2014 ኖቬምበር 14, ዓርብ

ደብረ ፀሐይ ቍስቋም ማርያም

እንኳን ለቊስቋም ማርያም ዓመታዊ ክብረ በዓል አደረሰን ።

አንድ አድርገን ህዳር 6 2007 ዓ.ም
ቁስቋም ማርያም በደርቡሾች ተቃጥሎ
እንደነበር - 1930 ዓ.ም.
የእመቤታችን በትልቅ የምስጋና አገልግሎት ከሚከበሩ በዓላት መካከል የወርሐ ጽጌ በዓል አንዱና በሊቃውንተ ቤተክርስቲያን ልብ ውስጥ ጥልቅ የልቦና ፍቅር ያለው የማኅሌትና የቅዳሴ በዓል ነው፡፡ወርሐ ጽጌ በመባል በቤተክርስቲያናችን የሚከበረው ይኽው የምስጋና በዓል ከመስከረም 26 ጀምሮ እስከ ኅዳር 6 ቀን ያለው ጊዜ ሆኖ የእመቤታችንን ስደት የምንዘክርበትና የምናስብበት ጊዜ ነው፡፡ ከዚህ ጋር ተያይዞ ስለ ደብረ ፀሐይ ቍስቋም ማርያም ትንሽ ካነበብነው ማካፈል ወደድን……

ደብረ ፀሐይ ቍስቋም ማርያም ጎንደር ከተማ በስተ ስሜን ምዕራብ ወጣ ብሎ በሚገኘው ደብረ ፀሐይ ቁስቋም የተሰራ ቤተክርስቲያን ነው። ደብረ ፀሓይ ቁስቋም በእቴጌ ምንትዋብ 1725 .. እስከ 1738.. ተገንብቶ የተጠናቀቀ ሲሆን በጊዜው 360 መስታዎቶች የነበሩት፣ በቀይና ሰማያዊ ሃር አልባሳት ያሸበረቀ፣ እንደ ደብረ ብርሃን ስላሴ በጥሩ ኪነት የተዘጋጀ፣ ከወርቅና ከብር የተሰሩ የቤተ ክርስቲያን ማገልገያወች የነበሩት፣ በጊዜው የተደነቀ ቤተ ክርስቲያን ነበር። ደብረ ፀሐይ በተመሰረተበት ዘመን የራሱ ጉልት የነበረው ሲሆን ይኼውም እብናት በለሳ እና አርማጭሆ ተሰባጥሮ ይገኝ ነበር፤ ስለሆነም 260 ቀሳውስትን በስሩ ያስተዳድር ነበር፡፡ ከህንጻ ይዘቱ አንጻር በዚሁ ዘመን በምንትዋብ ከተገነባው ናርጋ ስላሴ ጋር ይመሳስል እንደንበር ግንዛቤ አለ።

የቁስቋም ግቢ ሦስት ጊዜ ጉዳት ደርሶበታል። በመጀመሪያ 1858 ዓፄ ቴዎድሮስ መቅደላ ሊያሰሩት ላሰቡት ቤተ ክርስቲያን ከቤተክርስቲያኑ የተለያዩ ንዋያትን መውሰዳቸው ነበር። ሁለተኛው ጉዳት የደረሰው 1870ወች፣ ደርቡሾች ግቢውን በእሳት በማጋየት ያደረሱት ዋናው ጉዳት ነበር። በዚህ ቃጠሎ ቁስቋም ማርያም ሊፈርስ ችሏል። ቤተክርስቲያኑ አሁን የያዘውን ቅርጽ ያገኘው በጣሊያኖች ጊዜ ሲሆን ያሁኑ መልኩ ከድሮው እጅግ ይለያል። የእቴጌ ምንትዋብ፣ የልጇ ዳግማዊ እያሱ እና ልጅ ልጇ እዮዋስ አጥንቶች በመስታዎት ሳጥን ሆነው በዚህ ቤተክርስቲያን ይገኛሉ። ከእሳት የተረፉ የእቴጌ ምንትዋብ መገልገያዎች አሁን ድረስ በቤተክርስቲያኑ ይገኛሉ።

Source :- http://am.wikipedia.org/
ደብረ ቍስቋም 

የማያለቅስ ልጅ


ፎቶ - ሐራ ተዋሕዶ

ቅዱስ ሲኖዶስ የቤተ ክርስቲያንን ሕግ በተመለከተ አሠረ ሐዋርያትን የተከተለ ሆኖ እንዲጸድቅ አድርጓል፡፡ አባቶቻችን በቤተ ክርስቲያን ላይ ግለሰባዊ አምባገነንነትን አልፈቀዱም፡፡ ጸሎተ ሃይማኖቱም ‹ነአምን በአሐቲ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እንተ ላዕለ ኩሉ ጉባኤ ዘሐዋርያት›› በማት ቤተ ክርስቲያን ጉባኤ ዘሐዋርያት መሆንዋን ያመለክታል፡፡ በ50/51 ዓም በኢየሩሳሌም የተሰበሰበችው ሲኖዶስም ‹እኛና መንፈስ ቅዱስ› አለች እንጂ  ‹እኔ› የሚል ግለሰባዊ ድምጽ አልተሰማባትም፡፡
ኢትዮጵያውያን አበው የቅዱስ ሲኖዶስን ሥርዓት ብቻ ሳይሆን ሌሎችን የቤተ ክርስቲያን የአመራር ሥርዓቶች ከግለሰብ አምባገነንነት ለማውጣት መልካም የሆነ ሥርዓት ሠርተዋል፡፡ ቅዳሴው በአምስት ልዑካን እንዲሆን፣ አጥቢያው በሰበካ ጉባኤ እንዲመራ፣ ገዳማት በምርፋቅ (ጉባኤ አበው) ወይም በማኅበር እንዲመሩ፣ ጵጵስናን አንድ ጳጳስ (ፓትርያርክ እንኳን ቢሆን) ብቻውን እንዳይሰጥ፣ ቢያንስ ሦስት አበው ሊኖሩ እንደሚገባ፤ አንድ አባት ብቻውን ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን እንዳይለውጥ፤ አድርገው የሠሩበት አንዱ ምክንያት ግለሰባዊ አምባገነንነትን ለመቋቋም እንዲቻል ነው፡፡

ይህንን ማኅበራዊና ጉባኤያዊ የሆነ የቤተ ክርስቲያን አሠራርና አመራር ለማስወገድ በየዘመናቱ ጥረት ተደርጓል፡፡ የዚህም ምክያቱ ግልጽ ነው፡፡ ግለሰባዊ የሆነ አመራር ለሦስት ነገሮች የተጋለጠ ነውና፡፡ የመጀመሪያው ክህደትንና ኑፋቄን ለማስገባት ይመቻል፡፡ አንዱ ወሳኝ ሌላው ‹ኦሆ በሃሊ› ስለሚሆን እርሱ ትክክል ነው ያለው ትክክል፣ ስሕተት ነው ያለው ደግሞ ስሕተት ይሆናል፡፡ ቤተ ክርስቲያን ጉባኤያዊት በመሆንዋ አንዳንድ ግለሰቦች በየዘመናቱ ያመጡትን ክህደት በጉባኤ ተመልክታ በጉባኤ ለማውገዝ ጠቅሟታል፡፡ ደገኛ ትምርትና ድርሰት ሲገኝ ደግሞ እንዲሁ በጉባኤ ተመልክታ ለመቀበል ረድቷታል፡፡ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ መጽሐፈ ምሥጢርን ጽፎ በጨረሰ ጊዜ ጉባ ሊቃውንቱ ተመልክተው ‹አማንኬ ዮሐንስ አፈወርቅ ወቄርሎስ አፈ በረከት ተንሥኡ በመዋዕሊነ፡፤ ኢትዮጵያ ተመሰለት በቁስጥንጥንያ፤ ወተአረየታ ላዕለ እስክንድርያ - በእውነት ዮሐንስ አፈወርቅና አፈ በረከት የሆነው ቄርሎስ በዘመናችን ተነሥተዋ፡፡ ኢትዮጵያም ቁስጥንጥንያን መስላለች፤ ከእስክንድርያም ልቃ ከፍ ከፍ ብላለች›› ብለው ምስክርነታቸውን ሰጥተው ነበር፡፡
ሁለተኛው ደግሞ ለሌሎች አካላት ቁጥጥር ስለሚመች ነው፡፡ ጌታችን አስቀድሞ ኃይለኛውን ማሠር እንዳለው መሪውን የያዘ ቤተ ክርስቲያኒቱን አን ልቡ ለመዘወር ይመቸዋል፡፡
ይኼ ነገር በዘመነ ሱስንዮስ ጊዜ ታይቷል፡፡ ሮማውያን ግብጻዊውን ጳጳስ በሮማዊ ጳጳስ በመተካት ቤተ ክርስቲያኒቱን በሮማዊ ጳጳስ ለማስመራትና ለመቆጣጠር ፈልገው ነበር፡፡ ነገር ግን የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ጠባይ ማኅበራዊና ጉባኤያዊ በመሆኑ ጉባኤ ሊቃውንቱ ከግብጹ ጳጳስ ጋር ሆኖ ተቃወማቸው፡፡ ጳጳሱና ሊቃውንቱም እስከ ደም ማፍሰስ ድረስ መሥዋዕት ሆኑ፡፡ ጥቅምት 19 ቀን 1621 ዓም በምዕራብ ጎጃም በምትገኘው ደብረ መዊዕ የተሰበሰቡት የቤተ ክርስቲያን ማኅበርተኞች ለዚህ ማስረጃ ናቸው፡፡ በዚህ የደብረ መዊዕ ጉባኤ እስከ 7000 የሚደርሱ ምእመናን፣ ካህናት፣ መነኮሳትና ሊቃውንት ተሰባስበው ነበር፡፡ የጉባኤው መሪዎችም እነ አባ ተስፋ ኢየሱስ፣ አባ ዘጊዮርጊስ ዘዋሸራ፣ አባ እንጦንዮስ፣ አባ ግርማ ሥሉስ ዘውይት ነበሩ፡፡ የጉባኤው አፈ ጉባኤ ደግሞ አባ ግርማ ሥሉስ ነበሩ፡፡በዚህ ጉባኤ የተገኙት ሁሉ ንጉሡንና አዲሶቹን ሮማውያን የሃይማኖት መሪዎች ተቃውመው እንደ አንድ ልብ መክረው እንደ አንድ ቃል ተናግረው በተዋሕዶ ጸኑ፡፡ የንጉሥ ሱስንዮስም ጦር ጥቅምት 19 ቀን ከብቦ ፈጃቸው፡፡ 
እነዚህ ጽኑአን ጉባኤተኞች ነበሩ በኋላ ዐፄ ሱስንዮስ ሐሳባቸውን እንዲቀይሩና ‹ፋሲል ይንገሥ፣ ሃይማኖት ይመለስ› እንዲሉ ያደረጋቸው፡፡ ቤተ ክርስቲያን እንደ መኪና መሪውን የያዘ መኪናውን ወደ ፈለገው ሊወስደው የሚችልባት ቦታ ብትሆን ኖሮ ዘመነ ሱስንዮስን መሻገር ባልቻለች ነበር፡፡ 
ሦስተኛው ምክንያት ደግሞ ዘመን የፈቀደለት ሁሉ ልቡ የወደደውን በቤተ ክርስቲያን ላይ እንዳይጭን ነው፡፡ በተለያዩ ዘመናት የተነሡ መንግሥታት ለራሳቸው የሚመቻቸው መሪ በቤተ ክርስቲያን ላይ ለማስቀመጥ ሞክረው ነበር፡፡ የቤተ ከርስቲያን አሠራር፣ ሕግና ሥርዓት ግን በአንድ ሰው የሚዘወር ባለመሆኑ ገመዱን ከመበጣጠስ ያለፈ ጀነሬተሩን ማቋረጥ አልተቻላቸውም፡፡ የቤተ ክርስቲያን ውሳኔዎችም በጉባኤ እንጂ በአንድ ሰው ኅሊና ብቻ የሚወሰኑ ባለመሆናቸው አስተዳደራዊ ጥቅም ከማግኘትና በደል ከማድረስ ባለፈ አጥንቷን ለመስበር ዐቅም አላገኙም፡፡ 
ይህንን ታሪካዊና ቤተ ክርስቲያናዊ ሐሳብ ጠንቅቆ በመረዳት የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ቤተ ክርስቲያኒቱን ወደ ግለሰባዊ አምባገነንነት የሚወስደውን  መንገድ በማረም የቤተ ክርስቲያኒቱ ራስ ክርስቶስ፣ የቤተ ክርስቲያኒቱም የበላይ ወሳኝ አካል ቅዱስ ሲኖዶስ መሆኑን በሕገ ቤተ ክርስቲያን አጽንቶታል፡፡ 
የሀገራችን ሰው ሲተርት ‹የማያለቅስ ልጅ በእናቱ ጀርባ ይሞታል› ይላል፡፡ ይራበው አይራበው፣ ይታፈን አይታፈን፣ ይመመው አይመመው፣ ይመቸው አይመቸው አይታወቅምና፡፡ ምናልባትም ዝምታው እንደ ጨዋነት ታስቦለት ዘወር ብሎ የሚያየው ላይኖርም ይችላል፡፡ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት በቤተ ክርስቲያን ላይ፣ በቅዱስ ሲኖዶስ ላይና በሊቃነ ጳጳሳት መብት ላይ፣ ቤተ ክርስቲያንን ሊያገለግሉ በተነሡ ማኅበራትና ወጣቶች ላይ፣ በየገጠሩ በተሠማሩና የመከራ ገፈት በሚቀምሱ ካህናትና ምእመናን ላይ የሚደርሰውን በደልና ጫና እየሰሙና እያዩ ዝም ቢሉ በእናታቸው ጀርባ ላይ ሆነው መሞታቸው የማይቀር ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያኒቱን መብት ለማስከበር ደግሞ አስቀድሞ የቅዱስ ሲኖዶሱ መብት መከበር አለበት፡፡ ያልቆመ አንገት ራስን አይሸከምም እንዲሉ፡፡
የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት አንድ ሆነው የቅዱስ ሲኖዶሱን መብት እንዳስጠበቁትና ቤተ ክርስቲያኒቱንም ከግለሰብ አገዛዝ እንደታደጓት ሁሉ በአጠቃላይ የሰበካ ጉባኤውና በቅዱስ ሲኖዶሱ ጉባኤ የቀረቡትን በቤተ ክርስቲያን ላይ እየደረሱ ያሉ ችግሮችን አንድ ሆነው ለመፍታት በቀጣይ  መነሣት አለባቸው፡                                                                                                           

2014 ኖቬምበር 6, ሐሙስ

አሁን እንኳን እንንቃ! . . የተሐድሶ መናፍቃን ስውር ሴራ (VCD No 2)

  • «ኦርቶዶክስ እውነተኛ ቤተ ክርስቲያን ነበረች፤ ነገር ግን የተጫኑባት ገለባዎች አሉ፡፡ ስለዚህ ተሐድሶ ያስፈልጋታል፤ የጥንቷን ቤተ ክርስቲያን መመለስ አለብን»
  • «የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ስሕተት ናት፤ ትክክል አይደለችም»
  • ባለአደራዎች የሆኑ ብፁዓን አባቶቻችን ዛሬም ታላቅ ሓላፊነት አለባቸው፡፡ የተሐድሶ እንቅስቃሴ አንዱ ስልት በአባቶችና በልጆች መካከል መለያየትን መዝራት እንደሆነ ልብ ሊሉት ይገባል
  • የተሐድሶ ኑፋቄው ያልተቋረጠ ጥቃት ዋነኛ ዓላማ፤ ምእመናንን ከእናት ቤተ ክርስቲያን እቅፍ በማስኰብለል የበግ ለምድ ለለበሰ ተኩላ አሳልፎ መስጠት ነው
ውድ የቤተክርስቲያን የስስት ልጆች ሆይ፤ ከዚህ በፊት በተደጋጋሚ እንደተነገረው ቤተክርስቲያናችንን ለመውረስ ረቀቅ ያለ ዘዴ ቀይሰው እየተንቀሳቀሱ ያሉት መናፍቃን የእኛው በሆኑ ግን ለሆዳቸው ባደሩ ጥቂት የማይባሉ ባንዳዎች ሰርገው በመግባት በርካታ ጥፋት እያደረሱ ይገኛሉ፡፡ ይህ ሲነቃባቸውም “ተሀድሶ የለም” እያሉ የዋሁን ህዝብ ሊያታልሉ ይሞክራሉ፤ ስለዚህ እኛ ልጆቿ ልጅነታችንን በምግባራችን ልናረጋግጥና በቃችሁ ብለን ልናስቆማቸው ይገባል፡፡ ይህ ቪድዮ እውነታውን አውቀን እንድንጠነቀቅ በማህበረ ቅዱሳን የተዘጋጀና 4 ክፍሎች ያሉት ሲሆን በመመልከትና ላላዩት እንዲያዩት share በማድረግ እናታችን የምትጠብቅብንን ሀላፊነት እንድንወጣ የእግዚአብሔር ቸርነት፣ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት፣ የቅዱሳን ጸሎት አይለየን፡፡

ስለ ቤተክርስቲያን ካሰቡ ያንቡት ምስሉንም ይመልከቱና የራስዎን ሃላፊነት ብቻ ይወጡ

የተሐድሶ መናፍቃን ስውር ሴራ ክፍል 1

(ስምዐ ጽድቅ ሚያዝያ 1-15 2003 ዓ.ም)  የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ያሳለፈቻቸው ዘመናት ሁሉ አልጋ በአልጋ አልነበሩም፡፡ ሐዋርያዊ ተልእኮዋን ለማሳካት ዘርፈ ብዙ መንፈሳዊ አገልግሎቷን በመፈጸም ያለፈችባቸው ዘመናት በፈተናዎች የታጀቡ ናቸው፡፡ የፈተናው ዓይነትና መጠን፣ ጠባይና መገለጫው እንደየጊዜና ሁኔታው እየተፈራረቀባት፤ በቅዱሳን ሰማዕትነት፣ በሊቃውንት መምህራኗ፣ በአባቶች ካህናቷ፣ በአገልጋዮቿ ተጋድሎ ልጆቿ እየተጠብቁ በመሠረቷ ጸንታ ትገኛለች፡፡

የተሐድሶ መናፍቃን ስውር ሴራ ክፍል 2



የተሐድሶ መናፍቃን ስውር ሴራ ክፍል 3


የተሐድሶ መናፍቃን ስውር ሴራ ክፍል 4





አጽራረ ቤተ ክርስቲያን የሚያደርሱባት ጥቃት ግፊትና ተፅዕኖ አሁንም ሌላው ፈተና ነው፡፡ ከዚህ ቀደም «የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ስሕተት ናት፤ ትክክል አይደለችም» በማለት ከውጪ ሆነው ምእመናንን በማጠራጠርና ግራ በማጋባት ሲያስኰበልሉ የነበረው ጥረታቸው እንዳልተሳካ ተረዱት፡፡ ስለዚህ ቤተክርስቲያኒቷን ሙሉ በሙሉ ለማዳከምና ሐዋርያዊ ተልእኮዋም ተደናቅፎ ሕልውናዋን ለማሳጣት ለዘመናት የደከሙት ድካም ከግብ እንዳልደረሰ ሲገነዘቡት የተለየ ስልት ቀይሰው እየተንቀሳቀሱ ነው፡፡

ትምህርተ ሃይማኖቷ እምነቷና ሥርዐቷ ምሉዕ የሆነውን ቅድስት ቤተ ክርስቲያን፤ ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ርትዕት ሃይማኖት «እናድሳለን» በሚል ስልት ወደ ውስጧ ሠርጐ በመግባት ልጆቿን እስከ ሕንፃ ቤተክርስቲያኗ እንረከባለን ይላሉ፡፡

የበግ ለምድ የለበሱ ተኩላዎቻቸውን በማሰማራት በጎቿን በኑፋቄያቸው እያሳሳቱ ከመንጠቅ፣ በተለያዩ ርዳታዎች ስም እየደለሉ ከማስኰብለል ጀምሮ፤ ትምህርተ ሃይማኖትና ሥርዐቷን በማጣጣል፣ ቅዱሳት መጻሕፍቷን በማራከስ፣ መልካም ስምና ገጽታዋን በማጠልሸት የሚያደርጉት የጥፋት ጥረታቸው ዛሬም እንደቀጠለ ነው፡፡ በእናትነት እቅፏ ውስጥ ጡቷን ጠብተው ማዕዷን ተሳትፈው አድገው፤ ነገር ግን ንጹሕ እናትነቷን ክደው በውስጧ ሆነው በኑፋቄያቸው የሚቦረቡሯት ብዙዎች ናቸው፡፡

የተሐድሶ መናፍቃኑ እንቅስቃሴ፤ ቤተ ክርስቲያንን ለመለወጥ ወራጁ ውኃ ላይ ሳይሆን ምንጩ ላይ መሥራት ነው፤ በሚል ስልት፤ ምንጮች ናቸው የሚሉትን በመለየት ስስ ብልቶች ያሏቸውን መርጠው እየሠሩ ነው፡፡ በእነርሱ አባባል፤ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ወራጁ ውኃ ምእመናን ሕዝበ ክርስቲያኑ፤ ምንጮች ደግሞ፤ ሐዋርያዊ ተልእኮዋን ለማሳካት የዘርፈ ብዙ መንፈሳዊ አገልግሎቶቿ መሠረቶች የሆኑት፤ ገዳማትና አድባራቷ፣ የሊቃውንቷ፣ አገልጋይ ካህናቷና መምህራነ ወንጌሏ መፍለቂያዎች የሆኑት አብነት ትምህርት ቤቶች፣ መንፈሳዊ ኰሌጆቿ፣ የካህናት ማሠልጠኛዎቿ፣ መምህራኑና ደቀመዛሙርቱ፣ በየደረጃው የሚገኘው የቤተክህነት አስተዳደር ነው፡፡ ሰንበት ት/ቤቶች፣ መንፈሳውያን ማኅበራትና ጽዋ ማኅበራት ሁሉ የዚህ ስልታቸው ማስፈጸሚያ ዒላማዎቻቸው ናቸው፡፡

በእነዚህ ምንጮች ውስጥ ኦርቶዶክሳዊ መስለው ሠርገው እየገቡ፣ ለቤተ ክርስቲያን ተቆርቋሪ ሆነው በመታየት፣ በመዋቅሯ ውስጥ ቦታ እየያዙ የተሠወረ ሤራቸውን በስልት ለማስፈጸም ጥረት እያደረጉ ነው፡፡ ቀስ በቀስ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ሥርዐት፣ መዋቅራዊ አሠራርና መመሪያ እየጣሱ የትምህርት ጉባኤያቱን ኦርቶዶክሳዊ ላህይና ይዘታቸውን እየቀየሩ ነው፡፡ ከዚህ ቀደም በዐደባባይ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን «አሮጊቷ ሣራ መታደስ መለወጥ አለባት» እያሉ ሲያውኳት እንዳልቆዩና ለይቶላቸው እንዳልወጡ ሁሉ፤ አሁን ደግሞ በውስጧ ሆነው ተቆርቋሪ መስለው፤ «ኦርቶዶክስ እውነተኛ ቤተ ክርስቲያን ነበረች፤ ነገር ግን የተጫኑባት ገለባዎች አሉ፡፡ ስለዚህ ተሐድሶ ያስፈልጋታል፤ የጥንቷን ቤተ ክርስቲያን መመለስ አለብን» እያሉ በ«ምናለበት» ስብከት እየደለሉ በማታለል ለሃይማኖቱ ግድ የለሽ ምእመን ለመፍጠር ይተጋሉ፡፡

ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ የባሕርይ አምላክነት፣ ነገረ ማርያም፣ ነገረ ቅዱሳን፣ ጾም፣ ጸሎት፣ ስግደት... ወዘተ እንዲነሣባቸው አይፈልጉም፡፡ ስለ እነዚህ ጉዳዮች ማስተማር ለሕይወት የማይጠቅም እንደሆነ በመቀስቀስ ከምእመናን ዘንድ ማስረሳትና ሳያውቀው ለተሐድሶ ኑፋቄ ቅሰጣና የስሕተት ትምህርት ልቡን በመስጠት ተገዢ የሆነ ትውልድ መፍጠር በገሀድ የሚታይ ጥረታቸው አካል ነው፡፡

ሕዝበ ክርስቲያኑ በአባቶቹ ላይ ያለው እምነትና ተስፋ እንዲሸረሸር፣ አሠረ ክህነቱን፣ ሥርዐተ ምንኩስናን፣ የቤተክርስቲያኒቱን አስተዳደር እንዲጠላ በዚያው ተገፍቶ ጭራሹን ከቤተ ክርስቲያን እቅፍ እንዲወጣ ወይም እንዲኰበልል ለማድረግ የተለያዩ ዘዴዎችን እየተጠቀሙ ይሠራሉ፡፡

የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ትምህርተ ሃይማኖት፤ የዶግማና ሥርዐቷን ድንበር ለማጥፋት፤ መዋቅራዊ የአሠራር ሥርዐቷንና መመሪያዋን በድፍረት እስከመጣስ እየደረሱ ይታያል፡፡ እነዚህን ሁሉ የስሕተት ትምህርቶቻቸውን ለማሠራጨት፤ አድራሻና ባለቤት በሌላቸው የኅትመት ውጤቶች፤ መጻሕፍት፣ በራሪ ወረቀቶች ፣ የድምፅ ወይም የምስል ወድምፅ ካሴቶች ጭምር ይጠቀማሉ፡፡

ይህ የተሐድሶ ኑፋቄ እንቅስቃሴ ከግለሰብ ወደ ቡድን፣ ከቡድን ወደ ማኅበር ወይም ድርጅት ከዚያም ወደ ብዙ ድርጅቶች እያደገ መጥቷል፡፡ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ሐዋርያዊ ተልእኮ ለማደናቀፍና መንፈሳዊ አገልግሎቷን በማወክ ልጆቿንም ለማስኰብለል የሚደረገው ርብርብ ከፍተኛ ነው፡፡

በሕገ መንግሥታዊው ሥርዐታችን አንድ ዜጋ የፈለገውን እምነት የመከተል መብቱ የተረጋገጠ ነው፡፡ ሆኖም በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ስም እና ሽፋን በውስጧ ሆኖ እምነቷን፣ ሥርዐትና ትውፊቷን መጣስ እንዲሁም ከመመሪያዋ ውጪ መንፈሳዊ አገልግሎቷን ማወክ፣ ምእመናኗን እያሳሳቱ ማስኰብለል ሕጋዊ ተግባር እንዳልሆነ ሁሉም የሚገነዘበው ጉዳይ ነው፡፡ ስለዚህ የተሐድሶ ኑፋቄን ሤራ ምንነትና ሊያስከትል የሚችለውን ጥፋት በትክክል መረዳት ያስፈልጋል፡፡

በክርስቶስ ደም ተመሥርታ በእግዚአብሔር ቸርነት በቀደሙት ቅዱሳን አባቶች መንፈሳዊ ተጋድሎ እዚህ የደረሰች ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ባለአደራዎች የሆኑ ብፁዓን አባቶቻችን ዛሬም ታላቅ ሓላፊነት አለባቸው፡፡ የተሐድሶ እንቅስቃሴ አንዱ ስልት በአባቶችና በልጆች መካከል መለያየትን መዝራት እንደሆነ ልብ ሊሉት ይገባል፡፡ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ተሸሽገው መዋቅሯን ሽፋን አድርገውም ሆነ መልካም ስሟን እየተጠቀሙ ነገር ግን በስውር ተልእኮ ሤራቸውን ለማስፈጸም ቀን ከሌሊት እየተጉ ላሉት አመቺ የሆኑ ክፍተቶችን በጥንቃቄ መድፈን አለባቸው፡፡ በማናቸውም የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ጉዳዮች የቅዱስ ሲኖዶስን መንፈሳዊ ልዕልናና ሓላፊነት ማስከበር፣ ውሳኔዎቹን ማስፈጸም፣ የቤተ ክርስቲያንን መዋቅራዊ አሠራርና መመሪያዎች ተግባራዊነት መከታተል፣ ውጤታማ ማእከላዊ አሠራርን ማስፈን ይገባል፡፡

የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ቀኖናዋና ሕግጋቷ ተጠብቆ ዘርፈ ብዙ መንፈሳዊ አገልግሎቷ በተሳካ ሁኔታ እንዲከናወን በቁርጠኛነት መቆም አለባቸው፡፡በየደረጃው ያሉ የቤተ ክርስቲያን አባቶች ሊቃውንትና አገልጋዮች፤ ቆሞሳት፣ ቀሳውስት፣ ዲያቆናት፣ ሰባክያነ ወንጌል፣ ዘማርያን ሁሉ፤ በውጭም ሆነ በውስጥ ተደራጅቶ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን እውነተኛ ልጆች ምእመናንን ለመበተን ያለመታከት እየሠራ ያለውን የተሐድሶ ኑፋቄ እንቅስቃሴ ለመግታት ሃይማኖታዊ አደራና ሓላፊነታቸውን ለመወጣት መንቃት ይገባቸዋል፡፡ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ላይ የተቃጣው የተሐድሶ ሤራ አይመለከተኝም ወይም አላውቀውም በሚል ተገልለን የምንቆይበት ጉዳይ አይደለም፡፡ በመንፈስ ቅዱስ ጥበብ፣ በጾም በጸሎት በመትጋት፤ ምእመናንን መጠበቅ፣ ትምህርተ ሃይማኖቷን ስብከተ ወንጌልን ጠንክሮ ማስተማር፣ ሥርዐቷን፣ ትውፊቷንና ታሪኳን ምእመናን በሚገባ እንዲረዱት ማድረግ ይጠበቅባቸዋል፡፡

የሰበካ ጉባኤያቱን እንቅስቃሴና አደረጃጀት፣ የሰንበት ት/ቤቶችን የዕለት ተዕለት አገልግሎትና ሒደት መከታተል፤ የገዳማትና አድባራቱን እንቅስቃሴ በቅርብ ማወቅ፤ የአብነት ት/ቤቶቻችንን ሁኔታ ድክመትና ጥንካሬ መገንዘብ፣ ለሚፈጠሩ ችግሮች በሚመለከታቸው የቤተክርስቲያኒቱ አካላትም ሆነ በየሐላፊነት ደረጃቸው መጠን በወቅቱ መፍትሔ መስጠት ያስፈልጋል፡፡

ሰንበት ት/ቤቶቻችንና የዓውደ ምሕረት ጉባኤያትን ማጠናከር ስብከተ ወንጌሉን ማስፋፋት ቀሳጮች ገብተው ስውር ተልእኰአቸውን ለማስፈጸም እንዳይጠቀሙበትና ጉዳት እንዳያስከትሉ በቅርብ መቆጣጠር ተገቢ ነው፡፡

የቤተክርስቲያኒቱን መንፈሳዊ አገልግሎት ለመደገፍና ለማጠናከር ሥርዐቷንና መመሪያዋን አክብረው የተቋቋሙ መንፈሳውያን ማኅበራት ለዚህ የተሐድሶ ኑፋቄ እንቅስቃሴ በማወቅም ይሁን ባለማወቅ ሰለባ እንዳይሆኑ ከፍተኛ ጥንቃቄ ሊያደርጉ ይገባል፡፡ አባላቱ ለዚህ የቅሰጣ ተግባር እንዳይጋለጡ መከታተል፣ በትምህርተ ሃይማኖት የሚጠነክሩበትንና በመንፈሳዊ ሕይወት የሚያድጉበትን መንገድ ማመቻችትና ጠንክሮ መሥራት አለባቸው፡፡ ጽዋ ማኅበራትም የተሐድሶ ኑፋቄው ስውር ተልእኮ ዒላማ መሆናቸውን ተገንዝበው የትምህርት ሥርዐታቸውንና የአገልግሎት ሒደታቸውን ሁሉ፤ በቤተ ክርስቲያን ሥርዐት፣ በአባቶች ትክክለኛ ትምህርትና የቅርብ ክትትል መሠረት እንዲያከናውኑ ያስፈልጋል፡፡

የተሐድሶ ኑፋቄው ያልተቋረጠ ጥቃት ዋነኛ ዓላማ፤ ምእመናንን ከእናት ቤተ ክርስቲያን እቅፍ በማስኰብለል የበግ ለምድ ለለበሰ ተኩላ አሳልፎ መስጠት ነው፡፡ ከዚያም ባሻገር ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ሕልውና ለማሳጣት በሚደረገው የጥፋት ተልእኮ ማሰለፍ ነው፡፡ ምእመናን በማወቅም ሆነ ባለማወቅ እናታቸውን ለተሐድሶ ኑፋቄ ሤራ አሳልፈው ላለመስጠት ወይም ሕልውናዋን ለማሳጣት በሚደረገው የጠላት ሤራ ላለመሰለፍ መጠንቀቅ አለባቸው፡፡ የቅድስት ቤተክርስቲያናቸውን ትክክለኛ ድምፅ በጥንቃቄ ለይተው በመገንዘብ በእምነታቸው ጸንተው ሊቆሙ ይገባል፡፡

ቅድስት ቤተክርስቲያናችንን ከተሐድሶ ኑፋቄ ሤራና የጥፋት ተልእኮ መጠበቅ፣ በኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ሃይማኖታችን ጸንተን መገኘት የሁላችንም ሓላፊነት ነው፡፡ በቤተ ክርስቲያንም ሆነ በእግዚአብሔር ዘንድ ከተጠያቂነት ለመዳን እንንቃ፡፡


እንደ እግዚሐብሔር መልካም ፍቃድ ማህበረ ቅዱሳን በተሐድሶ ዙሪያ ያዘጋጀውን ‹‹የተሐድሶ መናፍቃን ዘመቻ በኢትዮጵያ ቤተክርስትያ ላይ›› መፅሀፍ ስካን አድርገን በpdf መልክ መፅሀፉን አግኝተው ማንበብ ላልቻሉ ሰዎች ራሳቸውን ፤ ቤተሰባቸውን እና ቤተክርስትያንን ነቅተው እንዲጠብቁ ብሎጋችን ላይ post አድርገነዋል ፡፡



አርዕስት፡-‹‹የተሐድሶ መናፍቃን ዘመቻ በኢትዮጵያ ቤተክርስትያ ላይ››


አዘጋጅ፡- የማህበረ ቅዱሳን ዶክመንቴሽን ክፍል
የታተመበት ጊዜ፡- ሚያዚያ 2003
የገፅ ብዛት:- 103
Soft Copy Size:- 20 MB
ዋጋ:- 15 ብር

 ‹‹እኛ ይህን መፅሀፍ እርስዎ ጋር በማድረስ ሀላፊነታችንን ተወጥተናል እርስዎ ላላነበቡት እንዲያነቡት በማድረግ ሃላፊነትዎን ይወጡ፡፡››

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

‹‹ሀሰት አንናገር እውነትን አንደብቅም››
 

2014 ኦክቶበር 13, ሰኞ

‹ቀራንዮ፣ መድኃኔዓለም፣ ካህናቱ›

                                                                                  
ቅዱስ ጳውሎስ ተከስሶ በቂሣርያው ገዥ በፊስጦስ ፊት በቀረበ ጊዜ አይሁድ ለብቻቸው ቀርበው በቅዱስ ጳውሎስ ላይ ይፈርድበት ዘንድ ጎትጉተውት፣ እነርሱ ማስረጃ ያሉትንም አቅርበውለት፣ ሕጋቸውንም ጠቅሰው ማሳመኛ አቅርበውለት ነበር፡፡ አሕዛባዊው ገዥ ፊስጦስ ግን እግዚአብሔርን እናውቃለንም፣ እንፈራለንም ከሚሉት አይሁድ ተሽሎ ያሉትን ከማድረግ ራሱን ከለከለ፡፡
ከጥቂት ቀናት በኋላ ንጉሥ አግሪጳና በርኒቄ ወደ እርሱ በመጡ ጊዜ ጉዳዩን አቀረበላቸው፡፡ ፊስጦስ አይሁድ ያቀረቡትን ስሞታ፣ ውትወታና ክስ ተቀብሎ በቅዱስ ጳውሎስ ላይ ያልፈረደበትን ምክንያት ለአግሪጳ ሲገልጥለት ‹‹ተከሳሹ በከሳሾቹ ፊት ለፊት ሳይቆም፣ ለተከሰሰበትም መልስ ይሰጥ ዘንድ ፈንታ ሳያገኝ፣ ማንንም ቢሆን አሳልፎ መስጠት የሮማውያን ሥርዓት አይደለም›› ብሎ መሆኑን ነግሮታል (የሐዋ.25÷16)፡፡
ይህ በሮማውያን ዘመን እጅግ የታወቀውን ራስን በእኩል ደረጃ የመከላከል መብት በተመለከተ ሮማዊው ታሪክ ጸሐፊ አፒያን (95-165ዓም) በጻፈው Civil War በተሰኘው መጽሐፉ (3:54) ላይ ‹‹የምክር ቤት አባሎች፣ ሕጉ የተከሰሰ ሰው የተከሰሰበትን ሰምቶ በእርሱ ላይ ከመፈረዱ በፊት መልስ የመስጠት መብት አለው ይላል›› ሲል አሥፍሮት ነበር፡፡ ፊሊክስ የጠቀሰው ይኼንን ነው፡፡ አበው በትርጓሜያቸው ‹አሕዛብ ፍርድ ይጠነቅቃሉ›› ሲሉ የመሰከሩት እንዲህ ያለው የሮማውያንን ሕግ ነው፡፡ ለዚህ ጥንቁቅ የፍርድ ሥርዓትም ሲሉ አያሌ የሮማውያንን የፍተሕና የፍርድ ሐሳቦች በቤተ ክርስቲያን የፍትሕ ሥርዓት ውስጥ (በቀኖና) እንዲገቡና እንዲሠራባቸው አድርገዋል፡፡


ይህንን የምትተረጉምና የምታስተምርን ቤተ ክርስቲያን እንወክላለን የሚሉ ሰዎች ናቸው ሰሞኑን ተሰብስበው ተከሳሹ በሌለበት ፍርድ ሲሰጡ ያየናቸው፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን ተሳሳተ ተብሎ እንኳን ቢሆን ቤተ ክርስቲያኒቱ ለአርዮስና ለንስጥሮስ፣ ለመቅዶንዮስና ለሰባልዮስ የሰጠችውን መብት ቤተ ክህነቱ ለማኅበረ ቅዱሳን ሊነፍገው አይገባም ነበር፡፡ በቀደዱላቸው ቦይ መንጎድ፣ ተጠልቷል ብለው በሚያስቡት ላይ መፍረድ ሃይማኖታቸው የሆነ፤ ፓትርያርኩን ምን ያስደስታቸዋል እንጂ የትኛው እውነት ነው ለሚለው የማይጨነቁ ሰዎች የክስ መዓታቸውን ሲያዘንቡ ማኅበሩ መልስ እንዲሰጥ ዕድል ሊሰጠው ይገባ ነበር፡፡ ነገር ግን ሰዎቹ ለበዓሉ የሚስማማውን ቀለም ትተው ለባለ ሥልጣኑ የሚስማማውን ቀለም መረጡ፡፡ ሊቁ ክፍለ ዮሐንስ ‹ካህን ከመሆን እረኛ መሆን ይሻላል› እንዳለው ከቤተ ክህነት ፊልክስ ተሽሏል፡፡
ፊሊክስ ለቅዱስ ጳውሎስ፣ ሠለስቱ ምእት ለአርዮስ፣ ማኅበረ ኤፌሶን ለንስጥሮስ የሰጡትን ዕድል ቤተ ክህነቱ ለማኅበረ ቅዱሳን ለመስጠት ፈቃደኛ አልሆነም፡፡ ለምን?
ሰዎቹ እውነቱን ለመጋፈጥ ዐቅም አንሷቸዋል ማለት ነው፡፡ የሚሉት ነገር የሆኑ አካላትን ስለማስደሰቱ እንጂ እውነት ስለመሆኑ ርግጠኞች አይደሉም፡፡ ስለዚህም ተከራካሪያቸውን ለመስማትና የእነርሱ ‹እውነት› ሲሞገት ለማየት ዐቅም ያንሳቸዋል፡፡ ወይም ደግሞ
ከክርክሩ በፊት ውሳኔውን ወስነው ጨርሰዋል፡፡ ፓትርያርክ አቡነ ቴዎፍሎስን ለደርግ አሳልፈው የሰጡት የቤተ ክህነት ሰዎች እንዲህ ነበር ያደረጉት፡፡ ፓትርያርኩን አሳልፈው ሰጥተዋል፡፡ ውሳኔውን ወስነዋል፡፡ ነገር ግን ለውሳኔው ምክንያት መፈለግ ነበረባቸው፡፡ ስለዚህም አቡነ ቴዎፍሎስ ሠሩ ያሏቸውን ጥፋቶች ለብቻቸው ተሰብስበው፣ ‹በደላቸውን› ዘርዝረው፣ እርሳቸው መልስ ሊሰጡ በማይችሉበት ሁኔታ ለደርግ አስተላለፉ፡፡ እነዚህ ሰዎች ለብቻቸው መሰብሰብ የፈለጉት፣ የፓትርያርኩንም መልስ የመስጠት መብት የነፈጉበት አንዱ ምክንያት ፓትርያርኩ በሚሰጡት መልስና በሚያቀርቡት ማስረጃ እውነታቸው ነፋስ ያየው ገለባ እንዳይሆንባቸው ነው፡፡ ወይም
እነዚህ ሰዎች የራሳቸውን ሥራ አይደለም እየሠሩ ያሉት፡፡ ቤተ ክርስቲያኒቱን ሲበጠብጡ የኖሩት ካህናተ ደብተራ (ከቤተ ክህነት ደመወዝ እየወሰዱ ለቤተ መንግሥት ሲሠሩ የኖሩ ካህናት ነን ባዮች) ዋናው መለያቸው የሚሠሩት የራሳቸውን ሥራ አለመሆኑ ነው፡፡ የመለካዊነት ጠባይ ስላላቸው ሌሎች ተናገሩ የሚሏቸውን ይናገራሉ፣ ፈጽሙልን የሚሏቸውን ይፈጽማሉ፤ አውግዙልን የሚሏቸውን ያወግዛሉ፤ አጽድቁልን የሚሏቸውንም ያጸድቃሉ፡፡ የሚሠሩት ሥራ የላኳቸውን ሰዎች ማርካቱን እንጂ የሚያስከትለውን ነገርና የሚያስከፍለውን ዋጋ አያውቁትም፡፡ እነዚህ ነበሩ አባ በጸሎተ ሚካኤልን ያሰደዱት፣ እነዚህ ነበሩ አባ ፊልጶስን ያንከራተቱት፣ እነዚህ ነበሩ እጨጌ ዕንባቆምን ለልብነ ድንግል ከስሰው ምንም ባላጠፋው ጥፋት ‹ጉንጽ› በተባለው ዓለም በቃኝ እስር ቤት ያሳሠሩት፤ በኋላም ለሀገሪቱ ጥፋትን ያመጡት፡፡ ጥይት የመታው ሰው ተናድዶ ‹‹ምነው እንዲህ ታበላሸኝ›› ቢለው ‹‹እባክህ እኔ አይደለሁም፣ እኔ ተተኮስኩ እንጂ ተኳሹ ሌላ ነው፤ እኔ መልክተኛ ነኝ›› አለው፡፡ ‹‹ተኳሹ የት አለ?›› ቢለው ‹‹እርሱማ አይታይም ተደብቆ ነው የሚተኩሰው፤ እርሱ ስለሚደበቅኮ ነው እኔ የመጣሁት›› አለው ይባላል፡፡
ወይም እነዚህ ሰዎች ስንፍናቸውን የሚያሳይባቸውን፣ ድካማቸውን የሚገልጥባቸውን፣ ሊያጠፉት ወድደዋል፡፡ ሰውዬው ዶሮውን በጦም አርዶ ለምን አረድከው ቢባል ‹‹እሱ ነው ጠዋት እየተነሣ መንጋቱን የሚያሳብቅብኝ፣ አርፌ እንዳልተኛበት፡፡እርሱ ባይጮህ ኖሮ መንጋቱን ማን ያውቅ ነበር? ተኛህ ብሎስ ማን ይከሰኝ ነበር›› አለ አሉ፡፡ ከመንቃት ይልቅ ማንቂያውን ማጥፋት፡፡ የ13ኛው መክዘ የደቡብ ሐዋርያ አቡነ አኖሬዎስ ታላቁ በካህናተ ደብተራ ተከስሶ ወደ ንጉሥ ሰይፈ አርእድ የቀረበበት ክስ አስቂኝ ነበር፡፡ ‹‹ከንጉሡ የሚበልጥ ቤተ ክርስቲያን ሠርቷል›› ነበር የተባለው፡፡ ጉዳዩን ሊያጣራ የሄደው የጉዳም አለቃ ያገኘው ቤተ ክርስቲያን ግን እንደተባለው አልነበረም፡፡ ነገር ግን ከክሱ ንጹሕ መሆኑ ቅጣቱን አላስቀረለትም፡፡ ከገዳሙ ወጥቶ በወለቃ በረሃ እንዲከራተት ሆኗል፡፡ ምናለ ከንጉሡ የሚበልጥ ቤተ ክርስቲያን ቢሠራ? የሚያስመሰግነው እንጂ የሚያስነቅፈው አልነበረም፡፡ ለካህናተ ደብተራ ግን ይኼ ስንፍናቸውን ይገልጠዋል፣ እንደ አውራ ዶሮውም መተኛታቸውን ያሳይባቸዋል፡፡
ቅዱስ ሲኖዶሱ አሁን መስቀለኛ መንገድ ላይ ቆሟል፡፡ የሚቀርቡት ክሶች ለምን ቀረቡ ማለት አይቻልም፡፡ ነገር ግን በአይሁድ አደባባይ ፍርድ ሲጓደል፣ እንደ ጲላጦስ ሚስት የሚያስጠነቅቅ ያስፈልጋል፡፡ ገለልተኛ አካል አቋቁሞ የተባሉትን ያጣራ፡፡ ራሱ የማኅበሩ አመራር ለተከሰሰበት መልስ ይስጥ፡፡ አሕዛባዊው ፊሊክስ ለቅዱስ ጳውሎስ የሰጠውን መብት ሲኖዶሱ ለማኅበሩ መስጠት አለበት፡፡ ተጣርቶ በተገኘው ማስረጃና ምስክር መሠረት ውሳኔ ይሰጥ፡፡ ጥፋተኛው ይታረም፤ እውነተኛው ይገለጥ፡፡
በዐፄ ኃይለ ሥላሴ ዘመን ቀራንዮ መድኃኔዓለም አለቅነት ተሾመው የሄዱትን አባት ካህናቱ አስቸገሯቸው፡፡ ለጥቂት ጊዜ የተላኩበትን ሊሠሩ ሞከሩ ግን አልሆነም፡፡ በመጨረሻም ለንጉሡ እንዲቀይሯቸው አመለከቱ፡፡ ንጉሡም ምነው ምን ገጠመህ? ቢሏቸው ‹‹ካህናቱም ካህናቱ፣ ቀራንዮም ቀራንዮ፣ መድኃኔዓለምም መድኃኔዓለም›› አሉ ይባላል፡፡ ሰቃይ ተሰቃይና የመስቀያ ቦታ አንድ ሲገናኙ ያ ነው ክፉ ዘመን፡፡
ማኅበሩን እንደ ተቋም፣ እንደ ጽ/ቤትና እንደ ድርጅት ማፍረስ ቀላል ነው፤ እንደ አስተሳሰብ፣ እንደ አመለካከት፣ እንደ የአገልግሎት መሥመርና አተያይ ግን ማፍረስ አይቻልም፡፡ ዛሬ ማኅበሩን በማፍረስ የሚጀመረው አጥር ንቅነቃ ግን መጨረሻው ሲኖዶሱን በማደንበሽ እንዳይጠናቀቅ ያሰጋል፡፡ ባለቤቱን ካልናቁ ነውና፡፡ 

                                   በአውሮጳ   የካህናት አንድነት ማኅበር ሊቋቋም መሆኑ ታወቀ በ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከመላዋ አውሮጳ   የተውጣጡ ካህናት፡” የ...