይነት ከወረስናቸው በዓላት ማለት በሦስቱም ጠባያት ከወረስናቸው በዓላት የየራሳቸው መልክ ያላቸው አሉ። ለምሳሌ ልደት፥ ጥምቀት፥ ዕርገት፥ ደብረ ታቦር እነዚህን የመሳሰሉት ከወንጌል የተማርናቸው ናቸው፤ በብሉይ የሉም። ፋሲካ፥ በዓለ ጰራቅሊጦስ ደግሞ ከኦሪት የተማርናቸው ናቸው። የዘመን መለወጫ በዓል ግን ከሕገ ልቡና ቃል በቃል ተምረን፥ በኦሪት የመጽሐፍ መሠረት አግኝተንለት በወንጌልም አጽንተን ይዘነው የኖርነው ሦስት የሥራ ዘመን ክፍል የተላለፈና እዚህ የደረሰ ነው። እኛ የዘመን መለወጫ ብለን በሀገራችን ባህል የምናከብረው ዓለም ካለመኖር ወደ መኖር የተገኘበት፥ ብርሃን፥ ጊዜ፥ ዕለት፥ ሰዓት የተፈጠሩበት፤ ለብርሃን፥ ለጊዜ፥ ለዕለት፥ ለወር ለዓመት ጥንት መሠረት የሆነ ቀን ነው። ይህንን ሁሉ በማስገኘት እግዚአብሔር ራሱን የገለጠበት፥ ዓለምን በመፍጠር ከሃሊነቱን ያረጋገጠበት ቀን ነው ብለን ነው የምናከብረው። ስለዚህም ጥንተ ብርሃን፥ ጥንተ ዕለት፥ ጥንተ ጊዜ፥ ጥንተ ፍጥረት ርእሰ ዐውደ ዓመት ብለን ነው የምናከብረው። በዚህ ስያሜ በዓሉ ርእሰ ዐውደ ዓመት፥ ቅዱስ ዮሐንስ፥ የዘመን መለወጫ ብለን እናከብረዋለን።
ቅዱስ ዮሐንስ
የኢትዮጵያ ዘመን መለወጫ በዓል ሌላው ስሙ ቅዱስ ዮሐንስ ይባላል። ቅዱስ ዮሐንስ የሚባልበትም ሁለት ጠባይ አለው። አንዱ፤ መጥምቁ ዮሐንስ በሄሮድስ አንቲጳስ ጊዜ ከጳጉሜን ቀን ጀምሮ ታስሮ ሰንብቶ በመስከረም ቀን ዐሳብ ስለ ተቆረጠበትና በመስከረም ቀን እንዲሞት ውሳኔ ስለ ተሰጠበት አንገቱን በሰይፍ ተቆርጦ ስለ ሞተ ሊቃውንት ይህንን በዓል እሱ ራሱ ለኦሪትና ለወንጌል መገናኛ መምህር ስለ ነበረ ይህም በዓል ላለፈው ዘመን መሸኛ፥ ለሚመጣው ዘመን መቀበያ እንዲሆን ብለው በመስከረም ቀን እንዲከበር ስላደረጉ በሱ ስም ቅዱስ ዮሐንስ እየተባለ ይጠራል። በሁለተኛው ግን ከአራቱ ወንጌላውያን አንዱ ወንጌላዊ ዮሐንስ የተሰየመበት ስለ ሆነ በአቆጣጠርም ተራ ወደ ኋላ ተመልሶ ቢቈጠር ዓለም የተፈጠረበት ዘመን በዘመነ ዮሐንስ እንዳጋጣሚ ሆኖ ስለሚገኝ ቅዱስ ዮሐንስ ተብሎ ይጠራል።

ዕንቍጣጣሽ
በዚያም ጊዜ የነበሩ ኖኅና ልጆቹ ሰማዩ በደመና በመክበዱ ምክንያት ማየ አይኅ እንደገና ይመጣ ይሆን፥ የጥፋት ውሃ እንደገና ይዘንም ይሆን እያሉ ሲደነግጡ ከርመው በመስከረም ወር መጀመሪያ ላይ ሙሉ የፀሓይ ብርሃን ስላዩ፥ ምድር በአበባ አሸብርቃ ስለ ተገለጠችና በዚህም የእግዚአብሔርን ቸርነት፥ የቃል ኪዳኑን መጽናት ስለ ተረዱ ይህንን በዓል ቀድሞ ከአባቶቻቸው እንደ ወረሱት ያው ጥንተ ብርሃን፥ ጥንተ ዓመት፥ ጥንተ ዕለት አድርገው አክብረውታል። ሲያከብሩትም እንግጫ ነቅለው፥ አበባ ጐንጕነው መጀመሪያ መሥዋዕት ይሠዉነት ከነበረው ቦታ ሄደው ለእግዚአብሔር ገጸ በረከት አቅርበው ከዚያ በኋላ ግን እርስ በርሳቸው የአበባ ስጦታ በመለዋወጥ አክብረውታል። ሲያከብሩትም ዕንቍጣጣሽ በሚል ቃል እውነት የመልካም ሞኞታቸውን ይገላለጡበት ነበር። ዕንቍጣጣሽ ማለትንም ብዙ ታሪክ ጸሓፊዎች በልዩ ልዩ መልክ ተርጕመውታል። እንዲያውም ንጉሡ ሰሎሞን ለሳባ ንግሥት የዕንቍ ቀለበት ሰጥቷት ነበርና «ዕንቍ ለጣትሽ» ማለት ነው ብለው የጻፉ ብዙ ሰዎችም አሉ፤ የሚናገሩም አሉ። ነገሩ ግን እንዲህ አይደለም። ዕንቍጣጣሽ ማለት ተንቈጠቈጠ፥ አንቈጠቈጠ ከሚለው ቃል ተወስዶ ምድር በአበባ አጌጠች፥ ሰማይም በከዋክብት አሸበረቀ እንደ ማለት ሰማይን በከዋክብት ያስጌጠ አምላክ ምድርንም በአበቦች አጎናጸፋት ለማለት የተሰጠ ቃል ነው እንጂ ስለ ሳባ ንግሥት የተሰጠ አይደለም። ሁለተኛም አባቶቻችን ኢትዮጵያን በሙሉ ሀብት ተረክበዋት ነበርና፤ «ዕንቍ ዕጣ ወጣሽ፤» ሲሉ ወደ አገራቸው ሲገቡ ለአገራቸው መታሰቢያ አድርገው የተጠቀሙበት ቃል ነው ይባላል። በመሠረቱ ግን የጥፋት ውሃ ቀርቶ ምድር ጸንታ፥ አበባ ቋጥራ፥ ፍሬ ለመስጠት ተዘጋጅታ መገኘቷን የሚያበሥር ቃል ነው።
መስከረም 
መስከረም የሚባለው ወርም ኖኅ በመርከብ ውሥጥ በነበረ ጊዜ እንደ ዕብራውያን አቈጣጠር ሰባተኛ በሆነው በመስከረም ወር መጀመሪያ ላይ መርከቢቱ አራራት ከሚባለው ተራራ ላይ ዐርፋ ምድር ጨብጣለች። በግእዝ ቋንቋ መርከብ መስቀር ይባላል። ከዘመን ብዛት በኋላ «» ወደ «» ተለውጦ መስከረም ተባለ እንጂ መስቀርም ምድር አገኘች፥ መርከብም ምድር ነካች ለማለት የተሰጠ የወሩ ስያሜ ነው።

ርእሰ ዐውደ ዓመት 

የምንለው፤ ዐውድ ማለት በግእዙ ቋንቋ ዙሪያ፥ ክብ የሆነ ነገር ማለት ነው። የዓመት ጠቅላላ ቀኖች መሠረታውያን ቀኖች የሚባሉት ሦስት መቶ ስድሳ አራት ቀኖች ናቸው። እነዚህም በኀምሳ ሁለት ሱባዔ ተከፍለው ለእያንዳንዱ ቀን በዓመት ውስጥ ለሰባቱ ዕለታት ኀምሳ ሁለት ኀምሳ ሁለት ቀን ይደርሳቸዋል። ከነዚህ ቀኖች የተሳሳበ የሴኮንድ፥ የደቂቃ፥ የሰዓት ዕላፊ ተጠራቅሞ ሦስት መቶ ስድሳ ዐምስተኛዋን የዘመን ማገጣጠሚያ ቀን ያስገኛል። ይህቺ ቀን እንግዲህ ዙሪያ፥ ክብ መግጠሚያ ናት ማለት ነው። በዚህች ቀን አማካይነት ወደ ዐዲሱ ዘመን መጀመሪያ እንተላለፋለን። ይህቺ ቀን ዕለት አዕዋዲት፥ ዕለተ ምርያ የመዘዋወሪያ ቀን ወይም የመጨረሻ ቀን ተብላ ትጠራለች። በአራት ዓመት ደግሞ ከዚህች መሳሳብ የምትገኝ አንዲት ቀን ትመጣለች። ሦስት መቶ ስድሳ ስድስተኛ። ይህቺ ቀን ዕለተ ሰግር ትባላለች። መረማመጃ ማለት ነው። አንድ ቀን ታስተላልፋለች። እንግዲህ እነዚህን ሁለቱን ቀኖች ተከትሎ የሚመጣው ቀን የዘመን መጀመሪያ፥ የዘመን ክብ መነሻና መድረሻ ተብሎ ርእሰ ዐውደ ዓመት ተብሎ በግእዙ ይጠራል። እነዚህ ቀኖች በኢትዮጵያውያን አቆጣጠር ተጠቃለው አንድ ጊዜ የሚገኙ ናቸው።

የኢትዮጵያ ቍጥር መሠረቱ መጽሐፈ ሔኖክ የሚባለው ነው። መጽሐፈ ሔኖክ በ፲፱፥ ፳፥ ፳፩ እና ፳፪ ምዕራፎች የሚሰጠን የፀሐይን፥ የጨረቃን ጉዞ መነሻ አድርጎ የወሮችን፥ የዕለታትን፥ የዓመታትን መነሻ፥ መድረሻ፥ መዘዋወሪያ ብተታቸውን፥ ጥንታቸውን ነው የሚያሳየው። ስለዚህም በሔኖክ ቍጥር የወር ቀኖች ቍጥር ሠላሳ ናቸው። በሦስት በሦስት ወር ግን አንድ ቀን ትከተላቸዋለች። እና ዓመቱ ለአራት ይከፈላል። በዘጠና አንድ በዘጠና አንድ ቀን። ጠቅላላው ይሄ ድምር ሦስት መቶ ስድሳ ስድስት ቀን ይመጣል። ይህ ካለቀ በኋላ አንዲት ቀን ለዘመን ማገጣጠሚያ ዕለተ ምርያ የምትባለው ትመጣለች። እንግዲህ በኢትዮጵያውያን ቍጥር ወሩ ከሠላሳ አያንስም፤ ከሠላሳ አይተርፍም። ለዓመቱም ሦስት መቶ ስድሳ ዐምስት ቀን መደበኛው አቆጣጠር ነው ማለት ነው። ይህ ነገር በአውሮፓውያን ቍጥርም አለ። ግን እነሱ ከዓመት ወሮች ሰባቱን ሠላሳ አንድ ሠላሳ አንድ አድርገው አራቱን ደግሞ ሠላሳ ሠላሳ አድርገው አንዷን ወር ሦስቱን ዓመት ሃያ ስምንት፥ በአራተኛው ዓመት ሃያ ዘጠኝአድርገው ያጣጧታል። 
እንግዲህ የአቀማመጡ ለውጥ ካልሆነ በስተቀር በቍጥር አካሄድ ዞሮ ዞሮ የዓመት ቀኖች ሦስት መቶ ስድሳ ዐምስት ወይም ሦስት መቶ ስድሳ ስድስት በመሆን አንድ ሆነዋል ማለት ነው። ልዩነቱ ግን የአቀማመጥ ለውጥ ነው። በኢትዮጵያ አቈጣጠር ግን ጠቅላላውን ፲፪ ወሮች መደባቸው ሠላሳ ብቻ ነው። እነዚያ በሔኖክ መጽሐፍ በጣልቃ ገብነት የነበሩት አራት ቀኖች ተጠቅለው ጳጉሜን በሚባል በዓመቱ መጨረሻ ላይ ተገኝተዋል። ዐምስተኛዪቱ ቀንም ከእነሱ ጋር ተገኝታለች። ይህም ለቍጥር ተራ ቅምር መቅናት የተደረገ እንጂ ቀኑን የሚለውጥ ምንም ነገር የለበትም። እና ከእነዚህ ቀኖች በኋላ የምናገኘው ቀን ርእሰ ዐውደ ዓመት ይባላል። ይህንን በዓል ከአዳም ጀምሮ እስከ ኖኅ ድረስ የነበሩ ዐሥሩም አበው በዐሥሩ ትውልድ እስከ ማየ አይኅ ድረስ ሲያከብሩት እንደ ቆዩና ኋላም የኖኅ ልጆች ከአባታቸው ተቀብለው ሲያከብሩት እንደ ነበረ ኩፋሌ የተባለው መጽሐፍ በምዕራፍ ያስረዳናል። እንግዲህ ኢትዮጵያ ይህንን ቀን የወረሰችው ከአበው ነው የምንለው በዚህ ምክንያት ነው።
  

  የዘመን ቁጥር ልዩነት

ፕ/ር ጌታቸው ኃይሌ የዘመን አቆጣጠር መለያየትን መነሻ እንዲህ በማለት ያብራራሉ፤ «ክብ የሆነ ነገር ሲከብ ከየትኛውም ቦታ መጀመር ይቻላል፤ የዘመን አቆጣጠር /ዓውደ ዓመትም/ ይኸው ነው፡፡ ዋናው ነገር አንድ ታላቅ ታሪካዊ ድርጊት ፈልጎ እርሱን መነሻ ማድረግ አንድ ታላቅ ታሪካዊ ድርጊት ፈልጎ እርሱን መነሻ ማድረግ ነው፤ የዘመን አቆጣጠሮቹም ልዩነት መንስኤው ይኸው ነው» ይላሉ፡፡ ባሕረ ሐሳብ፣ ጌታቸው ኃይሌ፣ ገጽ.65/ ለምሳሌነትም ሮማውያን የሮም ከተማ የተቆረቆረችበትን ጊዜ መነሻ ማድረጋቸውን/ በኋላም ታላቁ እስክንድር የነገሠበት ዘመን የዘመን ቆጠራ መነሻ ሆነው እንደነበር ይጠቅሳሉ፡፡ መሐመድና ተከታዮች ከመካ ወደ መዲና ያደረጉትን ስደት መነሻ የሚያደርገው ኢስላማዊ  የዘመን አቆጣጠርም ሌላው ተጠቃሽ ነው፡፡
የአይሁድን አቆጣጠር ትተን ከላይ ያየናቸው ሁለቱ የዘመን አቆጣጠሮች /የምዕራባውያኑ የጁልየስ ጎርጎርዮሳዊ አቆጣጠርና የኢትዮጵያና የግብጽ አቆጣጠር/ ሁለቱም ዘመንን የሚቆጥሩት ከክርስቶስ ልደት መነሻ አድርገው ነው፡፡ ይሁን እንጂ እኛ ዛሬ 2006ዓ.ም ነው ስንል እነርሱ ደግሞ 2014 ዓ.ም ነው ይላሉ፡፡ በመካከሉ የ7/8 ዓመታት ልዩነት አለ፡፡ እንግዲህ ጥያቄው ትክክለኛው የትኛው ነው? የሚለው ነው፡፡
ጉዳዩ መጻሕፍትን ሊያጽፍ የሚችልና በእርግጥም የተጻፉበት ቢሆንም ለማሳያ ያክል ሁለት ነገሮች እንመልከት፤

1. አሁን ባለው የምዕራባውያን አቆጣጠር ሄሮድስ የሞተው 4 ዓመት ቅ.ል.ክ ነው፡፡ ሄሮድስ የሞተው ጌታ ተወልዶ በስደት ሦስት ዓመት ያህል በግብጽ ከቆየ በኋላ ነው፡፡ ይህ ማለት በእርሱ አቆጣጠር ጌታ የተወለደው በ7 ዓመት ቅ.ል.ክ ነው ማለት ነው፡፡ እንግዲህ ጌታ በትክክል በተወለደበት በአንድ ዓ.ም እነርሱ ጌታ ሰባት ዓመት ሆኖታል ይላሉ ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ትክክለኛውን ቁጥር ለማግኘት አሁን ካላቸው ቁጥር ላይ ሰባት ዓመት መቀነስ አለባቸው፡፡

2. ፍላቪየስ ጆሴፈስ የተባለው የአይሁድን ታሪክ የጻፈው ሊቅ እንደመሰከረው ጌታ የተወለደበት ዓመት ነው ተብሎ በወንጌል ላይ የተጻፈው የቆጠራ ዓመት /ሕዝቡ ሁሉ የተቆጠረበትን ዘመን /ሉቃ.2.1/ በጎርጎሪያን ዘመን አቆጣጠር «7 ዓመተ እግዚአ /A.D/ ላይ ነው፡፡» በማለት መረጃ ትቶልናል ይህ ማለት ደግሞ ከምዕራባውያኑ ዘመን አቆጣጠር ላይ 7 ዓመቶች የግድ መቀነስ አለበት ማለት ነው፡፡ ያ ሲደረግ ደግሞ የኛን ዘመን አቆጣጠር ያመጣል፡፡

የዘመን መለወጫ ቀን ልዩነት

ሁለተኛው ጉዳይ የዘመን መለወጫ ወርና ዕለት ልዩነት ነው፡፡ እኛ መስከረም  1 አዲስ ዓመት ስንጀምር እነርሱ በ January 1 / በእኛ ታኅሣሥ 23/ አዲስ ዓመት ይጀምራሉ፡፡ ይህ ከየት የመጣ ልዩነት ነው?
የእኛ እና የግብጻውያን አቆጣጠር እዚህ ጉዳይ ላይ ከአይሁድ አቆጣጠር ጋር ይስማማል፡፡ በአይሁድ አቆጣጠር የመጀመሪያው ወር ኒሳን የሚባለው /በእኛ መጋቢት/ ሚያዝያ/ ነው፡፡
«ይህ ወር የዓመቱ የመጀመሪያ ወር ይሁናችሁ፣ በዚህም ወር በዐሥራ አራተኛው ቀን የአንድ ዓመት ተባዕት ላይ ወስደው ይረዱ፡፡ . . .»/ዘፀ.12.1-14/ ተብሎ የተሰጣቸውን የፋሲካ በዓል የሚያከብሩት በዚህ ወር ነው፡፡
ይሁን እንጂ አዲስ የዓመት በዓል አድርገው የሚያከብሩት «የሰባተኛው ወር የመጀመሪያ ቀን ዕረፍት ይሁናችሁ፡፡ በዚሁ በመለከት ድምጽ የሚከበር የተቀደሰ ጉባኤ ይኑራችሁ መስዋዕት ለእግዚአብሔር አቅርቡ እንጂ የተለመደ ተግባራችሁን አታከናውኑበት» /ዘሌ.13.23-25/ ተብሎ የተሰጣቸው የሮሽ ሆሻና፣/የመለከት በዓል ወይም በዓለ መጥቅዕ/ ተብሎ የሚጠራው በዓል ነው፡፡ ይህም ማለት አዲስ ዓመት የሚያከብሩት በሰባተኛው ወር በኢታኒም ወር /በእኛ መስከረም ጥቅምት/ ነው፡፡
በቤተክርስቲያናችንም ትምህርት ዓለም የተፈጠረው መጋቢት 29 ቀን ነው፡፡ መስከረም ደግሞ ከመጋቢት ጀምሮ ሲቆጠር ሰባተኛው ወር ነው፡፡ ይህም ከአይሁድ ዘመን አቆጣጠር ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡
አይሁድስ ቢሆኑ የመጀመሪያው ወር እያለ አዲስ ዓመትን ለምን በሰባተኛው ወር ያከብራሉ ለሚለው ጥያቄ ሁለት ዓይነት ምላሾች /ምክንያቶች/ ይሰጣሉ፡፡ የመጀመሪያው ምክንያት «ሰባተኛው ወር ኖኅ ከመርከብ የወጣበት ወር በመሆኑ ይህ የአዲስ ዓመት መጀመሪያ ተደርጎ መከበር በመጀመሩ ነው» የሚል ነው፡፡ በዘመን መለወጫ ዕለት ልጃገረዶች አበባ እና ለምለም ሣር መያዛቸው ርግቢቱ ለኖኅ ካመጣችው ለምለም ወይራ /ቄጠማ/ ጋር ተያይዞ የተጀመረ መሆኑን ይናገራሉ፡፡
ሁለተኛው ደግሞ መስከረም የቀንና የዕለቱ ርዝመት እኩል የሚሆኑበት ወር በመሆኑ ነው የሚል ነው፡፡ የመስከረም 1 ቀን ስንክሳር «የተባረከ የመስከረም ወር የግብጽና የኢትዮጵያ ዓመታት ወሮች ርእስ ነው፤ የቀኑ ሰዓትም ከሌሊቱ ሰዓት የተስተካከለ ዐሥራ ሁለት ነው» ይላል፡፡
እዚህ ላይ ማስተዋል የሚገባው ሌላው ጉዳይ በቤተክርስቲያናችን ትምህርት እመቤታችን ጌታን የጸነሰችው መጋቢት 29 ቀን ነው፡፡ ይህም ቅዱስ ጳዉሎስ ፣የዘመኑ ፍጻሜ በደረሰ ጊዜ እግዚአብሔር ከሴት ተወለደ» /ገላ.4.4/ እንዳለው የ5500 ዘመኑ ፍጻሜ /ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ/ ነው፡፡
ጽንሰትን መጋቢት 29 ካልን በኋላ ልደትን ታህሣሥ 29 ቀን እናከብራለን፡፡ ከመጋቢት 29 እስከ ታህሣሥ 29 ድረስ 9 ወር ከ5 ቀን ነው፡፡ /ጳጉሜን ጨምሮ/፡፡ ጳጉሜ 6 በምትሆንበት ጊዜ ደግሞ ታህሣሥ 28 ቀን ልደት ስለሚከበር አሁንም በመሐሉ ያለው ጊዜ 9 ወር ከአምስት ቀን ይሆናል፡፡

ማጠቃለያ  

በመጨረሻም የኢትዮጵያ የዘመን አቆጣጠር ፍፁም መፅሐፍ ቅዱሳዊ መሰረት ያለው ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ የሚቆጥር መሆኑን እንጂ እንደ ዘመኑ ነገስታት ፍላጎት በታሪክ ክስተትን መሰረት ያደረገ አለመሆኑን ከተረዳን ይህንን ሃሳባችንን የሚያጠናክርልን የሳምንታንት እና የወራት ስያሜዎቻችንን እንዲሁም የልሎቹ የቀን አቆጣጠር ምንጭን ከ እዚህ በታች ባሉት ሰንጠረዦች እንመልከት።ለምሳሌ እነኚህ የሳምንታንት ልዩነቶች አውሮፓውያን ከጥንት ከነበረ አምልኮት ጋር የትዛመደ ሲሆን የእኛ ግን እግዚአብሔር አለምን መፍጠር ከጀመረ የመጀመርያ ቀን ስንል እሁድ ማለታችንን ሁለተኛ ቀን ስንል ሰኑይ (ሰኞ) ማለታችንን ወዘተ እንረዳለን።
ማኅበረ ቅዱሳን አውደ-ርዕይ 2000 ዓም
ማኅበረ ቅዱሳን አውደ-ርዕይ 2000 ዓም

                                   በአውሮጳ   የካህናት አንድነት ማኅበር ሊቋቋም መሆኑ ታወቀ በ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከመላዋ አውሮጳ   የተውጣጡ ካህናት፡” የ...