2015 ጃንዋሪ 10, ቅዳሜ

የታክሲ ሾፌሮች፤ ረዳቶችና ተራ አስከባሪዎች ጉባኤ 8ኛ ዓመት ተከበረ


አትም ኢሜይል
ጥር 1 ቀን 2007 ዓ.ም.
በደመላሽ ኃይለ ማርያም
የብርሃናተ ዓለም ቅዱስ ጴጥሮስ ወጳውሎስ ቤተ ክርስቲያን ፍሬ ሃይማኖት ሰንበት ትምህርት ቤት ለታክሲ ሹፌሮች፣ ተራ አስከባሪዎችና ረዳቶቻቸው አገልግሎት እንዲሰጥ የመሠረተውን ጉባኤ 8ኛ ዓመት አስመልክቶ ታኅሣሥ 25 እና 26 ቀን 2007 ዓ.ም. “ለፍቅርና ለመልካም ሥራ እንድንነቃቃ እርስ በርሳችን እንተያይ” በሚል የመጽሐፍ ቅዱስ መሪ ቃል በቤተ ክርስቲያኑ ቅጥር ግቢ አባላቱና በርካታ ምዕመናን በተገኙበት ተከበረ፡፡

ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ የደብሩ አስተዳዳሪ እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በመርሐ ግብሩ ላይ የተገኙ ሲሆን፤ የታክሲ አገልግሎት ሥራን በሚመለከት ከቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ጋር አያይዘው “ኖላዊ” በሚል ርዕስ በተጋባዥ መምህራን ትምህርተ ወንጌል ተሰጥቷል፡፡

የታክሲ ሹፌሮች፣ ረዳቶቻቸው እና ተራ አስከባሪዎች ከማኅበረሰቡ ጋር ያላቸውን በጎ ያልሆነ ግንኙነት ለማሻሻል እና በክርስትና ሕይወታቸው ምሳሌ የሚሆኑ ዜጎችን ማፍራት እንዲቻል፤ እንዲሁም በእነሱ ቸልተኝነት እና ጥድፊያ በመኪና አደጋ እየጠፋ ያለውን የሰውን ሕይወት ለመቀነስ ታስቦ ጉባኤው መመስረቱን የሰንበት ትምህርት ቤቱ ሰብሳቢ ዲያቆን ያሬድ ያስረዳል፡፡

ዲያቆን ያሬድ አክሎም “የአባላቱን ቁጥር ከዚህ የበለጠ በማሳደግና በጉባኤው ውስጥ በማካተት ትምህርተ ሃይማኖት እንዲማሩ፤ የቤተ ክርስቲያኒቱን ዶግማ፤ ቀኖና እና ትውፊት እንዲያውቁ፤ በሥነ ምግባር የታነጹና ሥርዓት አክባሪዎች ሆነው ከማኅበረሰቡ ጋር ያላቸውን ግንኙነት ጤናማ ለማድረግ ከፈጣሪ ጋር እንጥራለን” ብሏል፡፡

ከተጋባዥ እንግዶች መካከልም የአዲስ አበባ ትራፊክ ፖሊስ ጽ/ቤት የሕዝብ ግንኙነት ሓላፊ ም/ኢንስፔክተር አሰፋ መዝገቡ ድንገተኛ፤ ለንስሐ እና ለኑዛዜ የማያበቃውን በትራፊክ አደጋ የሚደርሰውን ሞት ለመከላከል ምእመናን እና የታክሲ ሹፌሮች ጥንቃቄ እንዲያደርጉ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

በመጪው ዓመት ሃምሳኛ ዓመቱን የሚያከብረው ይህ የፍሬ ሃይማኖት ሰንበት ትምህርት ቤት እየሠራ ያለው ሥራ እጅግ በጣም ሊበረታታ የሚገባውና በሌሎችም ሰንበት ትምህርት ቤቶች ሊለመድና ሊሰራበት እንደሚገባ ጉባኤውን የተከታተሉ ምእመናን አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡

2015 ጃንዋሪ 9, ዓርብ

አባቶችና ምእመናን ‹‹ሸኚው ሸኚ ሲያጣ›› እስኪሉ ድረስ በመጣደፉ በእጅጉ ያዘኑበት የ106 ዓመት አረጋዊው የብፁዕ አቡነ አረጋዊ ሥርዐተ ቀብር ተፈጸመ



funeral of Abune Aregawi
ፎቶ: ማኅበረ ቅዱሳን

ዜና ሕይወቱ ወዕረፍቱ ለብፁዕ አቡነ አረጋዊ

ብፁዕ አቡነ አረጋዊ በ1901 ዓ.ም. ወልደው በፀለምት /ሰሜን ጎንደር/ ተወልደው ዕድሜአቸው ለትምህርት ሲደርስ ትምህርት ቤት ገብተው ንባብና ዳዊት እንዲኹም እስከ ፀዋትወ ዜማ አጠናቅቀው ከብፁዕ አቡነ ቄርሎስ ግብፃዊ ማዕርገ ዲቁናና ማዕርገ ቅስና ተቀብለዋል፡፡
በዋልድባ አብረንታንት ገዳም ገብተው ለዘጠኝ ዓመታት ያኽል (ከ1933 – 42 ዓ.ም.) ሥርዓተ ገዳሙን ከአጠኑና በግብዝና ከአገለገሉ በኋላ በዚኹ ገዳም መዓርገ ምንኵስናን ተቀብለዋል፡፡ ትምህርታቸውን በመቀጠል በሰሜን ምዕራብ ትግራይ በሚገኘው በደብረ ዓባይ ገዳም የደብረ ዓባይ መዝገበ ቅዳሴ ዜማ ተምረው በመምህርነት በቅተዋል፡፡
በ1943 ዓ.ም. በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ባስልዮስ ፈቃድና ትእዛዝ በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ገዳማትን እንዲያገለግሉ ተልከው ለአራት ዓመታት ያኽል አገልግለዋል፡፡ አኹንም በቅዱስ ፓትርያርኩ ፈቃድ ወደ ግብጽ ሔደው ለ16 ዓመታት ያኽል ነገረ መለኰትን በዓረብኛ ቋንቋ አጥንተው ተመርቀዋል፡፡funeral of Aba Aregawi 
ወደ ኢትዮጵያ ከተመለሱ በኋላ በሱዳን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን በሓላፊነት ለማገልገል ተልከው ለስድስት ዓመታት ያኽል በአስተዳዳሪነት ሠርተዋል፡፡ በዚኹ ሓላፊነት ሳሉም በ1968   ዓ.ም. ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት የኢትዮጵያ ፓትርያርክ ኹነው በተሾሙ ጊዜ በሱዳን የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንን ወክለው በመምጣት ለበዓሉ ከፍተኛ አስተዋፅኦ አድርገዋል፡፡
በ1972 ዓ.ም. በቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ወደ ሀገራቸው ተመልሰው በቅዱስ ፓትርያርኩ ፈቃድ የመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ሊቀ ሥልጣናት በመኾን አገልግለዋል፡፡
በጥቅምት ወር 1983 ዓ.ም. በሱዳን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳስ ኾነው በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ አንብሮተ እድ ተሾመዋል፡፡
ከመጋቢት 1985 ዓ.ም. ጀምሮ የኢሉባቦርና የጋምቤላ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ኾነው ለአንድ ዓመት ያኽል ሠርተዋል፡፡
ከየካቲት 1986 ዓ.ም. ጀምሮ የምስካየ ኅዙናን መድኃኔ ዓለም ገዳምና ት/ቤት የበላይ ሓላፊ ኾነው አገልግለዋል፡፡
ከሐምሌ 1968 ዓ.ም. ጀምሮ የሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ኾነው አገልግለዋል፡፡
ከግንቦት 1992 ዓ.ም. ጀምሮ ወደ አዲስ አበባ ተዛውረው የመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል የበላይ ሓላፊ ኾነው ሲሠሩ ቆይተዋል፡፡
በመጨረሻም በዚኹ ሥራ ላይ ሳሉ ባደረባቸው ድንገተኛ ሕመም ምክንያት በሕክምና ሲረዱ ቆይተው ጥር 1 ቀን 2007 ዓ.ም. በተወለዱ በ106 ዓመታቸው ከዚኽ ዓለም በሞተ ሥጋ ተለይተዋል፡፡
funeral of Aba Aregawi03
የቀብራቸው ሥነ ሥርዓትም በዚኹ ዕለት፣ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ባሉበትና የአድባራትና ገዳማት አስተዳዳሪዎች በተገኙበት ሥርዓተ ጸሎተ ፍትሐቱ ከተፈጸመ በኋላ በቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ተፈጽሟል፡፡
ልዑል እግዚአብሔር የብፁዕ አቡነ አረጋዊን ነፍስ ዕረፍተ መንግሥተ ሰማያትን ሰጥቶ በአብርሃም በይሥሐቅ በያዕቆብ አጠገብ ያኑርልን፤ በማለት እንሰናበታቸዋለን፡፡
About these ads

ሰበር ዜና – ብፁዕ አቡነ አረጋዊ ዐረፉ



  • ሥርዐተ ቀብሩ ዛሬ በ9፡00 በመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ይፈጸማል
His Grace Abune Aregawi
በተባሕትዎአቸውና በተመሰገነው ምንኵስናቸው የሚታወቁት የመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል የበላይ ጠባቂ ብፁዕ አቡነ አረጋዊ ዐረፉ፡፡ ብፁዕነታቸው ዛሬ፣ ዓርብ ጥር ፩ ቀን ፳፻፯ ዓ.ም. ጠዋት ያረፉት ለተሻለ ሕክምና በገቡበት ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ነው፡፡
ብፁዕነታቸውን ለኅልፈት ያደረሳቸው፣ ከአንድ ወር በፊት ለሐዋርያዊ ተልእኮ ወደ ደቡብ ሱዳን በሔዱበት ወቅት ያጋጠማቸው ቢጫ ወባ በኩላሊታቸውና በሳምባቸው ላይ ያስከተለው ጉዳት ነው፡፡
ከጉዟቸው መልስ ‹‹እኔ ንግግሬ ከእግዚአብሔር ጋራ ነው›› በማለት ያለሕክምና ርዳታ ለኹለት ሳምንት ያኽል በተዘጋ ማረፊያቸው የቆዩት ብፁዕነታቸው፣ በብፁዓን አባቶችና በቅርብ ወዳጆቻቸው ተማኅፅኖ በዘውዲቱ ሆስፒታል እና በሳንቴ የጤና ማእከል በተደረገላቸው ከፍተኛ ክትትል የተጎዳው ኩላሊታቸው አገግሞ እስከ ዛሬ ጠዋት ድረስ በተሻለ ኹኔታ ላይ ይገኙ እንደነበር ተጠቅሷል፡፡
ይኹንና ከዕድሜ አንጋፋነታቸው ጋራ ሕመሙ በሳምባቸው ላይ ባደረሰው ጉዳት የተፈጠረው ኢንፌክሽን ለኅልፈት እንደዳረጋቸው ተመልክቷል፡፡
በቅርበት የሚያውቋቸው ወገኖች÷ የዋልድባው መነኰስ ብፁዕ አቡነ አረጋዊ ሀብት ምክር ያላቸው፣ ታሪክ ዐዋቂና የታያቸውን በግልጽ የሚናገሩ መምህር ወመገሥጽ እንደነበሩ ይናገራሉ፡፡
www-st-takla-org-abune-paulos-in-alex-15-july-2007-017
አምስተኛው ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ በግብጽ ሐዋርያዊ ጉብኝት ባደረጉበት ሐምሌ ወር ፲፱፻፺፱ ዓ.ም.፣ ሐምሌ ፰ ቀን በጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ስም በተሠራው ቤተ ክርስቲያን በተገኙበት ወቅት፣ ብፁዕ አቡነ አረጋዊ የቅዱስነታቸውን ንግግር በልሳነ ዓረቢ እየመለሱ አሰምተው ነበር፡፡
የቀደምት ቅዱሳን አበውን ትውፊት በመከተል በግብጽ ገዳማት ለዐሥራ አምስት ዓመታት ያኽል በመቀመጥ ከአኃው መነኰሳት ጋራ መንፈሳቸውን ያስተባበሩት ብፁዕነታቸው፣ ልሳነ ዓረቢን አቀላጥፈው በመናገርም ይታወቃሉ፡፡ የቅድስት ሀገር ተሳላሚ ለመኾን የበቁትም በወጣትነታቸው ማለዳ ሳሉ ነበር፡፡
በፊት ስማቸው ሊቀ ሥልጣናት ገብረ ማርያም ገብረ ሥላሴ ይባሉ የነበሩት ብፁዕነታቸው፣ አቡነ አረጋዊ ተብለው ጥቅምት ፲፰ ቀን ፲፱፻፹፫ ዓ.ም. ኤጲስ ቆጶስነት የተሾሙት በአራተኛው ፓትርያርክ በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ አንብሮተ እድ ነው፡፡
ብፁዕነታቸው ቀድሞ ሊቀ ሥልጣናት በተባሉበት የመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል በበላይ ጠባቂነት ከመወሰናቸው በፊት፣ በሱዳን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ጳጳስ እንዲኹም የጎንደር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በመኾን አገልግለዋል፡፡
የብፁዕነታቸው ሥርዐተ ቀብር ዛሬ፣ ጥር ፩ ቀን ፳፻፯ ዓ.ም. ለረጅም ዓመታት በአገለገሉበት በመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል፣ በ9፡00 እንደሚፈጸም ተገልጧል፡፡
አምላከ ቅዱሳን እግዚአብሔር ለብፁዕ አባታችን ዕረፍተ ነፍስን ይስጥልን፡፡

2015 ጃንዋሪ 2, ዓርብ

“ወብዙኀን ይትፌሥሑ በልደቱ በመወለዱም ብዙዎች ደስ ይላቸዋል” ሉቃ.1፥14



አትም ኢሜይል
ታኅሣሥ 25 ቀን 2005 ዓ.ም.
ዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ
st. tekela
  • በዘመነ ብሉይ የእግዚአብሔር ድምፅና የመልአክ ብሥራት ብርቅ በነበረበት ወቅት ካህኑ ዘካርያስና ቅድስት ኤልሳቤጥ ልጅ መውለድ አጥተው ባረጁበት ዘመን የእግዚአብሔር መልአክ ካህኑ ዘካርያስን እንዲህ አለው፡፡
መልአኩም እንዲህ አለው “ዘካርያስ ሆይ፥ አትፍራ፤ ጸሎትህ በእግዚአብሔር ፊት ተሰምቶአልና፤ ሚስትህ ኤልሣቤጥም ትፀንሳለች፤ ወንድ ልጅንም ትወልድልሃለች፤ ስሙንም ዮሐንስ ትለዋለህ፡፡ ደስታና ሐሤትም ይሆንልሃል፤ በመወለዱም ብዙዎች ደስ ይላቸዋል፡፡ እርሱ በእግዚአብሔር ፊት ታላቅ ይሆናልና የወይን ጠጅና የሚያሰክርም መጠጥ ሁሉ አይጠጣም፤ ከእናቱ ማሕፀን ጀምሮም መንፈስ ቅዱስ ይመላበታል፡፡ ከእስራኤልም ልጆች ብዙዎችን ወደ አምላካቸው ወደ እግዚአብሔር ይመልሳቸዋል፡፡ እርሱም የአባቶችን ልብ ወደ ልጆች፥ የከሓድያንንም ዐሳብ ወደ ጻድቃን ዕውቀት ይመልስ ዘንድ፥ ሕዝብንም ለእግዚአብሔር የተዘጋጀ ያደርግ ዘንድ በኤልያስ መንፈስና ኀይል በፊቱ ይሄዳል፡፡”ሉቃ1፥13-18 ይህ ለመጥምቁ ዮሐንስ የተነገረ ቃል ቢሆንም ወላጆቹ (ካህኑ ዘካርያስና ቅድስት ኤልሳቤጥ) በእግዚአብሔር ፊት ጻድቃን እንደነበሩ በቅዱስ ወንጌል ተገልጿል /ሉቃ.1፥6-7/ እንደዚሁ ሁሉ ካህኑ ጸጋዘአብና ሚስቱ እግዚእ ሐረያ በእግዚአብሔር ሕግና ሥርዓት ይመሩ የነበሩ ደጋግ ክርስቲያኖች ነበሩ፡፡ ይህም ሊታወቅ በትሩፋት ሥራ፣ በጾም፣ በጸሎት፣ በምጽዋት የታወቁ ነበር፡፡ በተለይም የሊቀ መላእክት የቅዱስ ሚካኤል በዓልን ምክንያት በማድረግ ይመጸውቱ ነበር፡፡ የመልአኩም ጥበቃ ባለ ዘመናቸው ሁሉ አልተለያቸውም ነበር፡፡ ጌታችን በቅዱስ ወንጌል ላይ “መልካም ዛፍ ሁሉ መልካም ፍሬን ያፈራል፣” /ማቴ.7፥17/ እንዳለ፣ ለዓለም ሁሉ የወንጌልን ብርሃን የሚያበስር ሐዲስ ሐዋርያ በቅድስናና በክብሩ ከሃያ አራቱ ካህናተ ሰማይ ሃያ አምስተኛ ሆኖ ያመሰገነውን ጻድቅ ወለዱ፡፡ በሰሜን ሸዋ ጽላልሽ ልዩ ስሙ ኢቲሳ በተባለ ቦታ የተወለዱት ጻድቁ ተክለ ሃይማኖት በ12ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የተነሡና የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ትምህርት ከየመን እስከ ኬንያ ከሶማሌ እስከ ሱዳን ድረስ የተስፋፋበትን ወርቃማ ዘመንን ያስገኙ ጻድቅ አባት ናቸው፡፡
“ነገርን ከሥሩ ውኃን ከጥሩ” እንዲሉ የጻድቁን ታሪክ በአጭሩ እንደሚከተለው አቅርበነዋል፡፡

ቅዱሳኑ በትሩፋት ሥራ የተጠመዱ ነበሩ
ልጅ አጥተው ሲያዝኑ ይኖሩ የነበሩት ካህኑ ፀጋ ዘአብና ቅድስት እግዚእ ሐረያ፣ በየወሩ የቅዱስ ሚካኤልን በዓል ያከብሩ ነበርና መጋቢት 12 ቀን የተራበን ሲያበሉ ሞቶሎሚ ንጉሠ ዳሞት ሀገራቸውን ወርሮ ከእነርሱ ደረሰ፡፡ ጸጋ ዘአብም እንደማይምራቸው አውቀው አንከርት ወደሚባለው ባሕር ሮጡ፡፡ ከሞተሎሚ ጭፍሮች አንዱ ተከተላቸው፣ የማይደርስባቸው ሲሆን ሰይፉን ሊወረውርባቸው ቃጣ፡፡ ሰይፉ ከእጁ ተጠቅልላ ቀረች፡፡ በሌላ እጁ ሁለተኛ ሊወረውር ቢቃጣ አሁንም ተጠቅልላ ቀረች፡፡ እሳቸውም እንዳልተዋቸው አይተው ዘለው ከባሕር ገቡ፡፡ ከባሕር ውስጥ ሆነው እንዲህ አያሉ ይጮሁ ጀመረ…” ኀይል የምትሆነኝ ቅዱስ ሚካኤል፣ አምባ መጠጊያ የምትሆነኝ ቅዱስ ሚካኤል፣ ኀይልህ ወዴት ነው? ከኃሊነትህ ወዴት ነው? ተአምራት ማድረግህ ወዴት ነው? እንሆ መሞቻዬ ደረሰ፡፡ ዛሬ የሽብር ቀን ነው፡፡ ዛሬ የመከራ ቀን ነው፡፡ ዛሬ ጥፋት ተፈርዶብኝ፡፡ በበዓልህ ደስ ሳታሰኘኝ ታሳዝነኛለህን? እያሉ ያለቅሱ ጀመረ፡፡ እስመ ለመላእክቲሁ ይኤዝዞሙ በእንቲአከ ከመ ኢትትዐቀፍ በዕብን፤ እግርከ በመንገድህ ሁሉ ይጠብቁህ ዘንድ መላእክቱን ስለ አንተ ያዛቸዋልና፣ እግርህ በድንጋይ እንዳትሰናከል በእጆቻቸውም ያነሡሃል፡፡ እንዲል /መዝ.90፥11/ ቅዱስ ሚካኤል በውስጥ ሆኖ ተቀብሏቸዋል፡፡ “ወባሕርኒ ኮነቶ ከመ ደብተራ ዘድለት ለማኅደር” ይላል ባሕርም እንደ ድንኳን ሆነላቸው “ኦ ፍቁርየ ጸጋ ዘአብ አስመ አነ አዐቅበከ በይነ ዘይወጽእ እምሐቁከ፤ ወዳጄ ጸጋ ዘአብ ሆይ፥ ከአብራክህ ስለሚከፈለው ቅዱስ እጠብቅሃለሁና አትፍራ” አላቸው፡፡ ከዚህ በኋላ በሦስተኛው ቀን አውጥቶ ቤተ ክርስቲያን አድርሷቸዋል፡፡

በሌላ በኩል በሞቶሎሚ ወታደሮች የተማረኩት እግዚእ ሐረያ ለንጉሡ ሚስት ሊያደርጓቸው፣ ከቤተ መንግሥቱ አገቧቸው፡፡ ቅድስት እግዚእ ሐረያ ግን “ጌታዬ ፈጣሪዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ስንፍናዬን ለምን ተመለከትክ፡፡ በንጹሕ ሆኖ የሚያገለግል ባሪያህ ጸጋ ዘአብን ለምን አላሰብከውም አንተን ለሚክዱ ኃጥአን ለሚሆኑ ጠላቶች አሳልፈህ ለምን ሰጠኸኝ ሕግህን ሥርዓትህን ከማያውቅ ከሚያጸይፍ ባሪያ ልጅ ትሰጠኝ ዘንድ ወደድክን? ከዚያም ከንጹሕ አገልጋይህም ቢሆን አንተን ደስ የማያሰኝ ልጅ ካለሆነ ማኅፀኔን ዝጋው እልሃለሁ፡፡ አቤቱ የትድግና ባለቤት ዛሬ በእኔ ላይ ትድግናህን ግለጽ” በማለት ያመለክቱ ነበር፡፡ ጠባቂ መልአካቸው፡- ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ተገልጦ ከሠራዊት ሞቶሎሚ በመንጠቅ በክንፉ ታቅፎ ከዳሞት ዞረሬ በሦስት ሰዓት አደረሳቸው፡፡ በመጋቢት ሃያ ሁለት ቀን ጸጋ ዘአብ ከቤተ መቅደስ ገብተው ሲያጥኑና ስለ እግዚእ ሐረያ ሲለምኑ፣ መልአኩ ቅዱስ ሚካኤል ከቤተ መቅደስ አግብቶ ከዚያ ትቷቸው ወደ ሰማይ ዐረገ፡፡ ገድለ ተክለሃይማኖት ምዕ.12

በዚህ ሁኔታ በእግዚአብሔር ቸርነት፣ በመልአኩ ቅዱስ ሚካኤል ተራዳኢነት ደግም የተገናኙት ሁለቱ ቅዱሳን /ጸጋ ዘአብና እግዚእ ሐረያ/ መጋቢት ሃያ አራት ቀን ከአብራካቸው የሚከፈለውን ጻድቁ ተክለሃይማኖትን ፀነሱ፡፡ እነሆም ታኅሣሥ 24 ቀን ቅዱስ አባታችን ተወለዱ፡፡

“ገድለ ተክለሃይማኖት” የተባለው መጽሐፍ አባታችን ተክለሃይማኖት በተፀነሱበት መጋቢት 24 ቀን ለእናትና አባታቸው እግዚአብሔር ራእይ እንዳሳያቸው ይገልፃል፡፡ ቅድስት እግዚእ ሐረያ ያዩት ራእይ “የብርሃን ምሰሶ ከቤታቸው ውስጥ ቁሞ የሞሶሶው ራስ ከሰማይ ደርሶ በዓለም ያሉ ሕዝብ ሁሉ ነገሥታቱም ጳጳሳቱም በዙሪያው ቁመው እኩሌቶቹም ይሰግዱለታል፤ እኩሌቱቹም እሱን ጥግ አድርገው ይቀመጣሉ፡፡ በሱም ላይ ብዙ አዕዋፍ ተቀምጠውበታል፡፡እኩሌቶቹ ነጫጮች፣ እኩሌቶቹም ቀያዮች፣ እኩሌቶቹ አመድ አመድ ይመስላሉ፡፡ ዝጉርጉርም ናቸው፡፡ በሌላ በኩል ካህኑ ጸጋ ዘአብ ደግሞ በዚሁ ሌሊት ስላዩት ሕልም ለእግዚእ ሐረያ ሲነግሩ እንዲህ ብለዋል፡- “ከምንተኛበት አጎበር ሥር ፀሐይ ሲወጣ፥ስፍር ቁጥር የሌላቸው ብሩሃን ከዋክብት በክንፉ ላይ ተቀምጠው ለዓለሙ ሁሉ ሲያበሩ፣ ከብርሃኑም ብዛት የተነሣ ሀገሩ ሁሉ አበራ፡፡ ይህን ራእይ ዐይቼ ደንግጬ አለቀስኩ”

ከዚህ በኋላ መልአኩ ቅዱስ ሚካኤል የሁለቱንም ህልም ይተረጉሙላቸው ዘንድ ከእግዚአብሔር ተልኳል፡፡ በትርጓሜውም፡- “ከጸጋ ዘአብ ቤት ሲወጣ የታየው ፀሐይ ከአብራኩ የሚከፈለው ልጁ ተክለ ሃይማኖት ነው፡፡ በብርሃኑ ከምእመናን ላይ የኃጢአትን ጨለማ የሚያርቅ ይሆናል፤ በክንፉም ላይ ታዝለው፥የታዩት ከዋክብት በመንፈስ ቅዱስ በእርሱ ትምህርት ይወለዱ ዘንድ ያላቸው ልጆቹ ናቸው፡፡ የእግዚእ ሐረያ ሕልም ትርጉሙ እንዲህ ነው በቤታቸው የብርሃን ምሶሶ ቁሞ ራሱ ከሰማይ ደርሶ ያያቸው ልጅህ ነው፡፡ ነገሥታቱ ጳጳሳቱ ሲገዙለት ያየችውም በእውነት ነገሥታቱ ይሰግዱለታል፡፡ አሕዛብም ይገዙለታል፡፡ ለሁሉም መጠጊያ ይሆናል፡፡ ከነገሥታቱ በላይ ሆኖ ይኖራል፡፡ ተአምራቱ ከዛፍ ፍሬ ይበዛል ሥፍር ቁጥር የለውም፡፡ እንደሣዕረ ምድር ጸንቶ ይኖራል፡፡ ስሙም ለዘለዓለም ሲመሰገን ይኖራል፡፡ ሰማይ ከምድር በላይ እንደሆነ የሱም ስም አጠራሩ እንደሱ ካሉ ከቅዱሳን ምእመናን በላይ ሆኖ ይኖራል፡፡ የሕልማችሁ ትርጓሜ ይህ ነው፡፡” በማለት የሕልሙን ፍች አስታውቋቸዋል፡፡

በሚያስደንቅ ልዩ ልዩ ተአምራት በቅዱስ ሚካኤል ጥበቃና በእግዚአብሔር ቸርነት ከብዙ መከራ ተጠብቀው የኖሩት ሁለቱ ቅዱሳን ባልና ሚስት /ካህኑ ጸጋ ዘአብና ቅድስት እግዚእ ሐረያ/ ታኅሣሥ 24 ቀን ፃድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖትን ወለዱ፡፡

ከሠተ አፉሁ
ታኅሣሥ 26 ቀን /በተወለዱ ሦስተኛው ቀን/ በዕለተ ሰንበት ከጧቱ ሦስት ሰዓት ላይ እጆቻቸውን አንሥተው ወደ ሰማይ እየተመለከከቱ “አሐዱ አብ ቅዱስ አሐዱ ወልድ ቅዱስ አሐዱ ውእቱ መንፈስ ቅዱስ፤ ማለትም፦ ከወልድ ከመንፈስ ቅዱስ ጋራ በባሕርይ በሕልውና አንድ የሚሆን አብ በአካል በስም ልዩ ነው፣ ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ ጋራ በባሕርይ በህልውና አንድ የሚሆን ወልድ በአካል በስም ልዩ ነው፣ በህልውና አንድ የሚሆን መንፈስ ቅዱስ በአካል በስም ልዩ ነው” በማለት ሰማያዊያን  መላእክት ምድራውያን ጻድቃን ፈጣሪን በሚያመሰግኑበት ሥርዓት ሆነው አመሰገኑ፡፡ እናትየው እግዚእ ሐረያ ግን ይህንን በልባቸው እያደነቁ “ልጄ ፍሥሐ ጽዮን ምን ትላለህ ይህ ቃል የአባትህ ሥራ ነው፡፡ ላንተ ግን የሚገባህ ጡት መጥባት ነው” በማለት ተናገሩ፡፡ ጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ግን ክቡር ዳዊት “እም አፈ ደቂቅ ወሕፃናት አስትዳሎከ ስብሐት፡፡ በእንተ ጸላዒ ከመ ትንሥቶ ለጸላኢ ወለገፋዒ፤ ከሕፃናትና ከሚጠቡ ልጆች አፍ ምስጋናን አዘጋጀህ ስለ ጠላትህ ጠላትንና ቂመኛን ለማጥፋት” በማለት የተናገረው ቃል ተፈጽሞላቸዋል፡፡ መዝ.8፥2

“በመወለዱም ብዙዎች ደስ ይላቸዋል” ተብሎ በመጋቢ ሐዲስ በቅዱስ ገብርኤል የተነገረለት ዮሐንስ መጥምቅ /ሉቃ.1፥14/ ከእናት አባቱ አልፎ ብዙዎችን ከመድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያገናኘ የደስታ ምንጭ የሆነ ነቢይም ሐዋርያም ነው፡፡ በጻድቁ አቡነ ተክለሃይማኖት መወለድም፣ ለጊዜው ልጅ ባለማግኘት ለብዙ ዓመታት ሲያዝኑ ለነበሩ ወላጆቻቸው ታላቅ የምሥራችና ደስታ ሆኗል፡፡በፍጻሜው ግን ፈጣሪያቸውን ባለማወቅ በአጋንንት አገዛዝ ሥር ወድቀው የነበሩ በብዙ መቶ ሺህ የሚቆጠሩ ሰዎች በጸሎታቸው ኀይልና ግሩም በሆነው ትምህርታቸው ብርሃን ኢየሱስ ክርስቶስን ከባሕርይ አባቱ ከእግዚአብሔር አብና፣ ከባሕርይ ሕይወቱ መንፈስ ቅዱስ ጋር በአንድነት አውቀው ተረድተው ለስሙ እንዲገዙ አድርገዋል፡፡

ነቢዩ ኤርሚያስን ፈጣሪያችን ልዑል እግዚአብሔር ከእናቱ ሆድ ጀምሮ ለቅድስና ለክብር በነቢይነት እንደጠራው በመጻሕፋችን ተገልጦአል፡፡ /ኤር.1፥5/ ጻድቁ አቡነ ተክለሃይማኖትም ለኢትዮጵያ ሰዎች ሐዋርያ ሆነው ያገለግሉ ዘንድ በባለቤቱ በመድኀኔዓለም በኢየሱስ ክርስቶስ አንደበት “እስመ ረሰይኩከ ሐዲስ ሐዋርያ፤ አዲስ ሐዋርያ አድርጌ ሾሜሃለሁ” ተብሎ የተነገረላቸው ናቸው፡፡ በዚህም በጌታችን ቃል “በእኔ የሚያምን እኔ የምሠራውን ሥራ እርሱም ይሠራል ከዚያም የሚበልጥ ይሠራል” /ዮሐ.14፥12/ ተብሎ በተነገረው ቃል መሠረት፤ በሰው ሰውኛ ሊደረጉ የማይችሉ ታላላቅ ተአምራትን በመፈጸም ኢ-አማንያንን ወደ ሃይማኖት መልሰዋል፡፡ ተጋድሏቸውን የመዘገበው መጽሐፍ /ገድለ ተክለ ሃይማኖት/ እንደተመዘገበው በዛፍ ላይ አድሮ ሲያሰግዳቸውና ሲያስመልካቸው የነበረ ጋኔኑን አዋርደው እርሱን ከኢትዮጵያ ምድር አርቀው በአምልኮተ ባዕድ የነበሩ ሰዎችን ወደ ቤተ ክርስቲያን ኅብረት ቀላቅለዋል፡፡

ባለብዙ ገድል ጻድቁ ተክለ ሃይማኖት “ዳግማዊ ዮሐንስ” የሚል ስያሜ የተሰጣቸው ሐዋርያ ናቸው፡፡ ዮሐንስ መጥምቁ በተፀነሰ ጊዜ የአባቱን አንደበት የዘጋ፣ ሲወለድ ደግሞ የአባቱን አንደበት ዳግመኛ የከፈተ ነው፡፡ (ሉቃ.1፥62-66) መምህር ወመገስጽ ዘኢያደሉ ለገድ የተባለለት፥ ዮሐንስ መጥምቁ ንጉሥ ሔሮድስን ሳይፈራና ሳያፍር የገሰጸ እንደሆነ ሁሉ፤ አባታችን ተክለ ሃይማኖትም  እንደ ሞቶሎሚ ያሉ ጣዖት አምላኪና አስመላኪ ነገሥታትና ኀያላንን ሳይፈራ የተጠራለትን አገልግሎት በጽኑ መታመን የፈጸመ ነው፡፡

ፈጣሪያችን ከጻድቁ አባታችን ከተክለሃይማኖት በረከት ረድኤት ያሳትፈን፡፡ አሜን

በሊቀ ካህናት ክንፈ ገብርኤል አልታዬ ኅልፈት ‹‹ሐዘኑ የቤተ ክርስቲያን ነው›› /ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ/


  • ‹‹…ወንድማችንን እናውቃቸዋለን፤ በእውነቱ ለፌ ወለፌ የማይሉ ደረቅ ሊቅ ናቸው፤ በሃይማኖቱ ዘርፍ ከሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን፣ ከቀኖና ቤተ ክርስቲያን አንዲቱም ነጥብ እንዳትዛባ ከወንድሞቻቸው ጋራ ብዙ ትግል ያደረጉ አለኝታ ሊቅ ነበሩ፤ እርሳቸውን ማጣታችን ትልቅ ጉዳት ነው፤ ሐዘኑ የልጆቻቸውም አይደለም፤ ሐዘንተኛዋ ቤተ ክርስቲያን ናት፤ እግዚአብሔር ለዚኽች እናት ቤተ ክርስቲያን እርሳቸውን የመሰለ ይተካልን ከማለት በቀር ምንም ማድረግ አንችልም፡፡››
ከዘመናችን የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት መካከል መላ ዘመናቸውን ለሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን መጠበቅና መከበር በጽናት ሲያስተምሩ፣ ሲጽፉና ሲሟገቱ ኖረው ታኅሣሥ ፲፱ ቀን ፳፻፯ ዓ.ም. ወደ ዘላለም ዕረፍት የተጠሩት የሊቀ ካህናት ክንፈ ገብርኤል አልታዬ ሥርዓተ ቀብር ታኅሣሥ ፳ ቀን ፳፻፯ ዓ.ም. በመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ተፈጽሟል፡፡
የሊቁ ዜና ዕረፍት ከተሰማበት ጊዜ አንሥቶ ለሥርዓተ ጸሎተ ፍትሐቱና ሥርዐተ ቀብሩ በወጣው መርሐ ግብር መሠረት፣ ታኅሣሥ ፲፱ ቀን ለ፳ አጥቢያ ምሽት 3፡00 ጀምሮ በብዙ መቶዎች የሚቆጠሩና ከተለያዩ አድባራት የተሰባሰቡ ሊቃውንትና መዘምራን በመኖርያ ቤታቸው በመገኘት ሰዓታቱን ቆመው ማሕሌቱን ሲያደርሱ አድረዋል፡፡
ሊቁ አያሌ አገልግሎት የሰጡበት የሰበካቸው የቀበና መካነ ሕይወት ጻድቁ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ቤተ ክርስቲያን ካህናት ሰዓታቱንና ማሕሌቱን የመሩ ሲኾን ከጠዋቱ 12፡00 ጀምሮ ደግሞ ሥርዓተ ፍትሐቱን በማከናወን ጸሎተ ግንዘቱን ፈጽመዋል፡፡ በዚኹም ሰዓት መዘምራኑ አደራረሱን በዐቢይ ስብሐተ ነግህ አድርሰዋል፡፡
የሊቁ ዐፅም በመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል እንዲያርፍ በብፁዓን አባቶችና በቤተሰቡ ምክር በተወሰነው መሠረት÷ ከቀኑ 5፡00 ሲኾን ግራና ቀኝ ተሰልፈው መዝሙረ ሐዘን የሚያሰሙ የሰንበት ት/ቤት ተማሪዎችና ጥንግ ድርብ የለበሱ መዘምራን፤ ቃጭል የሚመቱ፣ መስቀልና ጃንጥላ የያዙ ዲያቆናት፤ ጽንሐሕና ጃንጥላ የያዙ ካህናት፤ የሊቁን ሥዕለ ገጽና የማዕርግ አልባሳት የሚያሳዩ ልኡካን፤ የአድባራት አለቆችና ሐዘንተኞች ምእመናን እንደ ቅደም ተከተላቸው አስከሬኑን የያዘውን መኪና በመሐል አድርገውና በክብር አጅበው ጉዞ ወደ ካቴድራሉ ኾኗል፡፡
Lique Kahinat Kinfe Gabriel Funeral service
አስከሬኑን የያዘው መኪና በካቴድራሉ ሲደርስ የደወል ድምፅ ተሰምቷል፤ በብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት መሪነትም ሥርዓተ ቅዳሴው ተከናውኖለታል፡፡ ጸሎተ ቅዳሴው እንዳበቃ አስከሬኑ ወደ ዐውደ ምሕረት ወጥቶ መርሐ ግብሩ በትንሣኤ ማሳተሚያ ድርጅት ዋና ሥራ አስኪያጅ ሊቀ ካህናት ብርሃኑ ገብረ ዐማኑኤል እየተመራ፣ ከየአድባራቱ የተሰባሰቡት ሊቃውንት ሰላም የተባለውን ድጓ አለዝበው ለዐሥራ አምስት ደቂቃ ያኽል አሸብሽበዋል፡፡ በማያያዝም ሊቁ በተለይም በየዓመቱ በኅዳር ጽዮን ማርያም ክብረ በዓል እየወረዱ የሚያገለግሏቸውና በርእሰ አድባራት ወገዳማት አዲስ ዓለም ደብረ ጽዮን ማርያም ገዳም ንቡረ እድ አባ ገብረ ሕይወት መልሴ የሚመሩ የገዳሟ ሊቃውንትም፡- አበ ኵልነ አባ ክንፈ ገብርኤል እያሉግሳዊ ጣዕመ ዝማሬ በሽብሻቦ አሰምተዋል፡፡
ከሊቀ ካህናት ክንፈ ገብርኤል ጋራ በሊቃውንት ጉባኤ ለረጅም ጊዜ አብረው እንደሠሩ የገለጹት መልአከ ታቦር ተሾመ ዘሪሁን ‹‹ወንድማችን ስለኾኑና አብረን ብዙ ዘመን ስለሠራን ኹላችንም ሐዘንተኞች ነን›› ካሉ በኋላ የሊቀ ካህናትን ታላቅነትና የኅልፈታቸውን አስደናቂነት የሚዘክር አንድ ሥላሴ ቅኔ አበርክተዋል፤ ወዳጃቸው መልአከ አርያም ሐረገ ወይንም አንድ መወድስ ቅኔ አሰምተዋል፡፡
የሊቁን ዜና ሕይወት ወዕረፍት የሚናገረው ታሪክ፣ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ጽ/ቤት የአስተዳደር ሓላፊ በነበሩትና አኹን ሰባኬ ወንጌል በኾኑት መልአከ ብርሃን ኢሳይያስ ወንድምአገኘኹ በንባብ ከተማ በኋላ የዕለቱ ትምህርት በሰሜን ምዕራብ ሸዋ – ሰላሌ ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ ተሰጥቷል፡፡ ሊቁ በት/ቤት ብዙ ከደከሙ በኋላ በተለይም ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን እንዳይዛባ በተገቢው መንገድ ያገለገሉና በሃይማኖት ጽናት የተከራከሩ አባት እንደነበሩ የመሰከሩት ብፁዕነታቸው፣ ተጠያቂውን ሊቅና ታላቁን ምሁር ማጣት ለቤተ ክርስቲያን ትልቅ ጉዳት እንደኾነ ገልጸዋል፡፡
የዐሥርት ዓመታት ድካም የሚጠይቀውን ትምህርት ተምሮ እንደሚገባው የሚያገለግል ሊቅ ለማግኘት ብዙ ጥረት የሚጠይቅ በመኾኑ፣ የዘመናት ባለቤት እግዚአብሔር በሕይወት የቀሩትን በጣት የሚቆጠሩ ሊቃውንት ዕድሜ አርዝሞ በጤና እንዲያቆያቸው፣ እንደ ሊቀ ካህናት ክንፈ ገብርኤል ድካማቸውን ፈጽመው በደኅና በተሸኙት ሊቃውንት እግር እንዲተካም ብፁዕነታቸው በትምህርታቸው ተማፅነዋል፡፡
የሊቁ ዕረፍት ክንፈ ገብርኤል ተብለው በተጠሩበት በመልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ክብረ በዓል ዕለት መኾኑ ግን የአካሔዳቸውን መልካምነት የሚያሳይ ትልቅ ምልክት እንደኾነ በመግለጽ ቤተሰቦቻቸውንና ሐዘንተኞችን አጽናንተዋል – ‹‹የክንፈ ገብርኤል ዋጋ ተከፍሏል ማለት ነው›› ሲሉም የቅዱሳን አምላክ ነፍሳቸው በተድላ ገነት እንዲያሳርፍ ጸልየዋል፤ የሊቁን ሥርዓተ ቀብር ለማስፈጸም በአገልግሎት ሲደክሙ ያደሩና የዋሉ ሊቃውንትንና መዘምራንንም ‹‹ለእናንተም ብድር ይግባችኹ፤ መቼም መሸኛኘት አይቀርም፤ ለእናንተም እንደዚኹ የሚያከብር ይላክላችኹ›› ሲሉ አመስግነዋቸዋል፡፡
His Grace Abune Qewostos
ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ፤ የሰሜን ምዕራብ ሸዋ – ሰላሌ ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ
በመንፈስ ቅዱስ ይመራ የነበረው ሊቁ ቅዱስ ያሬድ የእያንዳንዱን ቅዱስ አባት፣ የእያንዳንዱን ሊቅ ቅድስና፣ የሕይወት ታሪክ ቀደም ብሎ ስለታየው ምስክርነት ሰጥቷል፡፡ ‹‹ይህ ቅዱስ አባት ከሕፃንነቱ ጀምሮ ባለ ዘመኑ ኹሉ ከቤተ እግዚአብሔር ሳይለይ እግዚአብሔርን ያገለገለ ቅዱስ ነው፡፡ እናት አባት ለሌላቸው አባት ነው፡፡ ችግር ለጸናባቸው ባልቴቶች ችግራቸውን የሚያስወግድ ነው፡፡ በተቀደሰ ክህነት እግዚአብሔርን ያገለገለ የእግዚአብሔር አገልጋይ ነው፡፡›› ሲል ለብዙዎቹ መስክሯል፡፡ ከብዙዎቹ መካከል አንዱ አኹን ታሪካቸው በዝርዝር የሰማነው ሊቁ ሊቀ ካህናት ክንፈ ገብርኤል አልታዬ ናቸው፡፡
እኒኽ ታላቅ ሊቅ ቅዱስ አባት ዛሬ በጥሩ አካሔድ ነው የሔዱት፡፡ ሐዘኑ የቤተ ክርስቲያን ነው፤ የልጆቻቸውም አይደለም፡፡ ልጆቻቸውን አስተካክለዋል፤ ለወግ ለማዕርግ አድርሰዋል፡፡ ሐዘንተኛዋ ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ ተጠያቂ ሊቅ አጥታለች፤ ታላቅ ሊቅ ተለይቶናል፡፡
እኒኽ ታላቅ ሊቅ በትምህርት ቤት ብዙ ደክመዋል፤ ከት/ቤት በኋላ ቅድም በዜና ሕይወታቸው እንደተገለጸው በተገቢው መንገድ አገልግለዋል፡፡ ተጠያቂ ሊቅ ነበሩ፤ ለሃይማኖት የቆሙ ሊቅ ነበሩ፤ በሃይማኖቱም ዘርፍ ከሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን፣ ከቀኖና ቤተ ክርስቲያን አንዲቱም ነጥብ እንዳትዛባ ሽንጣቸውን ገትረው ይከራከሩ የነበሩ የቤተ ክርስቲያን ሊቅ፣ የቤተ ክርስቲያን ተጠያቂ፣ ታላቅ ምሁር እንደነበሩ እናውቃለን፡፡ እኒኽን ማጣት ትልቅ ሐዘን ነው፤ ትልቅ ጉዳት ነው፡፡
አዎ! ብዙዎች ባለዲግሪዎች አሉ፤ ዲግሪ ይፈለጋል፤ የሚናቅም አይደለም፡፡ ዳሩ ግን እንዲኽ እንደ እርሳቸው በቤተ ክርስቲያን ትምህርት ሳይደክሙ ወደ ቤተ ክርስቲያን ገብቶ በዲግሪው ብቻ ላገልግል ቢባል አይቻልም፤ ድግር ይኾናል ዲግሪው! የቤተ ክርስቲያን አካሔድ፣ ምስጢረ ሃይማኖቱ ከባድ ነው፡፡ ምስጢረ ተዋሕዶ ድካም ይጠይቃል፤ ኻያ፣ ሠላሳ፣ ዐርባ ዓመት የትምህርት ጊዜ ይጠይቃል፤ ኻያ፣ ሠላሳ፣ ዐርባ ዓመት ተምሮ ቤተ ክርስቲያንን እንደሚገባው የሚያገለግል ሊቅ ለማግኘት ስንት ጥረት ይጠይቃል? ትልቅ ጉዳት ነው፡፡
ትልቅ ጉዳት ነው፤ ወንድማችንን እናውቃቸዋለን፤ በእውነቱ ደረቅ ሊቅ ናቸው፤ ለፌ ወለፌ የማይሉ፣ ከወንድሞቻቸው ጋራ ቤተ ክርስቲያንን ለመጠበቅ ብዙ ትግል ያደረጉ አለኝታ ሊቅ ነበሩ፡፡ እርሳቸውን በማጣታችን አዝነናል፡፡ እግዚአብሔር ለዚኽች እናት ቤተ ክርስቲያን እርሳቸውን የመሰለ ይተካልን ከማለት በቀር ምንም ማድረግ አንችልም፡፡
ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን÷ በእውነቱ ከሌሊቱ ሰዓት ጀምራችኹ ያቀረባችኹት አገልግሎት፣ የከፈላችኹት መሥዋዕት እጅግ በጣም የሚያስመሰግን ነው፡፡ እግዚአብሔር ይባርካችኹ፤ ዋጋችኹን ይክፈላችኹ፤ ለእናንተም ብድር ይግባችኹ፡፡ መቼም መሸኛኘት አይቀርም፤ አይደለም? ለእናንተም እንደዚኹ የሚያከብር ይላክላችኹ፡፡
ልጆች ልታዝኑ አይገባችኁም፤ አስታማችኋል፤ እናውቃለን ተንገላታችኋል፤ መቼም ሥጋ የለበሰ መንገላታቱ አይቀርም፤ ነገር ግን አካሔዳቸው የቅዱሳን አካሔድ ነው፤ ደክመው ወጥተው ወርደው እጫፉ ላይ ደርሰዋል፤ ሰባ ሰማኒያ ዘመን አይደለም የተወሰነው፤ ሰባውን ጨርሰዋል፤ ትንሽ ነበር የቀራቸው በደኅና ተሸኝተዋል፡፡ በዚኽ ቅዱስ ቦታ ከወንድሞቻቸው አጠገብ እንዲያርፉ ብፁዕ ወቅዱስ አባታችን ፈቅደው መካነ መቃብራቸው ተዘጋጅቷል፡፡
እንግዲኽ መቼም ምንም ቢኾን ጉዳይ ሲፈጽም የኖረ ታላቅ ሰው የተለየ ዕለት እሰይ ተብሎ አይሸኝም፡፡ በእውነቱ እኛ የምንወደው ሽማግሌዎቹ ሊቃውንት አልጋቸው ላይ ተኝተውም ቢኾን እንዲጠየቁ እንጂ እንዲለዩብን አንሻም፡፡ እዚያው እየተከባከብን ጥያቄ ሲመጣ እስኪ መምህር እገሌን ጠይቁ እያልን ብንልክ ነው ደስ የሚለን፡፡ አኹንም በጣት የሚቆጠሩ አባቶች ሊቃውንት አሉ፤ የእነርሱን ዕድሜ እግዚአብሔር ያርዝምልን፤ የወንድማችንን የሊቁን ነፍስ በተድላ ገነት ያኑርልን፡፡
እግዚአብሔር ለወዳጆቹ ቃል ኪዳን ሲሰጥ፣ ‹‹በስምኽ የተጠራውን ከአንተ ጋራ ዋጋውን እከፍለዋለኹ›› አለ፡፡ ሊቁ ወንድማችን፣ ክንፈ ገብርኤል ተብለው ሲጠሩ ዕረፍታቸውን የመልአኩ የቅዱስ ገብርኤል በዓል በሚከበርበት ቀን አደረገው፡፡ ይህም አንድ ትልቅ ምልክት ነው፡፡ የክንፈ ገብርኤል ዋጋ ተከፍሏል ማለት ነው፡፡ የወንድማችንን የክንፈ ገብርኤልን ነፍስ በተድላ ገነት ያኑርልን፤ ለእናተንም የድካማችኹን ዋጋ ይክፈላችኹ፡፡

የሊቁ የሕይወት ታሪክ በሚነበብበት ወቅት በካቴድራሉ ደቡባዊ አንቀጽ ከሚገኝ ታላቅ የጥድ ዛፍ ላይ ማንም ሳይነካው አንድ ትልቅ ቅርንጫፍ ተገንድሶ መውደቁ ብፁዕነታቸው ከጠቀሱት የምልክት ጉዳይ ጋራ ተያይዞ የበርካታ ሐዘንተኞች መነጋገርያ ኾኗል፡፡ ይህንንም ድንቅ ከአስተዋሉት ሐዘንተኞች አንዱ የኾነው የነገረ ቤተ ክርስቲያን ተመራማሪው ዲያቆን ዳንኤል ክብረት የትልቁ ዋርካ ትልቁ ቅርንጫፍ በሚል ርእስ የሊቁን ዕረፍት አስመልክቶ በጡመራ መድረኩ ባሰፈረው ማስታዎሻ፡- ‹‹በቦታው የነበሩ፣ ይህንንም ነገር የተመለከቱ ኹሉ ታሪኩን በካሜራቸው ሲቀርፁና ከታላቋ ዋርካ ከቤተ ክርስቲያን ብዙዎችን የያዘው አንዱ ታላቅ ቅርንጫፍ ሊቀ ካህናት ክንፈ ገብርኤል ዛሬ መሰናበቱን በሐዘን ሲተረጉሙ ነበር፤›› በማለት አትቶታል፤ የቅርንጫፉን ቅጠልም ብዙዎች ተሻምተው ሲወስዱ መመልከቱን ጦማሪው በማስታዎሻው ገልጧል፡፡

good omen on the funeral service of Archpriest Kinfe Gabriel
ከታላቋ ዋርካ ከቤተ ክርስቲያን አንዱ ታላቅ ቅርንጫፍ ሊቀ ካህናት ክንፈ ገብርኤል ዛሬ ስለ መሰናበቱ…
ከርእሰ አድባራት ቁልቢ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን የበዓል አከባበር ጉዟቸው እንደተመለሱ ከስፍራው መድረሳቸው የተገለጸው ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ በሰጡት ቃለ ምዕዳን÷ ‹‹እግዚአብሔር አምላክ ጥሪውን ሲልክ ከሰዓቱ የሚያልፍ ባለመኖሩ ወንድማችን ከእኛ በሥጋ ተለይተዋል፤ በዐጸደ ነፍስ ግን ሕያው ናቸው፤ ለትውልድ የሚተርፍ ሥራ ሠርተዋልና›› በማለት ሐዘንተኞችን አጽናንተዋል፤ ለአስከሬኑ ዑደት ከተደረገ በኋላም በምሥራቃዊ አንቀጽ የተዘጋጀው መካነ መቃብር በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩና በብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ተባርኮ ሥርዓተ ቀብሩ ተፈጽሟል፡፡
ከሊቃውንት የተበረከቱ ቅኔዎች
 ሥላሴ ዘመልአከ ታቦር ተሾመ ዘሪሁን
እንዘ ሞት መሬታዊ ዘሰማያዊ ለእሊአኹ
መኑ አዘዘ ይዕዜ ወተአደወ ሥርዓተ
ገብርኤል በክንፉ ከመ ይጹር ሞተ
ወቤተ ክርስቲያን ዘኮንኪ ዘክንፈ ገብርኤል ቤተ
አስምዑ ምድረ ወሰማያተ
ይግበሩ ለኪ እምዕለት ዕለተ
ዘከማሁ አእላፈ ኖሎተ፡፡
መወድስ ዘመልአከ አርያም ሐረገ ወይን ደምሴ
እስራኤል አዕፅምት አመ ተጼወዉ መቃብረ አበው የኀድር
እንዘ በአካል ኢይፃሙ፡፡
ልዑከ ኤርሚያስ ባሮክ ለክንፈ ገብርኤል ዐፅሙ
በክሳደ ንስር አስቆቅዎ ለኤርሚያስ ከመ ተፈነወ
ጳውሎስ ማኅተሙ፡፡
ድቀተ እስራኤል ኀዘነ ልብ ከመ ለዘመን ቀርበ
ጽሑፈ ይንግሮሙ፡፡
ለዓለም
ዕረፍትሂ ዘይዕዜ ለአቤሜሌክ ንዋሙ
ለክንፈ ገብርኤል ይኤድሞ ወይትርአዮ በውስተ ሕልሙ፡፡
አምጣነ ፈነዎ ኤርሚያስ ባቢሎናዊ ሕማሙ
በቆጽለ በለስ ለሕሙማን ኃይላተ ፈጣሪ ይፈውሶሙ፡፡
የሊቁ በረከታቸው ይደረብን፤ እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን፤ አሜን፡፡


2014 ዲሴምበር 31, ረቡዕ

እነሆ ዛሬ በዳዊት ከተማ መድኀኒት ተወልዶላችኋል




መጋቤ ብሉይ አእምሮ ዘውዴ                                                                           
  
እንኳን ለጌታችን ለመድኀኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓል በሰላም አደረሳችሁ፡፡

የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ልደት እንደ እንግዳ ደራሽ እንደ ውኃ ፈሳሽ  አይደለም፡፡ ከጥንት ከመሠረት ጀምሮ በመላእክት፤ በነቢያት  ሲነገር፤ ሲሰበክ የመጣ ነው እንጂ፡፡ ማቴ.1፥18፡፡

ሰው የመሆኑን ምሥጢር ለመጀመሪያ ጊዜ በማእከለ ገነት የተናገረ እርሱ እግዚአብሔር ነው፡፡
yeledeteአባታችን አዳም ከእግዚአብሔር ትእዛዝ ወጥቶ ዕፀ በለስን በልቶ ከጸጋ እግዚአብሔር በተራቆተ ጊዜ /አዳም ኮነ ከመ አሐዱ እምኔነ/ አዳም ከእኛ እንደ አንዱ ሆነ ዘፍ.3፥22 ብሎ ከሦስቱ ቅዱስ አንዱ ቅዱስ እግዚአብሔር ወልድ በተለየ አካሉ ከእመቤታችን ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሷ ነፍስ ነስቶ ሰው እንደሚሆን ተናግሯል፡፡ በዚህ ቃል መሠረት /መሪነት/ ቅዱሳን መላእክት ምሥጢረ ትንቢት ተገልጾላቸዋል፡፡ እነሱም የተገለጸላቸውን ምሥጢረ ትንቢት ኀላፍያትንና መጻእያትን ለሚናገሩ ነቢያት ነግረዋቸዋል፡፡ ቅዱሳን ነቢያትም ከእግዚአብሔር ያገኙትን ከመላእክት የሰሙትን መነሻ አድርገው በተለያዩ ጊዜያት በተለያዩ ምሳሌያት በተለያዩ ዘመናት የወልደ እግዚአብሔርን ሥጋዌ ሰብከዋል /ገልጸዋል/ ዕብ.1፥1፡፡ ከጥንት ጀምሮ እግዚአብሔር በብዙ ዓይነትና በብዙ ጎዳና ለአባቶቻችን በነቢያት ተናግሮ፥ሁሉን ወራሽ ባደረገው ደግሞም ዓለማትን በፈጠረበት በልጁ በዚህ ዘመን መጨረሻ ለእኛ ተናገረን፡፡
የጌታችን ልደት በትንቢተ ነቢያት
ከዓበይት ነቢያት መካከል አንዱ የሆነው ነብየ እግዚአብሔር ኢሳይያስ የሚከተለውን ትንቢት ተናግሯል፡፡
እነሆ ድንግል በድንግልና ፀንሳ በድንግልና ትወልዳለች ስሙንም አማኑኤል ትለዋለች ኢሳ.7፥14፣ ሕዝ.44፥1/ ፡፡ በኅቱም ድንግልና ተፀንሶ በኅቱም ድንግልና የተወልደው አማኑኤል ጌታ ነው፡፡ ትርጉሙም  እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ሆነ ማለት ነው፡፡ነቢዩ  በጎላና በተረዳ ነገር “ሕፃን ተወልዶልናል ወልድም ተሰጥቶናል አለቅነትም በጫንቃው ላይ ይሆናል፡ ስሙም ድንቅ መካር ኀያል አምላክ የዘለዓለም አባት የሰላም አለቃ ተብሎ ይጠራል“ በማለት የሚወለደው ሕፃን የባሕርይ አምላክ የዘለዓለም አባት የሰላም አለቃ ሥልጣን የባሕርይ ገንዘቡ እንደሆነ እና ለሥልጣኑም ወሰን ድንበር እንደሌለው ተናግሯል፡፡

ከደቂቀ ነቢያት መካከል አንዱ ሚክያስም በቤተልሔም ስለመወለዱ፡-
  • የኤፍራታ ምድር አንቺ ቤተልሔም ከይሁዳ አለቆች ከቶ አታንሽም ሕዝቤን እስራኤልን የሚጠብቅ ንጉሥ ከአንቺ ይወጣልና ሚክ.5፥2፣ ማቴ.2፥6/ ብሏል፡፡
  • ነቢየ እግዚብሔር ቅዱስ ዳዊትም እነሆ በኤፍራታ ሰማነው ዛፍ በበዛበትም ቦታ አገኘነው እንግዲህስ ወደ እግዚአብሔር ማደሪዎች እንገባለን ብሎ የወመለዱን ምሥጢር ተናግሯል መዝ.131፥6
  • ነቢዩ ዕንባቆምም አቤቱ ድምፅህን ሰምቼ ፈራሁ ሥራህንም ዐይቼ አደነቅሁ በሁለት እንስሶች መካከል አየሁህ ዘመኑ እንደደረሰ አድርጌ አውቅህአለሁ ዘመኑም በደረሰ ጊዜ ተገለጥክ ብሎ በቤተልሔም በረት በተወለደ ጊዜ አድግና ላኅም እስትንፋሳቸውን እንደሚገብሩለት ዕንባቆም 3፥1 ተናግሯል፡፡

christmas 1ከዚህ በኋላ የዘመኑ ፍጻሜ ሲደርስ እግዚአብሔር መልአኩ ቅዱስ ገብርኤልን ወደ ድንግል ማርያም በመላክ አብሥሯታል፡፡ “ማርያም ሆይ፥ በእግዚአብሔር ፊት ጸጋ አግኝተሻልና አትፍሪ። እነሆም፥ ትፀንሻለሽ ወንድ ልጅም ትወልጃለሽ፥ ስሙንም ኢየሱስ ትዪዋለሽ።እርሱ ታላቅ ይሆናል የልዑል ልጅም ይባላል፥ ጌታ አምላክም የአባቱን የዳዊትን ዙፋን ይሰጠዋል" በማለት፡፡ ሉቃ. 1፡32

እመቤታችንም በብዙ ኅብረ አምሳል ትንቢት ሲነገርለት፤ ምሳሌ ሲመሰልለት፤ ሱባኤ ሲቆጠርለት የነበረውን ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በቤተልሔም ግርግም /ዋሻ/ ወለደችው፡፡

ይህንንም ብስራት በቤተልሔም ዋሻ መንጋቸውን ነቅተውና ተግተው ይጠብቁ ለነበሩ እረኞች መጋቤ ሐዲስ አብሣሬ ትስብዕት ቅዱስ ገብርኤል ፤ እነሆ ዛሬ መድኀኒት በዳዊት ከተማ ተወልዶላችኋል ይኸውም ቡሩክ መርገመ ሥጋ መርገመ ነፍስ የሚያርቅ በረከተ ሥጋ በረከተ ነፍስ የሚያድል ከዓለም በፊት ንጉሥ የነበረ ዛሬም ከዳዊት ባሕርይ /ዘር/ በቤተልሔም ዋሻ ዓለምን ለማዳን የተወለደ የዳዊት ልጅ ንጉሠ ነገሥት ኢየሱስ ክርስቶስ ተወለደ ሲል አበሰራቸው፡፡ መዝ.73፥12

የጌታችንን ልደት ስናነሣ ሁለት ልደታት እንዳሉት እናምናለን፡፡ እኒሁም ልደታት /ልደት ቀደሚዊና/ /ልደት ደኃራዊ/ ናቸው፡፡
ልደት ቀዳማዊ፡ ቅድመ ዓለም ከአብ አካል ዘእም አካል ባሕርይ ዘእም ባሕርይ ከእግዚአብሔር አብ ያለ እናት የተወለደው ልደት ሲሆን /ነቢዩ ዳዊት እንዲህ ይገልጸዋል፡፡ ወለድኩከ እምከርሥ እምቅድመ ኮከበ ጽ    ባህ መዝ.109፥3 ከአጥቢያ ኮከብ አስቀድሞ ወለድኩህ ፤አንተ ልጄ ነህ እኔም ዛሬ ወለድኩህ መዝ.2፥7

ልደት ደኃራዊ ፤ አምስት ሺህ አምስት መቶ ዘመን ሲፈፀም በሀሙስ ዕለት ወበመንፈቃ ለዕለት እትወለድ እምወለተ ወለትከ እንዲል ቃሉ፡፡ ቅድስት ድንግል ከምትሆን ከእመቤታችን እንበለ ዘርዓ ብዕሲ ያለ አባት ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በቤተልሔም የተወለደው ልደት ነው፡፡

ቀዳማዊ ልደቱ ጥንትና ፍጻሜ የሌለው የማይመረመር ስለሆነ ቀዳማዊ ልደቱን ለመግለፅ ቅድመ ዓለም ያለ እናት ከአብ እንደ ተወለደ ድኅረ ዓለምም ከእመቤታችን /እንበለ ዘርዓ ብዕሲ/ ያለ አባት ተወለደ፡፡ እሱም እመቤታችን ያለ አባት የወለደችው ፤ እግዚአብሔርም ያለ እናት የወለደው ወልድ ዋሕድ ኢየሱስ ክርስቶስ

በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ልደት ሰባቱ መስተጻርራን /ተቃራኒ ነገሮች አንድ ሆነዋል
ሕዝብና አሕዛብ፤ በጠብና በክርክር ይፈላለጉ የነበሩ ሕዝብና አሕዛብ በጌታችን ልደት ታርቀዋል፡፡ ይኸውም ሊታወቅ ከዚህ አስቀድሞ ቤተ መቅደሱን ለማፍረስ ንዋየ ቅድሳቱን ለመዝረፍ ሕዝቡን ለመማረክ ምታ ነገሪት ብለው ይመጡ የነበሩ  የሩቅ ምስራቅ /የፋርስ የባቢሎን ሰዎች በጌታችን ልደት ምክንያት ወርቅ፣ ዕጣን፣ ከርቤ አይቴ ሀሎ ዘተወልደ ንጉሠ አይሁድ የተወለደው የአይሁድ ንጉሥ ወዴት ነው ማቴ.2፥4 እያሉ መጥተው ወርቅ፣ እጣን፣ ከርቤ ገብረውለታል፡፡

ነፍስና ሥጋ፡- በሲዖልና በመቃብር ተለያይተው የነበሩ ነፍስና ሥጋ ከእመቤታችን ከነፍሷ ነፍስ ከሥጋዋ ሥጋ ነሥቶ በተዋሕዶ ሰው በሆነ ጊዜ ነፍስና ሥጋን አስታርቋል፡፡

ሰውና እግዚአብሔር፡- አባታችን አዳም አትብላ የተባለውን ዕፀ በለስ በልቶ የሰውና የእግዚአብሔር የፍቅር ግንኙነት ለአምስት ሺህ አምስት መቶ ዘመን ተቋርጦ ነበርና ጌታችን የሰውን ሥጋ ተዋሕዶ በተወለደ ጊዜ እርቀ ሰላም ተገኝቷል፡፡

ሰውና መላእክት፡- አባታችን አዳም ከእግዚአብሔር ጋር በተጣላ ጊዜ ቅዱሳን መላእክትም ስለተጣሉት በምትገለባበጥ ሰይፈ እሳት አስፈራርተው ከገነት ከአስወጡት በኋላ ወደ ገነትም እንዳይገባ ገነትን ይጠብቁ ነበር፡፡ ጌታችን በተወለደ ጊዜ አንድ ሆነው ዝማሬ አቅርበዋል፡፡ ይኸውም ዮም አሐደ መርኤተ ኮኑ መላእክት ወሰብእ ከመ ይሰብህዎ ለክርስቶስ እንዲል፡፡ ሰውና መላእክት ክርስቶስን ለማመስገን አንድ ሆኑ  እንዳለ ሊቁ፡፡

ቤተ ክርስቲያን ጌታችን የተወለደባት እና ሰባቱ መስተጻርራን አንድ የሆኑባት፤ ሰውና መላእክት የዘመሩባት የብርሃን ጎርፍ የጎረፈባት እንስሳት እስትንፋሳቸውን የገበሩባት ቤተልሔም በቤተ ክርስቲያን ትመሰላለች፡፡

ቤተልሔም፡- ተለያይተው የነበሩ ሕዝብና አሕዛብ ፤ሰውና እግዚአብሔር፤ ነፍስና ሥጋ ፤ሰውና መላእክት አንድ ሆነው በቤተልሔም እንደዘመሩ ዛሬም የፍቅር ተምሳሌትና የአማኞች ሁሉ እናት በሆነችው ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በዘር፣ በጎሣ፣ በጥቅም፣ በሥልጣን ሳንከፋፈል አንዲት ቤተ ክርስቲያንን በፍቅር እንድናገለግል በቤተልሔም የተደረገው የልደቱ ምሥጢር ይህን ያስተምረናል፡፡
ክርስቲያኖች የጌታን መወለድ የምናስበው በዚህ መንፈስ ነው፡፡

2014 ዲሴምበር 30, ማክሰኞ

ስለ ገና በዓል እና ጾም አንዳንድ ጥያቄዎች

የገና እና የጥምቀት በዓላት ሲደርሱ በምእመናኑ ዘወትር የሚጠየቁ ጥያቄዎች አሉ፡፡ እነዚህን እና መሰል የሕዝቡን የዘወትር ጥያቄዎች መልስ የያዘ የማያዳግም ጥራዝ ማውጣት ከሊቃውንት ጉባኤ የሚጠበቅ ነው፡፡ አብዛኞቹ ጉዳዮች አበው ቀድመው ሥርዓት የሠሩባቸው እና ማብራርያ ብቻ የሚያስፈልጋቸው ናቸውና፡፡ ለዛሬ ሦስቱን ብቻ እንመልስ፡፡

ገና እና ጥምቀት ዓርብ እና ረቡዕ ቢውሉ ይበላባቸዋል ወይስ ይጾማሉ?

ፍትሐ ነገሥት፡ ዳግመኛ በየሳምንቱ ዓርብ እና ረቡዕን መጾም ነው፡፡ በዓለ ሃምሳ፣ የልደት እና የጥምቀት በዓል የተባበሩባቸው ጊዜ ካልሆነ በቀር /ዐንቀጽ 15፣ ቁ566/

የዓርብን እና የረቡዕን ጾም ግን ከልደት፣ከጥምቀት እና ከበዓለ ሃምሳ በቀር ዘወትር ይጹሙ /ዐንቀጽ 15፣ቁ 603/

የገና እና የጥምቀት ቅዳሴ ስንት ሰዓት ነው?

ፍትሐ ነገሥት፡ ስለ ልደት እና ጥምቀት ግን በዚያ ዘመን በኒቂያ የተሰበሰቡ ሊቃውንት ቅዳሴው በሌሊት ይሆን ዘንድ አዘዙ /ዐንቀጽ 15፣ ቁ 595/

ልደት ጋድ አለው?

ፍትሐ ነገሥት፡ የልደት እና የጥምቀት በዓላት ጋድ አላቸው /ዐንቀጽ 15፣ ቁ 566/

     ትንታኔ፡ የገና ጾም 44 ቀናትን ይይዛል፡፡

                   40 ጾመ ነቢያት

                     3 ጾመ አብርሃም ሶርያዊ

                    1 ጋድ

               ድምር 44

የገና ጋድ ከጾሙ ተያይዞ የተቀመጠ እንጂ ለብቻው የተቀመጠ አይደለም፡፡ ለምሳሌ ሰሙነ ሕማማት ለብቻው የሚቆጠር ጾም ነው፡፡ /ዐንቀጽ 15፣ቁ 565/ ነገር ግን አንድ ሰው ዐቢይ ጾምን ሳይጾም ከርሞ ሕማማትን ለብቻው መጾም አይችልም፡፡ የገናም ጋድ እንዲሁ ነው፡፡

ይህንን ጋድ የልደትን ጾም የማይጾሙ ሰዎች እንዲጾሙት የተሠራ ነውን?

መልስ፡ በቤተ ክርስቲያን ላልተጠመቁ፣ ለማይቆርቡ፣ ንስሐ ለማይገቡ፣ ለማያስቀድሱ፣ ለማይጾሙ ሰዎች ተብሎ የተሠራ ልዩ ሥርዓት የለም፡፡ በፍትሐ ነገሥት ዐንቀጽ 15፣ ቁ 565 እንደተገለጠው ሰባቱ አጽዋማት «ለክርስቲያን ሁሉ» የታዘዙ ናቸው፡፡ ስለዚህም የገናን ጾም ክርስቲያን ሁሉ ጾመው በበዓለ ልደት ሊገድፉ ይገባቸዋል፡፡ ፍትሐ ነገሥት ስለ ገና ጾም ሲገልጥ «መጀመርያው የኅዳር እኩሌታ ፋሲካው የልደት በዓል ነው» ይላል /ዐንቀጽ 15፣ ቁ 568/፡፡ ይህም ከገና ጾም ተሸርፎ የሚጾም ነገር እንደሌለው ያሳያል፡፡

መልካም በዓል

                                   በአውሮጳ   የካህናት አንድነት ማኅበር ሊቋቋም መሆኑ ታወቀ በ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከመላዋ አውሮጳ   የተውጣጡ ካህናት፡” የ...