2015 ማርች 11, ረቡዕ

እረፍቱ ለአቡነ ገ/መንፈስ ቅዱስ


Written By Hulubante Abebe 

 የእግዚአብሔር ዓይኖች ወደ ጻድቃን ጆሮቹም ወደ ጩኸታቸው ናቸውና። መታሰቢያቸውን ከምድር ያጠፋ ዘንድ የእግዚአብሔር ፊት ክፉን በሚያደርጉ ላይ ነው። ጻድቃን ጮኹ፥ እግዚአብሔርም ሰማቸው ከመከራቸውም ሁሉ አዳናቸው።” 
                                 
 መዝ ፴፫፡፲፭-፲፯ 
መጋቢት 5 በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስትያን አማኞች ዘንድ የፃድቁ አቡነ ገ/መንፈስ ቅዱስ ዓመታዊ ክብረ በዓል በደመቀ ሁኔታ ተከብሮ ይውላል 
በዚህ እለት እምናከብረው የእረፍት መታሰቢያቸውን ሲሆን ከገድላቸውም እንዲህ ተፅፎ እናገኘዋለን 
ፃድቁ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ የተወለዱት ግብፅ ንሂሳ በምትባል ቦታ ከአባታቸው ስምዖን ከእናታው አቅሌስያ ነው። በአጠቃላይ የኖሩበት ዕድሜ 562 አመት ሲሆን 300 ዓመቱን በግብጽ 262 ቱን በኢትዮጵያ 100 ዓመት በዝቋላ በተጋድሎ ያሳለፉ ታላቅ አባት ናቸውኢትዮጵም የአስራት ሐገራቸው ሆና በቃልኪዳን ተሰጣቸዋለች  እናታቸው ሳትታቀፋቸው ወተት ሳይጠጡ በመንፈስ ቅዱስ አድገው በ፫ ዓመታቸው ቅዱስ ገብርኤል መጥቶ እስከ ሰባቱ ሰማያት አውጥቶ ወደ እግዚአብሔር አቀረበው፤ ባረከውም፤ ድንግል ማርያም ጻድቃን ሰማዕታት ወዳሉበት ተወስዶ ተባርኮ በጌታችን ቃል ተቀብሎ ወደ አባ ዘመደ ብርሃን ወዳሉበት አውርዶ በዚያም አድጎ መንፈሳዊ ሥራን በአጭር ጊዜ በማጠናቀቅ ተጋድሎውን ጀምሯል። በበረሃ ሲኖሩ 60 አንበሳና ነብር የተሰጣቸው ሲሆን አንበሳ እና ነምሮቹም የሚበሉትም የቅዱሱን እግር ያረፈበትን ቦታ በመላስ ነው። የአባታችን ገድል እንደሚያስረዳው እንደ ሰው ልብስ ለብሰው ሳይሆን ልብሳቸው በጸጋ የተሰጣቸው ጠጉር ነበር እሱም ልክ እንደ ልብስ ያገለግላቸው ነበር
 ከሚያስገርመው ገድላቸው ውስጥ አባታችንን ለመጠየቅ የመጡት አባ ሳሙኤል ዘዋልድባ ከሁለት ጓደኞቻቸው ጋር መጥተው እንግዶቹን አንበሶቹ በልተው አባታችን አቡነ ገ/መንፈስ ቅዱስም በመንፈስ መምጣታቸውን አውቆ ሲነግሯቸው ለምን ያልተፈቀደላችሁን በላችሁ ብለው የበሉትን አንበሶች የበላችሁትን አንድም ሳታስቀሩ ትፉ ብሏቸው ወደ እግዚአብሔር ጸልየው በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ተነሱ ባሉ ጊዜ የተበሉት ነፍስ ዘርተው እነ አባ ሳሙኤል ዘዋልድባም በሰላም ወደ ባእታቸው በአባታችን በአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ጸሎት በሠላም ገብተዋል።
መጋቢት 5 በገድለ አቡነ ገ/መንፈስ ቅዱስ
ዕለቱ ቅዳሜ ለእሁድ አጥቢያ ሰዓቱ ከሌሊቱ ስድስት ሰዓት ሆኗል፤ አሁንም ህማሙን እየታገለ እያላበው በድካም ለፍጥረቱ ሁሉ ይለምናል፤ “አቤቱ ህዝብህን አድን ርስትህን ኢትዮጰያንም ባርክ” ይላል። ህመም የጀመረው መጋቢት 3 ዓርብ ቀን ነው፤መታመሙን የሰሙ እንደርሱ ቅዱሳን የሆኑት ዘርአ ቡሩክ፤ ፍሬ ቅዱስ፤ያዕቆብ፤ብንያምና ዮሴፍ እንዲሁም በወቅቱ የኢትዮጰያ ንጉስ የነበረው እንድርያስ ሊጠይቁት ተሰብስበዋል ወደ አጠገቡ መድረስ ግን አልተቻላቸውም አባታችን ገብረመንፈስ ቅዱስ የሚጋርደው እንጨት ዛፍ በሌለበት በርሃ እንደ አንበሳ ተኝቶ አዩት በላዩ ያረፈው የእግዚያብሔር ጸጋ ከፊቱ የሚወጣው ብርሃን ቀይ መልኩ ረዥም የራስ ጠጉሩ እንደ ነጭ ሐር የሚሆን ጽሕሙ አስደነቃቸው። ከሌሊቱ ሰባት ሰዓት ሲሆን ከሰማይ ታላቅ ነጎድጓድ ድምጽ ተሰማ ጌታችን መላአክትን አስከትሎ ወደ አባታችን ወረደ፤ ከሰማይ ወደ ምድር ህብሩ አምሳያው ልዩ ልዩ የሆነ እንደ ጸሐይና እንደ ጨረቃ የሚያበራ እንደ ወንጪፍ ድንጋይ ይወረወር ነበር ከዚያ የነበሩ ሁሉ ፈሩ ወደ ኃላም ሸሹ ምድር ራደች ተራሮች ኮረብቶች ተናወጡ ብርቱ ጩኸት
ንውጽውጽታ ሆነ። “ወዳጄ ገብረመንፈስ ቅዱስ ሰላም ላንተ ይሁን” እነሆ የማይታበል ቃል ኪዳን እገባልኃለው ስምህን የጠራ መታሰቢያህን ያደረገውን፤ እጣን ቋጥሮ ግብር ሰፍሮ መባ ይዞ ቤትህ የመጣውን እምርልኃለው አንተ ከገባህበት ገነት መንግስተ ሰማያት አገባዋለሁ አለው፤ አባታችንም “አቤቱ ጌታ ሆይ የኢትዮጰያን ህዝብ ማርልኝ” አለው፤ እነሆ ምሬልኃለው አስራት በኩራት አድርጌም ሰጥቼሃለው፤ ከመጋቢት አምስት ቀን ጀምሮ ዝክርህን ያድርጉ በአማላጅነትህም ይማጸኑ አለው። ከዚህ በኃላ ሰባቱ ሊቃነ መላእክት የአባታችንን ነፍስ ሊቀበሉ ወረዱ በታላቅ ምስጋናም ወደ ሰማይ አሳረጉት ስጋውንም ይዘውት ሄዱ የት እንደተቀበረ ግን እስካሁን አይታወቅም አንዳንዱ በእየሩሳሌም ነው ይላሉ፤ ሌላው በምድረ ከብድ ነው ይላል ግን እስካሁን ልክ እንደ ሊቀ ነብያት ሙሴ ስጋ የት እንደተቀበረ አይታወቅም። ገድሉ ትሩፋቱ ከሰማይ ከዋክብት ከምድር አሸዋ ይበዛል ኢትዮጰያን አብዝቶ ይወዳታል፤ ምድራዊ ምግብ አልተመገበም የእናቱን ጡት እንኳን አልጠባም፤ ልብስ፤ መጠለያ አልፈለገም፤ የክረምት ቁር የበጋ ሐሩር እየተፈራረቀበት በተጋድሎ 562 ዓመት ኖረ፤ በዛሬዋ ቀን ሩጫውን ጨረሰ። ለእግዚያብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም ከአባታችን በረከት ያሳትፈን።
የአባቶችን የቅዱሳንን ታሪክ እንድናውቅ ከሚፈለግባቸው ምክንያቶች ውስጥ አንዱ ከነርሱ ገድል ተምረን እኛም ወደአምላክ መንገድ እንድንቀርብብበት ነውና አምላከ ገ/መንፈስ ቅዱስ መንገዱን ያብራልን ። ገድሉንም ሰሚወች ብቻ ሳንሆን እምንማርበት ያድርግልን ።
መጋቢት 5 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
1.አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ጻድቅ /አባ ገብረ ሕይወት/                                     2.ቅዱስ አባ ሰረባሞን /በምድረ ግብፅ ምንኩስናን ካስፋፉ ታላላቅ ቅዱሳን አንዱ/                 3.አባ ግርማኖስ ጻድቅ /ሶርያዊ/                                                         4.ቅድስት አውዶክስያ ሰማዕት /ከከፋ የኃጢአት ሕይወት ተመልሳ ለቅድስና የበቃች እናት/ 
5.ቅዱሳን ስምዖንና ሚስቱ አቅሌስያ /የአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ወላጆች/

                       ወስብሐት ለእግዚአብሔር

2015 ማርች 10, ማክሰኞ

እየደመሰሱ መቅዳት

ለረዥም ዓመታት በአንድ ሬዲዮ ጣቢያ የሠራ ጋዜጠኛ ለአንድ ጥናት ወደ ጣቢያው ይሄዳል፡፡ ከ30 ዓመታት በፊት እርሱ ራሱ ያደረገው ቃለ መጠይቅ ነበር፡፡ ቃለ መጠይቁ የተደረገላት ሴት አሁን በሕይወት የለቺም፡፡ ለዚህ ነበር እርሷ የሰጠቺውን ቃል ፍለጋ ወደ ሬዲዮ ጣቢያው የሄደው፡፡ ያገኘው ግን የጠበቀውን አልነበረም፡፡ የተቀዳው ቃለ መጠይቅ የለም፡፡ ምነው? አለ ጋዜጠኛው፡፡ ‹‹ብዙ ካሴቶችን እየደመሰስን ቀድተንባቸዋል፡፡ በዚያ ምክንያት ያንን ቃለ መጠይቅ አሁን አታገኘውም›› አሉት፡፡ እርሱም በዚህ አዝኖ ወጣ፡፡
ለነገሩ እርሱ በካሴቱ አዘነ እንጂ ከኢትዮጵያ ታሪክ መገለጫዎች አንዱ እየደመሰሱ መቅዳት ነው፡፡ የሚመጣ መንግሥት ወይም ባለሥልጣን፣ ዐዋቂ ወይም ታዋቂ፣ ታሪክ ጸሐፊ ወይም ዐቅድ ነዳፊ ከእርሱ በፊት ለነበረው ነገር ዋጋ ሰጥቶ፣ የየራሱን ሥራ ከመሥራትና የዘመኑን አሻራ ከማኖር ይልቅ ያለፈውን መደምሰስ ይቀናዋል፡፡ 

ሀገር የማታልቅ ሕንጻ ናት፡፡ መሠረቷ ዛሬ አልተጣለም፡፡ መሠረቷ ከተጣለ ቆየ፡፡ እያንዳንዱ ትውልድ የየራሱን ድርሻ እየገነባ ይቀጥላል፡፡ የመጣው ሁሉ ባለው ላይ አዳብሮ፣ አሻሽሎ ወይም አሣምሮ የሚጨምር ከሆነ ሀገር እያደገች፣ እየበለጸገችም ትሄዳለች፡፡ የመጣው ትውልድ ሁሌም ከሥር ከመሠረቱ የሚያፈርሳት ከሆነ ግን ሀገር ባቢሎን ትሆናለች፡፡ ቅርስ እንጂ ሕይወት፣ ታሪክ እንጂ ዕድገት፣ ስም እንጂ ክብር አይኖራትም፡፡ ለጉብኝት እንጂ ለኑሮ አትሆንም፡፡ 
 ባቢሎን በታሪክ ቀድመው ከሠለጠኑ ሀገሮች ተርታ ነበረቺ፡፡ ነገር ግን የገዛት ሁሉ ከመሠረቷ እያፈረሰ እንደገና ሲሠራት፣ የመጣዉ ሁሉ እየደመሰሰ ሲቀዳባት ይሄው ዛሬም አላልፍላት ብሎ የጦር አውድማ ሆናለቺ፡፡ ስለ ኢራቅ ጥንታዊ ታሪክ የሚተረከውና የዛሬዋ ኢራቅ አይጣጣሙም፡፡ የመጡት ሁሉ በባቢሎን ካሴት ላይ እየደመሰሱ ሲቀዱ፣ መሠረት አልባ ጣራ ሊያቆመ ሲደክሙ፣ አሁን የመጡባት አሸባሪዎች ደግሞ ጨርሰው ታሪካዊ ቅርሶቿን በድጅኖ መናድ ጀመሩ፡፡ እየደመሰሱ መቅዳት ካንሰር መሆን ሲጀምር ይሄው ነው፡፡
ይኼ እፉኝታዊ ጠባይ ነው፡፡ እፉኝት የምትባል የእባብ ዘር አለች አሉ፡፡ አፈ ማኅፀኗ ጠባብ ነው፡፡ ከወንዱ ጋር ስትገናኝ የወንዱን አባለ ዘር ትቆርጠውና ወንዱ ይሞታል፡፡ ልጆቿን በማኅፀኗ ፈልፍላ ስትወልዳቸው ደግሞ ለመውጣት ስለማይችሉ ሆዷን እየቀደዱ እናታቸውን ገድለዋት ይወጣሉ፡፡ ልጆቹ ልጅ የሚሆኑት አባትና እናታቸውን ገድለው ነው፡፡ ያለፈውን ካልደመሰሱ መኖር አይችሉም፡፡
የመጣንበትንና የነበርንበትን ማንጠር ጠቢብነት ነው፡፡ መደምሰስ ግን እፉኝትነት፡፡ ማንጠር ማለት ደግሞ እንደ ቅቤ ነው፡፡ እናቶቻችን ቅቤ የሚያነጥሩት ለሁለት ነገር ነው፡፡ በአንድ በኩል ቅቤው ሲነጠር አንጉላው ተለይቶ ይቀራል፡፡ ቅቤውም ኮለል ብሎ ይወርዳል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ቅመማ ቅመም በመጨመር በቅቤው ላይ ጣዕም ያክሉበታል፡፡ ወይም ቅቤውን ላቅ ወዳለ ሌላ የጣዕም ደረጃ ያሸጋግሩታል፡፡ ማንጠር ሲባል እንደዚሁ ነው፡፡ በታሪካችን፣ በባሕላችን፣ ወይም በልማዳችን ውስጥ እንደ አንጉላ ያሉ ነገሮች ተጨምረው ከሆነ በዕውቀትና ምርምር፣ በግልጽ ወይይትና ክርክር እሳት ላይ ጥዶ ማንጠር ነው፡፡ አንጉላውን ከለየን በኋላ ደግሞ በነበረው እሴታችን ላይ ሌላ እሴት መጨመር፡፡ 
ቅቤን ማንም አያነጥረውም፤ ባለሞያ ይጠይቃል፡፡ አንጉላውን የማስወገጃ መንገዱ ራሱ ልዩ ሞያ ጠያቂ ነው፡፡አንጉላ መስሎን ቅቤዉን ጭምር እንዳያስወግደው እንደ ዶሮ ላባ ባለ ስስ ነገር እየለዩ ማንጠርን ይጠይቃል፡፡
ታሪካችንንና ባሕላችንን፣ ወጋችንንና ልማዳችንን ስንመረምርና አንጉላውን ስንለይ፣ እንደ ቅቤ አንጣሪው በሞያ መሆን አለበት፡፡ ስሜት ቦታ ሊያገኝ አይገባም፡፡ ቅቤ አንጣሪ ስሜት ውስጥ ከገባ ምች ይመታዋልና፡፡ አረሙን እንነቅላለን ብለን ስንዴውን ጨምረን እንዳንነቅለው ጥንቃቄ ያስፈልገዋል፡፡ ለጊዜያዊ የፖለቲካ ፍጆታ ብለን የምንሠራቸው ሥራዎች አዙሪት ውስጥ እንዳይጥሉን ጉዳዩን የሞያና የዕውቀት ጉዳይ ማድረግ ይገባናል፡፡ ‹ዕውቀት አጠር፣ ስሜት መር› ከሆነው ጉዟችን ይልቅ ‹ዕውቀት መር፣ ስሜት አጠር› ወደሆነው ሥልጣኔ ካልወጣን በስተቀር እዚያው ጨለማው ውስጥ ስንኳትን እንኖራለን፡፡ 
ቅቤ አንጣሪ ሰው ሞያ ብቻ ሳይሆን ጥንቃቄም ያስፈልገዋል፡፡ ምች እንዳይመታው፡፡ የቅቤ ምች ያጠናግራል ይባላል፡፡ ቅቤውን በጥንቃቄ ያነጠረቺ ባለሞያ ናት ‹‹ቅቤ አንጣሪዋ እያለቺ ጎመን ቀንጣሿን ምች መታት› ብላ የተሳለቀቺው፡፡ ነባሩን ነገራችንን ስናነጥር ሞያ ብቻ ሳይሆን ጥንቃቄም ወሳኝ ነው፡፡ የዘመን ምች መትቶ እንዳያጠናግረን፡፡ ጎጠኛነት፣ የፖለቲካ ፍጆታ፣ የሥልጣን ፍቅርና ጊዜያዊ ጥቅም የሚባሉ ምቾች አደገኞች ናቸው፡፡ እነዚህ ምቾች የመቱት ሰው ቅቤውን በሚገባ ማንጠር ቀርቶ ሌላ በሽታ በራሱ ላይ ይጨምራል፡፡ ጤነኛ የነበረው አንጣሪ ተጣሞ፣ ዓይኑ ጠፍቶ፣ ፊቱ ቆሳስሎ ይወጣል፡፡ ከዚያ በኋላ እርሱ ያለፈው ታሪኩን ሁሉ የሚያየው በማንጠሪያ ዓይኑ ሳይሆን በተጠናገረ ዓይኑ ነው፡፡ 
አሁን በደምስሶ መቅዳት ሥራ ላይ የተሠማሩት ብዙዎቹ ወገኖቻችን ምች የመታቸው ናቸው፡፡ ዓይነ ልቡናቸውን ምች ስለ መታው ቅቤውንና አንጉላውን መለየት አልቻሉም፡፡ አንጉላ መስሏቸው ሁሉንም ነባር ቅቤ ሊያስወግዱ የቋመጡ ናቸው፡፡ የዛሬውን መንግሥተ ሰማያት ለማሰኘት የትናንቱን ሲዖል ማድረግ፣ የእነርሱን ዘመን የተድላ ዘመን ለማድረግ አላፊውን ዘመን የመከራ ዘመን ማድረግ፣ የአሁኑን አስተሳሰባቸውን ዘመናዊ ለማድረግ ያለፈውን ሁሉ ኋላ ቀር ማሰኘት የግድ ይመስላቸዋል፡፡ ያለፈው የተቀዳበትን ካሴት አዳምጠው ቀጥሎ የራሳቸውን ከመቅዳት ወይም አዲስ ካሴት ከመጠቀም ይልቅ ደምስሰው ካልቀዱ አይረኩም፡፡ አዲስ ሲሠሩ ከሚደሰቱት በላይ ነባሩን ሲያጠፉ የሠለጠኑ ይመስላቸዋል፡፡
ሰው በአንድ ቦታ ስለተሰበሰበ ብቻ ሀገር አይሆንም፡፡ እንዲያ ቢሆን ኖሮ እሥራኤላውያን አሜሪካና ፖላንድ መኖር ይበቃቸው ነበር፤ ለፍልስጤማውያንም ዮርዳኖስና ሊባኖስ የሚኖሩት የካምፕ ኑሮ በቂ ነበር፡፡  ሰፊ መሬት ብቻውንም ሀገርን አይመሠርትም፡፡ እንዲያ ቢሆን ኖሮ አንታርክቲካ ሀገር ይሆን ነበር፡፡ ሀገር ግን ከሰውም ከመሬትም በላይ ናት፡፡ ሰው በመሬቱ ላይ ሲኖር የሠራው ታሪክ፣ ያካበተው ባሕል፣ የደነገገው ወግና ሥርዓት፣ ያዳበረው ቋንቋ፣ ያመጣው ለውጥ፣ የፈጠረው ዘዴ፣ የገነባው ሥነ ልቡና፣ የተከተለው እምነት፣ የእርስ በርሱ መስተጋብር፣ ዓለምን የሚያይበት ርእዮተ ዓለም፣ ሥነ ቃሉ፣ ሌላም፣ ሌላም፣ ሌላም ተዋሕደው የሚፈጥሩት ነገር ነው - ሀገር፡፡ 
 
እነዚህን የተሠራንባቸውን ነገሮች ነው ማንጠር የሚያስፈልገው፡፡ መጀመሪያ እንሰብስባቸው፣ እንመዝግባቸው፣ እንለያቸው፣እንዘግባቸው፣ እንቀርሳቸው፣ እንወቃቸው፡፡ ከዚያ እናጥናቸው፣ እንመርምራቸው፡፡ በመጨረሻም እናንጥራቸው፡፡ ገመዱ ውስብስብ ነው፡፡ ለዘመናት የተፈተለና የተገመደ፡፡ ርጋታ፣ ትዕግሥትና ጥበብ ይጠይቃል፡፡ ወስነን አይደለም ማወቅ ያለብን ዐውቀን ነው መወሰን እንጂ፡፡ አንዳንዴ መጀመሪያ እንወስናለን፣ ከዚያ እንሰይማለን፣ ቀጥለንም እንፈርጃለን፣ በመጨረሻም እንመታለን፡፡ በዚህ ሁሉ ሂደት ውስጥ ግን ዕውቀት፣ ጥናትና ማንጠር ቦታ አይሰጣቸውም፡፡ እንዴው ዝም ብሎ ‹ስቅሎ ስቅሎ› ነው፡፡ ‹ትዕዛዝ ከበላይ፣ እግር ወደላይ› ይሆናል መመሪያው፡፡
 
በዚህ መንገድ ስንቱን እየደመሰስን ቀዳን፡፡ ስንቱን ነባር ዕውቀት ሳንጠቀምበት እንደ ገናሌ ወንዝ ፈስሶ ፈስሶ ቀረ፡፡ ከሞኝ ደጃፍ ሞፈር ይቆረጣል የተባለው በራሳችን ላይ ደርሶ ብልሆቹ አውሮፓውያን የራሳችንን መጻሕፍት ሰብስበው፣ ባሕላችንን አጥንተው፣ ታሪካችንን ፈትሸው፣ ነባር ዕውቀቶችን መርምረው - በውስጣቸው ያገኙትን ጥበብ ለዘመናዊ ሥልጣኔያቸው ተጠቀሙባቸው፡፡ እኛ ግን እየደመሰስን ስንቀዳ፣ አንድም ትናንት ሳይኖረን ዛሬን እናቆማለን ብለን መከራ እናያለን፡፡ በጣም የሚገርመው ግን እኛ የትናንቱን ደምስሰን እየቀዳን፣ የነገዎቹ የኛን አይደመስሱም ብለን ማመናችን ነው፡፡ ይኼንኑ አሠራር አይደል እንዴ የምናቆያቸው፡፡   

የኢሬቻ በዓል በደብረ ዝቋላ እንደሚከበር የተላለፈው ዘገባ ማስተባበያ እንዲሰጥበት ተወሰነ

debra zeq
  • ለአፈጻጸሙ የወረዳው እና የዞኑ አስተዳደር ባለሥልጣናት ሓላፊነት ወስደዋል
  • ከመጋቢት ፭ ክብረ በዓል በፊት ማስተባበያው እንዲተላለፍ ከስምምነት ተደርሷል
  • ከኹሉም አካላት የተውጣጣ የሽማግሌዎች ኮሚቴ የችግሩን ቆስቋሾች ያጣራል
  • በክብረ በዓሉ ቀን የተጠናከረ ጥበቃ እንዲደረግ መመሪያ ተሰጥቷል
* * *
  • ‹‹ለእኛ ዐዲስ ነገር ነው፤ እዚኽ ቦታ ኢሬቻ የለም፤ በአራት ወይም በስምንት ዓመት አንዴ ዝናም እምቢ እንዳይለን ገዳሙን አስፈቅደን ከምንፈጽመው ሥርዐት ውጭ በተነገረው መልኩ የሚከበር በዓል የለም፡፡ ያስተላለፉት መጠየቅ አለባቸው፡፡››
/የአባ ገዳ ተወካዮች/
  • ‹‹ኅብረተሰቡን ከእኛ ጋራ ሊያጣሉ የሚፈልጉ ግለሰብ አመራሮች አሉ፡፡… ለተላለፈው መልእክት ሓላፊነት የሚወስድ አካል ካልተገኘ፣ የመጋቢት ፭ ክብረ በዓል ከመድረሱ በፊት በስሕተት የተላለፈ መኾኑ ይገለጽልን፡፡››
/የገዳሙ አስተዳደር/
  • ‹‹እናንተ ሰላም ፍጠሩ፤ [በክብረ በዓሉ] ከተለመደው ውጭ አንዳችም የሚደረግ አይኖርም፤ ጥበቃውም እንዲጠናከር ይደረጋል፤ የተላለፈውን ዘገባ አጣርተን በኦሮምኛ እና በአማርኛ ማስተባበያ እንዲሰጥበት እናደርጋለን፡፡››
/የዞን የአስተዳደርና ጸጥታ ሓላፊዎች/

2015 ማርች 5, ሐሙስ

በዝቋላ ገዳም ዙሪያ የተቀሰቀሰው የእሳት ቃጠሎ እየተዛመተ ነው


  • የሄሊኮፕተር እገዛ አልያም የውኃ ቦቴ መኪኖች ድጋፍ እየተጠየቀ ነው


በምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት በዝቋላ ደብረ ከዋክብት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም፣ ትላንት ጠዋት የተቀሰቀሰው የእሳት ቃጠሎ አሞራ ገደልበሚባለው አቅጣጫ መዛመቱ ተገለጸ፡፡
በሰሜን በኩል ወንበር ማርያም እየተባለ በሚጠራው የገዳሙ መውጫ ትላንት ጠዋት 2፡00 የተቀሰቀሰው ቃጠሎ፣ በአዱላላ ወረዳ ሠራተኞችና በነዋሪው ሕዝብ ርብርብ ማምሻውን መጥፋቱ ከተገለጸ በኋላ ነው አሞራ ገደል በሚባለው የገዳሙ ደቡባዊ ገጽ በዛሬው ዕለት 5፡00 ላይ ዳግመኛ መቀስቀሱ የተሰማው፡፡
በገዳማውያኑ የጥሩንባ ልፈፋ በተሰባሰበው የገጠሩ ነዋሪና የወረዳው አስተዳደር ሠራተኞች እሳቱን አፈር በማልበስና በቅጠል በመተምተም  ለማጥፋት የተቻለ ቢመስልም አንድ የገዳሙ መነኰስ በስልክ እንዳስረዱት፣ ‹‹በደንብ ሳይጠፋ ቀርቶ የታፈነ ነበር፡፡ ዛሬ አሞራ ገደል ጫካ ውስጥ ገብቷል፡፡ ዛፉ እርጥበት አለው፤ ጢሱ ያፍናል፡፡››  
ቃጠሎው፣ በአካባቢው ከባድ ነፋስ እየበረታ ከገደሉ ሽቅብና ወደ ጎን ወደ አዱላላ አቅጣጫ የተወሰነ የደኑን ክፍልና እዳሪ መሬት እየበላ በአስጊ ፍጥነት እየተስፋፋ እንደሚገኝ ተጠቅሷል፡፡ አኹን ባለው አካሔድ ሳይገታ ወደ ምሥራቅ ከዞረና ጠበል ሜዳውን ካገኘ ወደ ደኑ በጥልቀት ስለሚገባ በእጅጉ አውዳሚ እንደሚኾን የገዳሙ መነኰስ ተናግረዋል፡፡
ከቦታው ገደላማ መልክአ ምድራዊ ገጽታ አንጻር የሚያፍነው ጢስና የቃጠሎው ፍጥነት የመከላከል ሥራውን አስቸጋሪ እንዳደረገው ያስረዱት የገዳሙ መነኰስ፣ አመቺ የሚኾነው አስቸጋሪውን ዐቀበት በመውጣት ለሰው ኃይሉ ውኃ ማቅረብ በሚችሉ መኪኖች አልያም በአየር ርጭትበመኾኑ ከደብረ ዘይት አየር ኃይል የሄሊኮፕተር አልያም የቦቴ መኪኖች እገዛ በሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ በኩል እንዲጠየቅ አመልክተዋል፡፡
የትላንቱን ቃጠሎ ለመከላከል በተደረገው ርብርብ ከደብረ ዘይት ከተማ ተጉዘው ሌሊቱን ቃጠሎው በጀመረበት ስፍራው የደረሱ ምእመናንየእሳቱን መስፋፋት የሚገቱ የመከላከል ሥራዎችን ሲሠሩ አድረው መመለሳቸው ተገልጧል፡፡ የከተማው ሰንበት ት/ቤቶችና የማኅበረ ቅዱሳን የወረዳው ማእከል አባላት፣ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች እንዲኹም ምእመናን÷ መሬቱን ቆፍሮ በአፈር የመከተር፣ ተቀጣጣይ ጉቶዎችንና ቁጥቋጦዎችን የመመንጠር የመከላከል ሥራ እስከ ንጋት ድረስ ሲሠራ ማደሩ ታውቋል፡፡
ዛሬ ቀትር ላይ መዛመቱ የታወቀውን ቃጠሎ ለማጥፋት ከገዳማውያኑ የድረሱልን ጥሪ መተላለፉን የገለጸ አንድ ምእመን፣ በከተማው በስምንቱም አጥቢያ አብያተ ክርስቲያን ሰንበት ት/ቤቶችና በሠርክ ጉባኤያት ምእመናንንና በጎ አድራጊዎችን በመቅስቀስና በማስተባበር በአፋጣኝ ወደ ስፍራው ለመድረስ ጥረት እንደሚደረግ ተናግሯል፡፡


zequulla
በምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊበን ዝቋላ ወረዳ አዱላላ ከተማ በሚገኘው የዝቋላ ደብረ ከዋክብት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም ዙሪያ የእሳት ቃጠሎ መቀስቀሱን የገዳሙ መነኰሳት እየተናገሩ ነው፡፡
ከጠዋቱ 2፡00 ገደማ የተቀሰቀሰው የእሳት ቃጠሎው የጀመረው ወንበር ማርያም እየተባለ በሚጠራው በገዳሙ ሰሜናዊ አቅጣጫ ነው፡፡
ይህ አቅጣጫ፣ የገዳሙ ሞፈር ቤት የሚገኝበት መውጫ መንገድ ሲኾን በአኹኑ ሰዓት በበርካታ ቦታዎች ጭስ እንደሚታይ በመነኰሳቱ ተገልጧል፡፡
የቃጠሎው መንሥኤ በውል ባይታወቅም እሳቱ በአካባቢው ባለው ከባድ የነፋስ ኃይል ወደ ገዳሙ መውጫና በገዳሙ ዙሪያ እንዳይስፋፋ ተሰግቷል፡፡
ziquwala_17የአቅራቢያው ነዋሪ ኅብረተሰብ በጥሩንባ በተላለፈው የድረሱልን ጥሪ የተሰባሰበ ሲኾን ወደ ወረዳው ጽ/ቤትም ተደውሎ የአስተዳደሩ አባሎችና የፖሊስ ኃይል በስፍራው መድረሳቸው ተገልጧል፡፡ ‹‹ቃጠሎውን በቅጠልና በአፈር ለመከላከልና መዛመቱን ለመቀነስ የነፋሱን ጋብ ማለት እየተጠባበቅን ነው ብለዋል፤›› አንድ የገዳሙ መነኰስ፡፡
በጥንታዊውና ታሪካዊው ገዳም ዙሪያ የእሳት ቃጠሎ ሲደርስ የአኹኑ የመጀመሪያ አይደለም፡፡ መጋቢት ፲ ቀን ፳፻፩ ዓ.ም. በደረሰው የእሳት ቃጠሎ እንደ አርዘ ሊባኖስና የሐበሻ ጥድ ያሉት አገር በቀል ዛፎች በስፋት ወድመዋል፡፡ መጋቢት ፰ ቀን ፳፻፬ ዓ.ም. የተቀሰቀሰው ቃጠሎ ደግሞ ተኣምራዊና ግራ አጋቢ ጠባይዕ የታየበት ነበር፡፡ በምሥራቃዊ አቅጣጫ በሚገኘው የመንግሥት ደን ውስጥ ተከሥቶ በአንድ ገጽ ኃይሉ ሲቀንስ በሌላ አቅጣጫ እየተዛመተ ገዳሙን ጨርሶ ለማጥፋት በተቃረበበት ኹኔታ ከአዲስ አበባ፣ ከቢሾፍቱና ከአዳማ በተመሙ የሰንበት ት/ቤት ወጣቶች፣ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች፣ በጎ አድራጊ ምእመናንና አካላት መተባበር እንዲኹም በመከላከያና በፖሊስ ኃይሎች እገዛ መገታቱ የሚታወስ ነው፡፡
በመጪው መጋቢት ወር መጨረሻ በገዳሙ የጠበል – ሐይቅ የኢሬቻን በዓል ለማክበርና በደብረ ዝቋላ የአባ ገዳ ሐውልት ለመትከል በኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት የባህልና ቱሪዝም ቢሮ መታቀዱንና በመንግሥት ብዙኃን መገናኛ መገለጹን ተከትሎ ቤተ ክርስቲያናችን በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ በኩል ለክልሉ ርእሰ መስተዳድር በጻፈችው ደብዳቤ ተቃውሞዋን በማሰማት ላይ እንዳለች ይታወቃል፡፡DSC_0642[1]ጥንታዊውና ታሪካዊው የዝቋላ ደብረ ከዋክብት ጻድቁ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም ዛሬ በሚታወቅበት ቦታ ላይ ከተገደመ ከ700 ዓመታት በላይ አስቆጥሯል፡፡ በገዳሙ ደጅ ጠኚውን፣ አፈር ጠባቂውንና የአብነት ትምህርት መምህራንና ደቀ መዛሙርትን ሳይጨምር እስከ 350 መነኰሳትና መነኰሳዪያት እንደሚገኙበት ተዘግቧል፡፡

ሰበር ዜና:- በዝቋላ ገዳም ዳግም የእሳት ቃጠሎ ተቀሰቀሰ


የካቲት 24 ቀን 2007 ዓ.ም.
በእንዳለ ደምስስ
abune gebre menfes kidus 004በደብረ ከዋክብት ዝቋላ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ አንድነት ገዳም ደን ላይ በዛሬው እለት የእሳት ቃጠሎ መቀስቀሱን ከገዳሙ የደረሰን መረጃ ያመለክታል፡፡

ከተራራው ሥር ከወንበር ማርያም እና አዱላላ አቅጣጫ የተነሳው ቃጠሎ በገዳሙ ደን ላይ ጉዳት ያደረሰ ሲሆን፤ ማኅበረ መነኮሳቱና ተማሪዎች፤ እንዲሁም የአካባቢው ምእመናንን ባደረጉት ርብርብ ለጊዜው አፈር በማልበስ ለማጥፋት ተችሏል፡፡ ነገር ግን በአካባቢው ካለው ነፋሻማና ሞቃታማ አየር ምክንያት ዳግም እንዳይቀሰቀስ ገዳማውያኑ እየተጠባበቁ እንደሚገኙ የገዳሙ አበምኔት አባ ገብረ ማርያም ገልጸዋል፡፡

'ዛሬ ጠዋት እየኾነ ያለው እንዲህ ነው'

2015 ማርች 4, ረቡዕ

የሆሳዕና ደብረ ገነት ቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን ተቃጠለች


አትምኢሜይል
የካቲት 23 ቀን 2007 ዓ.ም.
በዘማች አዩኔ /ከሆሳዕና ማእከል/
001 hosaen mariamበኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሀድያ እና ስልጤ ሀገረ ስብከት የሆሳዕና ደብረ ገነት ቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን የካቲት 21 ቀን 2007 ዓ.ም ከቅዳሴ በኋላ ድንገተኛና ለጊዜው መንስኤው ባልታወቀ ሁኔታ ተቃጠለች፡፡

የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ወርኃዊ በዓል ለማክበር ምእመናን በቤተ ክርስቲያን ተገኝተው የቅዳሴ ሥነ-ሥርዓት እንደተጠናቀቀ እና ቡራኬ ተቀብለው ወደየቤታቸው በተመለሱ በ20 ደቂቃ ውስጥ ካህናት እና ዲያቆናት ገና በደጀ ሰላም እያሉ ከቤተ መቅደሱ ውስጥ ቃጠሎው እንደጀመረም ተናግረዋል፡፡

በወቅቱ ሁሉም የቤተ ክርስቲያኗ በሮች ከውጭ ተቆልፈው ስለነበር ቁልፎቹን በቅርበት ለማግኘት ስላልተቻለ እሳቱን ቶሎ በቁጥጥር ለማዋል አልተቻለም፡፡ በዚህም ምክንያት በውስጥ የነበሩት ንዋያተ ቅድሳት ሙሉ ለሙሉ ወድመዋል፡፡

የደብሩ ካህናትና ዲያቆናት የቤተ ክርስቲያኗን በር ሰብረው በመግባት በዕለቱ ቅደሴ የተቀደሰበትን ታቦት አፈር በማልባስ ከእሳቱ ለመከላከል ተችሏል፡፡

ከተመሠረተች ከአንድ መቶ ዓመት በላይ ያስቆጠረችው ቤተ ክርስቲያን በቃጠሎው ሙሉ በሙሉ ብትወድምም በቤተ መቅደስ ውስጥ የነበሩት ታቦታት ምንም ዓይነት ጉዳት ሳይደርስባቸው በእግዚአብሔር ቸርነት ተርፈዋል፡፡

ከቃጠሎው የተረፉት ታቦታት እሳቱ ከጠፋ ከሦስት ሰዓታት በኋላ በካህናት፣ በዲያቆናት እና ምዕመናን ታጅበው ለጊዜው ወደተዘጋጀላቸው ማረፊያ ገብተዋል፡፡

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሀድያ እና ስልጤ ሀገረ ስብከት የሆሳዕና ደብረ ገነት ቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን የተመሠረተችው በ1901 ዓ.ም ሲሆን፤ አካባቢው በሌሎች የእምነት ድርጅቶችና እና በ ኢ-አማንያን የተከበበ በመሆኑ ምእመናን በሃይማኖት በምግባር ጸንተው እንዲኖሩ በደብሩ በተለያዩ ጊዜያት ጉባኤ በማዘጋጀት የተጠናከረ የስብከተ ወንጌል አገልግሎት ሲሰጥበት የቆየ ቦታ ነው፡፡

e

2015 ፌብሩዋሪ 20, ዓርብ

ከመረጥሁት ጋር ቃል ኪዳኔን አደረግሁ መዝ.88-3

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ለእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከፍተኛ ክብር ትሰጣለች፡፡ ክብሯ ልዕልናዋን ዘውትር በጸሎት፣በምስጋና ትጠራለች፡፡በስሟ በዓላትን ታከብራለች፡፡አጽዋማትን በሰሟ ስይማ ልጆቿ እንዲጾሙ ታረድጋለች፡፡ልጇ ኢየሱስ ክርስቶስ ዓለምን ለማዳን ወደዚህ ዓለም ሲመጣ እርሷ የነበራትን የድኅነት ተሳትፎና ቃልኪዳን ትዘክራለች፡፡ በስሟ ጽላት ቀርጻ፣ቤተክርስቲያን ሰይማ፣በስዓላት፣ በመጻሕፍት አማለጅነቷን ክብሯን ለልጅ ልጅ ታስተላልፋለች፡፡
ከስሟ ጋር ዘርፍ /ቅጽል/ በማድረግ ንጽሕናዋን፣ ቅድስናዋን፣ ድንግልናዋን፣ ወዘተ ይወሳል ፣ይጣራል፣ይጸለያል፡፡ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን አመስጥረው ከተረጐሙት መካከል፡- ምልዕተ ጸጋ፡- እግዚአብሔር አባታችን አዳምን ከፍጥረት ሁሉ አልቆ በአርአያውና በአምሳሉ ፈጥሮት ነበር፡፡ ነገር ግን በኃጢአት ምክንያት የተሰጠው ሙሉ ጸጋ ተገፈፈ፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከፍጥረት ሁሉ ተመርጣ ከእናቷ ማኅፀን ጀምሮ እግዚአብሔር የጠበቃት፣ ያደረባት «የከተመባት ረቂቅ ከተማ» መሆኗን መልአኩ በመሰከረበት ቃል «ምልዕተ ጸጋ» እያልን እንጠራታለን፡፡ ሉቃ.1-26፡፡ እመቤታችን የተለየች ናትና «ጸጋ የሞላብሽ» /የጸጋ ግምጃ ቤት/ ተብላለች፡፡
እምነ ጽዮን፡- እግዚአብሔር ወልድ ኢየሱስ ክርስቶስን አባት «አባታችን ሆይ» ብለን እንደምንጠራው ሁሉ ወላዲተ አምላክንም እናታችን ብለን እንጠራታለን፡፡ ማቴ.6-9፡፡ ቅዱስ ዳዊትም «እምነ ጽዮን ይብል ሰብእ፡ ሰው ሁሉ እናታችን ጽዮን ይላል» በማለት እመቤታችን አማናዊት ጽዮን መሆኗን አስረድቷል፡፡ መዝ.86-5፡፡ እምነ ጽዮን ማለት እናታችን ጽዮን ማለት ነው፡፡ በመጀመሪያይቱ የሰው ልጆች ሁሉ እናት ሔዋን አማካኝነት ከርስታችን ወጥተን መጠጊያ አጥተን ነበር በዳግማዊቱ ሔዋን በድንግል ማርያም ደግሞ ወደ ርስታችን ተመልሰናልና እናታችን ጽዮን እንላታለን፡፡ ጽዮን ማለት አንባ መጠጊያ ማለት ነው፡፡
መጽሐፍ ቅዱስም ድንግል ማርያምን ጽዮን በማለት ይጠራታል፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት «እግዚአብሔር ጽዮንን መርጦአታልና ማደሪያውም ትሆን ዘንድ ወድዶአታልና እንዲህ ብሎ ይህች የዘላለም ማደሪያዬ ናትና በዚህች አድራለሁ፡፡» መዝ.131-13፡፡ በማለት የተናገረው ትንቢት ፍጻሜ ልዑል እግዚአብሔር ከሴቶች ሁሉ ለይቶ ድንግል ማርያምን ለእናትነት የመረጣት መሆኑንና ማደሪያውም ትሆነው ዘንድ የወደዳት መሆኑን የሚያስገነዝብ ነው፡፡ መዝ.47-12፤86-5፡፡
መድኃኒታችን በዕለተ ዓርብ በቀራንዮ በመስቀሉ ላይ ሳለ ለፍቁረ እግዚእ ዮሐንስ «እነኋት እናትህ» በማለት በደቀ መዝሙሩ አማካኝነት እናቱን ድንግል ማርያምን ሥጋውን ለቆረሰላቸው ደሙን ላፈሰሰላቸው ምእመናን እናት ትሆን ዘንድ ሰጥቷታልና ፡፡ ጽዮን የድንግል ማርያም ስም ነውና ጌታችን እናት አድርጎ የሰጠንን እመቤት እምነ ጽዮን /እናታችን ጽዮን/ እንለታለን፡፡
እመ ብርሃን፡- እመ ብርሃን ማለት የብርሃን እናት ማለት ነው፡፡ «እኔ የዓለም ብርሃን ነኝ» ያለውን ብርሃነ ዓለም /የዓለም ብርሃን/ መድኃኔ ዓለም ክርስቶስን የወለደች ናትና የብርሃን እናቱ /እመ ብርሃን/ ትባላለች፡፡ ዮሐ.8-22፡፡ ጌታውን ይወድድ የነበረና ጌታውም ይወደው የነበረ የከበረ ደቀ መዝሙር ቅዱስ ዮሐንስ «ለሰው ሁሉ የሚያበራው እውነተኛው ብርሃን ወደ ዓለም ይመጣ ነበር፡፡» በማለት የመሰከረለትን ጌታ በብሥራተ መልአክ በግብረ መንፈስ ቅዱስ አማናዊውን /እውነተኛውን/ ብርሃን ጌታችንን ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን ጸንሳ የወለደች በመሆኗ እመ ብርሃን እንላታለን፡፡ ሊቁ «እመ ብርሃን አንቲ ነዓብየኪ በስብሐት ወበውዳሴ፡- አምላክን የወለድሽ እመቤታችን ሆይ የብርሃን እናት ነሽና አንቺን በክብር በምስጋና እናገንሻለን» በማለት እንዳመሰገናት፡፡
ሰአሊተ ምሕረት፡- ሰዓሊተ ምሕረት ማለት ምሕረትን የምትለምን ማለት ነው፡፡ በቅዱስ ገብርኤል ምስክርነት እንደምናገኘው ድንግል ማርያም በእግዚአብሔር ፊት ሞገስን ያገኘች እመቤት ናትና ልመናዋ /ምልጃ ጸሎቷ/ ይሰማል የእናት ልመና አንገት አያስቀልስ ፊት አያስመልስ ነውና፡፡ ሉቃ.1-30፡፡
በእግዚአብሔር ፊት ሞገስ ያገኙ ቅዱሳን ምሕረት ቸርነትን ለምነው አግኝተዋል፡፡ ዘፍ.18-3፣ 23-32፡፡ እግዚአብሔር ሙሴን በፊቴ ሞገስን ስላገኘህ በስምህ ስላወቅሁህ ስለ ሕዝቡ የለመንኸኝን ሁሉ አደርጋለሁ ብሎታል፡፡ ዘጸ.33-12-20፡፡ «ስለ ሙሴ ቃልም ዘወትር ለሕዝቡ ይራራላቸው ነበር» ዘጸ.32-11-14፡፡ ሙሴ በእግዚአብሔር ፊት ሞገስ በማግኘቱ በለመነ ጊዜ እግዚአብሔር እንደ ቃልህ ይቅር አልሁ ይለው ነበር፡፡ ዘኁ.14-20፡፡ በመልአከ ብሥራት በቅዱስ ገብርኤል «በእግዚአብሔር ፊት ሞገስ አግኝተሻል» ተብሎ የተመሰከረላት ድንግል ማርያም የተሰጣት ሞገስ እንደ እናትነቷ ከሁሉ የበለጠ በመሆኑ አጠያያቂ አይደለምና ሰአሊተ ምሕረት እንላታለን፡፡ ማርያም ንጽሕት ድንግል ወላዲተ አምላክ ዠማዕምንት ሰአሊተ ምህረት ለውሉደ ሰብእ፡- ንጽሕት ድንግል ማርያም የታመነች አምላክን የወለደች ናት ለሰዎች ልጆችም የምሕረት አማላጅ ናት» /ውዳሴ ማርያም ዘዓርብ አንቀጽ 6/
እመቤታችን፡- እመቤት ማለት በአንድ ቤተሰብ መካከል አስተዳዳሪና ሓላፊ የሆነች ታላቅ ሴት ማለት ነው፡፡ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን «ማርያም» የሚለውን በምሥጢራዊ ዘይቤ ሲተረጉሙ እግዝእተ ብዙኃን /የብዙኀን እመቤት/ ብለው ተርጉመውልናል፡፡
በአዳምና በሄዋን አማካኝነት ወደ ዓለም የገባውን መርገም የሻረ ጌታ እግዚአብሔር ከእርስዋ በመወለዱ እምቤታችን /የብዙዎች እመቤት/ ትባላለች፡፡ ሮሜ.5-6-11፡፡ እንዲሁም ዓለም ሁሉ በዳነበት በክርስቶስ የማዳን ሥራ ያመን ክርስቲያኖች ሁሉ በክርስቶስ አንድ ቤተሰብ በመሆናችን ቅድስት እናቱ ድንግል ማርያም እመቤታችን ናት፡፡ ዮሐ.19-26፡፡ ልጇ ጌታችን ነውና እርሷም እመቤታችን ናት፡፡ ሉቃ.1-43፡፡
ቤዛዊተ ዓለም፡- የዓለም መድኃኒት ማለት ነው ድንግል ማርያም የዓለም መድኃኒት ኢየሱስ ክርስቶስን ያስገኘችልን በመሆኗ ቤዛዊተ ዓለም እንላታለን በልጇ ቤዛነት ድነናልና፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለቤዛ ዓለም /ለድኅነተ ዓለም/ በቀራንዮ ኮረብታ የቆረሰው ሥጋ ያፈሰሰው ደም ከድንግል ማርያም የነሣው በመሆኑ ቤዛዊተ ዓለም ትባላለች፡፡ ዕብ.9-22፡፡ የሕያዋን ሁሉ እናት ድንግል ማርያም ለሔዋን ካሣዋ እንደሆነች ሁሉ ለአንስተ ዓለም ሁሉ ካሣ ቤዛ ናት ስድበ አንስትን ወቀሳ ከሰሳ አንስትን አስቀርታለችና፡፡ እንዲሁም ለዓለሙ ሁሉ የምታማልድ በልመናዋ ፍጥረትን የምታስምርና መንግሥተ ሰማያት መርታ የምታስገባ በመሆኗ ቤዛዊተ ዓለም እንላታለን፡፡
ወላዲተ አምላክ፡- ወላዲተ አምላክ ማለት አምላክን የወለደች ማለት ነው፡፡ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል «ከአንቺ የሚወለደው ቅዱሱ የእግዚአብሔር ልጅ ይባላል፡፡» በማለት የጌታችንን አምላክ ወልደ አምላክነት የድንግል ማርያምን እመ አምላክ ወላዲተ አምላክነት አስረድቶአል፡፡ ሉቃ.1-35 ቅድስት አልሳቤጥም «የጌታዬ እናት ወደ እኔ ትመጣ ዘንድ እንዴት ይሆንልኛል?» ሉቃ.1-44 በማለት እንዳስረዳችው ድንግል ማርያም ጌታችንን የወለደች የጌታችን እናት ናትና ወላዲተ አምላክ እንላታለን፡፡ ድንግል ማርያም «ወላዲተ አምላክ» «አምላክን የወለደች» ተብላ እንድትጠራ ለመጀመሪያ ጊዜ በ431 ዓ.ም በኤፌሶን ከተማ በ200 ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን አማካኝነት ተዘጋጅቶ በቅዱስ ቄርሎስ አፈ ጉባኤነት የተመራው 3ኛው ዓለም አቀፋዊ የቤተ ክርስቲያን ሲኖዶስ ነው፡፡

በዚህ ጉባኤ የቀረበው የንስጥሮስ የክህደት ትምህርት «ድንግል ማርያም ወላዲተ አምላክ ልትባል አይገባትም» የሚል ሲሆን ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ንስጥሮሳዊውን ትምህርት አውግዘው ድንግል ማርያም ቅድመ ዓለም የነበረውን አምላክ ለዘመን በሥጋ ስለወለደችው በእውነት አምላክን የወለደች /ወላዲተ አምላክ/ ናት በማለት ትምህርተ ሐዋርያትን አጽንተዋል፡፡

በቤተ ልሔም በከብቶች ግርግም ከድንግል የተወለደው የዓለም ፈጣሪ እግዚአብሔር ነው፡፡ ስለዚህ ድንግል ማርያም ፣ እመ እግዚአብሔር ፣ ወላዲተ አምላክ ተብላ ትጠራለች፡፡ 1ዮሐ.5-20፤ ቲቶ.2-13፡፡

ቅድስተ ቅዱሳን፡- ይህ ስም ከፍጡራን በላይ ከፈጣሪ በታች ለሆነች ቅድስት ድንግል ማርያም ንጽሕናና ቅድስና መገለጫ ሆኖ የተሰጣት ልዩ ስም ነው፡፡ ቅድስተ ቅዱሳን ማለት ከተለዩ የተለየች ከተመረጡ የተመረጠች፣ ከተከበሩ የተከበረች ማለት ነው፡፡ ሊቁ ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊ ድንግል ማርያምን ባመሰገነበት ክፍል ተሰመይኪ ፍቅርተ ኦ ቡርክት እምአንስት አንቲ ውእቱ ዳግሚት ቀመር እንተ ትሰመይ ቅድስተ ቅዱሳን፡- ከሴቶች ሁሉ ተለይተሽ የተባረክሽ ሆይ የተወደድሽ ተባልሽ ከተለዩ የተለየሽ» በማለት ቅድስናዋን መስክሯል /የእሑድ ውዳሴ ማርያም አንቀጽ 1/
ከአንስተ ዓለም ተለይተው ቅድስናን ገንዘብ ያደረጉ በርካታ ሴቶች ቢኖሩም ድንግል ማርያም ግን የነዚህ ሁሉ ፊት አውራሪ /ግንባር ቀደም/ እና ከሌሎች አንስት የተለየች ቅድስት /ቅድስተ ቅዱሳን/ ትባላለች፡፡ «አንቺ ከሴቶች ሁሉ ተለይተሽ የተባረክሽ ነሽ» በማለት መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል መስክሮላታል፡፡ ሉቃ.1-28፡፡ ከዚህም ጋር በተግባረ ቃል ቅዱስ ኤፍሬም በውዳሴው «የዐቢ ክብራ ለማርያም እምኲሎሙ ቅዱሳን፡- ከቅዱሳን ክብር የማርያም ክብር ይበልጣል» / ዘረቡዕ ውዳሴ ማርያም አንቀጽ .7/ በማለት የድንግል ማርያምን ቅድስና መስክሯል፤ ከዚህም የተነሳ በከበረ ስሟ ቅድስተ ቅዱሳን እያልን እንጠራታለን፡፡
ንጽሕተ ንጹሐን፡- ነጽሐ ነጻ ካለው ግሥ የወጣ ሲሆን ንጽሕት ማለትም የነጻች የጠራች ማለት ነው፡፡ ቅዱሳት መጻሕፍት ስለ ንጽሕና «ዘንጹሕ ልቡ ወንጹሕ እደዊሁ፡- እጆቹም ልቡም ንጹሕ የሆነ»፣ «ብፁዓን ንጹሓነ ልብ ወይለብሱ ንጹሐ፡- ልበ ንጹሖች ብፁዓን ናቸው ንጽሕናን ይለብሳሉ»፣ «ሕያዋት ወንጹሓት፡- ሕያዋንና ንጹሓን»፣ «ንጽሕት ወብርህት፡- የነጻች የምታበራ» በማለት የንጽሕናን ሁኔታ ያስረዳሉ፡፡ መዝ.23፣ ማቴ.5-8፣ ራእ.15፣ ዘሌ.14-4፡፡ ውዳሴ ማርያም ዘአርብ፡፡
በዚህ ዓለም ከሚኖሩ ሴቶች የልማደ አንስት ኃጢአት ሰውነታቸውን ያላጐደፋቸው ወይም ያላረከሳቸው ብዙዎች ናቸው፡፡ ይሁንና ከገቢረ ኃጢአት ንጹሓን ይሁኑ እንጂ ከነቢብና ከሐልዮ ኃጢአት /በመናገርና በማሰብ ከሚሠራ ኃጢአት/ አልነጹም፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ግን ከገቢር ከነቢብ ከሐልዮ ኃጢአት ንጽሕት ስለሆነች ንጽሕተ ንጹሐን እንላታለን፡፡
ወትረ ድንግል /ዘላለማዊት ድንግል/፡- ቅድስተ ቅዱሳን ወላዲተ አምላክ ማርያም ጌታን ከመጽነሷ በፊት፤ ጌታን በጸነሰች ጊዜ፤ ከጸነሰችም በኋላ፤ ከመውለዷ በፊት፤ በወለደች ጊዜ፣ ከወለደች በኋላ ድንግል ናት ከዚህም የተነሳ ድንግል ዘላለም እንላታለን፡፡ ክህነትን ከነቢይነት ጋር አስተባብሮ የያዘው ሕዝቅኤል ዘላለማዊ ድንግልናዋን መስክሯል፡፡ ሕዝ.44-1-2፡፡
የአንጾኪያው ሊቀ ጳጳስ ቅዱስ ሳዊሮስ ስለ ቅድስት ድንግል ማርያም ዘላለማዊ ድንግልና በተናገረበት ክፍል «አምላክን የወለደች ማርያም ለዘለዓለሙ ድንግል እንደሆነች መውለዷም የማይመረመር ድንቅ እንደሆነ ከወለደችም በኋላ በድንግልና ጸንታ እንደኖረች አስረዳን» በማለት ስለ ዘላለማዊ ድንግልናዋ መስክሯል፡፡ ኢሳ.7.14፤ ሉቃ.1.27፡፡
ድንግል በክልኤ፡- በሁለት ወገን ድንግል ማለት ነው፡፡ በሁለት ወገን በሥጋም በነፍስም በሐልዮ /በሐሳብ/ በገቢር /በመሥራት/ በውስጥ በአፍአ ድንግል መሆኗን ያመለክተናል፡፡
ሌሎች ሰዎች ከገቢር ከነቢብ ቢጠበቁ ከሐልዮ /ከሃሳብ/ ኃጢአት መጠበቅ ግን አይቻላቸውም፡፡ ድንግል ማርያም ግን በሁለት ወገን ንጽሕት ቅድስት ናት ስለዚህ ድንግል በክልኤ /በሁለት ወገን ድንግል/ ትባላለች፡፡


ድንግል ወእም፡- እናትም ድንግልም ማለት ነው፡፡ እናትነትን ከድንግልና ጋር አስተባብሮ መገኘት ለፍጥረታዊ ሰው የማይቻል ቢሆንም ድንግል ማርያም ግን ሁለቱንም አስተባብራ ይዛለችና ድንግል ወእም ትባላለች፡፡
ሴቶች በልጅ ጸጋ ከከበሩ ድንግልናቸውን ያጣሉ በድንግልና ተወስነው ጸጋ እግዚአብሔርን ለማግኘት ከወሰኑ ደግሞ ከልጅ ጸጋ ይለያሉ፡፡ ሁለቱንም አስተባብረው ይዘው መገኘት አይሆንላቸውም፡፡ ድንግል ማርያም ግን ድንግልናን ከእናትነት እናትንትን ከድንግልና ጋር አስተባብራ ይዛ የተገኘች በመሆንዋ ድንግል ወእም እናትም ድንግልም ሆናለች፡፡ ሉቃ.1-26-38፡፡
ልጇ ክርስቶስም አምላክ ወሰብእ /ፍጹም አምላክ ፍጹም ሰው/ ሲባል እንዲኖር እርሷም ድንግል ወእም ስትባል ትኖራለች ስትወልደው ማኅተመ ድነግልናዋ እንዳልተለወጠ ሁሉ ባሕርየ መለኮቱ አልተለወጠም «እኔ እግዚአብሔር አልለወጥም» እንዳለ፡፡ ሚል.3-6፡፡


ኪዳነ ምሕረት፡- የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር መዓቱን በምህረት ቁጣውን በትዕግሥት በመመለስ የሰውን ሕይወት ለዘለዓለሙ ለመጠበቅ በመጀመሪያ ከስህተቱ በንስሐ ከተመለሰው ከአዳም፣ ቀጥሎም ከጻድቁ ከኖኅ፣ ከዚያም በእምነትና በምግባሩ ቀናነት የእግዚአብሔር ወዳጅ ተብሎ ከተሰየመው ከአብርሃም.... ከሌሎችም ቅዱሳን ጋር ለመላው የሰው ዘር የሚሆን የምህረትና የበረከት ቃል ኪዳን ገብቷል፡፡
«ከመረጥሁት ጋር ቃል ኪዳኔን አደረግሁ» መዝ.88-3 በማለት በተናገረው መሠረት ከምርጦቹ ጋር ቃል ኪዳን የሚያደርግ ልዑል አምላክ ከተመረጡ የተመጠረች በመሆኗ /ዋ/ ከእናቱ ከቅድስት ድንግል ማርያም ጋር የካቲት 16 ቀን ቃል ኪዳን ሰጥቷታል፡፡ ለዚህም በየዓመቱ የካቲት 16ቀን በዓለ ንግሥ ወር በገባ በ16 ቀን ወርኃዊ በዓሏን እናከብራለን፡፡
ይህንንም ለማመልከት ኪዳነ ምሕረት /የምሕረት ቃል ኪዳን የተቀበለች/ ትባላለች፡፡ በዚህም ምክንያት፡-
በእንተ ማርያም መሐረነ ክርስቶስ 
ቅድስት ሆይ ለምኝልን
በእንተ ስማ ለማርያም ወዘተ
በማለት የተሰጣትን ቃል ኪዳን መማጸኛ በማድረግ እንጠራታለን፡፡ ምሳሌዋ የሆነች ሐመረ ኖኅ /የኖኅ መርከብ/ በተሰጣት ቃል ኪዳን ከማየ አይኅ /ከጥፋት ውኃ/ ነፍሳትን እንደ አዳነች ቅድስት ድንግል ማርያምም በተሰጣት ቃል ኪዳን ከመከራ ሥጋ ከመከራ ነፍስ ታድነናለችና ኪዳነ ምሕረት /የምሕረት ቃል ኪዳን/ የተሰጠሽ እንላታለን፡፡


ከላይ የተጠቀሱት ሁሉም ምሥጢራዊና ትርጉም ያላቸው የእመቤታችን ስሞች የተገለጹት /የተነገሩት/ በራሱ በልዑል እግዚአብሔር እንዲሁም በቅዱሳን ነቢያት፣ በቅዱሳን ሐዋርያት፣ በቅዱሳን ጻድቃን ሰማዕታትና በሌሎችም ቅዱሳን አባቶች ነው፡፡
ይህም ምሥጢር የትምህርተ ሃይማኖት አንዱ አካል ሲሆን እኛም በቅዱሳን የተገለጸውን የእመቤታችንን ምሥጢራዊና ትርጉም ያላቸው ስሞች ተረድተን የትምህርተ ሃይማኖት ዕውቀታችንን ልናሳድግ ቅድስት ድንግል ማርያምንም ልናከብር እንዲገባን መገንዘብ አለብን፡፡ የቅዱሳንም አስተምህሮት ይህ ነውና፡፡
ረድኤቷ፣ በረከቷ፣ አማላጅነቷ አይለየን፡፡


አትምኢሜይል

                                   በአውሮጳ   የካህናት አንድነት ማኅበር ሊቋቋም መሆኑ ታወቀ በ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከመላዋ አውሮጳ   የተውጣጡ ካህናት፡” የ...