2015 ኤፕሪል 15, ረቡዕ

ኹራፋተ አምሳሉ ፡- መረጃና ማስረጃ አልባው እንቶፈንቶİ


                                                ዲ/ን ዶክተር መሐሪ ወሰን /ከጅማ/
ዶክተር ደረጄ ዓለማየሁ ይባላሉ፡፡መጋቢት 1992 ዓ.ም. ‹‹ በአጭር የተቀጨ ረጅም ጉዞ፡- መኢሶን በኢትዮጵያ ሕዝቦች ትግል ውስጥ›› በሚል ርእስ በአቶ አንዳርጋቸው አሰግድ ተዘጋጅቶ በታተመው መጽሐፍ ውስጥ የጽሑፍ ድርሻ ነበራቸው፡፡ ይኸውም መቅድም መጻፍ ነበር፡፡ በጻፉት መቅድም ውስጥ በጥላቻ ቁመናው ከኹራፊው አምሳሉ ገብረ ኪዳን ጋራ ተመሳሳይ የሆነ ሰውን የጥላቻ ክርክር ጠቅሰዋል፡፡ እንዲህ ጽፈውታል፡፡
በደርግ ዘመን በየጊዜው ጤፍ ከአዲስ አበባ ይጠፋ እንደነበረ የሚታወስ ነው፡፡ በዚያው ዘመን ከአንድ የማውቀው (የተማረ) ሰው ጋር ጨዋታ ጀመርንና ጤፍ የጠፋው በአንቶኖቭ እየተጫነ ወደ ሶቭዬት ኅብረት ስለሚጓዝ ነው፤ አለኝ፡፡ ‹‹ራሽያኖች እንጀራ መብላት ጀመሩ እንዴ?›› ብዬ ጠየቅሁት፡፡ ‹‹አይ ለቮድካ ሊጠቀሙበት ነው፤አለኝ›› መልሶ፡፡ ‹‹ኧረ ተው ኢትዮጵያ ውስጥ በዓመት የሚመረተው ጤፍ በሙሉ ወደ ሶቭዬት ኅብረት ቢጋዝ እዚያ በአንድ ቀን የሚወጣውን ቮድካ ለመጥመቅ አይበቃም፤›› አልኩት፡፡ ‹‹ አይ እንደ ቅመም ሊጠቀሙበት ነው አሉ፤›› አለኝ፡፡ ‹‹ተው እንጂ እንደ ቮድካ፣ እደ ውስኪ ያሉት ስመ ጥሩ መጠጦች ሲጠመቁ ዋናው ጥበብ እኮ ለዘመናት ተለምዶ የቆየ ጣዕማቸው እንዳይቀየር ማድረግ ነው፤ ስለዚህ ገና ያልተለመደ፣ ኢትዮጵያ ውስጥ ብቻ የሚገኝ ቅመም ለመጨመር ምክንያት የሚኖራቸው አይመስለኝም፤ ብዬ ይህን የማይረባ ክርክር ዘጋሁ፡፡ (ደረጀ፤1992፣2)
በዚያን ወቅት ከዚህ ሰው ጋር ሶቭዬት ኅብረት በዓለም አቀፍ ደረጃና በተለይ በሀገራችን የምትከተለውን ፖለቲካ በሚመለከት ተቃሞውን (ኧረ እንደውም ጥላቻውን) ለመጋራት ችግር አልነበረብኝም፤ የሚሉት ዶክተር ደረጄ ዓለማየሁ፤‹‹ለእኔ ግን ይህን አቋም ለማጠናከር ሩሲያን በጤፍ ሌብነት መክሰስ አያስፈልገኝም ነበር፡፡ ይህ ወዳጄ ግን ለሩሲያ ተቃውሞውና ጥላቻው በምንም ላይ ያልተመሠረቱ ግምቶችን ጭምር መሰብሰብ ነበረበት፡፡ ከዚያም አልፎ ሩሲያ የተወሰነው የዓለም ክፍል ጨቋኝና በዝባዥ ነች፤ የጤፍ ሌባ ግን አይደለችም፤ ያለውን (ሁሉ) በሶቭዬት ኅብረት ደጋፊነት ከመክሰስ አይመለስም ነበር፡፡›› ብለዋል፡፡ ‹‹መረጃ ላይ መመሥረት ያለበትን ታሪክ ነክ ወይም ፖለቲካ ነክ ክርክር ከእንደዚህ ዓይነት ሰው ጋር ማካኼድ አይቻልም›› ሲሉም አክለው ያስረዳሉ፡፡ (ደረጀ፤1992፣2)
ከዚህ አኳያ ኹራፊው አምሳሉ ገብረ ኪዳን ከዶክተር ደረጄ ዓለማየሁ ወዳጅ የሚለየው፤ ከዐሥራ ሁለተኛ ክፍል የዘለቀ ትምህርት የሌለው የትምህርት ሽፍታ፣ በሠዓሊነቱም ስሙን እንደማዓረግ ይጠቀምበት ካልሆነ ከተግባሩ የሌለበት እና አማተር ፖለቲከኛ መሆኑ ብቻ እንጂ በጥላቻ ቁመናው በእጅጉ ይመሳሰላል፡፡
 ዲያቆን ዳንኤል ክብረት የቱንም ያህል የሥርዓቱን ታሪካዊና ሃይማኖታዊ ጠላትነቱን የሚገልጹ ጽሑፎች ቢጽፍም፣ ቃለ መጠይቆችን ቢሰጥም፣ በኹራፊው አምሳሉ ደረጃ ወርዶ ወያኔን ‹‹የጤፍ ሌባ ነው›› ዓይነት ክስ እስካልከሰሰ ድረስ፤ ዳንኤልን በወያኔነት ከመክሰስ የማይመለስ ኹራፊ መሆኑን የሚያጋልጡ ሦስት ጽሑፎችን ከሰሞኑ አነበብኩ፡፡ የመጀመሪያው ‹‹ በአይሁዶች መርዘኛ ጥርስ የገባች ሀገር ኢትዮጵያ ! ››በተሰኘ ፀረ ሴማዊነት ርእስነት የለጠፈብንን ነው ፡፡ ሁለተኛ ‹‹የሀገርና የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ጠላት ስውሩ ተኩላ ዳንኤል ክብረት›› በሚል ድልዝ ‹ርእስነት› የለጠፈውን የሐሳብ ውራጅ ሲሆን፤ ሢሰልስ ደግሞ ‹‹ዳንኤል ክብረትና ሌላው የወያኔያዊ ተግባሩ መግለጫ›› በሚል የተደባጨ ‹ርእስነት› የሰነቀረውን የአስተሳሰብ ስብራቱ ነው፡፡
በሐሳብ ውራጅ እና በአስተሳሰብ ስብራት ውስጥ የሚገኝ ኹራፊ ፍጥረት መሆኑን ያጋለጠበትን ቁርጥራጮች አንብቤ ስጨርስ ሦስት ዓይነት ስሜቶች ተሰምተውኛል፡፡ የመጀመሪያው የሐዘን ነው፡፡ የወያኔን የጥፋት ሥርዓት በተላላኪነትና በአስተኳሽነት እያገለገሉ የሚገኙት እንደ አምሳሉ ገብረ ኪዳን ዓይነት ኹራፊዎች ለቤተ ክርስቲያኒቱ ልዕልናና ክብር መመለስ አበክረው በሚታገሉት እንደ ዲያቆን ዳንኤል ክብረት ያሉትን ቁርጥ የቤተ ክርስቲያንና የሃገር ልጆች በወያኔነት ሲፈርጆ ማየት እጅግ ያሳዝናል፡፡
ሁለተኛው የመደነቅ ነው፡፡ ትናንት ከአጉራ ዘለል ባሕታውያን ነን ከሚሉት ጋራ፣ ዛሬ ደግሞ አሸናፊ መኮንንን ከመሳሰሉት የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ መናፍቃንና ውጉዛን ጋራ በመወዳጀት የቤተ ክርስቲያኒቱን መሠረተ እምነት፣ ሥርዓተ አምልኮ፣ ትውፊትና ታሪክ በስውር እየቆነጻጸለ፣ እየቀሰጠ የሚገኘው ጎጠኛው አምሳሉ ገብረ ኪዳን፣ የዘመናችን ርቱዕ ሃይማኖትና ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ጠበቃ የሆነውን ዲያቆን ዳንኤል ክብረትን በሀገርና በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ጠላነት ፈርጆ ሃይማኖቱን ሲጠራጠር ከመመልከት በላይ ምን ይደንቅ?
ሦስተኛው ደስታ ነው፡፡ ደስታው ደግሞ ስለ ሁለት ነገር ነው፡፡ አንደኛው ኹራፊው መምህራችንን ዲያቆን ዳንኤል ክብረትን አጋጣለሁ ብሎ በጻፈው ቁርጥራጭ ራሱን ማጋለጡ ነው፡፡ ሁለተኛው ደግሞ ራሱን በፀረ ወያኔነት ቆብ የገለጠው አምሳሉ ከማኅበረ ቅዱሳን አባላት እስከ ኤልያስ ገብሩ ያሉትን ወንድሞች እንዲሰልል የተሰጠውን ተልእኮ ሳይጨርስ፤ ከዚህ በኋላሰለአርሱ በተከታታይ እንድንጽፍ ምክንያት የሆነችውን አብሪ ጥይት ተኩሶ እኛን በመጋበዙ ነው፡፡ እነዚህ ሦስት በተጨባጭ እውነታ የተመሠረቱትን ስሜቶቼን ከግንዛቤ በማስገባት ለዛሬ በዋናነት ሦስቱን ቁርጥራጭ ‹‹ጽሑፎቹን›› ከእውነትነት፣ ከታሪካዊ ሁነት፣ ከቤተ ክርስቲያን ትምህርትና ከፖለቲካዊ ቅሌት አንፃር ብቻ በመፈተሽ ተጋላጩ ዲያቆን ዳንኤል ክብረት ወይስ ኹራፊው አምሳሉ ገብረ ኪዳን የሚለው ወሳኝ ጥያቄ በመመለስ ጽሑፌን እደመድማለሁ፡፡
1 - በተቆርቋሪነት መለዮ የተሰነቀረ ኑፋቄ!
ኹራፊው አምሳሉ ገብረ ኪዳን የጌታችን የመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በዓለ ልደት አስመልክቶ በፌስ ቡክ ገጽ ላይ፤     ‹‹ … የመውለጃዋ ጊዜ በደረሰ ጊዜ ጌታዋ ፈጣሪዋ የኋላ ልጇ ለመለኮታዊ ክብሩ፣ ለልዑልነቱ፣ ለሁሉን ቻይነቱ፣ ለፈጣሪነቱ፣ ንጹሕ ነገር ፈላጊ፤ ለንጹሐ ባሕርይነቱ በምትስማማ መልኩ ምንም ምክንያት እንዳይገኝባት አድርጎ ንጹሕ ጽዱ ፍጹም ቅድስት አድርጎ ፈጥሮ አዘጋጃትና ሰዓቱ ሲደርስ ያንን ንጹሕ ፍጹም ጽዱ ሥጋዋን ወርሶ ተወለደባት ፤ በዚህ ሥጋውም ዓለሙን ሁሉ ተቤዠው፡፡›› የሚል ኑፋቄን ከእውነተኛው ትምህርት ጋራ የቀየጠ ጽሑፍ አስፍሮ ነበር፡፡
በዚህ ጽሑፍ ውስጥ ሦስት መሠረታዊ የኑፋቄ ትምህርቶች አሉበት፡፡ የመጀመሪያው ‹‹የኋላ ልጇ›› የሚለው ነው፡፡ እመቤታችን ድንግል ማርያም ከጌታችን ከመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በፊት ሌላ ልጅ እንደአላት አድርጎ ጌታችንን ‹‹የኋላ ልጇ›› ሲል ኑፋቄውን ጽፏል፡፡ በቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮ መሠረት እመቤታችን ድንግል ማርያም ምስጋና ይግባትና ተከታይም ሆነ ቀዳሚ ከሌለው ከጌታችን ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ውጪ ሌላ የበኩር ልጅ የላትም፡፡ በዚህም ‹‹ በኩር›› የሚለው ቃል አንድ ወልድ በቀዳማዊ ልደቱም ሆነ በደኀራዊ ልደቱ ተቀዳሚ ተከታይ ተመሳሳይ እኩያ የሌለው መሆኑን የሚያስረዳ ነው፡፡
ኹራፊው አምሳሉ ገብረ ኪዳን እንዲህ አድርጎ ያቀረበውን ኑፋቄያዊ አስተምህሮ ዲያቆን ዳንኤል ክብረት በቤተ ክርስቲያ አስተምህሮ መሠረትነት ‹‹ኦርቶዶክስ መልስ አላት›› በሚል ርእስ ከፕሮቴስታንቶች ለሚነሡ አንዳንድ ጥያቄዎች በሰጠው የመልስ መጽሐፍ ውስጥ እምነቱ የአደረገውን የቤተ ክርስቲያኒቱን እምነት እደሚከተለው ገልጧል፡፡
‹‹ የበኩር ልጅ ማለት መጀመሪያ የተወለደ ማለት ነው፡፡ ወይም የእናቱን ማኅፀን የሚከፍት ማለት ነው፡፡ ‹ በእስራኤል ልጆች ዘንድ ከሰውም ከእንስሳትም ማኅፀን የሚከፍት በኩር ሁሉ ለእኔ ቀድስልኝ፤ የእኔ ነው፤› ዘፀ. 13 ፥ 2፤ ይህ ትእዛዝ የሚፈጸመው ሌላ ልጅ እስኪወለድ ድረስ ተጠብቆ ሳይሆን ወዲያው ልጅ እንደተወለደ ነው፡፡ ምክንያቱም ያን ልጅ በኩር ለማሰኘት የግድ ሌላ ልጅ በቀጣይ መወለድ የለበትምና፡፡ አባ ሄሮኒመስ ይህንን የበለጠ ሲያብራራው፤‹ ለእናቱ አንድያ የሆነ ልጅ ሁሉ በኩር ነው፤ በኩር ሁሉ ግን አንድያ አይደለም፤›› (ዳንኤል፣2002፣89)
ከዚህም በተጨማሪ ዲያቆን ዳንኤል፤ እመቤታችን ጌታን ከመውለዷ በፊት ይቅርና በኋላም ልጅ እንዳልወለደች፤ የቤተ ክርስቲያችንን ትምህርት መሠረት በማረግ፤‹‹ እመቤታችን… ልጆች ቢኖሯት ኖሮ በአደራነት ለዮሐንስ ወንጌላዊዉ ባልተሰጠች ነበር፡፡ (ዮሐ. 19 ፥ 25) ጌታችን ዐሥራ ሁለት ዓመት ልጅ ሆኖ ከእመቤታችን እና ከዮሴፍ ጋር ወደ ቤተ መቅደስ በወጣ ጊዜ ዮሴፍ፣ እመቤታችን እና ጌታችን ብቻ ነበሩ፤ (ሉቃ. 2 ፥ 43)፡፡ በዐሥራ ሁለት ዓመታት ውስጥ ያልተወለዱ ልጆች ከየት ይመጣሉ?›› ሲል መልስ ሰጥቷል፡፡ (ዳንኤል፣2002፣96)
ሁለተኛው የኹራፊው አምሳሉ ኑፋቄ፤‹‹ ሥጋዋን ወርሶ ተወለደባት›› የሚለው ነው፡፡ በኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችን፤‹‹ሥጋዋን ነሥቶ ወይም ተዋሕዶ›› ይባላል እንጂ በፍጹም ‹‹ሥጋዋን ወርሶ›› አይባልም፡፡ ምስጢረ ተዋሕዶውም በእንዲህ ዓይነት ወሊጥ ቃል ተገልጾም አይታወቅም፡፡ ሲቀጥልም ‹‹ተወለደባት›› አይባልም፡፡ ‹‹ሥጋዋን ነሥቶ ወይም ተዋሕዶ ተወለደ፤›› እንላለን እንጂ ‹‹ሥጋዋን ወርሶ ተወለደባት›› አንልም፡፡ ‹‹ሥጋዋን ወርሶ ተወለደባት›› የምንል ከሆነ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፤‹‹እንበለ ኅድረት - ያለ ኅድረት፤ ከእመቤታችን ከድንግል ማርያም በነሣው ወይም በተዋሐደው ሥጋ ተወለደ›› የሚለውን የቤተ ክርስቲያናችንን መሠረተ እምነት ያፋልሳል፡፡ ስለዚህ ቤተ ክርስቲያናችን እንዲህ ዓይነቱን ወሊጠ ቃል አትጠቀምም፡፡
ዲያቆን ዳንኤል ክብረት ግን ኹራፊው አምሳሉ ገብረ ኪዳን፤‹‹ ሥጋዋን ወርሶ ተወለደባት›› የሚለውን ኑፋቄያዊ ሕፀጽ፤ ‹‹ነገረ ድኅነት›› በሚል ርእስ በአዘጋጀው መጽሐፉ ላይ፤ ‹‹የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን፤ እግዚአብሔር ወልድ ከእመቤታችን በነሣው ሥጋ‹‹አደረ›› ብላ አታምንም፤ አታስተምርምም፡፡ እንዲህ ብሎ ማስተማር ሥጋ ለቃል ማኅደሩ፣ ልብሱ ሆነ ብሎ ማስተማርም ማመንም ይሆናል፡፡ ይህ ደግሞ፤ ቃል እና ሥጋ እንደ ወዳጅ አብረው ይኖራሉ እንጂ ባሕርያዊና አካላዊ ተዋሕዶ የላቸውም፤ ብሎ እንደ መናፍቁ ንስጥሮስ ማመን ነው፡፡ በመሆኑም ሥጋ የቃል ማደሪያ፤ ቃልም በሥጋ ኀዳሪ አይደሉምና፡፡ በቃልና በሥጋ ተዋሕዶ ኅድረት የለባትም፡፡›› ሲል ያቀናዋል፡፡ (ነገረ ድኅነት፤ 1993፣19)
 የዲያቆን ዳንኤል ክብረት ትንተና የቤተ ክርስቲያን ትምህርት ስለመሆኑ ሲረጋገጥ ቅዱስ ቄርሎስ በሃይማኖት አበው ያለውን እደሚከተለው መመልከት ጠቃሚ ነው፡፡
‹‹የባሕርይ አምላክ የሚሆን የእግዚአብሔር ልጅ እግዚአብሔር እርሱ አንድ አካል፣ አንድ ባሕርይ ነው ብለን በጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ እናምናለን፡፡ ከእግዚአብሔር አብ የተወለደ ቃል ከዘመናት አስቀድሞ ከእርሱ ጋር ነበር፡፡ በኋለኛው ዘመንም እርሱ ዳግመኛ ከድንግል ማርያም በሥጋ ተወለደ፤ የተዋሐደውን የተገዥ ባሕርይንም ራሱ ተዋሐደው እንጂ ሌላ ማኅደር አላደረገም፡፡›› (ሃይማኖተ አበው 77 ፣ 43)
የኹራፊው አማሳሉ ገብረ ኪዳን ሦስተኛው ኑፋቄያዊ ሕፀጽ፤‹‹… በዚህ ሥጋውም ዓለሙን ሁሉ ተቤዠው›› የሚለው ነው፡፡ ይህ ደግሞ በነገረ ድኅነት ትምህርታችን ትልቁ ኑፋቄ ነው፡፡ ይህም በሁለት መልኩ ይገለጻል፡፡ የመጀመሪያው፤ ‹‹ድኅነተ ዓለም የተፈጸመው በሥጋ ነው›› የሚል ኑፋቄን ሲያመጣ፣ በሁለተኛ ደረጃ ደግሞ፤‹‹ ሥጋ መለኮትን ውጦና አጥፍቶ በሩቅ ብእሲ ሥጋ ድኅነት ሆነ›› የሚለውን ኑፋቄ ያስከትላል፡፡ ይህ ደግሞ ቤዛ ዓለም አልተፈጸመም እንደማለት ነው፡፡
ቃል ከሥጋ ጋር በተዋሐደ ጊዜ ተዋሕዶው ፍልጠት የለበትም፡፡ ተዋሕዶው እንደ ነፍስና ሥጋ ነው፡፡ አንድ ሰው ሁለት ባሕርይ እንደማይባል ሁሉ መለኮትና ሥጋም ከተዋሕዶ በኋላ መንታነት፣ ሁለትነት የለም፡፡ ስለዚህ ሥጋው ብቻ ተነጥሎ ‹‹ዓለሙን ተቤዠው›› ማለት እጅግ ክህደት ነው፡፡ ቅዱስ ቄርሎስ ከተዋሕዶ በኋላ ምንታዌ አለመኖሩን ሲገልጽ፤‹‹ከሥጋዌ በኋላ ይህ የቃል ነው፤ ያኛው የሥጋ ነው አይባልም፡፡… በክርስቶስ ሥጋዌ ምንታዌ የለምና፡፡›› ብሏል፡፡ (ጎርጎርዮስ፤1978፣136-138)
እንግዲህ አይደለም መለኮት በሥጋ ቢዋጥ ቢጠፋ ይቅርና፤ ሥጋ በመለኮት ቢዋጥ ቢጠፋ መለኮት ሊሞት አይችልምና ድኅነተ ዓለም ባልተገኘ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ በተዋሕዶ ምንታዌ የለበትም፡፡ ከተዋሕዶ በኋላም ‹‹ሥጋ ተቤዠ፤ መለኮት ተቤዠ›› ተብሎ አይነገርም፡፡ ምክንያቱም ቡዐዴን ያስከትላልና፡፡
ታላቁ መምህራችን ዲያቆን ዳንኤል ክብረት ይህንን የቤተ ክርስቲያናችንን ትምህርት መሠረት በማድረግ የኹራፊውን የአምሳሉ ገብረ ኪዳንን ኑፋቄያዊ ሕፀጽ ‹‹ነገረ ድኅነት›› በተባለው መጽሐፉ፤‹‹ቡዐዴ መለየት መለያየት ማለት ነው፡፡ ሁለት ነገሮች አንድ ላይ ከሆኑ በኋላ መለየት መነጠል ሲቻል ቡዐዴ ይባላል፡፡… የክርስቶስ ሰው የመሆን ምስጢር ግን ከዚህ የተለየ ነው፡፡ ከተዋሕዶ በኋላ ሥጋና መለኮትን ለያይቶ ለየብቻ ይህ መለኮት ነው፡፡ ይህ ሥጋ ነው አይባልም፡፡ እንደ ብረትና እሳት ፍጹም ተዋሕዶ ስለሆነ መነጣጠል አይቻልም፡፡ ስለዚህ ክርስቶስ ሰው የሆነው እንበለ ቡዐዴን ነው፡፡›› በማለት ያብራራዋል፡፡ (ነገረ ድኅነት፤1993፣22)
ኢትዮጵያዊው ሊቅ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ የዲያቆን ዳንኤልን ትንታኔ ሊቃዊ ነፍስ ሲዘራበት፤ ‹‹ፍልብያኖስ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን መለኮቱና ትስብእቱ የተለያዩ ሁለት አካላት ናቸው፤ ይላል፡፡ እኛ ግን ፈጣሪያችን መለኮትና ትስብእት ከተዋሐዱ በኋላ አንድ አካል አንድ ገጽ እላለን፡፡›› ብሏል፡፡ (መጽሐፈ ምስጢር፤2001፣3)       
በአጭሩ የኹራፊው አምሳሉ ገብረ ኪዳን፤‹፣ … የኋላ ልጇ … ሥጋዋን ወርሶ ተወለደባት ፤ በዚህ ሥጋውም ዓለሙን ተቤዠው፡፡›› የሚለው ፍጹም ኑፋቄያዊ ሕፀጽ፤ ‹‹ዓለምን የተቤዠው ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንበለ ውላጤ፣ እንበለ ሚጠት፣ እንበለ ኅድረት፣ እንበለ ቡዐዴ፣ እንበለ ትድምርት፣ እንበለ ቱሳኤ በተዋሕዶ ነው፡፡›› ከሚለው ርቱዕ ትምህርት ጋር የሚጋጭ ክህደት ነው፡፡
ከዚህ አኳያ ከቤተ ክርስቲያናችን መሠረተ እምነት፣ ከሊቃውንቱ (ከቅዱስ ቄርሎስ እና ከአባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ) ትንተና በተቃርኖና በፍንገጣ የቆመው ኹራፊው አምሳሉ ገብረ ኪዳን ነው ወይስ የቤተ ክርስቲያኒቱን መሠረተ እምነትን እምነቱ ያደረገውና በቅዱስ ቄርሎስ እና በአባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ ትንተና የተመሠረተው ዲያቆን ዳንኤል ክብረት ነው  በሃይማኖት መጠርጠር ያለበት? የቤተ ክርስቲያን ጠላትስ  ማነው? ለእኔ ጠላትም ሆነ ከሐዲው ኹራፊው አምሳሉ ገብ ኪዳን ነው፡፡
ኹራፊው አምሳሉ ገብረ ኪዳን መች ከዚህ ኑፋቄያዊ ሕፀጹ ብቻ ተገትቶ፡፡ ከተዘፈቁ አይቀር እንዲህ ነው፤ ‹‹በአይሁዶች መርዘኛ ጥርስ የገባች ሀገር ኢትዮጵያ!›› በሚል ርእስ ተሸካሚነት ፀረ ሴማዊነቱንና ለዚህ ፀራዊ ስሜቱ የቤተ ክርስቲያኒቱን ትምህርት በማዛባት በገለጠበት በዚያ ማወየቢያ ጽሑፉ ውስጥ ሁለት ትምህርተ ሃይማኖታዊ ርእሰ ጉዳዮችን አዛብቶ አቅርቧል፡፡
የመጀመሪያው፤  ‹‹ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ‹ ለይሁዳ ወለዱ ወለ ዉሉደ ዉሉዱ ይደምሰስ › ትላለች፤›› ተብሎ፤ በማትለውና ግድፈት በተሞላበት ግእዝ የተገለጠው አሳበ ጥቅስ ነው፡፡ ተዛብቶ የቀረበውና ቤተ ክርስቲያን ብላው በማታውቀው (ግእዝ አይሉት አማርኛ) መንገድ የቀረበው አሳበ ጥቅስ፤ ቤተ ክርስቲያኒቱ በምትለው ትክክለኛ ግእዝ ሲቀመጥ፤‹‹ለይሁዳ ወልዱ ወለ ዉሉደ ወልዱ ይደምሰስ››በሚል ነው፡፡ እንግዲህ ተመልከቱ በዕለተ ስቅለት ብቻ በቤተ ክርስቲያን የዋለ ሰው እንኳን የማይገድፈውን አሳበ ጥቅስ የገደፈው ኹራፊው አምሳሉ ገብረ ኪዳን ነው፡፡ ይኸው ሰው ነው፤ የአባ ጊዮርጊስን ‹‹ውዳሴ መስቀል››፣ በ‹‹አራቱ ኃያላን›› መጽሐፍ ውስጥ የተካተቱትን የአቡነ በጸሎተ ሚካኤል፣ የአቡነ ፊልጶስ፣ የአቡነ አኖሬዎስ እና የአቡነ አሮን ገድላትን ተርጉሞና ጥልቅ ጥናታዊ ማብራሪያ የሰጠውን ዲያቆን ዳንኤል ክብረትን፤ ያለአንዳች ተጨባጭ ማስረጃ፤ በግእዝ ጨዋነት ለመጠርጠር የዳዳው፡፡
ኹራፊው አምሳሉ ይህ ግድፈቱ ሳያንሰው በዚሁ በገደፈው ግእዙ የራሱን ፀረ ሴማዊ ፍላጎት በመቀንበብ፤ ቤተ ክርስቲያን ‹‹ለይሁዳ ወልዱ ወለ ዉሉደ ወልዱ ይደምሰስ››በሚል  የሚለውን አሳበ ጥቅስ በዕለተ ዓርብ የምትጠቀመው፤ ‹‹አይሁዶችን ለማውገዝ ነው›› ሲል የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንን በፀረ አይሁድነት ፈርጆ ሊያስፈርጃት ይጣጣራል፡፡
     እውነታው ግን ወዲህ ነው፡፡ የአስቆሮቱ ይሁዳ ከአሥራ ሁለቱ ሐዋርያት አንዱ ነበር፡፡ ነገር ግን የተመረጠበትን ሐዋርያዊ ተግባር ትቶ ከሰቃልያነ እግዚእ ጋር ተባብሮ ጌታውንና መምህሩን አሳልፎ በመስጠቱ፤ በኋላም በጥፋቱ ተፀፅቶ እንደ ጴጥሮስ ንስሐን ሳይሆን በብልጠት ምሕረትን ስለፈለገና ራሱን ስለገደለ የእርግማን እርግማን ተፈጽሞበታል፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን ይህን ለመዘከር፤ ልዩ ልዩ መዝሙራትን በማስተዛዘል በሚጸለይበት ጊዜ ‹‹ለይሁዳ ወልዱ ወዉሉዱ ይደምሰስ›› የሚል የመርገም ቃል አዝማች እንዲነገር ታደርጋለች፡፡ ይህንን ለማሳየት በትርዒት መልክ የሚፈጸም ሥርዓትም አላት፡፡ ይኸውም በመቋሚያ ጫፍ ላይ ጧፍ ተደርጎ (ታስሮ) አንደኛውን የዳዊት መዝሙር (መዝ. 1 ፥ 1 - 6) በማስተዛዘል ከተነበበ በኋላ፤ ‹‹ወፍኖቶሙሰ ለኃጥዕ ከመዝ ትጠፍዕ፤ የኃጥዓን መንገድ እንደዚህ ትጠፋለች›› ከሚለው ላይ ሲደረስ፤ ማኅበረ ካህናቱ በያዙት መቋሚያ በአንድ ላይ ውርጂብኝ በማውረድ በመቋሚያው ጫፍ ላይ የታሰረውን ጧፍ መብራት ያጠፉታል፡፡ ጧፍ ሰይጣን በልቡ የገባ የይሁዳ ምሳሌ ነው ፡፡ መቋሚያ የጌታ ምሳሌ ነው ፡፡ መቋሚያ ላይ መታሰሩ በክርስቶስ መሠረትነት ላይ ለሐዋርያነት ለዓለም ብርሃንነት መመረጡን ግን ይህን ክብሩን በማቃለሉ መውደቁን    ያመልክታል፡፡ ቀጥቅጠው ማጥፋታቸው ሰውን ያሳተው ዲያብሎስ በመስቀል ኃይል መመታቱን፣ ድል መነሳቱን ለማዘከር ነው፡፡
በመጨረሻም፤ ‹‹ንሴብሖ ለእግዚአብሔር ስቡሐ እንዘተሰብሐ፤ እግዚአብሔርን እናመስግነው የተመሰገነ ምስጉን›› በማለት የክርስቶስን ቤዛነቱን ያበሥራሉ፡፡ (ዐቢይ ጾምና ሰሙነ ሕማማት)፡፡ እናም ኩላዊት የሆነችው ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን፤ ‹‹ለይሁዳ ወልዱ ወዉሉዱ ይደምሰስ›› የሚለውን አሳበ ጥቅስ የምትጠቀመው ከላይ በገለጥነው አግባብ እንጂ ኹራፊው አምሳሉ ገብረ ኪዳን እንዳለው‹‹አይሁዶች ይወገዙበታል›› በሚለው አግባብ አይደለም፡፡
ከዚህ ፀራዊ አስተሳሰብ ብቻ እንኳን ተነሥተን እንፈርጅ (ፍረጃ ተገቢ ባይሆንም) ብንል፤ በፀረ ሴማዊነት እኩይ መንፈስ አብዶ ፣ የቤተ ክርስቲያኒቱን ትምህርት ለፀረ ሴማዊነት ወይም ለፀረ አይሁድነት ቅስቀሳ አዛብቶ በመጠቀም፤ ኩላዊት የሆነችውን ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በፀረ አይሁድነት ፈርጆ ሊያስፈርጅ እየዳከረ የሚገኘው ኹራፊው አምሳሉ ገብረ ኪዳን ነው እንጂ፤ ቅዱስ ጳውሎስ በገላትያ መልእክቱ፤ ‹‹አይሁዳዊ ወይም የግሪክ ሰው የለም፤ ባሪያ ወይም ጨዋ ሰው የለም፤ ወንድም ሴትም የለም፤ ሁላችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ አንድ ሰው ናችሁና፡፡›› (ገላ. 3 ፥ 28) ያለውን የፀረ ዘረኛነት መልእክቱን መልእክቷ ያደረገችውን ቤተ ክርስቲያን፤ ከፀራውያን ጠብቆ፣ ፀራዊ አለመሆኗን ላለፉት ሃያ ዓመታት የሰበከው፣ የጻፈውና የተከራከረው ዲያቆን ዳንኤል ክብረት አይደለም ፡፡
በሁለተኛ ደረጃ፤ ‹‹በአይሁዶች መርዘኛ ጥርስ የገባች ሀገር ኢትዮጵያ!›› በሚል ጥላቻዊ ርእስነት በአተተው ጽሑፉ ውስጥ የዘራው ኑፋቄያዊ ሕፀጽ፤‹‹… በሥርዓቱ መሠረት አንድ ካህን በትዳር ሕይወት እያለ ባለቤቱ ወይም ሚስቱ ሰርቃ ከሌላ ወንድ ብትደርስና ከሌላ ወንድ መድረሷን አወቀም አላወቀ ከሌላ ከደረሰች በኋላ እሱ ቢደርስባት ሥልጣነ ክህነቱ ይፈርሳል፡፡ ከዚያ በኋላ በዚያ ሥልጣነ ክህነት መጠራትና ማገልገል አይችልም፤ መቅደስ ውስጥም መግባት ፈጽሞ አይችልም፡፡›› የሚለው ነው፡፡
በየትኛው ሥርዓት መሠረት እንደሆነና የሥርዓቱም ድንጋጌ በየትኛ አንቀጽና ቁጥር እንደሚገኝ ያልገለጸው ኹራፊው አምሳሉ ገብረ ኪዳን የራሱን ድንጋጌ ‹‹በሥርዓቱ መሠረት›› በሚል ሽፋን የዋሃንን ለማደናገር ቢሞክርም ለዛሬ አልተሳካለትም፡፡ በየትኛውም የሥርዓት መጽሐፋችን ውስጥ እንዲህ ዓይነት የቅጥፈት ድንጋጌ የለም፡፡
ዐይናማው ሊቅ (ነፍስ ኄር) ሊቀ ካህናት ክንፈ ገብርኤል አልታዬ ‹‹ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን›› በተባለው መጽሐፋቸው ውስጥ ሥልጣነ ክህነትን ከጋብቻ ጋራ ተያይዞ ስለሚፈርስበት ሁኔታ ፍትሕ መንፈሳዊን አንቀጽ ስድስትና ሰባትን መሠረት አድርገው ሲያብራሩ ቄስ ከሆነ፤ ‹‹ሁለት ጊዜ ያገባ፤ ሁለት ሚስት ያለው፤ ከሴሰኛ ሴት የደረሰ፤ በአገልግሎት ምክንያት ሚስቱን የተለየና የፈታ፤ እመነኩሳለሁ፣ ተባሕትዎ እይዛለሁ ብሎ ሚስቱን ያሰናበተ ካህን ከሹመቱ ይሻራል፡፡›› ብለዋል፡፡ ዲያቆን ከሆነ ደግሞ፤‹‹ሁለት ሴት ያገባ፣ ወይም በተሾመ ጊዜ ከሴት ርቄ ንጽሕና ጠብቄ እኖራለሁ ብሎ ተሥሎ ከተሾመ በኋላ ሥዕለቱን አፍርሶ ሚስት ያገባ ወይም ከዘማዊት ሴት የደረሰ፣ ተደብቆ ተክሊል ያደረሰ ወይም እመነኩሳለሁ ተባሕትዎ እይዛለሁ ብሎ ሚስቱን የፈታ ከዲቁናው ማዕረግ ይሻራል፡፡›› ሲሉ ያስረዳሉ፡፡ (ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን፤ 1993፣ 120–123)
ይህን የሊቁን ትንታኔና የፍትሕ መንፈሳዊ ድንጋጌ ይዘን የኹራፊውን የአምሳሉ ገብረ ኪዳንን ግለ ድንጋጌ ስንፈትሽ፤ እውነት አልባ መሆኑን ከመረዳት ባሻገር፤ አንድ ካህን ያለ ራሱ በደል ክህነቱን የሚያጣበት ምንም ዓይነት ቀኖናዊ መሠረት የሌለ መሆኑን እናረጋግጣለን፡፡ በሚስቱ ስርቆት ተፈጸመ ቢባልና ይህም በማስረጃ ተረጋገጠ ቢባል በቀኖና ቤተ ክርስቲያን መሠረት ሚስቱ በዝሙት ወድቃ ተገኝታለችና ጋብቻው ሊፈርስ ይችላል እንጂ ክህነቱ ሊፈርስ የሚችልበት ምንም ዓይነት ቀኖናዊ መሠረት የለውም፡፡
ቀኖና ቤተ ክርስቲያንን እንዲህ አዛብቶና አጣሞ ያቀረበው የቤተ ክርስቲያን ጠላት ኹራፊው አምሳሉ ገብረ ኪዳን ነው? ወይስ፤ ዕድሜ ዘመኑን ለቀኖና ቤተ ክርስቲያን ዋጋ የከፈለው ዲያቆን ዳንኤል ክብረት?
ቤተ ክርስቲያን በሥርዓቷ አፅራረ ቤተ ክርስቲያን ብላ የምትጠራቸው መሠረተ ዕምነቷን ያፋለሱትን፣ ሥርዓተ አምልኮዋን ያዛቡትንና ትምህርቷን የቀሰጡትን ጭምር ነው፡፡ ከዚህ አንጻር ኹራፊው አምሳሉ ገብረ ኪዳን በተጨባጭ እንደተመለከትነው፤ በነገረ ድኅነት ላይ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ያላትን መሠረተ እምነት አፋልሷል፡፡ የሥርዓተ አምልኮዋ ምሰሶ የሆነውን የሥርዓተ ክህነቷን ድንጋጌ አዛብቷል፡፡ የዕለተ ዓርብ ትምህርቷንና ተዕይንቷን በመቀሰጥ ለፀረ ሴማዊ ቅስቀሳው ተጠቅሞበታል፡፡ ይህ ድርጊቱ ደግሞ ከአፅራረ ቤተ ክርስቲያን እንደ አንዱ እንዲታይ ያደርገዋል፡፡

2 - በታሪክ ‹ተፋለስ› ስም የተገለጠው መንደርተኝነት!
ኹራፊው አምሳሉ ገብረ ኪዳን አስቀድመን እንደገለጥነው ሃይማኖታዊ ድቀት ብቻ ሳይሆን ታሪካዊ ድቀትም አግኝቶታል፡፡ አሰላለፉም ከወያኔያዊ ማንነቱ እንደሚመነጭ ያረጋገጠልንን ነጥቦችን እንመልከት፡፡
የመጀመሪያው፤ ‹‹ተኩላው፤ ‹‹ስማችሁ የለም›› በሚል ርእስ ባሳተመው መጽሐፍ ላይ እጅግ በጣም በሚገርም ድፍረት የወያኔነቱን ተልእኮ ከውኗል፡፡ በዚያ መጽሐፍ ውስጥ ‹‹የሌለውን ፍለጋ›› በሚል ርእስ በጻፈው ጽሑፍ ላይ… በክብረ ነገሥት ላይ ሰፊ ሽፋን ተሰጥቶ የሚተረከውን በዓለማውያኑ የታሪክ ጸሐፍት ዘንድ ‹‹ሰሎሞናዊ›› በቤተ ክርስቲያን ደግሞ ‹‹የዳዊት መንግሥት›› እየተባለ የሚጠራውን ሥርዎ መንግሥት በሀገራችን አልነበረም በማለት ክብረ ነገሥትንና ይኼንን የክብረ ነገሥትን ታሪካዊ ትረካ የሚጠቅሱና የሚያረጋግጡ ከገድላት እስከ ድርሳናት፣ ከተአምራት እስከ ፍካሬያት፣ ከሊቃውንት እስከ ትርጓሜያት ያሉትን የቤተ ክርስቲያን መጻሕፍት ሐሰተኞች አድርጓቸዋል፡፡›› በሚል ያልተባለውን እንደ ተባሉ አድርጎ ያቀረበው ነጥብ ነው፡፡
በአንደኛ ደረጃ በዚህ በኹራፊው ጽሑፍ ውስጥ የሐቅ (Fact) ችግር አለ፡፡ ይኸውም ዲያቆን ዳንኤል ክብረት‹‹የሌለውን ፍለጋ›› በሚል ርእስ፤ ኢትዮጵያዊ ዕሴቶችን በመናድ ለተጠመደው ተስፋዬ ገብረ አብ ምላሽ በሰጠበት ጽሑፍ ውስጥ፤ ‹‹… ‹ሰሎሞናዊ› የሚባል የተለየ መንግሥት አልነበረም፡፡ ነገሥታቶቻችን ሁሉ ራሳቸውን ከኢየሩሳሌም ጋር ያያይዙ ነበር፡፡ ዐፄ ካሌብም ከናግራን ዘመቻ መልስ ዘውዳቸውን ኢየሩሳሌም ነው የላኩት፡፡ የዐፄ ገብረ መስቀል ልጅ ሙሴም መጀመሪያ ወደ ኢየሩሳሌም በኋላም ወደ ሶርያ በመጓዝ በዚያ መንነው ገዳም መሥርተዋል፡፡ ገዳማቸውም ‹‹ሙሴ አል ሐበሽ ገዳም›› ይባላል፡፡ የዛግዌ ነገሥታትም ሰሎሞናውያን የማይሆኑበት ምክንያት የላቸውም፡፡ በገድሎቻቸው ላይ ኢየሩሳሌምን አብዝተው የሚያነሡ፣ ማኅተሞቻቸው ሁሉ የዳዊት ኮከብ የሆኑ፣ በውቅር ቤተ ክርስቲያኖቻቸው የዳዊትን ኮከብ የቀረፁ የዛጉዌ ነገሥታት እንዴት ሰሎሞናውያን አይሆኑም?›› አለ እንጂ ኹራፊው አምሳሉ ገብረ ኪዳን፤ ‹‹ሰሎሞናዊ ሥርዎ መንግሥት በሀገራችን አልነበረም›› ብሎ የገለጸው ዓይነት ዐረፍተ ነገር በዲያቆን ዳንኤል ጽሑፍ ውስጥ በጭራሽ የለም፡፡ (ስማችሁ የለም እና ሌሎች፤ 2006፣ 138)
ይህም ቢሆን ዛጉዌያውያንን አግልሎ በራሱ የቆመ ሥርዎ መንግሥት አለመኖሩን ለመግለጥ ነው እንጂ ኹራፊው እንደሚለው፤ ‹‹ገድላቱን የድርሳን መጻሕፍቱንና ትርጓሜያቱን ሐሰተኞች›› ለማስባል አይደለም፡፡ የእነርሱ እውነተኛነት በራሳቸው የሚለካ እንጂ በሌላው ትረካ የሚለካ አይደለም፡፡
በሁለተኛ ደረጃ፤ በዚህ በኹራፊው ጽሑፍ ውስጥ የእውቀት ችግር እናገኛለን፡፡ ይኸውም ‹‹በዓለማውያን የታሪክ ጸሐፍት ዘንድ ‹‹ሰሎሞናዊ›› በቤተ ክርስቲያን ደግሞ‹‹የዳዊት መንግሥት›› በማለት ሁለት የተለያዩ ፅንሰ ሐሳቦችን አንድ በማድረግ አቅርቧል፡፡ በመጀመሪያ ቤተ ክርስቲያንም ‹‹ሰሎሞናዊ›› የሚለዉን ቃል እንደምትጠቀመው ሁሉ የታሪክ ጸሐፍቱም ‹‹የዳዊት መንግሥት›› የሚለውን ቃል ይጠቀማሉ፡፡ አንዱን ቃል ለአንዱ ብቻ መስጠት አይቻልም፡፡ ሲቀጥል ደግሞ የታሪክ ምሁራኑም ሆኑ የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ‹‹የዳዊት መንግሥት›› የሚሉት ከዳዊት ዘር ሲወረስ ሲወራረስ የመጣውን ቅብዓ ንግሥና የፈጸምንና ስዩመ እግዚአብሔር ነን ብለው የዳዊትን ኮከብ የመንግሥታቸው መለያ ያደረጉ ነገሥታትን በሙሉ ሲሆን፤ ‹፣ሰሎሞናዊ›› የሚሉት ደግሞ በ1270 ዓ.ም. ተመለሰ የሚባለውን የይኩኖ አምላክን መንግሥት ነው፡፡ እንግዲህ እግዚአብሔር ያሳያችሁ የእነዚህን ሁለተ ፅንሰ ሐሳቦች ልዩነት ሳያውቅ ነው የጨነገፈ ብዕሩን ለትችት ያነሣው፡፡
በሦስተኛ ደረጃ በዚህ በኹራፊው ጽሑፍ ውስጥ አምታችነት እናያለን፡፡ ይኸውም ‹‹ክብረ ነገሥትን እና ይኼንን የክብረ ነገሥትን ታሪካዊ ትረካ የሚጠቅሱና የሚያረጋግጡ ከገድላት እስከ ድርሳናት፣ ከተአምራት እስከ ፍካሬያት፣ ከሊቃውንት እስከ ትርጓሜያት ያሉትን መጻሕፍት ሐሰተኞች አድርጓቸዋል፡፡›› በሚል አምታቻዊነት ሰብዕና የቀረበው ሐሰት ነው፡፡ በመጀመሪያ ከገድላት እስከ ድርሳናት፣ ከተአምራት እስከ ፍካሬያት፣ ከሊቃውንት እስከ ትርጓሜያት ያሉት መጻሕፍት እውነተኛነትና ትክክለኛነት የሚረጋገጠው በራሳቸው በያዙት አሳበ ቁመና እንጂ በሌላው አሳበ ቁመና አለመሆኑን መረዳት ያስፈልጋል፡፡ በይቀጥላል ደግሞ ክብረ ነገሥትን የሚጠቅሱም ሆኑ የሚያረጋግጡ አንተ የጠቀስካቸውን ዓይነት መጻሕፍት እስከ አሁን አልደረስኩባቸውምና የታተሙበትን ዓመተ ምሕረትና ገጻቸውን እየጠቀስክ ብትነግረኝ ጥሩ ነበር፡፡ እኔ ባለኝ መረጃ ግን ክብረ ነገሥትን የሚጠቅሱ ገድላትም ሆኑ የድርሳን መጻሕፍት፣ የተአምርም ሆኑ የትርጓሜ መጻሕፍት የሉም፡፡ እናም የሌለባቸውን አለባቸው በማለት መጻሕፍቱን ሐሰተኞች ያደረጋቸው ኹራፊው አምሳሉ ገብረ ኪዳን እንጂ ዲያቆን ዳንኤል ክብረት አይደለም፡፡
ሁለተኛው በታሪክ ‹‹ተፋለሰ›› ስም ጎጣዊ ደዌውን የገለጠበት፤
‹‹ከእነኝህ ክብረ ነገሥት ከሚተርከው የዳዊት (ሰሎሞናዊ) ሥርዎ መንግሥት ትረካ በተለያየ መንገድ ከሚያረጋግጡት ከሚተርኩት የቤተ ክርስቲያን መጻሕፍት አንዱ የሆነውን የአቡነ ተክለ ሃይማኖት ገድል ይወስድና አቡነ ተክለ ሃይማኖት በኢትዮጵያ የመንግሥት ሥልጣን በመሐል ከገቡት ከዛጉዌ ሥርዎ መንግሥት ተመልሶ ወደ ዳዊት ሥርዎ መንግሥት እንዲመለስ ስለማድረጋቸውና ከይኩኖ አምላክም ለቤተ ክርስቲያን ሲሦ ድርሻ ስለ መስጠታቸው የሚተርከውን የገድላቸውን ክፍል፤ እንዲህ የሚል ነገር በአቡነ ተክለ ሃይማኖት ገድል ላይ ፈጽሞ የለም ሲል ወያኔያዊ ክሕደቱን በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ላይ ፈጽሟል፡፡… የደብረ ሊባኖስ ገዳም ያሳተመውን ‹ገድለ ተክለ ሃይማኖት› የሚለውን መጽሐፍ ገልጦ ምዕራፍ 26 ን እና 27 ን ቢያነብ ይኼ ተኩላ ያለአንዳች ፍርሐትና ሐፍረት በድንቁርና ድፍረት የለም ሲል የካደውን ታሪክ እንዳለ ሊያረጋግጥ ይችላል፡፡ ተኩላው በጠቀሳቸውና ባልጠቀሳቸው ታላላቅ ገዳማት ያሉ የአቡነ ተክለ ሃይማኖት ገድላት ላይም ይኼ ታሪክ በሚገባ አለ፡፡ ተኩላው የለም የሚለው የሌለ መስሎት ወይም እንዳለ ሳያውቅ ቀርቶ እንዳይመስላችሁ በጎሳና በፀረ አማራ መርዘኛ መርፌ ተወግቶ ከተመረዘ በኋላ በወያኔነቱ መሥራት ካለበት ሥራችና ከተሰጠው ተልእኮ አንዱና ዋነኛው በመሆኑ እንጂ፤ … አገው ነኝ ባይ ሆኗል፡፡
ይህንን የክብረ ነገሥትንና የአቡነ ተክለ ሃይማኖትን ገድል ታሪክ ውሸት ነው፣ ተረት ነው፣ ፈጠራ ነው ሲል በሱ ቤት ዛጉዬዎች (አገዎች) ወገኖቹ ስለሆኑና የዳዊት (ሰሎሞናዊው) ደግሞ አማራ ስለሆነ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ካላቸው ቅድስና በአኀት አብያተ ክርስቲያናት ዘንድ ካቸው ዓለም አቀፋዊ ተቀባይነት አንጻር በእሳቸው ገድል ላይ ይኼ ነገር ሰፍሮ መገኘቱ የታሪኩን እውነተኛነት ስለሚያረጋግጥ ለእሱና እሱን ለመሰሉት ደግሞ እንዲህ መሆኑ ስለማይመቻቸው ስለማይወዱት ስለማይፈልጉት ነው በገድላቸው የለም ሲል ዐይን ባወጣ የጅል ድፍረት ሸምጥጦ ሊክድ የቻለው፡፡›› የሚለው ማወረቅ ነው፡፡
በዚህ ንባቡ ውስጥ ዲያቆን ዳንኤል ‹‹የሌለውን ፍለጋ›› በሚለው ጽሑፉ በፍጹም ያላለውን ‹‹በገድለ ተክለ ሃይማኖት ውስጥ ስለ ሰሎሞናዊ ሥርዎ መንግሥትና ስለ ሲሦ ድርሻ የሚተርከውን ታሪክ የለም ብሎናል›› ሲል እንደ አለ አድርጎ አቅርቧል፡፡ ዳንኤል ግን፤ ‹‹ከላስታ ወደ ሸዋ የመንግሥት ዝውውር ሲደረግ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ሐይቅ እስጢፋኖስ በትምሕርት ላይ ነበሩ፤ (የሚጣቅ አማኑኤል ገድለ ተክለ ሃይማኖት እና ገድለ ኢየሱስ ሞአ በዝርዝር እንደሚተርከው) በዚህ የሥልጣን ዝውውር ላይ ይበልጥ ተሳታፊ የነበሩት አቡነ ኢየሱስ ሞአ ዘሐይቅ ናቸው፡፡ በዚህም ምክንያት ሐይቅ የዐቃቤ ሰዓትነት ሥልጣን ነበረው፡፡ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ሲሦ መንግሥት አግኝተዋል፤ የሚለው ትረካ፤ መንግሥት ወደ ጎንደር ከተቀየረ በኋላ (በ17ኛው መ. ክ. ዘ.) በተጻፈው በ‹ብዕለ ነገሥት› ላይ  የተገለጠ ነው፡፡ ብዕለ ነገሥት የነገሥታትን ሃብት ለማሳየት የተጻፈ ነው፡፡ በዚህ መጽሐፍ ነው፤ ከ ይኩኖ አምላክ ጋር ቃል ገብተዋል ተብሎ የተጻፈው፡፡›› አለ አንጂ ስለ ደብረ ሊባኖሱ ገድለ ተክለ ሃይማኖት ያነሣው ነገር የለም፡፡ ቅጥፈት ይሉታል እንዲህ ነው፡፡
ዲያቆን ዳንኤል ክብረት፤ ኹራፊው አምሳሉ ገብረ ኪዳን በገለጸው አግባብ ቢጽፍ እንኳን ስሕተቱ ምኑ ላይ ነው? የገድለ ተክለ ሃይማኖት ብዙ ቅጂዎች እዳሉ ይታወቃል፡፡ ከእነዚህ ቅጂዎች ውስጥ ደግሞ የመጀመሪያው ወይም ኦሪጂናል የሚባለው የገድለ ተክለ ሃይማኖት ቅጂ በአሥራ አራተኛው መቶ ክፍለ ዘመን የተጻፈው በተለምዶ ‹የዋልድባው› የሚባለውና በፈረንሳይ ሙዚየም በ‹‹Bib. Nat 138›› መለያ ቁጥር ተመዝግቦ የሚገኘው እና የሐይቅ እስጢፋኖሱ ገድለ ተክለ ሃይማኖት ነው፡፡ በእነዚህ ገድላት ውስጥ ‹‹ከዛግዌ ሥርወ መንግሥት ወደ ሰሎሞናዊ ሥርወ መንግሥት የተደረገውን ሽግግር ያከናወኑ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ናቸው፡፡ ለዋሉት ውለታ ለቤተ ክርስቲያን ሲሦ መንግሥት ተሰጠ›› የሚል  የለም፡፡
ይህ ደግሞ በታሪክ ሊቃውንት ጭምር የተረጋገጠ ታሪካዊ እውነታ ነው፡፡ ፕሮፌሰር ታደሰ ታምራት‹‹Church and State in Ethiopia››በተባለው ታዋቂ መጽሐፋቸው ይህንኑ ሲያረጋግጡ፤ አቶ አበባው አያሌው የተባሉ የታሪክ ምሁር ደግሞ በየካቲት 1998 ዓ.ም. ‹‹በታሪክ ጥናት ትልቁ ወንጀል›› በሚል ርእስ በ‹‹ሐመር›› መጽሔት ላይ በጻፉት መጣጥፍ፤ ‹‹… ዐፄ ይኩኖ አምላክ፤ ‹ ሲሦውን የግዛቴን ክፍል ለቤተ ክርስቲያን እሰጣለሁ፤› ለማለታቸው ምንም ዓይነት የታሪክ ምንጭና ማስረጃ የለም፡፡ ዘውድ ጭነው ንጉሠ ነገሥት ከሆኑ በኋላም እንደ ማንኛውም ንጉሠ ነገሥት ጉልት በመጎለት እና ሕንፃ በማሳነፅ ቤተ ክርስቲያንን ደገፉ እንጂ ከግዛታቸው ሲሦውን ለቤተ ክርስቲያን አልሰጡም፡፡ በእነዚህ በሁለቱ ተለምዶአዊ አነጋገሮችና አፈ ታሪኮች የተነሣ ለዘመናት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የአገሪቱ መሬት ሲሦ ባለቤት ተደርጋ ስትጠቀስ ኖራለች፡፡ ታሪካዊ እውነታው ግን ቤተ ክርስቲያኗ መሬት በጉልትነት ይዛ ኖራለች፤ ነገር ግን ይህ በጭራሽ የአገሪቱ ሲሦ መሬት አይደለም፡፡›› በማለት አጽንዖት ሰጥተው ነበር፡፡ /ሐመር፣1998 ፣ /
‹‹ሐመር›› መጽሔትም የገድላቱን ሐቀኛ ትረካ እና የምሁራኑን የታሪክ ትንተና በማስረገጥ (እንግዲህ ኹራፊው አምሳሉ እርምህን አውጣ)፤ ‹‹በአሥራ ሦስተኛው ክፍለ ዘመን ሁለተኛ አጋማሽ በዛግዌና ሰሎሞናዊው ሥርወ መንግሥቶች መካከል በነበረው የሥልጣን ሽኩቻ ጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ሁለቱን ተቃራኒ ወገኖች በማስማማት፣ ዘውድ ከዛግዌ ሥርወ መንግሥት ወደ ሰሎሞናዊው ሥርወ መንግሥት በሰላም እንዲተላለፍ አድርገዋል፡፡ አስቀድሞ ቃል በገባላቸው መሠረት ዐፄ ይኩኖ አምላክ ሲሦውን (1/3ኛውን) የግዛት ክፍል ለቤተ ክርስቲያን ሰጥቷቸዋል፤ የሚለው አፈ ታሪክ ነው፡፡›› ሲል ይደመድማል፡፡/ዝኒ ከማሁ፣ /
ዲያቆን ዳንኤል ክብረት ይህን ገድላዊና ታሪካዊ ምንጭ ያለውን እውነታ በተጠየቃዊ መንገድ ‹‹የሌለውን ፍለጋ›› በተባለው ጽሑፉ፤ ‹‹ተስፋዬም ሆነ ሌሎች እንደሚሉት አቡነ ተክለ ሃይማኖት ከቅድስና ሥራ በቀር የገቡበት ፖለቲካ የለም፡፡ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ሐዋርያዊ አገልግሎታቸውን ፈጽመው ወደ ደብረ አስቦ ሲገቡ ይኩኖ አምላክ በመንበሩ ላይ ነበር፡፡ ነገር ግን የጠበቃቸው ዘንዶ ይመለክበት የነበረ ዋሻ እንጂ ከሲሦ መንግሥት የተገኘ ግብር አልነበረም፡፡ … ሃያ ስምንት ዓመት በደብረ አስቦ ሲቀመጡም የጎበኛቸው ንጉሥ አልነበረም፡፡ ደቀ መዝሙሮቻቸው ከዝንጀሮ ጋር እየተሻሙ እህል ዘርተው ከማብቀል ውጪ የተለየ ርስት አልነበራቸውም፡፡››ሲል ምሁራዊ ምልከታውን አተመበት፡፡-(ስማችሁ የለም እና ሌሎች፤2006፣139)
3 - በጥላቻ የተለወሰው አማተር ፖለቲከኝነት!
እነዚህን በማስረጃ ላይ የተመሠረቱ ትንታኔዎች ለመገንዘብ የሚያስችለውን አእምሮ በጭፍን ጥላቻ ያጣው እና ዲያቆን ዳንኤል ክብረት ‹‹የሌለውን ፍለጋ›› በተባለው ጽሑፉ ያላለውን እንደ አለ አድርጎ በማቀረብ ስምዐ ሐሰት የሆነው ኹራፊው አምሳሉ ገብረ ኪዳን፤ በዚያ ዘባተሎ ‹‹ጽሑፉ›› ዲያቆን ዳንኤልን በፀረ አማራነት፣ በወያኔነት፣ በድንቁርና ከስሶታል፡፡ ለፀረ አማራነቱ ‹‹አገው›› መሆኑን ሲጠቅስ፤ ለወያኔነቱ ደግሞ የባለቤቱን ‹‹ትግሬነት››ና ‹‹ሰሎሞናዊ ሥርወ መንግሥትና ሲሦ መንግሥት የለም›› ብሏል በማለት ጭራሽ በሐሰት በተሞላ የፈጠራ ክስ ነው፡፡
ሊቃውንቱ ‹‹ጨዋ ደፋር ነው›› እንደሚሉት ያለምንም ሐፍረት ያቀረሸውን የጎጠኛነትና የጥላቻ ፖለቲካዊ ቅርሻቱን እንመርምር፡፡ በመጀመሪያ ደረጃ እንደ ኹራፊው አምሳሉ አገላለጽ ከሆነ ‹‹አገው›› ማለት ፀረ አማራነት ነው፡፡ ኹራፊው አምሳሉ፤ አገዎች ‹‹ፀረ አማራዎች›› ስለሆኑና ዳንኤል ደግሞ አገው ስለሆነ ‹‹ፀረ አማራ›› ነው፤ አለን፡፡ ይህን ከራሱ ከአምሳሉ አመክንዮ አንጻር ስንገለብጠው አማራዎችም ፀረ አገው ናቸው ማለት ነው፡፡ ኹራፊው አምሳሉ ደግሞ ራሱን የአማራ ጠበቃ አድርጎ ስለአቀረበ ፀረ አገው ነው ማለት ነው፡፡ ስለዚህ በዲያቆን ዳንኤል ላይ በጥላቻ የተነሣው ከፀረ አገውነቱ እንጂ የተለየ በደል በ‹‹አገው›› ዳንኤል ላይ ስለአገኘበት አለመሆኑን አረጋገጠ፡፡ ይሁንና ከእውነታ አንፃር ግን ዲያቆን ዳንኤል የአገው ተወላጅ አይደለም፡፡ እኔ አገው ነኝ ብሎም አያውቅም፡፡ ሰለ አንድ ሕዝብ እውነትን ለመናገር ከዛ ሕዝብ መውለድ የግድ አያስፈልግም፡፡ ሰው መሆንና እውነተኛ መሆን ይበቃል፡፡ እነ ሲልቪያ ፓንክረስት ከኢትዮጵያ ምድር የተገኙ ኢትዮጵያውያን ሆነው አይደለም በዚያ በወረራ ዘመን ሰለ ኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን አብዝተው የተናገሩት ፡፡ እንግዲህ እግዜር ያሳያችሁ ስለኢትዮጵያዊነት ለመቀባጠር የተነሣው እንዲህ ዓይነቱ ጎጠኛ ነው፡፡
ሲቀጥል ደግሞ ዲያቆን ዳንኤል ክብረት ወያኔ ነው ለማለት የጠቀሰው አንደኛ ማስረጃ የባለቤቱን ‹‹ትግሬነት›› ነው፡፡በዚህ ደግሞ የፖለቲካ አቋም ከጎጥ ማንነት እንደሚመነጭ አድርጎ ያቀርባል፡፡ ይህ ደግሞ ትግሬ የሆነ ሁሉ ወያኔ ነው ያስብላል፡፡ ይህ ደግሞ ትልቅ ስሕተት ነው፡፡ እንዲህ ዓይነቱ የደመ ነፍስ ፍረጃ ደግሞ የኹራፊው አምሳሉ መገለጫ ነው፡፡ ከዚህ ማንነቱ በመነሣት ነው እንግዲህ ዳንኤል ባለቤቱ ትግሬ ስለሆነችና ትግሬ ደግሞ ወያኔ ስለሆነ በባለቤቱ በኩል ‹‹ወይኗል›› የሚል ድንቁርናን የሚሰብከን፡፡ እንግዲህ ትግሬነት ወያኔነት ከሆነና ወያኔነትም በጋብቻ የሚወረስ ከሆነ፤ አደንቃቸዋለሁ የሚላቸው የፕሮፌሰር መስፍን ወልደ ማርያም የቀድሞ ሚስታቸው ትግሬ ናቸውና ፕሮፍ ወይነው ይሆን?
እንግዲህ በአምሳሉ ትንታኔ መሠረት ትግሬነት ወያኔነት ከሆነ ወያኔን በመቃወም ብቻ በወያኔ እስር ቤት መከራውን እያየ ያለው የነጻነት ታጋዩን አብርሃ ደስታን ወያኔ ልንለው ነው? በተቃውሞ ጎራ ተሰልፈው ለአለፉት ሃያ ዓመታት ወያኔን ሲታገሉ የነበሩት ዶክተር ኃይሉ አርአያ ትግሬ ናቸውና ወያኔ ይሆኑ?
 ከእውነታ አንፃር ደግሞ እስቲ እንመልከት፤ የዲያቆን ዳንኤል ክብረት ባለቤት ወ/ሮ ጽላት ጌታቸው ትባላለች፡፡ ምንም እንኳን ትግሬ መሆን ነውር ባይሆንምትግሬ አይደለችም፡፡ የአማራ ተወላጅ ከሆኑ ቤተሰቦች የተገኘች፣ አዲስ አበባ ተወልዳ ያደገች፣ ኢትዮጵያዊት ናት፡፡ ለማንኛውም ‹‹ጽላት›› በሚል የሚጠሩ ሁሉ ትግሬዎች ናቸው ከተባለ፤ ኢትዮጵያ ውስጥ ያሉት ታቦታቱን ማደሪያ ያደረጉት ጽላቶች  ሁሉ ትግሬዎች ናቸው ማለት ነው? ይህ ደግሞ ‹‹ትግሬነት ወያኔነት ነው›› በሚለው የአምሳሉ ስሌት ከተኼደ ታቦታቱ ሁሉ ‹‹ወያኔዎች›› ናቸው ያስብላለል፡፡ ይህ ደግሞ ትልቅ ክሕደት ነው፡፡ ስለዚህ አምሳሉ ገብረ ኪዳን ከሐዲ ነው ያስብላል፡፡
ሌላው ዲያቆን ዳንኤል ክብረት ‹‹ወያኔ ነው›› ለማለት እንደ ማስረጃ የጠቀሰው ‹‹ሰሎሞናዊ ሥርወ መንግሥትና ሲሦ መንግሥት የለም›› ብሏል፤ የሚለውን ነው፡፡ ይህን ከሦስት አቅጣጫ እንፈትሸው፡፡ የመጀመሪያው ከወያኔ የታሪክ ትንተና አቋም አንፃር ነው፡፡ ወያኔ ዲያቆን ዳንኤል ክብረት እንደሚለው፤ ‹‹ሰሎሞናዊ የሚባል የተለየ መንግሥት አልነበረንም፡፡ ሲሦ መንግሥት ለቤተ ክርስቲያን በአቡነ ተክለ ሃይማኖት በኩል አልተሰጠም፤›› አይልም፡፡ ወያኔ ‹‹አዲስ ራእይ›› በተባለው ንድፈ አሳባዊ መጽሔቱም ሆነ ለኢንዶክትሪኔሽን በአዘጋጀው መጻሕፍቱ፤ ‹‹በሰሎሞናዊው እና በዛግዌ ሥርወ መንግሥታት መካከል በነበረው ሽኩቻ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ለይኩኖ አምላክ አድልተውና ይኩኖ አምላክም የሸዋ ሰው ስለሆነ ለዘራቸው አድልተው መንግሥትን ከዛዌ ሥርወ መንግሥት ወደ ሰሎሞናዊ ሥርወ መንግሥት እንዲሸጋገር አድርገዋል፡፡ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ለሰሎሞናዊ ሥርወ መንግሥት በዋሉት ውለታ ለቤተ ክርስቲያን ሲሦ መንግሥት ተሰጠ፡፡›› ነው የሚለው፡፡ ይህ ደግሞ ተስፋዬ ገብረ አብ፤ ‹‹የስደተኛው ማስታወሻ›› በተሰኘ መጽሐፉ ውስጥ፤ ‹‹የፍስሐ ጽዮን ፖለቲካ›› በሚል ርእስ ስለ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ከጻፈውና የዚህ ጽሑፍ ቀጥታ ቅጂ ወይም ፎቶ ኮፒ ከሆነው ከኹራፊው አምሳሉ ገብረ ኪዳን አቋም ጋር አንድ ነው፡፡
ስለዚህ በኹራፊው ስሌት መሠረት የአቋም ተጋሪነት የሚያወይን ከሆነ ከወያኔ አቋም በተቃራኒ፤ ‹‹ሰሎሞናዊ የሚባል የተለየ ሥርወ መንግሥት አልነበረንም፡፡ በአቡነ ተክለ ሃይማኖት በኩል ሲሦ መንግሥት ለቤተ ክርስቲያን አልተሰጠም፡፡›› ያለው ዲያቆን ዳንኤል ክብረት ሳይሆን፤ የወያኔን አቋም የራሳቸው አቋም አድረገው፤ ‹‹በዛግዌ እና ሰሎሞናዊው ሥርወ መንግሥታት መካከል በነበረው ሽኩቻ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ለይኩኖ አምላክ አድልተውና ይኩኖ አምላክም የሸዋ ሰው ስለሆነ ለዘራቸው አድልተው መንግሥትን ከዛግዌ ሥርወ መንግሥት ወደ ሰሎሞናዊ ሥርወ መንግሥት እንዲሸጋገር አድርገዋል፡፡ ለዚህም ውለታ ለቤተ ክርስቲያን ሲሦ መንግሥት ተሰጥቷቸዋል፡፡›› ያሉት ተስፋዬ ገብረ አብ እና ኹራፊው አምሳሉ ገብረ ኪዳን ናቸው፤ የወየኑት ማለት ነው፡፡
ሁለተኛው ከታሪክ ምሁራኑ ትንታኔ አንፃር ነው፡፡ አስቀድመን በስም የጠቀስናቸው ፕሮፌሰር ታደሠ ታምራት፤ ‹‹Church and State in Ethiopia›› በሚል ርእስ ከዛሬ አርባ ሦስት ዓመታት በፊት በአሳተሙት መጽሐፋቸው፤ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የታሪክ መምህር የሆኑት አቶ አበባው አያሌው ደግሞ፤ ‹‹በታሪክ ጥናት ትልቁ ወንጀል›› በተሰኘ ርእስ ከዛሬ ዘጠኝ ዓመት በፊት በ‹‹ሐመር›› መጽሔት ላይ በጻፉት መጣጥፍ፤ ስለ ሰሎሞናዊ ሥርወ መንግሥት እና ሲሦ መንግሥት፤ ዲያቆን ዳንኤል ክብረት ከሚያራምዳቸው አቋሞች ጋር ተመሳሳይ አቋሞችን አራምደዋል፡፡ እንግዲህ በኹራፊው አምሳሉ ገብረ ኪዳን ስሌት መሠረት የዲያቆን ዳንኤልን ታሪካዊ ትንታኔ ምሁራዊ ምልከታን ያጎናጸፉትን እነዚህን የታሪክ ምሁራን ወይነዋል ልንል ነው?
ሦስተኛው ከ‹‹ሐመር›› መጽሔት ምልከታ አንፃር ነው፡፡ ዲያቆን ዳንኤል ክብረት፤ ‹‹ጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ለዘራቸው አድልተው መንግሥት ከዛግዌ ሥርወ መንግሥት ወደ ሰሎሞናዊ ሥርወ መንግሥት እንዲሸጋገር አድርገዋል፡፡ በውለታም ለቤተ ክርስቲያን ሲሦ መሬት ተሰጥቷቸዋል፤›› የሚለውን ትረካ አጽንዖት ሰጥቶ ‹‹የለም›› ያለውን፤ ‹‹ሐመር›› መጽሔት ከዘጠኝ ዓመታት በፊት ‹‹አፈ ታሪክ›› ብሎታል፡፡ ስለዚህ በኹራፊው በአምሳሉ ገብረ ኪዳን የፍረጃ ስሌት መሠረት ‹‹ሐመር›› መጽሔት እንዲህ በማለቷ ከዛሬ ዘጠኝ ዓመት በፊት የወያኔ ልሳን   ነበረች ልንል ነው? የፖለቲካ ድንቁርና ይሉታል ይኼ ነው፡፡
ከላይ ከጠቀስናቸው የፍረጃ ነጥቦች ባሻገር ኹራፊው አምሳሉ ገብረ ኪዳን ዲያቆን ዳንኤል ክብረትን፤ ‹‹የወያኔ ተልእኮ አስፈጻሚ ነው›› ለሚለው አሉባልታው እንደ ማስረጃ የጠቀሰው፤ ‹‹የቅዱስ ሲኖዶስ መንበር አይሰደድም›› የሚለውን አቋም ነው፡፡ ይኼ አቋም ደግሞ የዲያቆን ዳንኤል አቋም ብቻ ሳይሆን የማኅበረ ቅዱሳንም የጸና አቋም ነው፡፡ የማኅበረ ቅዱሳንም ብቻ ሳይሆን የቤተ ክርስቲያኒቱ ሊቃውንትና የእውነተኞቹ ኦርቶዶክሳውያን ምሁራን አቋምም ነው፡፡
ከዛሬ ሃያ ሦስት ዓመታት በፊት በዲያስጶራነት የሚገኙት አበው፤ ‹‹የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሕጋዊ ስደተኛ ሲኖዶስ አቋቁመናል፤›› ብለው ሲያውጁ ማኅበረ ቅዱሳን፤ ‹‹ሐመረ ጽድቅ›› በተሰኘው ልዩ ዕትሙ ተቋቋመ ስለተባው ‹‹ስደተኛ ሲኖዶስ›› የቤተ ክርስቲያንን ቀኖና ከመንበራቸው የተሰደዱ ቅዱሳን አባቶችን አብነት በመጥቀስ፤ ‹‹የቅዱስ ሲኖዶስ መንበር አይሰደድም›› የሚለውን አቋሙን ግልጽ ማድረጉ ይታወሳል፡፡
ይሁንና ኹራፊው አምሳሉ ገብረ ኪዳን ማኅበረ ቅዱሳን በ1997 ዓ.ም ‹‹ሰው እንጂ መንበር አይሰደድም›› የሚለውን ሃይማኖታዊ አቋሙን ለመተንተንና ለኦርቶዶክሳውያን ግንዛቤ ለማስጨበጥ ከአዘጋጀው ጽሑፍ ውስጥ፤ ምንም ዓይነት ምንጭ ሳይጠቅስ ራሱ እንዳዘጋጀው ጽሑፍ አድርጎ ያለ መልኩ ‹‹የስደት ሲኖዶስ›› መቋቋምን ትክክለኛነት ለማስረዳት ሲጠቀምበት አስተዋልኩ፡፡ በዚህም የዚህን ሰው ጤነኛነት በእጅጉ ተጠራጠርኩ፡፡ ያለ አንዳች ሐፍረት ደግሞ፤ ‹‹ለአራት ኪሎ አባቶች በመጽሔት ላይ መልስ ስሰጣቸው፤ እሽ የሳቸው (ብጹዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆርዮስ) መሰደድ እንደ ጥፋት አይቆጠር ሲኖዶስ ግን አይሰደድም መንበረ ፓትርያርክም አይሰደድም ብለው እዚያ ማቋቋማቸው ትክክል አይደለም፤ ማለት አመጡ፡፡ እኔም አስከተልኩና… ›› እያለ ይቀጥልና፤ ‹‹ድርጊቱ ፀረ ክርስትና ነው›› በማለት ጎጣዊ ዝምድና የወለደውን ርካሽ ፖለቲካውን ይደሰኩራል፡፡ በመጀመሪያ በ‹‹አራት ኪሎ ያሉት አባቶች›› ያላቸው አባቶቻችን በየትኛውም ኦፊሴላዊ መግለጫዎቻቸው ሆነ በሌላ ‹‹የአቡነ መርቆርዮስ መሰደድ እንደ ጥፋት አይቆጠርም፤ ይቆጠራልምም፤›› ብለው አያውቁም፡፡ ሲቀጥል ደግሞ የኹራፊው የአምሳሉ ገብረ ኪዳን ጽሑፍ ለቅዱስ ሲኖዶስ ምኑ ነውና ነው ‹‹የአቡነ መርቆርዮስ መሰደድ እንደ ጥፋት አይቆጠርም›› የሚል መግለጫ የሚሰጠው?  ማንስ አንብቦት ነው? ማንስ እሱነቱን አውቆ ነው? ይህ መቼም እጅግ ሲበዛ አቅምን እና ደረጃን አለማወቅ ድፍረት ነው፡፡
ወደ ጥንተ ነገራችን እንመለስና፤ ከማኅበረ ቅዱሳን ባሻገር ‹‹መንበር አይሰደድም›› የሚለውን የዲያቆን ዳንኤል ክብረትን ሃይማኖታዊ አቋም በመጋራት ‹‹መንበር ይሰደዳል›› የሚለውን ፖለቲካዊ አቋም በመንቀፍ ከጻፉት ምሁራን አንዱ ፕሮፌሰር ጌታቸው ኃይሌ ናቸው፡፡ ፕሮፌሰር ጌታቸው ኃይሌ ከዛሬ ሰባት ዓመታት በፊት፤ ‹‹ በግሌ ሕይወቴ ከደረሰውና ካጋጠመኝ አንዳፍታ ላውጋችሁ›› በተሰኘው መጽሐፋቸው ላይ እንዲህ ብለው ነበር ፡፡
‹‹ … መሠረታዊውና ዋናው ጥያቄ ግን ይህ ነው ፤ ሲኖዶስ እንደቤተ ክርስቲያን ፓርላማ ከታየ አሜሪካ ላይ የሚቋቋመው ሲኖዶስ የየትኛው ቤተ ክርስቲያን ፓርላማ ለመሆን ነው ?ለአንድ አገር ከአንድ የበለጠ ፓርላማ ሊኖረው እንደማይችል ሁሉ ለአንድ ቤተ ክርስሰቲያንም ከአንድ የበለጠ ሲኖዶስ ሊኖራት አይችልም ፡፡ ሲኖዶስ ፈጣሪዎቹ መፍትሔ አድርገው ያዩት ሌላ ቤተ ክርስቲያን ማቋቋም ነው ፡፡ እንግዲህ ሲኖዶስ ቤተ ክርስቲያንን የሚያገለግል መሆኑ ቀርቶ የነሱን ሲኖዶስ የምታገለግል ቤተ ክርስቲያን ሊፈጥሩ ነው ፡፡ … አሁን ደግሞ የስደተኞቹን ጳጳሳት ፍትወት ለማርካት ሌላ ግንጠላ ሊያመጡባት ተማምለው ተነሥተዋል ፡፡ …ጎጠኛ መሆን ቤተ ክርስቲያንን መክዳት መሆኑን ጎጠኞች ተከታዮቻቸው የተገነዘቡት አይመስለኝም ፡፡ ›› /ጌታቸው ኀይሌ፣2000 ፣251 /
ይኼንኑ አቋማቸውን በማጠናከር ደግሞ ከዛሬ ሦስት ዓመት በፊት ‹‹እናት ቤተ ክርስቲያናችን አልተከፈለችም›› በሚል ርእስ በጻፉት መጣጥፍ ላይ እንደሚከተለው ብለው ነበር፡፡
‹‹ለአንድ ቤተ ክርስቲያን የሚኖራት አንድ ሲኖዶስ፣ አንድ አመራር ብቻ ነው፡፡  ይህንን ሕግ ሁለት ሲኖዶስ የፈጠሩት አዲስ አበባ ያሉትና ስደተኞቹ ካህናት ያውቁታል፡፡ ከኢትዮጵያ ውጪ ያለነው ሕዝበ ክርስቲያን፣ ካህናቱን ጨምሮ፣ የፖለቲካና የኢኮኖሚ ስደተኞች ነን፡፡ የምናደርገው ትግል ሀገራችን ነጻ ሆና እንድንኖርባት ነው እንጅ፤ ይህን ካላገኘን ብለን በተሰደድንበት ዓለም ኢትዮጵያዊ መንግሥትና ኢትዮጵያዊት ቤተ ክርስቲያን ልናቋቁም አይደለም፡፡ ስለዚህ የተሰደዱትን ካህናት የምጠይቃቸው፤‹‹የእኛን ሲኖዶስ ተከተሉ›› እያሉ ሕዝብ ማስጨነቃቸውንና የመከፋፈል ምክንያት መሆናቸውን ትተው፤ የድዮስጶራው ሕዝብ ወያኔን ሲቃወም ተጨማሪ ኃይል እንዲሆኑ ነው፡፡ ‹‹የእኛን ሲኖዶስ ተከተሉ›› ማለት የሃይማኖት ስደተኞች ሳንሆን፤ የሃይማኖት ስደተኞች ሁኑ፤ ከኢትዮጵያው ሕዝበ ክርስቲያን ተለዩ፤›› ማለት ነው፡፡ ብዙዎች የሚከተሏችሁ ወያኔ የተጠቃላቸው መስሏቸው ቢቸግራቸው ነው እንጂ፤ ኢትዮጵያ ካለው ሕዝበ ክርስቲያን መለየት ፈልጎ አይደለም፡፡ የአንድ ቤተ ክርስቲያን ሲኖዶስ ማእከል ከሕዝቡ መካከል መሆን እንዳለበት መካድ አይቻልም፡፡ ስለዚህ በሕዝብ መሐል ያለውን የኢትዮጵያውን ጭቁን ሲኖዶስና ቤተ ክርስቲያንን አመራር ታግሎ፣ ከወያኔ እጅ ነጻ አውጥቶ ከመውሰድ ይልቅ፤ ከኢትዮጵያ ውጪ ሌላ ሲኖዶስ ማቋቋም ሕጋዊ አለመሆኑን ሲኖዶስ አቋቋሚዎቹ ያውቁታል፡፡ መፍትሔ አድርገው ያዩት የኢትዮጵያውን ሲኖዶስ፤ ‹ሕገ ወጥ› እነሱ ያቋቋሙትን፤ ‹ሕጋዊ› ማለት ነው፡፡ ግን ሁለቱም ሕገ ወጥ ናቸው፡፡ ልዩነቱ የኢትዮጵያው ሲኖዶስ ‹ሕገ ወጥ› የሆነው መንግሥት አስገድዶት ሲሆን፤ የውጪዎቹ ካህናት ሲኖዶስ ያቋቋሙት በስደተኛው ሕዝብ ብዛትና ብሶት በመጠቀም ነው፡፡ በወያኔ ጭቆና የተሰደደው ሕዝብ ብዙ ባይሆን፤ ስዱዳን ጳጳሳት ምንም ብዙ ቢሆኑ ብቻቸውን ሲኖዶስ አያቋቁሙም ነበር፡፡ በሲኖዶስ ስም የተደራጁት ለአገልግሎት እንዲመቻቸው ብቻ ከሆነ፤ ሕገ ወጥ ሲኖዶስ ሳያቋቁሙ የሚፈለገውን አገልግሎት መስጠትና ሕዝበ ክርስቲያኑን አስተባብሮ የወያኔን ክንድ መመከት ይቻላል፡፡ ሕገ ወጥ ሲኖዶስ ማቋቋም ግን ሕዝብ ስለሚከፋፍል መንበሩን ከመልቀቅ የከፋ ጥፋት መጨመር ነው፡፡›› (ጌታቸው ኃይሌ፤2004፣4-5)
እንግዲህ ‹‹መንበር ይሰደዳል›› ብሎ ፖለቲካዊ አቋም ከያዘው ኹራፊው አምሳሉ ገብረ ኪዳን ተለይቶ፤‹‹መንበር አይሰደድም›› ብሎ ሃይማኖታዊ አቋም የያዘውን ዲያቆን ዳንኤል ክብረት የወያኔ ተልእኮ አስፈጻሚ የሚያሰኘው ከሆነ፤ ኹራፊው ራሱ እንዳለው በየጊዜው የወያኔ ጅራፍ የሚያርፍበት ማኅበረ ቅዱሳን፤ ‹‹መንበር አይሰደድም›› የሚል ሃይማኖታዊ አቋም አለውና የወያኔ ተልእኮ አስፈጻሚ ነውን? ከተጠረጠሩ በአማራ ብሔርተኛነት እና በፀረ ወያኔነት ይጠረጠሩ ካልሆነ በስተቀር በወያኔ ተልእኮ አስፈጻሚነት በፍጹም የማይጠረጠሩት ፕሮፌሰር ጌታቸው ኃይሌ፤‹‹መንበር አይሰደድም፤ ሕገ ወጥ ሲኖዶስ ማቋቋም ግን ሕዝብ ስለሚከፋፍል መንበሩን ከመልቀቅ የከፋ ሌላ ጥፋት መጨመር ነው፡፡›› የሚለውን ሃይማኖታዊ አቋም በፖለቲካ ተዋስዖ/Discourse / ተንትነው ያቀረቡት የወያኔ ተልእኮ አስፈጻሚ ስለሆኑ ይሆን? ከኹራፊዉ አምሳሉ ገብረ ኪዳን ውጪ ሌላ ሰው አዎን የሚል ያለ አይመስለኝም፡፡
4- አቅጣጫ የሳተና በተቃርኖ የተሞላ የሴራ ትንተና!
ኹራፊው አምሳሉ ገብረ ኪዳን ኢስላማዊውን ነቢይ ‹‹መሐመድ ›› ብሎ ዘርጥጦ የጠራቸውን፤ዲያቆን ዳንኤል ክብረት በኢትዮጵያዊ ጨዋነት ኢስላማዊ ነቢይነታቸውን አክብሩ ‹‹ነቢዩ መሐመድ ›› ብሎ መጥራቱን እንደ ጥፋት በመቁጠር በ‹‹ደፋርነት›› ከስሱታል  ፡፡
በኢስላም አስተምህሮ አለማመን እና የእነርሱን ነቢያት አለመቀበል አንድ ነገር ሆኖ መሪያቸውን ክብረ ነክ በሆነ አጠራር መጥራትን ትክክል የሚያደርግ የክርስትና አስተምህሮ የለም ፡፡ሌላው ቢቀር ሰብአዊ ፍጡርነታቸው ያስከብራቸዋል ፡፡ ዲያቆን ዳንኤልም የፈጸመው ይህንኑ ነው ፡፡ ኹራፊው እንዳደረገው መሆን ግን ኢ ክርስትና ነው ፡፡
ኹራፊው አምሳሉ ገብረ ኪዳን ምን ያህል ሚዛኑን የሳተ መሆኑን የሚያርጋግጥል በአንድ በኩል የሙስሊም ወንድሞቻችን ነቢይ የሆኑትን ነቢዩ መሐመድን በቃለ አክብሩ አትጥሯቸው ፤‹‹ መሐመድ በሉት›› እያለ በሌላ በኩል ደግሞ ከወያኔ ጋር የሚያደርጉትን ስላማዊ ትግል ለተንሻፈፈው ፖለቲካዊ ፍትወቱ ይጠቀምበታል ፡፡ መሪያቸውን እየዘረጠጡና ክብር እየነሱ በዲያቆን ዳንኤል የኦሪት ፍየልነት  የሰላማዊ ትግላቸው ተከባካቢና ጠባቂ ሆኖ መገለጥ አይቻልም ፡፡በተወሰኑ ሰዎች ዘንድ ተችሉም ከሆነ እጅግ ሲበዛ ሞራለቢስነት ነው ፡፡ወያኔስ የሚያደርገው ይህንኑ አይደለም ፡፡
ዲያቆን ዳንኤል ክብረት ‹‹አክራሪ እስልምና የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን አስቸጋሪ ፈተና ›› በተሰኘው ጥልቅ ጥናታዊ ወረቀቱ  የክርስትናችን አስቸጋሪ ፈተና ‹‹ አክራሪ አስልምና ›› አለ እንጂ ኹራፊው አምሳሉ ‹‹የሀገርና የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ጠላት ስውሩ ተኩላ ዳንኤል›› በተሰኘው ግልብ ጹሑፉ ላይ እንደተመለከተው የክርስትናችን አደጋ ‹‹ ከፊሉ እስላም ነው ›› አላለም ፡፡የዲያቆን ዳንኤል ክብረት ጥናት ለራሱ ለእስልምናውም ፈተና የሆኑትን አክራሪዎችን የክርስታናችን ፈተና አድርጉ ሲያቀርብ ፤የኹራፊው አምሳሉ ግልብ ጹሑፍ ግን ‹‹እስላም የሆነ ሁሉ አክራሪ ነው ›› በሚል ስሌት መሠረት ‹‹ ከፊሉ እስላም ››በሚል አገላጽ የክርስትናችን አደጋ ግማሹ ሙስሊም ሙሉ በሙሉ  እንደሆነ አድርጉ አቅርቧል፡፡ ሰለዚህ ኹራፊው አለ በሚለው ክርስቲያኑንና ሙሲሊሙን የማፋጠጥ የወያኔ ሴራ ሰተት ብሎ የገባው ኹራፊው እንጂ ዲያቆኑ አይደለም ማለት ነው ፡፡
ኹራፊው አቅጣጫ የሳተበትና በተቃርኖ የተሞላበት ሌላው ነጥብ ‹‹ ‹አራቱ ኀያላን › የሚለውን መጽሐፍ ያዘጋጀበት ምክንያት የአማራ ነገሥታትን ስምን ለማጥፋት በማሰብ ነው ፡፡ ›› የሚለው ነው ፡፡ይኸው ሰው ‹‹ አራቱ ኀያላን የሚለው መጽሐፍ የተጻፈው የአማራ ነገሥታትን ስም ለማጥፋት በማሰብ ነው ›› ብሎ ከደመደመ በኃላ ይህንኑ አገላለጹንእና ሰለዲያቆን ዳንኤል ያለውን የሐሰት ክስ በመቃርን ‹‹ዲ/ን ዳንኤል እየሠራ ያለው ሥራ በእውነት አጅግ የሚያስመሰግነው ነው ፡፡ … የዚህ መጽሐፍ (የአራቱ ኀያላን መጽሐፍ ማለቱ ነው) ዋነኛ ዓላማው የሚመስለኝ በዚህ ዘመን ያሉ አባቶች መንፈሳዊና ግብረ ገባዊ ብቃት ከቀድሞቹ አባቶቻችን ጋራ ሲነጻጻር ምን ደረጃ ላይ እንዳለ ለማሳየትና የቀደሙቱ አባቶቻችንን የዓላማ ጽናት በአርአያነት እንዲወስዱ ማድረግ የሚሞክር ወይም መሆን አለበት ፡፡ ›› በማለት ያፈርሰዋል ፡፡
ኹራፊው በመርሕ ላይ የተመሠረተ ተቃውሞም ሆነ ድጋፍ የማያደርግ መሆኑን ከዚህ መረዳት ይቻላል ፡፡ የትኛውንም አሙን በየትኛውም ጊዜ ለመተው በቂ ምክንያትና ማሰብ አያስፈልገውም ፡፡ ፕሮፌሰር መስፍንን ሲያወድስና ዲያቆን ዳንኤልን ሲያራክስ ምክንያት የለውም ፤ተስፋዩ ገብር አብን ደግፎ ፣ዲያቆን ዳንኤልን ሲቃወም ተጠየቅ የለውም ፤አቶ ኤርሚያስን ደግፎ፣ዲያቆን ዳንኤልን ሲቃወም አመክንዩ የለውም ፡፡በጭፍን ይደግፋል፤ በጭፍን ይቃወማል ፡፡ ለእርሱ መውደድና መጥላት በቂ ነው ፡፡ የዘመናችን ‹‹ድንግል በክልኤ›› እንግዲህ ይህ ነው ፡፡
ከዚሁ ጋራ በተጨባጭ የማውቀውን እንደሱሯጽ (as side issue)ልንገራችው ፡፡ኹራፊው አምሳሉ በተለይ ከአቶ ኤርሚያስም ለተስፋዬ የተሰጠው ምላሽ ያንገበገበው ስለ ሁለት ነገር ነው ፡፡አንደኛው በ1990ዎቹ ውስጥ የካድሬነት መልማይ የጡት አባት በመሆን ትንሽ የወያኔን ፍርፋሪ እንዲያገኘ ያደረገው ተስፋዬ ነበር ፡፡ሁለተኛው ሥራ በፈታባቸው ዓመታት ውስጥ እንጀራ የሆኑት የተስፋዬ የጥፋት መጻሕፍት ነበሩ ፤አሁን ደግሞ የአቶ ኤርሚያስ መጽሐፍ፡፡እኛም በመጽሐፍ ቅርጽ እያዘጋጀ የሚሸጣቸውን ፎቶ ኮፒ ‹መጽሐፍ› ገዝተን ያነበብ ነው እርሱ ከአሰማራቸው መጻሕፍት አዟሪዎች ነበር ፡፡ከእነዚህ በቀጥጣ ከማውቃቸው መረጃዎች ተነሰቼ ስደመደም ዲያቆን ዳንኤል ክብረት አስቀድሞ ለተስፋዬ በኃላ ለአቶ ኤርሚያስ በሰጠው ጹሑፍ መደምደሚያ ላይ‹‹ ሌላውንም ነገር የሚነግሩን እንዲህ ሐሰት ይዘው ነው ማለት ነው›› ማለቱ አስቆጥቱታል ማለት ነው ፡፡ ዲያቆን ዳንኤል እንዲህ መደምደሙ መጻሕፍቱ በሰፊው ተሰራጭተው፣ ሰዉ አንብቧቸው ፣የሥርዐቱን ፀረ ዲሞክራሲያዊነት እንዳይረዱና የተአማኔነት ችግር እንዲገጥማቸው ሊያደርግ ይችላል ከሚል በጎ መንፈስ ሳይሆንመጻሕፍቱን መረጃ ተአማኔነት ዋጋ በማሳጣት ገዥ ሊያሳጣኝ ይችላል ከሚል ጥቅመኝነት የመነጨ ቁጣ ይመስለኛል ፡፡
ኹራፊው አምሰሉ ገብረ ኪዳን ዲያቆን ዳንኤል ክብረት ‹‹በአገሪቱ ስላለው ሰብአዊ መብት ገፈፋ፣ ስለሙስና መሰራፋት፣ ሰለኑሮ ውድነት፣ እምነትን በነጻነት የማራመድ መብት ማጣትን፣በዋልድባም ሆኑ በሌሎች ገዳማት ላይ በሚደርሱ ጥቃቶች ላይ  አልጻፈም፤እንደጸሐፊ አይደለም እንደ ዜጋ እንኳን በእነዚህ ነገሮች ላይ አንድም ነገር ተናግሮ ተንፍሶ አያውቅም ፡፡ ››ሲልም በሐሰት ይከሰዋል ፡፡ክሱ ምን ያህል በሐሰት የተሞላ መሆኑን ለማረጋገጥ ዲያቆን ዳንኤል ክብረት ‹‹የሃይማኖት ፖሊሲ ፣ሕግና ተቋም የሌላት ሃይማኖተኛ ሀገር ፣‹‹ውልድብና ›› እና ኢውልድብና››፣ዝቋላ ሀገሩ የትነው? ፣100% ፣እኔ በሞትኩ በማግስቱ ፣ለምጣዱ ሲባል ፣‹‹ስኳሬ›› ‹‹ዘይቴ›› ፣ከ2000 ዓመት በኃላ እንደ አዲስ እንመዘገባለን ፣እንደ አዲስም እንታወቃለን ፣መጀመሪያ ሰው ነኝ ››በሚል ርእሶች ያዘጋጃቸውን እነዚህን ጹሑፎች ብቻ ማንበብ በቂ ነው ፡፡በርግጥ ጹሑፎቹ ወያኔን በሐሳብ ልዕልና ይሞግታሉ እንጂ እንደኹራፊው ‹‹ወያኔ የጤፍ ዱቄት ሌባ ነው›› ዐይነት ተራ አሉባልታዎች አይደሉም፡፡ የኹራፊው የ‹‹እንዲህ ››አላለም ‹ፖለቲካ› ጨዋታ የጨዋዎቹ በመሆኑ እዚህ ጋ አልሠራም ፡፡
ማጠቃለያ
ኹራፊው አምሳሉ ገብረ ኪዳን ‹‹ዳንኤል ክብረትና ሌላው የወያኔያዊ ተግባሩ መገለጫ! ››በሚል ርእስ በለጠፈብን ማወረቅ ጹሑፉ ‹‹በሀገሬ ፣በቤተ ክርስቲያንና በዚህ ውድ ሕዝብ ሸፍጦች ሲፈጸሙ አልችልም ፡፡ … ዘለፋው ይገርማችሃል እንዴ ! እውነቴን ነው የምላቹህ ፈንጅ በእጄ ቢኖር አንድ ሰው የማስተርፍ አይምሰለኝም ፡፡›› ብሎንም ነበር ፡፡
የሆነው ግን ሌላ ነው፡፡ ነውረኛና በሐስት መርዝ የተለወሰውን ዘለፋውን በተግባር ያዋለው ለሀገሩ ፣ለቤተ ክርስቲያኑና ለውድ ሕዝቡ በሚደክመው በዲያቆን ዳንኤል ክብረት ላይ ነው ፡፡ በሕሊናውም በፈንጅ ያጋየው ይኼንኑ የሀገር ፣የቤተ ክርስቲያንና የሕዝብ ባለውለታ የሆነውን ዲያቆን ዳንኤል ክብረት ነው ፡፡ ነስፍ ገዳይነት የሚጀምረው በሕሊና ገዳይነት ነውና የዲያቆን ዳንኤል ክብረት አጥፊው ነፍስ በላው አምሳሉ ገብረ ኪዳን ነው ማለት ነው ፡፡ ይህ ደግሞ ከሞራል ተጠያቂነት ባሻገር የሕግ ተጠያቂነትን ያስከትላል ፡፡
ይሁንና ያልሆነው ግን ያለውን ነው ፡፡ ‹‹ በሀገሬ ፣በቤተ ክርስቲያንና በውድ ሕዝቧ ሸፍጥ ሲፈጸም አልችልም፤ በፈንጅ ነው የምፈጀው ›› እያለና እየቀባጠረ በፀረ ወያኔ ቆብ ከወያኔ ባልተናነሰ በወያኔያዊ መንገድ በሀራችን ሕዝብ አብሮነት ላይ ሸፍጥ እየፈጸመ የሚገኘው ተስፋዬ ገብረ አብን አይደለም በፈንጅ በብዕር ምንም አላለውም ፡፡ ተስፋዬ ‹‹ የቡርቃ ዝምታ ›› በተሰኘው መጽሐፉ ኦሮሞውንና ትግሬውን በአማራው ላይ ቀስቅሶበታል ፤ ‹‹በጋዜጠኛው ፣ በደራሲውና በስደተኛው ማስታወሻ ››በተሰኙ እኩይ መጻሕፍቱ አማራው ፣ ኦሮሞውና ሌላው ጎሳ በትግሬው ላይ እንዲነሳሳ ዘምቷል፤ ‹‹ የጀሚላ እናት ›› በተሰኘው ሰይጣናዊ መጽሐፉ ደግሞ ኦሮሞው በኢትዮጵያዊነት መቃብር ላይ ኦርቶዶክሳዊነትን እንዲቀብር አጥብቆ ሰብኳል ፡፡ዳሩ ግን የኹራፊው አምሳሉ ዶልዶም ብዕር የተሰበቀው ለእንዲህ ዐይነቱ ፀረ ኢትዮጵያዊነትና ኦርቶዶክሳዊነት ሳይሆን በኢትዮጵያዊውና በኦርቶዶክሳዊው በዲያቆን ዳንኤል ነው ፤ኹራፊው በፀረ ወያኔያዊ ለምድ የተገለጠ የወያኔ ተኩላ የሚያሰኘውም አንዱ ይህ ነው ፡፡
 በ‹‹ቤተ ክርስቲያኔ ሸፍጥ ሲፈጸም አልችልም፤በፈንጅነው የምፈጀው ›› ባዬ ኹራፊው አምሳሉ በፀረ ወያኔነት ካባ የታጀለውና የሻቢያ የጥፋት እጅ የሆነው ተስፋዬ ገብር አብ ‹‹የስደተኛው ማስታወሻ ››በተሰኘው የጥፋት መጽሐፉ የቤተ ክርስቲያናችን የመካከለኛው ዘመን የሐዋርያዊ አገልግሎት ማዕዘን በሆኑትን በጻዲቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ላይ ‹‹የፍስሐ ጽዮን ፖለቲካ ››በሚል ርእስ በጻፈው ነውረኛ ጹሑፉ ሲሳለቅ  ምንም ሳይለው፣ በጸሎት ብዛት የተቆረጠውን እግራቸውን ‹‹ሰይጣን ፈንግሏቸው የተቆረጠ ነው››ብሎ ሲጽፍ ሳያንገበግበው ፣ዲያቆን ዳንኤል  ክብረት ‹‹የሌለውን ፍለጋ ›› በተሰኘው ጹሑፉ ‹‹ተስፋዬ‹የፍስሐ ጽዮን ፖለቲካ› በሚል ርእስ ሰለ አቡነ ተክለ ሃይማኖት የማያውቀውን ነገር ጽል፡፡ሰለማያውቀው ነገር የጻፈው ባለማወቁ ብቻ አይመስለኝም ፡፡አንድም ለማወቅ ባለመፈለጉ፣አሊያም ሆን ብሎ የማፍረስ ዓላማ ይዞ ይመስለኛል ፡፡›› ብሎ መልስ መስጠቱ አጥወለወለው፤ዳግም ለተስፋዬ ድፍረት ‹‹… ሰባት ዓመት ሙሉ ለጸሎት የቆሙበት እግራቸው በጸሎት ብዛት በመቆረጡ እንጂ ሰይጣን ‹‹ ፈንግሏቸው›› አለመሆኑን ኤርትራውያን እናቶች በሚገባ ያውቁታል፡፡..››ብሎ የሰጠው መልስም አንገበገበው፡፡እንግዲህ ይህ ሰው ነው ራሱን የኢትዩጵያዊነትና ኦርቶዶክሳዊነት ጠበቃ አድርጉ የሚቆጥረው ፡፡ እረ እፈር ሊባል የሚገባ ሰው ነው ፡፡
በመጨረሻ አንድ ነገር ብቻ ልበል ፡፡ ዶክተር ደረጄ በመቅድም ጹሑፋቸው እንደተመለከቱት የተቃውሞ ፖለቲካን ክርክርን በጤፍ ዱቄት ሌብነት ደረጃ አውርዶ ከሚያስበውና ይህንኑ የማያደርጉትን በወያኔነት ከሚፈርጀው ኹራፊ ጋር  ‹‹መረጃ ላይ መመሥረት ያለበትን ታሪክ ነክ ወይም ፖለቲካ ነክ ክርክር  ማካኼድ አይቻልም›› ፡፡ ይህም ጹሑፍ ሲዘጋጅ ይህን በመገንዘብና ኹራፊው ያዋረደውን አንባቢ በማክበር የተቃውሞ ፖለቲካን ክርክርን  ወደ ቀደመ ክብሩ ለመመለስ ነው እንጂ ኹራፊውን በማሰብ አይደለም ፡፡ ሆኖም ግን የኹራፊው አምሳሉ ማወረቅ ጹሐፎች በርግጠኝነት አንድ ቁም ነገር ያስተምራሉ ፡፡ ይኸውም አንድ ጹሑፍ እንዴት እንደማይጻፍ!!




2015 ኤፕሪል 7, ማክሰኞ

ሃይማኖታዊና ትውፊታዊ ክንዋኔዎች በሰሙነ ሕማማት


አትምኢሜይል
መጋቢት 29 ቀን 2007 ዓ.ም.
በዓቢይ ጾም ከሰርከ ሆሳዕና ጀምሮ እስከ ትንሳኤ ሌሊት ያሉት ዕለታት የሚገኙበት ሳምንታት ሰሙነ ሕማማት ይባላሉ፡፡ ዕለታቱም የዓመተ ፍዳ፤ የዓመተ ኩነኔ መታሰቢያ ናቸው፡፡ በእነዚህ ዕለታት ውስጥ የተለያዩ ትውፊታዊ እና ሃይማኖታዊ ክንዋኔዎች አሉ፡፡ ከእነዚህ ክንዋኔዎች ውስጥ አለመሳሳም፤ አክፍሎት፤ ቄጤማ ማሰር፤ ጥብጣብ፤ ጉልባን እና ሕጽበተ እግር ይገኙበታል፡፡ ስለ እነዚህ ክንዋኔዎች በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ስላለው ትውፊታዊ አፈጻጸም መዛግብት አገላብጠን፤ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንን አነጋግረን እንደሚከተለው አቅርበናል፡፡

አለመሳሳም፡-
በሰሙነ ሕማማት ምእመናን መስቀል እንደማይሳለሙት ሁሉ መጨባበጥ፤ መሳሳምና የትከሻ ሰላምታ መለዋወጥን አይፈጽሙም፡፡ ሰላምታ የማንለዋወጥበት ምክንያት አይሁድ ጌታን ለመስቀል ሰኞ እና ማክሰኞ መከሩ አልሰመረላቸውም፡፡ ምክራቸው የተፈጸመው ረቡዕ ነው፡፡

ስለዚህ አይሁድ እያንሾካሾኩ €œእንስቀለው . . . እንግደለው€ ብለው ይማከሩ ነበር፡፡ ያንን ለማስታወስ ሰላምታ አንለዋወጥም፤ መስቀልም አንሳለምም፡፡ ሳምንቱ የክፋት ምክር የተመከረበት እንጂ የፍቅርና የደስታ ሰላምታ የታየበት ባለመሆኑ ይህንን በማሰብ ሰላምታ አንለዋወጥም፡፡

ይሁዳ ጌታን በጠላቶቹ ለማስያዝ €œእኔ የምስመው እርሱ ነው ያዙት ብሎ በሰላምታው ምልክት ሰጣቸው፤ ይህ ሰላምታ አምሐ ቅድሳት /የተቀደሰ ስጦታ/ አይደለም፤ ተንኮል የተሞላበት እንጂ፡፡ የዲያቢሎስም ሰላምታ ተመሳሳይ ነው፡፡ ሄዋንን €œሰላም ለኪ€ ብሎ ነው ያታለላት፡፡ ስለዚህ ይህንን ወቅትና ሁኔታ ለማሰብም በሰሙነ ሕማማት የሰላምታ ልውውጥ አይደረግም፡፡

ሕጽበተ እግር፡-
የጸሎተ ሐሙስ ዕለት ጌታ በፍጹም ትሕትና የደቀመዛሙርቱን እግር ያጠበበት፤ ከሐዋርያት ጋር ግብር የገባበትና የክርስትና ሕይወት ማሕተም የሆነውን ምስጢረ ቁርባን ያከናወነበት ዕለት ነው፡፡

ሕጽበተ እግር ጌታችን €œእናንተ ለወንድማችሁ እንዲህ አድርጉ€ በማለት የደቀመዛሙርቱን እግር በማጠቡ ምክንያት የተሰጠ ምሳሌ ነው፡፡ ይህም የሚያሳየው €œእኔ ለእናንተ እንዳደረግሁ እናንተ ደግሞ ታደርጉ ዘንድ ምሳሌ ሰጥቻችኋለሁና፤ እውነት እውነት እላችኋለሁ ባሪያ ከጌታው አይበልጥም፤ መልእክተኛም ከላከው አይበልጥም፤ ይህን ብታውቁ ብታደርጉትም ብፁዓን ናችሁ€ /ዮሐ.13፡16-17/ በማለት ትሕትናውን አሳይቷል፡፡

ጌታ በዚህ ዕለት የደቀመዛሙርቱን እግር ሲያጥብ €œእኔ መምህራችሁ ስሆን እግራችሁን ካጠብኳችሁ አርአያን ሰጥቻችኋለሁ፤ እናንተም የወንድማችሁን እግር ታጥቡ ዘንድ ይገባል፡፡ ነገር ግን ከእናንተ አንዱ ለሞት አሳልፎ ይሰጠኛል€ አለ፡፡ ደቀመዛሙርቱም €œማን ይሆን?€ አሉ፡፡ ጌታም ኅብስት ቆርሼ፤ ከወጡም አጥቅሼ የምሰጠው እርሱ ነው€ አላቸው፡፡ ደቀመዛሙርቱም ደነገጡ፡፡ ይሁዳን ማመልከቱ ነበር፤ ለጊዜው ግን አልገባቸውም፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሐዋርያቱን እግር በማጠብ ትሕትናን ካስተማራቸው በኋላ፤ ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን በመስጠት የኦሪትን መስዋዕት የሻረው እና መስዋዕተ ሐዲስን የሠራው በዚሁ ዕለት ነው፡፡

በዚህ ሃይማኖታዊ መነሻነትም በገጠሪቱ ኢትዮጵያ የሚከናወኑ ድርጊቶች አሉ፡፡ ለምሳሌ፡- በወሎና በጎንደር ከጉልባን በተጨማሪ በተለይ በጸሎተ ሐሙስ ዕለት ብቻ የሚጋገር የተለየ ዳቦ አለ፡፡ ይህ ልዩ ዳቦ በወሎ €œትኩሴ€፤ በጎንደር ደግሞ €œሙገራ€ ይባላል፡፡ ይህ ዳቦ ጌታ ለሐዋርያት የሰጣቸውን ኅብስት አምሳያ ነው ተብሎ ስለሚታሰብ ከዚህ ቀን ውጪ በሌላ ጊዜ አይጋገርም፡፡ በመሆኑም ሰው ሁሉ ዳቦውን ለመብላት የሚጠባበቀው በታላቅ ጉጉት ነው፡፡ አልፎ አልፎ ግን ሃይማኖታዊ ሥርዓት በሚከበርባቸው እንደ ማኅበርና ሰንበቴ በመሳሰሉት መንፈሳዊና ማኅበራዊ ትውፊቶች የሚቀርብበት ጊዜ አለ፡፡

በሰሜን ወሎ ሀገረ ስበከት በቅዱስ ላሊበላ አጠገብ በሚገኘው የይምርሐነ ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን ጣርያ ላይ ካህኑ €œትኩሴ€ ዳቦ ሲባርክ የሚያሳይ ሥዕል አለ፡፡

በትግራይ በዕለተ ስቅለት ከተለመደው የጾምና የስግደት ሥርዓት በተጨማሪ የሚከናወኑ ድርጊቶች አሉ፡፡ በዕለቱ የጌታችን የመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስቅለት መታሰቢያ ሲባል ወንዶች ልጆች በሙሉ ጸጉራቸውን እንዲላጩ ይደረጋል፡፡ ያን ቀን ያልተላጨ ልጅ €œኃጢአት ይሆንበታል€ ስለሚባል ሳይላጭ የሚውል የለም፡፡ ልጃገረዶች በበኩላቸው በዛፍ ላይ ገመድ በማሰር ዥዋዥዌ ይጫወታሉ፡፡ ይህንንም የሚያደርጉት የጌታን እንግልትና መስቀል ለማዘከር ነው ተብሎ ይነገራል፡፡

እነሆ ይህንን ዕለት በማስታወስ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከሊቃነ ጳጳሳት ጀምሮ እስከ ቀሳውስት ያሉት አባቶች በያሉበት አጥቢያ /ደብር/ በመገኘት በመዓርግ የሚያንሷቸውን የካህናት፤ የዲያቆናት እና የምእመናንን እግር ያጥባሉ፤ የሚያጥቡትም የወይራና የወይን ቅጠል በውኃ በመዘፍዘፍ ነው፡፡

አክፍሎት፡-
በሰሙነ ሕማማት ዕለተ ዓርብ ከስግደት በኋላ ምእመናን በየቤታቸው ጥቂት ነገር ለቁመተ ሥጋ ቀምሰው እስከ እሁድ /የትንሳኤ ሰዓት/ ይሰነብታሉ፡፡ ይህ አክፍሎት ይባላል፡፡ ከአርብ እስከ ቅዳሜ ለእሑድ አጥቢያ ብዙዎች ያከፍላሉ፡፡ አንዳንዶች ግን ከሐሙስ ጀምረው ያከፍላሉ፡፡ ይህም እመቤታችን፤ ያዕቆብና ዮሐንስ የጌታን ትንሳኤ ሳናይ እህል ውኃ አንቀምስም ብለው እስከ ትንሳኤ መቆየታቸውን ተከትሎ የመጣ ትውፊት ነው፡፡

ይህንን ትውፊት አስመልክቶ ሄሬኔዎስ፤ አውሳብዮስ የተባሉ ጸሐፍት፤ ሐዋርያት በሰሙነ ሕማማት ከደረቅ ዳቦ እና ከትንሽ ውኃ በቀር እንደማይመገቡ፤ ከሐሙስ ጀምረው እንደሚያከፍሉም ጽፈዋል፡፡ ይህም ብቻ ሳይሆን ሐዋርያት ሌሎቹንም እንዲያከፍሉ እንዳሳሰቡና ከሐሙስ ጀምሮ ያልተቻለው ቢያንስ ከዓርብ ጀምሮ እንዲያከፍል ማዘዛቸውን ጽፈዋል፡፡ የእኛ ቤተ ክርስቲያን ትምህርትም ይኸው ነው፡፡

ጉልባን
ጉልባን ከባቄላ ክክ፤ ከስንዴ ወይም ከተፈተገ ገብስ ጋር አንድ ላይ ተቀቅሎ የሚዘጋጅና የጸሎተ ሐሙስ ዕለት የሚበላ ንፍሮ ነው፡፡ የጉልባን ትውፊት እስራኤላውያን ከግብፅ ተሰደው በሚወጡበት ጊዜ በችኮላ ስለነበር አቡክተው ጋግረው መብላት ያለመቻላቸውን ሁኔታ ያመለክታል፡፡ ያን ጊዜ ያልቦካውን ሊጥ እየጋገሩ ቂጣ መብላት፤ ንፍሮም ቀቅለው ስንቅ መያዝ ተግባራቸው ነበር፡፡ ይህን ለማሰብ በሰሙነ ሕማማት ቂጣና ጉልባን በማዘጋጀት በዓሉ ይታሰባል፡፡

በጸሎተ ሐሙስ ይህንን መሠረት በማድረግ የሚዘጋጀው ጉልባን እንዲሁም ቂጣ ጨው በዛ ተደርጎ ይጨመርበታል፡፡ ጨው ውኃ የሚያስጠማ በመሆኑ የጌታን መጠማት ያስታውሳል፡፡ ይህ ትውፊታዊ ሥርዓት ከእስራኤላውያን የመጣ ሲሆን፤ በኢትዮጵያም አብዛኞቹን የትውፊት ክንዋኔዎች የብሉይ ኪዳን መነሻ ስላላቸው ሥርዓቱ ዛሬም ይታሰባል፡፡

ጥብጣብ፡-
በሰሙነ ሕማማት ዕለት ዓርብ የስቅለቱ መታሰቢያ ነው፡፡ ምእመናኑ በሰሙነ ሕማማት የሠሩትን ይናዘዛሉ፡፡ ካህናቱም በወይራ ቅጠል ትከሻቸውን እየጠበጠቡ ቀን ከሰገዱት ስግደት በተጨማሪ ሌላ ስግደት ያዟቸዋል፡፡ ጥብጠባው የተግሳፅ ምሳሌ ነው፡፡ ጥብጣብ የሚደረግለት ሰው በሕማማት ወቅት የፈጸመው በደል ወይም ኃጢአት ካለ ይህንኑ በመናገር የስግደቱ ቁጥር ከፍ እንዲል ይደረጋል፡፡

ሕዝበ ክርስቲያኑ በዕለተ ስቅለት ሲሰግድ፤ ሲጸልይ፤ ሲያነብ ከዋለ በኋላ ሰርሆተ ሕዝብ /የሕዝብ መሰነባበቻ/ ከመሆኑ በፊት በወይራ ቅጠል እያንዳንዱን ምእመን ጀርባ ቸብቸብ መደረጉ የጌታን ግርፋት ለማሰብ ነው፡፡ ማቴ.27፡26፤ 19፤1-3/

ቄጤማ፡-
በቀዳም ስዑር ቀሳውስቱና ዲያቆናቱ ቃጭል /ቃለ ዓዋዲ/ እየመቱ ገብረ ሰላመ በመስቀሉ ትንሳኤሁ አግሃደ€ የሚለውን ያሬዳዊ ዜማ በመዘመር ጌታ በመስቀሉ ሰላም እንደሰጠን እና ትንሳኤውንም እንደገለጠልን በማብሰር ቄጤማውን ለምእመናን ይሰጣሉ፡፡ ምእመናኑም ገጸ በረከት ያቀርባሉ፤ ቄጤማውንም በራሳቸው ያስራሉ፡፡ ይህም አይሁድ ጌታችንን እያሰቃዩ ሊሰቅሉት ባሉ ጊዜ የእሾህ አክሊል ጭንቅላቱ ላይ ያሰሩበትን ድርጊት የሚያስታውስ ነው፡፡

በዚህ ዕለት ልብሰ ተክህኖ የለበሱ ካህናትና ዲያቆናት ቄጤማ ተሸክመው፤ ቃጭል ሲያቃጭሉ መታየታቸው ዕለተ ትንሳኤውን ለሚናፍቁ ምእመናን ትልቅ ብስራት ነው፡፡

ምንጭ፡- ስምዐ ተዋሕዶ፤ ከሚያዝያ 1-5 ቀን 2004 ዓ.ም.

2015 ኤፕሪል 2, ሐሙስ

ዕለታተ ሰሙነ ሕማማት ወምስጢራት


አትምኢሜይል
በዲ.ቸሬ አበበ 

ከአባታችን አዳም በደል ወይንም ስሕተት በኋላ በሕማማት፣ በደዌያት፣ በመቅሰፍታት፣ ወዘተ በብዙ መከራ የሰው ልጅ ሊኖርባቸው ግድ የሆነባቸው ዘመናት ጥቂቶች አልነበሩም፡፡ ጥሮ ግሮ ወጥቶ ወርዶ ለፍቶ ማስኖ የዕለት ጉርስ የቀን ልብስ ማግኘት እጅግ አዳጋች ነበር፡፡ ሁልጊዜ የሰው ልጅ ቢያጠፋ ቢበድል ከሕገ እግዚአብሔር ቢወጣ እንኳ የዋህ፣ ታጋሽ፣ ቸር፣ አዛኝ የሆነ አምላክ የጠፋውን ሊፈለግ የተራበውን ሊያጠግብ የታረዘውን ሊያለብስ፣ ፍቅር ያጣውን ፍጹም ፍቅር ሊለግስ፣ ሰላም ለሌለው ፍጹም ሰላም ሊሰጥ፣ ተስፋ የሌለውን ተስፋ ሊያጐናጽፍ ከሰማይ ወረደ፤ ከድንግል ማርያም ተወለደ፤ በገዳመ ቆሮንቶስ አርባ ቀንና ሌሊት ጾመ፡፡ በጾሙም የኃጡአት ሥሮች ወይም ራሶች የተባሉትን ስስትን፣ ትዕቢትንና ፍቅረ ንዋይን ድል አደረገልን፡፡ እኛ እርሱ የጾመውን ጾም እንድናከብር እንድንጾም ምሳሌ ሆነን፡፡ ዲያብሎስን ድል አድርጐ ድል እንድንነሣው ኃይልና ምሳሌ ሆነን፡፡
 
ሰሙነ ሕማማት ምንድን ነው? 

ሰመነ ስምንት /ሳምንት/ አደረገ ማለት ነው፡፡ ይኸውም ከዕለተ ሆሣዕና ሰርክ እስከ ትንሣኤ ሌሊት ያለውን ጊዜ ወይም ቀናት የሚያመለክት ነው፡፡ ሐመ ማለት ታመመ ማለት ሲሆን ይህም የሰውን ዘር ሁሉ ከዲያብሎስ ባርነት ነፃ ለማውጣት ጌታችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በፈቃዱ የተቀበላቸውን ጸዋትወ መከራዎች የሚያሳስብ ነው፡፡ ዕለታቱ የዓመተ ኩነኔ ወይም የዓመተ ፍዳ ምሳሌዎች ናቸው፡፡ ክርስቲያኖች የክርስቶስን ውለታ እያሰቡ እጅግ የሚያዝኑበት፣ የሚያለቅሱበት፣ የሚሰግዱበት ቤት ንብረታቸውን ትተው ከሌላው ቀናትና ጊዜያት በተለየ መልኩ ቤተ ክርስቲያናቸውን የሚማጸኑበት፤ ጧት ማታ ደጅ የሚጠኑበት፤ ኃጢአታቸውን በቤተ ክርስቲያን አደባባይ ለካህኑ የሚናዘዙበት በዓመት አንድ ጊዜ ብቻ የሚገኝ ሳምንት ነው፡፡

በዚህ ሳምንት ብዙ አዝማደ መባልእት አይበሉም፤ ይልቁን በመራብ በመጠማት በመውጣት በመውረድ በመስገድ በመጸለይ በመጾም በየሰዓቱ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ጸዋትወ መከራዎች በማሰብ አብዝቶ ይሰገዳል፡፡ መከራውን፣ ሕማሙን፣ ድካሙን የሚያስታውሱ ከቅዱሳት መጻሕፍት ኢሳይያስ፣ ኤርምያስ መዝሙረ ዳዊት ግብረ ሕማማት ወዘተ በየሰዓቱ ይነበባል፡፡

መስቀል መሳለም የለም፡፡ ካህናትም እግዚአብሔር ይፍታህ አይሉም የሳምንቱ ሥርዓተ ፍትሐት አይደረግም፡፡ ይኸውም ይህ ሳምንት ከሞት ወደ ሕይወት የተሸጋገርንበት ከጨለማ ወደ ብርሃን የተጓዝንበት የመሸጋገሪያ ወቅት ምሳሌ በመሆኑ ነው፡፡ በዕለተ ምጽአት መላእክት የመለከት ድምጽ በማሰማት የዳግም ምጽአትን ዕለት ለማሳሰብ ምእመናን ጥሪውን ሰምተው ለዚህም አስቀድመው ተዘጋጅተው የበዓሉ ታዳሚዎች መሆናቸውን በማጠየቅ በዚህ ሳምንት ዲያቆኑ ቃጭል እየመታ በየሰዓቱ ምእመናኑን ያሳስባል፡፡

በሰሙነ ሕማማት የሚገኙ ዕለታትና ስያሜያት

ዕለተ ሰኑይ /ሰኞ/

ይህ ዕለት አንጾሖተ ቤተ መቅደስ /የቤተ መቅደስ መንጻት/ እና መርገመ በለስ የተፈጸመበት ዕለት ነው፡፡ /ማር.11-11፣ ማቴ.21-18-22 ሉቃ.13-6-9/፡፡ ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃስ «ወመሰለ ሎሙ ወይቤሎሙ አሐዱ ብእሲ በለሰ ቦቱ ውስተ አጸደ ወይኑ ወየሐውር ይንሣእ ፍሬሃ ወኢይረክብ ...»፤ ይህንም ምሳሌ አለ ለአንድ ሰው በወይኑ አትክልት የተተከለች በለስ ነበረችው ፍሬም ሊፈልግባት ወጥቶ ምንም አላገኘም፡፡ በማለት በበለስ ስለተመሰለ የሰው ልጅ ሕይወት በማሰብ እንዲመለስ ንስሐ እንዲገባ በሕይወትም እንዲኖር እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስ ማሳሰቡን ያጠይቃል፡፡ ንስሐ አልገባም አልመለስም ያለም በለሷ እንደጠወለገችና እንደተቆረጠች ሁሉ ፍሬ ባለማፍራታቸው እንደሚቆረጡ እንዲሁም ወደ እሳት እንደሚጣሉ መጽሐፍ ቅዱስ በግልጽ ያስረዳል፡፡ በለስ የተባለች ቤተ እስራኤል ፍሬ የተባለ ደግሞ ሃይማኖትና ምግባርን ነው፡፡ ሁላችን ቤተ እስራኤላውያን ፍሬ ሃይማኖት ወምግባር አስተባብረን ይዘን መገኘት ይገባናል፡፡ ፍሬ አልባ እንዳንሆን ጌታ ሲመጣም እንዳናፍር የመጽሐፉን ቃል ልንጠብቅና ልንፈጽም ይገባናል፡፡ በዚህ የሕማማት የመጀመሪያ ቀን ዕለተ ሰኑይ የምናስበው የምንዘክረው የሰው ልጅ ሕይወት በከንቱ በቸልተኝነት እንዳይደክም እንዳይጠወለግ እንዳይደርቅ ወደ እሳትም እንዳይጣል ማድረግ ይገባናል፡፡

ዕለተ ሠሉስ /ማክሰኞ/

ይህ ቀን ጌታችን ሰኞ በተናገረውና ባደረገው ላይ አይሁድ ጥያቄ ያቀረቡበት እርሱም መልስ በመስጠት ያስተማረበት ዕለት ነው፡፡ በዚህም ምክንያት የጥያቄ እና የትምህርት ቀን በመባል ይታወቃል፡፡ ጥያቄውም ጌታ ባደረገው አንጽሖተ ቤተ መቅደስ ምክንያት ለጸሐፍትና ፈሪሳውያን ይኸውም ትምህርት ማስተማር፣ ተአምራት ማድረግ፣ ገበያ መፍታትን በማን ሥልጣን ታደርጋለህ? ይህንስ ሥልጣን ማን ሰጠህ?» የሚል ነበር፡፡ /ማቴ.21-23-27/፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ማቴዎስ «ወይቤሎሙ ኢየሱስ አማን እብለክሙ ከመ መጸብሓውያን ወዘማውያት ይቀድሙክሙ ውስተ መንግሥተ እግዚአብሔር»፤ ኢየሱስ እንዲህ አላቸው እውነት እላችኋለሁ ቀራጮችና ጋለሞቶች ወደ እግዚአብሔር መንግሥት በመግባት ይቀድሙአችኋል ሲል አስተምሯል፡፡ /ማቴ.21-28/

ዕለተ ረቡዕ

ይህ ዕለት ደግሞ የአይሁድ ሊቃነ ካህናትና ጸሐፍት ጌታን እንዴት መያዝ እንደሚችሉ ምክር የጀመሩበት ቀን ነው፡፡ በዚህም ምክንያት ዕለቱ የምክር ቀን በመባል ይጠራል፡፡

ዕለተ ሐሙስ

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ዕለት ፍጹም ሰው ፍጹም አምላክ መሆኑን ለመግለጥ እና ለአርአያነት ጸሐፍት ፈሪሳውያን የአይሁድ ካህናት መጥተው እስኪይዙት ድረስ ሲጸልይ በማደሩ ምክንያት ጸሎተ ሐሙስ በመባል ይታወቃል፡፡ ትሕትና ፍቅር መታዘዝ እንዲሁም የአገልግሎትን ትርጉም ለማስረዳትና ለማስገንዘብ የደቀ መዛሙርቱን እግር በማጠቡ ሕጽበተ ሐሙስ በመባልም እንደሚጠራ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ይናገራሉ፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስም «ወሶበ ኀፀቦሙ እገሪሆሙ ነሥአ አልባሲሁ ወረፈቀ ካዕበ ወይቤሎሙ አእመርክሙኑ ዘገበርኩ ለክሙ ... ወሶበ አነ እንከ ሊቅክሙ ወእግዚእክሙ ኀፀብኩክሙ እገሪክሙ ከማሁኬ አንትሙኒ ይደልወክሙ ትኅፅቡ እግረ ቢጽክሙ፡፡»፤ «እግራቸውንም አጥቦ ልብሱንም አንሥቶ ዳግመኛ ተቀመጠ እንዲህም አላቸው ያደረግሁላችሁን ታስተውሉታላችሁን?... እንግዲህ እኔ ጌታና መምህር ስሆን እግራችሁን ካጠብሁ እናንተ ደግሞ እርስ በእርሳችሁ ትተጣጠቡ ዘንድ ይገባችኋል ሲል ተናግሯል፡፡ /ዮሐ.13-12-20/፡፡

ይህ ስለ እናንተ በመስቀል ላይ የሚቆረሰው ሥጋዬ ነው እንካችሁ ብሉ፤ ይህ ስለ እናንተ የሚፈስ ደሜ ነው ከእርሱ ጠጡ በማለት ምሥጢረ ቁርባንን የመሠረተበት ወይም ራሱ ምስጢረ ቁርባንን የጀመረበት ቀን በመሆኑ የምስጢር ቀን ተብሎ ይጠራል፡፡ ይኸውም የሰው ልጆች ሥጋውንና ደሙን ተቀብለን ከእርሱ ጋር አንድነትና ኅብረት እንዲኖረን ጥንተ ጠላት ዲለብሎስንም ፍጹም ድል ነሥተን ሰማያዊት ርስት መንግሥተ ሰማያትን እንድንወርስ ለማስቻል ነው፡፡ /ማቴ.26-26-29/፡፡

አይሁድ ጌታችንን ለመያዝ በእነርሱ ጥበብና ፍላጐት ቀስ ብለው መጥተው የያዙበት ቀን ስለሆነ በዚህ ዕለት በለሆሳስ /ብዙ የድምጽ ጩኸት ሳይሰማ/ የቅዳሴ ሥርዓት ይፈጸማል፡፡ ስለሆነም መላው ሕዝበ ክርስቲያን በዚህ የሕጽበት፣ የምስጢር፣ የጸሎት ቀን በተባለው በዚህ ዕለት በንስሓ ታጥበው ሥጋ ወደሙ እንዲቀበሉ ቤተ ክርስቲያን በአጽንኦት ታስተምራለች፡፡

ዕለተ ዐርብ

ሐዋርያው ቅዱስ ጳዉሎስ «አውቀውስ ቢሆን የክብርን ጌታ ባልሰቀሉት» /1ቆሮ.1-18/፡፡ እንዳለ ይህ ዕለት የአይሁድ ካህናት ያለበደል ያለጥፋት ንጹሕና ጻድቅ የሆነውን ጌታ የሰቀሉበት ዕለት ነው፡፡ ዕለቱም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የዓለም ሁሉ መድኃኒት ለአዳምና ለልጆቹ ሲል በመልእልተ መስቀል በቀራንዮ አደባባይ ተሰቅሎ መዋሉን የምናስብበት ታላቅ ቀን ነው፡፡ /ማቴ.27-35-75/፡፡ በዚያን ጊዜ አሳልፎ የሰጠው ይሁዳ እንደተፈረደበት አይቶ ተጸጸተ ሠላሳውንም ብር ለካህናት አለቆችና ለሽማግሎች መልሶ ንጹሕ ደም አሳልፌ በመስጠቴ በድያለሁ አለ፡፡ እነርሱ ግን እኛስ ምን አግዶን?  አንተው ተጠንቀቅ አሉ፡፡ ብሩንም በቤተ መቅደስ ጥሎ ሔደና ታንቆ ሞተ፡፡ የካህናት አለቆችም ብሩን አንሥተው የደም ዋጋ ነውና ወደ መባ ልንጨምረው አልተፈቀደም አሉ፡፡ ተማክረውም የሸክላ ሠሪ መሬት ለእንግዶች መቃብር ገዙበት፡፡ ስለዚህ ያ መሬት እስከ ዛሬ ድረስ የደም መሬት ተባለ፡፡ /ማቴ.27-3-9/

የሰው ልጆች በዘር ኃጢአት /ቁራኝነት/ ይኖሩበት የነበረው የጨለማ ሕይወት ያከተመበት ፍጹም ድኅነት ያገኙባት ታላቅ ዕለት ናት፡፡ ክርስቲያኖች ሁልጊዜም ዕለተ ዓርብ ሲመጣ ሕማሙን ስቅለቱን ሞቱን የሚያስቡበት ጊዜ ነው፡፡ በሮማውያን ሕግና ሥርዓት መስቀል የወንጀለኞች መቅጫ ምልክት የሕይወት መቅጫ አርማ ሆኖ ሳለ ለእኛ የዲያብሎስ ድል መንሻ ስላደረገው በስቅለቱና በሞቱም ሕይወትን ስለአገኘን በዚህም ምክንያት መልካሙ ዓርብ በመባል እንደሚታወቅ የቤተ ክርስቲያን አባቶች ያትታሉ፡፡

ቀዳሜ ስዑር

ዕለተ ቅዳሜ እግዚአብሔር የሚታዩትንና የማይታዩትን፣ በእግር የሚሄዱትን እና በክንፍ የሚበሩትን በባሕር የሚዋኙትን እንስሳትን በመጨረሻም ሰውን በአርአያውና በአምሳሉ ፈጥሮ ያረፈበት ዕለት ነች፡፡ ይህች የመጀመሪያው ቅዳሜ ለእግዚአብሔር የዕረፍት ዕለት ናት እግዚአብሔርን ሥነ ፍጥረት ፈጥሮ ስላረፈበት ሰንበት ዐባይ /ታላቋ ሰንበት/ ትባላለች ታላቋን ሰንበት እስራኤላውያን እንዲያከብሯት ታዟል፡፡ ዘፍ.1፡3፡፡

ዕለተ ቀዳሚት /ሰንበት ዐባይ/ በዘመነ ሐዲስም የተለየ የደኅነት ሥራ ተከናውኖባታል፡፡ ጥንት ሥነ ፈጥረትን በመፍጠር ዕረፍት እንደ ተደረገባት ሁሉ የፍጥረት ሁሉ ቁንጮ የሆነውን አዳምን ለማዳን ሕማምና ሞት የተቀበለው ቸሩ አምላክ በመቃብር አርፎባታል፡፡ ማቴ.27፡61፡፡

በዚህች ዕለት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በከርሰ መቃብር ዐርፎ የዋለባት ዕለት በመሆኗ «ቀዳሜ ስዑር » ትሰኛለች፡፡ ስዑር ቀዳሜ የተባለችው በዓመት አንድ ቀን ስለ ምትጾም ነው፡፡ ምክንያቱም እናቱ ድንግል ማርያም ወዳጆቹ ቅዱሳን ሐዋርያት ጌታ ተላልፎ ከተሰጠበት ዕለት አንስተው ብርሃነ ትንሣኤውን እስኪያዩ ድረስ እህል ውኃ በአፋቸው አልዞረም፡፡ ይመኩበትና ተስፋ ያደረጉት የነበረ አምላካቸው በመቃብር ስላረፈ ዕለቷን ሞቱን በማሰብ ትንሣኤውን በመናፈቅ በጾም አክብረዋታል፡፡

ከቅዱሳን ሐዋርያት ሲወርድ ሲወራረድ በመጣው ትውፊት መሠረት ቅዱሳን ሐዋርያት በማዘን በመጾምና በመጸለይ ዕለቷ እንዳከበሯት የተዋሕዶ ልጆች የተቻላቸው ከዓርብ ጀምረው የሚያከፍሉ /የሚጾሙ/ ለሁለት ቀን እህል ውኃ ሳይቀምሱ ያድራሉ ያልተቻላቸው ደግሞ ዓርብ ማታ በልተው ቅዳሜን በመጾም ትንሣኤን ያከብራሉ፡፡

በዚህ ዕለት ከሰኞ ከሆሣዕና ማግሥት ጀምረው እስከ ስቅለተ ዓርብ ድረስ በስግደት እና በጾም ያሳለፉ ምእመናን በዕለተ ቅዳሜ በቅጽረ ቤተ ክርስቲያን ይሰበሰባሉ፡፡ የጠዋቱ ጸሎት ሲፈጸም ካህናቱ «ገብረ ሰላመ በመስቀሉ፡-በመስቀሉ ሰላምን መሠረተ» የምሥራች እያሉ በቤተ ክርስቲያን ለተሰበሰቡት ምእመናን ቄጠማ ይታደላል ቄጠማው የምሥራች ምልክት ነው፡፡ ቄጠማው የምሥራች ምልክት ተደርጐ የተወሰደው በኖህ ዘመን ከተፈጸመው ታሪክ ጋር በማቆራኘት ነው፡፡ ቅዱስ መጽሐፍ እንደሚነግረን በጻድቁ ኖኅ ዘመን የነበሩ ሕዝቦች ከሕገ እግዚአብሔር ውጪ ሆነው እጅግ የሚያሳዝን ኃጢአት በሠሩ ጊዜ በንፍር ውኃ ተጥለቅልቀዋል፡፡ በወቅቱ ጻድቁ ኖኅ ወደ መርከብ ይዞአቸው ከገባው እንስሳት መካከል የውኃውን መጉደል ለመረዳት ርግብን በመርከብ መስኮት አሾልኮ ይለቃታል፤ እርሷም ቄጠማ በአፍዋ ይዛ ትመልሳለች፡፡ ዘፍ.9-1-29፡፡ ኖኅም በዚህ ቄጠማ የውኃውን መድረቅ ተረድቶ ተደስቷል፡፡

«ቄጠማ»፣ ለጥፋት ውኃ መድረቅ የምሥራች መንገሪያ እንደሆነ አሁንም በክርስቶስ ሞት ሞተ ነፍስ ከሰው ልጆች ተወገደ ስትል ቤተ ክርስቲያን ለልጆቿ ቄጠማ ታድላለች፡፡ ምእመናንም የምሥራች ተምሳሌት የሆነውን ቄጠማ በግንባራቸው ያስሩታል፡፡

የክርስቶስ ተከታዮች ሁሉ ከጨለማ ወደ ብርሃን ከሚያቃጥለው ዋዕየ ሲኦል /የሲኦል ቃጠሎ/ ወደ ልምላሜ ገነት ጥንተ ማኅደራቸው መመለሳቸውን በዚህ አኳሃን እየገለጡ በዓለ ትንሣኤን በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ያከብራሉ፡፡ 
 
ከበዓሉ ረድኤት በረከት ያሳትፈን፡፡አሜን፡
ወስብሐት ለእግዚአብሔር

2015 ማርች 19, ሐሙስ

በተመሳሳይ ኃጢአት እየወደቅኩ ተቸገርኩኝ፡፡ ምን ላድርግ?


(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ሐሙስ መጋቢት 10 ቀን፣ 2007 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሑደ አምላክ አሜን!!!
        ውድ መቅረዛውያን እንዴት አላችኁ? በዛሬው ጽሑፋን ከአንባብያን ከተላኩልን ጥያቄዎች አንዱን ካህናትን ጠይቀን መልስ ይዘን መጥተናል፡፡ መልሱን የሚሰጡን በቀበና መድኃኒዓለም ቤተ ክርስቲያን የስብከተ ወንጌል ኃላፊ እንዲኹም በታዕካ ነገሥት ባዕታ ለማርያም ገዳም የመጻሕፍተ ሐዲሳት የ5ኛ ዓመት ደቀ መዝሙር የኾኑት ቀሲስ ፋሲል ታደሰ ናቸው፡፡ ለርሳቸው ተናጋሪ አንደበት ለእኛም ሰሚ እዝነ ልቡና ያድለን፡፡ አሜን!!!
ጥያቄ፡- “እንደምን አላችኁ መቅረዞች? እባካችሁ አንድ ኃጢአት በተደጋጋሚ እሠራለሁ፡፡ ንስሐ አባቴ ጋር በተደጋጋሚ ብሔድም ኃጢአቴን መተው አልቻልኩም፡፡ ምን ላድርግ? እባካችሁ ጉልበት የሚኾነኝ ምክር ስጡኝ፡፡ እግዚአብሔር ይስጥልኝ፡፡”
 
        ቀሲስ ፋሲል ታደሰ፡- አንድ ሰው “ምን ላድርግ?” ብሎ ሲጠይቅ መንፈሳዊ ሕይወትን መፈለጉ ማሳያ ነው፡፡ አንድ ክርስቲያን “ምን ማድረግ ይገባኛል?” የሚል ጥያቄ ካነሣ ለማደግ መፈለጉን፣ መንፈሳዊ መፍትሔ መሻቱን፣ እግዚአብሔር እንደሚረዳው በማያጠያይቅ መንገድ ማመኑን ያመለክታል፡፡ መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ በሚያስተምርበት ጊዜ ሕዝቡ፣ ቀራጮች እንዲኹም ጭፍሮች እየመጡ፡- “ምን እናድርግ?” ይሉት ነበር /ሉቃ.3፡10-14/፡፡ ስለጠየቁም “ለንስሐ የሚገባ ፍሬ አድርጉ” ብሏቸዋል /ማቴ.3፡8/፡፡ ሐዋርያት ሲያስተምሩ፡- “ወንድሞች ሆይ! ምን እናድርግ?” ያሉት የገባቸው ናቸው /ሐዋ.2፡37/፡፡ ስለዚኽ ምንም ደካሞች ብንኾንም ድካማችንን ከእኛ የሚያርቀው አምላካችን ልዑል እግዚአብሔር “በርሱ ቃል እታነፃለኁ፤ እመከራለኁ” ብሎ “ምን ላድርግ?” ብሎ መጠየቅ ታላቅነት፣ አንድም ትሕትና፣ አንድም የመንፈሳዊ ሕይወት ፍላጎትን የሚያሳይ ነውና ኹል ጊዜ ጠያቂዎች ለካህናት፣ ለቤተ ክርስቲያን መምህራን “ምን ማድረግ ይገባኛል?” ብለው ሲጠይቁ ሊበረታቱ ይገባቸዋል፡፡ በመኾኑም ውድ ጠያቂያችን ምሥጢራቸውን በማካፈል የኃጢአት ልምምድ ድል መንሻ ጥበባትን እንድንማማር ምክንያት ስለኾኑን በልዑል እግዚአብሔር ስም ላመሰግናቸው እወዳለኁ፡፡
ጥያቄው የብዙ ሰዎች ጥያቄ ነው፡፡ አበው ሲናገሩ፡- “ሰው ኾኖ የማይበድል እንጨት ኾኖ የማይጤስ” እንዲሉ እንደየኑሮአችን ደረጃ፣ እንደየሥራችን ዓይነት ይለያይ እንደኾነ እንጂ ክርስትና ሕይወታችን ስንመላለስ አንድ ከሚያደርጉን ነገሮች ውስጥ ኃጢአት የሚስማማን መኾኑ ነው፡፡ ጥያቄአችንም ጠያቄአችን እንዳነሡት “ምን እናድርግ?” ነው፡፡ በርግጥም “ምን እናድርግ?”፡-
1.     የኃጢአቱን ምንነትና መነሻውን ማወቅ፡- አንድ ሰው የሚወድቅበት ሌላኛው የማይወድቅበትና ትኩረት የማይሰጠው ሊኾን ይችላል፡፡ ከዚኽ አንጻር ጠያቂው “በተመሳሳይ ኃጢአት ደጋግሜ እወድቃለኁ” ያሉት ኃጢአት ምንድነው? እየተደጋገመ ያስቸገራቸው ምንድነው? ከምንም በፊት የኃጢአቱን ምንነትና መነሻውን ያጢኑት፡፡ መፍትሔው የሚዠምረው ከዚኽ ነው፤ የኃጢአቱን ምንነትና መነሻውን ከማወቅ፡፡
2.    የኃጢአቱን ምንነትና መነሻውን ከለዩ በኋላ ለዚያ ከሚዳርጉን ቦታዎች፣ ወይም ጓደኞች፣ ወይም ኹኔታዎች መሸሽ ነው፡፡ በተደጋጋሚ ወደምንወድቅበት ኃጢአት የሚገፋፉ ኹኔታዎችን፣ ቦታዎችን ወይም ጓደኛን በአጠቃላይ እንደየኃጢአቱ መነሻነት መራቅ ያስፈልጋል፡፡ “ከንጹሕ ጋር ንጹሕ ኾነህ ትገኛለህ፤ ከጠማማም ጋር ጠማማ ኾነህ ትገኛለህ” ይላል ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት /መዝ.18፡26/፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም፡- “አትሳቱ፤ ክፉ ባለንጀርነት መልካሙን አመል ያጠፋል” ይላል /1ኛ ቆሮ.15፡33/፡፡ በዚኽ መሠረት ጠያቂያችን ብቻ ሳይኾኑ ኹላችንም ኃጢአትን ደጋግመን የምንሠራው በኹኔታዎች ተጽዕኖ ነው? ወይስ በጓደኞች ግፊት? ወይስ በምንሰማው፣ በምናየው፣ በምንዳስሰው ተጽዕኖ? ይኽን በአግባቡ ከለየን በኋላ ከምንጩ ለማድረቅ ለዚያ ከሚዳርጉ ኹኔታዎች መሸሽ ነው፡፡ ይኽን ስናደርግም ከምንም በፊት ኅሊናን ማሳመን ይጠይቃል፡፡ በመቀጠልም አካላዊ ውሳኔ መስጠትን ነው፡፡ ለኃጢአት በሚዳርግ ቦታ ተቀምጠን “በፍጹም አይነካኝም፤ አይደርስብኝም” ማለት መመጻደቅ ነው፡፡ ሰይጣንም እኛን ለመጣል አያርፍምና የምንወድቅበትንም መንገድ ያዘጋጃልና በኅሊናም በአካልም ከዚያ መሸሽ ያስፈልጋል፡፡ የጴጢፋራ ሚስት ዮሴፍን ለክፉ ሥራ ስትከጅለው ቆሞ አልተሟገተም፤ ጥሏት ሸሸ እንጂ /ዘፍ.39/፡፡ ስለዚኽ ለተደጋጋሚ ኃጢአት ከሚዳርጉንና ከሚገፋፉን ነገሮች “እችለዋለኁ፤ እቋቋሟዋለኁ” ብሎ መመጻደቅ ሳይኾን መሸሽ ካለብን መሸሽ ያስፈልጋል፡፡ እንደየኹኔታው በይበልጥም ከክፉ ቦታዎች፣ እንደየኃጢአቱ መነሻነት መሸሽ ያስፈልጋል፡፡
3.    ኃጢአቱ በሥጋም በነፍስም ጎጂ እንደኾነ ማስተዋል፡፡ ይኽ በተመሳሳይ እየወደቅንበት ያለው ኃጢአት በሥጋም ጭምር የሚጎዳን ይኾናል፡፡ ከክርስትና ሕይወት ባሻገር ስብእናን የሚያጎድፍ፣ ጤናን የሚያውክ ሊኾን ይችላል፡፡ ከዚኽ አንጻር የዚኽ ጉዳት በጥልቀት ማስተዋል ያስፈልጋል፤ ጉዳት ማሰብ ለመጠንቀቅ ይረዳልና፡፡
4.    ከመምህረ ንስሐ፣ ከመምህራን እንዲኹም ከመጻሕፍት ትምህርት ማግኘት፡፡እድገት በደረጃ ነው፡፡ በአንድ ጀምበርም ለውጥ ላይመጣ ይችላል፡፡ በመኾኑም በሒደት ያንን የመተው መስመር ውስጥ እንድንጠነክር ከዚኽ ኹኔታም ፈጽመን ለመራቅ በራሳችን ጉልበት ብቻ አንችልም፡፡ “ያለ እኔ ምንም ልታደርጉ አትችሉም” ብሎናልና /ዮሐ.15፡5/፡፡ በዚኽም መሠረት ከመምህራን የምንሰማው የእግዚአብሔር ቃል፣ ከመጻሕፍት የምናገኘው፣ ከመምህረ ንስሐም በጸሎትና በምክር የምናገኘው ሐሳብ ያ እያጠቃንና እየጣለን ያለውን እንዲኹም የምንደጋግመውን ኃጢአት ለማስወገድ ኃይል ይኾነናል፡፡
5.    መንፈሳዊ ተግባራትን ማዘውተር፡፡ እንግዲኽ እንደየ ክስተቱ ለየትኛውም የኃጢአት ተግባር መንፈሳዊ ሕይወት፣ መንፈሳዊ ተግባር ድል መንሻው ነው፡፡ ይኽም “እንዲኽ ያለውን ክፉ መንፈስ ያለ ጾም ያለ ጸሎት ከእናንተ አይወጣም” እንዳለ /ማር.9፡29/ ጾምን፣ ጸሎትን፣ ንስሐን የሕይወታችን መሠረት ማድረግ ነው፡፡
6.    መተውን መለማመድ፡፡ ይኽም ማለት ጠቢቡ “ቀኑን ሙሉ እግዚአብሔርን በመፍራት ኑር” እንዳለ /ምሳ.23፡17/ “እስኪ ዛሬ ተቆጥቤ ልዋል” ብሎ መወሰን ማለት ነው፡፡ ከዚያ ከምንጠላው ግን ደግሞ እየወደቅንበት ካለው ስሕተት ተቆጥበን ከዋልን ማታ ላይ ተመስገን ብሎ ጸልዮ ማደር ነው፡፡ ነገም ሲነጋ “ዛሬም እንዲኹ እንደ ትናንትናው መንፈሳዊ መንገድና ሒደት ልዋል፡፡ ዛሬም እንዲኽ ካለው ተግባር ፍጹም ተቆጥቤ መዋል አለብኝ፡፡ ደግሞም እችላለኁ፡፡ እግዚአብሔር ያስችለኛል፡፡ ኃይልን በሚሰጠኝ በክርስቶስ ኹሉን እችላለኁ፡፡ እግዚአብሔር ያበራታኛል” ስንልና ዕለት ዕለት ኹኔታውን እየኰነንነው፣ እያወገዝነው፣ “በዚያ መንፈስ ዛሬ አልውልም፡፡ ይልቁንም በመንፈሳዊ መንገድና በጥንካሬ እውላለኁ” ብለን ስንወስን ያን ውሳኔአችንን እያደነቅን ስለተደረገልን ጥንካሬም ተመስገን እያልን ልምምድ ማድረግ ይቻላል፡፡ ደጋግመን የምንሠራው ኃጢአት እጅግ ብዙ ዘመናት ከእኛ ጋር የቆየ ሊኾን ይችላል፡፡ ነገር ግን ከእግዚአብሔር ኃይል በላይ የኾነ ኃጢአት የለም፡፡ ዋናው የእኛ ውሳኔ ነው፡፡ ብዙዎቻችን የምንታለለው እዚኽ ጋር ነው፡፡ ለመተው እንፈልጋለን፤ ለመተው ግን በተግባር አንወስንም፡፡ ንስሐ መግባት የማይፈልግ ሰው የለም፤ በተግባር ወስኖ የሚገባ ግን ጥቂት ነው፡፡ ሥጋ ወደሙን ተቀብሎ መኖር የማይፈልግ ክርስቲያን አይኖርም፡፡ ብዙዎች መቁረብ ይፈልጋሉ፤ ወስነው የሚቆርቡት ግን እጅግ ጥቂቶች ናቸው፡፡ ብዙ ሰዎች ከዝሙት ኃጢአት መራቅ እንደሚፈልጉ ይናገራሉ፡፡ ነገር ግን ዝሙትን የሚያበረታቱ ማስታወቂያዎችን፣ ዝሙትን የሚያበረታቱ ምስሎችን እንዲኹም የቴሌቪዥን ፕሮግራሞችን፣ ዝሙትን የሚያበረታቱ ዘፈኖችን እንዲኹም ጽሑፎችን፣ ዝሙትን የሚያበረታቱ ንግግሮችን ሲያደርጉ ይገኛሉ፡፡ እነዚኽን ሰዎች ስናያቸው በውስጣቸው ከዚያ ኃጢአት የመራቅ ፍላጎት አለ፤ ተግባሩ ላይ ግን ከዚያ የሚያሸሻቸው አይደለም፡፡ ለዚኽም ነው ጌታ፡- “ብዙዎች ይፈልጋሉ፤ አይችሉምም” ያለው /ሉቃ.13፡24/፡፡ ስለዚኽ ከኃጢአት መራቅ የሚፈልግ ሰው የመተው ልምምድን አኹንኑ መዠመር አለበት፡፡ “ዛሬ ዘፈን አላዳምጥም፡፡ ዛሬን በዚኽ ምትክ መዝሙር አዳምጣለኁ” ብሎ መለማመድ አለበት፡፡ በዚኽ ውሳኔው ጸንቶም ዛሬን ይውላል፤ ያድራልም፡፡ ሌሎች ነገሮችም እንደዚኽ ናቸው፡፡ የመጠጥ ልምድ ያለው ሰው “ዛሬ አልጠጣም፤ ዛሬ በምጠጣበት ሰዓት እዚኽ ቦታ እሔዳለኁ፡፡ እዚያ ሒጄ እውላለኁ፡፡ በበጎ ነገር አሳልፈዋለኁ” ሲል ዛሬን ይውላል፡፡ ማታ ላይ ሲመሽ “ለካ ይቻላል፡፡ ለካስ እኔ ከበረታኁ እግዚአብሔር ያስችለኛል” የሚለውን በኅሊናው ያሳምናል፡፡ ነገሮችን የመተው ልምምድ በተግባር ማሳየት ማለት ይኸው ነው፡፡ ይኽን ያደረግን እንደኾነ በአጭር ጊዜ ውስጥ ያ ያስቸግረን የነበረው ተደጋጋሚ ኃጢአት ታሪክ ይኾናል፤ ለሌላ ሰው መካሪ ኾነን ራሳችንን በለውጥ ቦታ ላይ እናገኟለን፡፡

 ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡         

2015 ማርች 14, ቅዳሜ

ደብረ ዘይት




መጋቢት 26 ቀን 2005 ዓ.ም.
በአባ ዘሚካኤል ደሬሳ
የዓለሙ ፍጻሜ ምልክቱ ምንድ ነው?/ማቴ. 24፣3/

በዓቢይ ጾም ውስጥ ካሉት ሳምንታት ደብረ ዘይት 5ኛው ሳምንት ላይ ይውላል፡፡ ደብረ ዘይት ትርጉሙ የወይራ ዛፍ ተራራ ማለት ሲሆን፣ ይህም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በኢየሩሳሌም በሚገኘው በደብረ ዘይት ተራራ ቅዱሳን ሐዋርያት” የዓለሙ ፍጻሜስ ምልክቱ ምንድነው?”/ማቴ. 24፣3/ ብለው ጠይቀውት እርሱም የማይቀረውን የዓለም ፍጻሜና አስቀድመው የሚፈጸሙ ምልክቶችን አስረድቷቸዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያንም ይህንኑ በደብረ ዘይት ሳምንት ታስበዋለች፤ ለምእመናኑም ከዘመኑ ሁኔታ አንጻር በመጻሕፍት የተጠቀሱትን የትንቢት ምልክቶቹን ከተግባራዊ የዓለም ክንዋኔዎች አንጻር በማገናዘብ ታስተምራለች፡፡ በመሆኑም በቤተ ክርስቲያናችን በደብረ ዘይት ሳምንት ምጽአትን አስመልክቶ የሚነገሩ ምስጢራት እጅግ ሰፊ ናቸው፡፡ ነገር ግን በዚህ ጽሑፍ በመጠኑ የምናየው ከቅዱሳት መጻሕፍት አንጻር በዓለም እየተከሰቱ ካሉ ወቅታዊ ምልክቶች ጋር በማገናዘብ ይሆናል፡፡

የሰው ልጅ ከሥነ ፍጥረት መነሻ ጀምሮ ስለ ራሱ መጨረሻና ስለ ዓለም ፍጻሜ ምንነት ማወቅን እንደሚሻ ቅዱሳት መጻሕፍት ያስረዱናል፡፡ ከነዚህም በተለይ ቤተ ክርስቲያን በደብረ ዘይት እለት የምታስተምረው፤ ቅዱሳን ሐዋርያት’ የዓለሙ ፍሳሜስ ምልክቱ ምንድነው?/ማቴ. 24፥3/’ በማለት የጠየቁት ጥያቄ ቅድሚያ ይሰጠዋል፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሐዋርያት ከመለሰላቸው ዋናውና ቀዳሚው የምጽአቱ ምልክት የሐሳዊ መሲህ መምጣት ነው፡፡ ሐሳዊ መሲሕ ማለት በቀጥታ ትርጉሙ ሐሰተኛ የሆነ በስሙ ማለትም በኢየሱስ፣ በክርስቶስ፣ በአምላክ ስም የሚመጣ የክርስቶስ ተቃዋሚ ማለት ነው፡፡ ትርጉሙን አስፍተን ስናየው፣ ደግሞ ከሃይማኖት ጋር ተያያዥ የሆኑና ያልሆኑ በዓለም እየተካሄዱ ያሉ ሐሰተኛ ጉዳዮችንና የጥፋት መንገዶችን ያጠቃልላል፡፡ የሐሳዊ መሲሕ የጥፋት ሥራዎች ሳያውቁም ሆነ በተለይ ሆን ብለው በዓለማውያንና በክፉ መናፍስት ተከታዮች እየተፈለሰፉ በሚከሰቱ ሁኔታዎች የሚካሄዱ ናቸው፡፡ ከእግዚአብሔር የተገኙ የሃይማኖት የሥነ ተፈጥሮ የጋብቻና የመሳሰሉ ድንበሮች ማፍለስን ዓላማ ያደረጉ፤ እንዲሁም መንፈሳዊ ባህል፣ ሰብአዊ ክብርና የእድሜ፣ የቅደም ተከተል ትስስርና ክብር እንዲጠፋ የሚሠሩ ሁሉ ከሐሳዊ መሲሕ መደብና ከዓለም ፍጻሜ ምልክትአንጻር የሚታዩ ናቸው፡፡ በዝርዝር ለማየት የሚከተሉትን ነጥቦች እንመልከት፣

1. የሃይማኖት ድንበርን ማፍለስ፡- ”አባቶችህ ያኖሩትን /የሠሩትን/ የቀድሞውን የድንበር ምልክት አትፍልስ” ምሳ.22፥28፣ 23፥10 አፈጻጸሙ ሰዎች የእግዚአብሔርን ማንነት እንዳያውቁ ከማድረግ ይጀምራል፡፡ከዚህም አንዱ ሐሳዊ መሲሕ በእግዚአብሔር ስም በተለያየ ሁኔታና መንገድ መገለጥ ነው፡፡ ”እስመ ብዙሃን ይመጽኡ በስምየ እንዘ ይብሉ አነ ውእቱ ክርስቶስ፤ እኔ ክርስቶስ ነኝ እያሉ ብዙ ሰዎች በኔ ስም ይነሣሉና” /ማቴ. 24፣5/፡፡ ይህም እንደ መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትምህርትና የቅዱሳን ሐዋርያት ስብከት መሠረት፣ ከክርስቶስ ወደ ሰማይ ማረግ በኋላ የሚመጣ፣ ክርስቶስን የእግዚአብሔር የባሕርይ ልጁ ነው ብሎ የማይሰብክ ሁሉ፤ ሌላ አምላክን የሚሰብክ ሁሉ መደቡ ከሐሳዊ መሲሕ ትምህርት ይመደባል፡፡ በመሆኑም ከዚህ በፊት ያለፉ፣ አምላክ ነን ብለው የተነሡ እንደ ቴዎዳስ ዘግብጽና ይሁዳ ዘገሊላ /ሐዋ. ሥራ. 5፣36-37/ የመሰሉ ሁሉ ከዚያም በኋላ በየጊዜው የተነሡና በዚህም ወቅት የዋሁን ሕዝብ ”ኢየሱስ ነኝ፣ ኢየሱስ በኛ ዘንድ አለ” እያሉ የሚያጭበረብሩ ሁሉ ሐሳውያነ መሲሖች ናቸው፡፡ ከዚህም ሌላ ክርስቶስን ከአብ የሚያሳንሱ፣ ”ሎቱ ስብሐት” ነቢይ ነው ብለው የሚያምኑ፣ በመናፍስት አሠራር የሚጠነቁሉ፣ በማቴሪያሊስት /ቁሳውያን/ ወይም በኢቮሉሽን /በዝግመተ ለውጥ/ ትምህርት አምነው አምላክ የለም የሚሉ ሁሉ፣ ወዘተ የሐሳዊው መሲሕ አካላት ናቸው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ በመልእክቱ ”ኢየሱስ ክርስቶስም በሥጋ እንደ መጣ የማይታመን መንፈስ ሁሉ ከእግዚአብሔር አይደለም፤ ይህም የክርስቶስ ተቃዋሚው መንፈስ ነው፤ ይህም እንደማመጣ ሰምታችኋል፥ አሁንም እንኳ በዓለም አለ።” /1ዮሐ. 4፣3/ በማለት ይመሰክርባቸዋል፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ አሁንም በመልእክቱ ”ልጆች ሆይ፥ መጨረሻው ሰዓት ነው፥ የክርስቶስም ተቃዋሚ ይመጣ ዘንድ እንደ ሰማችሁ አሁን እንኳ ብዙዎች የክርስቶስ ተቃዋሚዎች ተነሥተዋል፤ ስለዚህም መጨረሻው ሰዓት እንደ ሆነ እናውቃለን።” /1ዮሐ. 2፥18/ ይለናል፡፡ ከዚህ የምንረዳው የክርስቶስ ተቃዋሚ መምጣት የምጽአት ጊዜው መቃረብ ምልክት መሆኑን የማያሻማ ሀሳብ ያደርገዋል፡፡ በተጨማሪም የምጽአትን መቅረብ የሚያመለክቱ፣ ስለ ሐሳዊው መሲሕ እና ከርሱ ጋር ተያያዥ ስለሆኑ ወቅታዊ ጉዳዮች ተዛማጅ የሆኑትን የሚከተሉትን ትንቢቶች እንመልከት፣

ሀ. ”የአውሬው ምስል ሊናገር እንኳ ለአውሬውም ምስል የማይሰግዱለትን ሁሉ ሊያስገድላቸው፥ ለአውሬው ምስል ትንፋሽ እንዲሰጠው ተሰጠው። ታናናሾችና ታላላቆችም ባለ ጠጋዎችና ድሆችም ጌታዎችና ባሪያዎችም ሁሉ በቀኝ እጃቸው ወይም በግምባራቸው ምልክትን እንዲቀበሉ፥ የአውሬውም ስም ወይም የስሙ ቍጥር ያለው ምልክት የሌለበት ማንም ሊገዛ ወይም ሊሸጥ እንዳይችል ያደርጋል። ጥበብ በዚህ አለ። አእምሮ ያለው የአውሬውን ቍጥር ይቍጠረው፤ ቍጥሩ የሰው ቍጥር ነውና፥ ቍጥሩም ስድስት መቶ ስድሳ ስድስት ነው።” /ራእ. ዮሐ. 13፥16-18/ የሚለው የቅዱስ ዮሐንስ ራእይን ሊፈታ ከሚችልበት ትርጉም አንዲት ቅንጣት ብቻ ከዘመኑ አንጻር ብናይ ’የሚናገር የአውሬው ምስል’ ማለትም ለሱ ያልተገዙትን ወይም ቁጥሩን ያልያዙትን የሚናገርባቸው፤ ምልክቱን ያልተቀበሉትን ሊገዙና ሊሸጡ እንዳይችሉ ያደርግል ማለት መኖር፣ መሥራት፣ መሸጥ፣ መለወጥ ወዘተ የሚያግዳቸው ሲል አሁን ባለን ወቅታዊ የዚህ ዓለም አኗኗር አንጻር ሲታይ ተመሳሳይ ጉዳዮች አሉ፡፡ ለምሳሌ፣ መታወቂያ ወረቀት፣ ፓስፖርት፣ ቪዛ፣ የመኖሪያ ፈቃድ ወዘተ በዓለም አጠቃላይ አሠራር እና ባንድ ሰው የመኖር ማንነት ሚና ላይ ተጽእኖ የሚያደርጉ ነገሮች ናቸው፡፡ እነዚህ መታወቂያ ወረቀቶች የሌሉት ሰው ካለበት የትም መንቀሳቀስ አይችልም፡፡ ከዚህም በላይ ጉዳዩን ስናሰፋው በሰለጠኑት ዓለማት አሠራር የእያንዳንዱ ሰው የጣት አሻራ ኮምፒውተራይዝድ በሆነ መንገድ የተደራጀ በመሆኑ፣ እዚያ አደረጃጀት ውስጥ ካልተካተተ በቀር እዚያ ሀገር ሊኖር፣ ሊዘዋወር፣ ሊሠራ፣ ሊነግድ ወዘተ አይችልም፡፡ ለምሳሌ፣ አንድ እዚህ የኮምፒውተር ድር አደረጃጀት ውስጥ ያለ ሰው የትም ዓለም ቢሄድ በጣቱ አሻራ ይታውቃል፡፡ በትንቢቱ” አእምሮ ያለው የአውሬውን ቍጥር ይቍጠረው፤ ቍጥሩ የሰው ቍጥር ነውና፥ ቍጥሩም ስድስት መቶ ስድሳ ስድስት ነው።”  የሚለው ይህን የሚያደራጀው ጉዳዩን የሚያስተሳስረው ሌላ አካል ሳይሆን ሰው መሆኑን የሚያመለክት ነው፡፡ ስድስት መቶ ስድሳ ስድስት የሚለው ቁጥር የሰው ልጅ የጅማት ቁጥር ነውና፡፡

ለ. ሌላው የምጽአት መቃረብ ምልክት የሐሳዊው መሲሕ ዘመቻን አውቀው በድፍረት፣ ላላወቁት በረቀቀ መንገድ እግዚአብሔርን ያመለኩ አስመስሎ የእግዚአብሔርን ስም፣ እመቤታችንን ቅድስት ድንግል ማርያምን፣ ቅዱሳንን፣ ባጠቃላይ በሰማይ የሚያድሩትን መስደብ ነው፡፡ እነዚህም ተግባራት በተለያዩ ዘመናት ሲፈጸሙ የቆዩ ናቸው ዛሬም ተጠናክረው እየተፈጸሙ ይገኛሉ፡፡ ለምሳሌ፣ ሩቅ ሳንሔድ ዛሬ ቤተ ክርስቲያናችንን እየተፈታተነ ያለው የተሐድሶ ሤራ ዋናው ተቃውሞው የወልድን አምላክነት፣ የድንግል ማርያምን ክብርና አማላጅነት፣ የታቦትንና የመስቀልን ክብር፣ የቅዱሳንን ክብርና አማላጅነት ነው፡፡ በመሆኑም ተሐድሶ በሥራው የአውሬው መንፈስ አራማጅና መንገድ ጠራጊ መሆኑን ቅዱስ ዮሐንስ በራእዩ እንዲህ በማለት ያረጋግጥልናል፡፡ ”ለዘንዶውም ሰገዱለት፥ ለአውሬው ሥልጣንን ሰጥቶታልና፤ ለአውሬውም፡- አውሬውን ማን ይመስለዋል፥ እርሱንስ ሊዋጋ ማን ይችላል? እያሉ ሰገዱለት። ታላቅንም ነገርና ስድብን የሚናገርበት አፍ ተሰጠው፥ በአርባ ሁለት ወርም እንዲሠራ ሥልጣን ተሰጠው። እግዚአብሔርንም ለመሳደብ ስሙንና ማደሪያውንም በሰማይም የሚያድሩትን ሊሳደብ አፉን ከፈተ። ቅዱሳንንም ይዋጋ ዘንድ ድልም ያደርጋቸው ዘንድ ተሰጠው፥ በነገድና በወገንም በቋንቋም በሕዝብም ሁሉ ላይ ሥልጣን ተሰጠው። ከዓለምም ፍጥረት ጀምሮ በታረደው በግ ሕይወት መጽሐፍ ስሞቻቸው ያልተጻፉ በምድር የሚኖሩ ሁሉ ይሰግዱለታል።” /ራእ. ዮሐ. 13፣4.8/ እንዲል፡፡

ሐ. ሌላው በዓለም ላይ የሚታየው በሰዎች ዘንድ ክብር፣ ዝናና ታዋቂነትን ለማግኘት ሲባል ራስን ከፍ ማድረግና እንደ አማልክት መቁጠር ከሐሳዊው መሲሕ ያስመድባል፡፡ ከዚህ በተመሳሳይ ሊቀ ነቢያት ሙሴ እንደገለጸው የሰናዖር ሰዎችን ኀጢአት ስናሰተውል የተነሡበት ዋናው ነጥብ ’ስማችንን እናስጠራ’ የሚለው ነበር፡፡” ኑ ለእኛ ከተማና ራሱ ወደ ሰማይ የሚደርስ ግንብ እንሥራ፤ በምድር ላይ ሳንበተንም ስማችንን እናስጠራው አሉ።” /ዘፍ. 11፥4/ ነው የሚለን፣ በዚህ እኩይ አሳብ ምክንያት እግዚአብሔር ቋንቋቸውን ደባለቀባቸው፡፡ የሰናዖር ሰዎች ያሰቡትናየተመኙት ትውልዱ እግዚአብሔርን ማድነቅ ትቶ፣ ለዘለዓለም ስማቸውን ሲጠራቸው፣ ሲያደንቃቸው መኖርን ነበር፡፡ ዛሬም ብዙዎቹ ይህንን የሰናዖርን ኀጢአትና የጥፋት ጉዞ እንደ ዓላማ ይዘው በመንቀሳቀስ ላይ ይገኛሉ፡፡
2. የሥነ ተፈጥሮ ሕግ ድንበር መጣስ አንዱ የጊዜው መቃረብ ምልክት ነው፡፡ እግዚአብሔር የፈጠረው ፍጥረት ፍጹም በመሆኑ፣ ይህ ቀረህ፣ ይህ ይጨመርልህ የሚባል አይደለም፡፡ ነገር ግን በዚህ ወቅት፣ ሰው ለተለያየ ጥቅም በሚል ሰበብ ዝርያቸው የተለያዩ የሆኑትን ፍጥረታት ማዳቀልንና ማደበላለቅን ተያይዞታል፡፡እንስሳትና ተክሎችን ለማባዛት የማያደርገው ጥረትና  የማዳቀል ዘዴ የለም፡፡ በተቃራኒውም የሰውን ቁጥር ለመቀነስ የማያደርገው ሩጫ የለም፡፡ በመሆኑም ውጤቱ የሰውን ቁጥር ለመቀነስ ሲባል በሚደረጉ ሕክምናዎች ሰዎች ለተለያዩ በሽታዎች ተዳርገዋል፡፡ በሚደረገውም ማበረታታት በሠለጠኑት ዓለም ብዙዎቹ የግብረ ሰዶም ፈጻሚና አስፈጻሚ ሆነዋል፡፡ ይህ አሠራር አምላክ የሠራውን የፍጥረት ሕግ በማጣጣል ሰው ላሻሽል ወደሚል ያዘነበለ በመሆኑ የሰውን ልጅ ቅጥ ያጣ ድፍረት ያሳያል፡፡ እግዚአብሔር ግን ሥነ ፍጥረቱን እንዲያደባልቁበት አይፈልግም፡፡እግዚአብሔር ለሊቀ ነቢያት ሙሴ ”ሥርዓቴን ጠብቁ። እንስሳህ ከሌላ ዓይነት ጋር አይደባለቅ፤ በእርሻህም ሁለት ዓይነት ዘር አትዝራ” /ዘሌ. 19፣ 19፤/ ማናቸውም ሰው ከሴት ጋር እንደሚተኛ ከወንድ ጋር ቢተኛ ሁለቱ ጸያፍ ነገር አድርገዋል፤ ፈጽመው ይገደሉ፤ ደማቸው በላያቸው ነው።” /ዘሌ 20፣ 13/ በማለት ያሰተምረናል፡፡

3.    በጋብቻ ላይ የሚደረግ ርኩሰትን ስንመለከትም በየትኛውም ዓለም የፍርድ ቤቶች ትልቁ ሥራ ማፋታት ሆኗል፡፡ ምክንያቱም ተጋቢዎች ባንድ ላይ እንዳይኖሩ አውሬው /አስማንድዮስ/ የጋብቻ ጠላት በመሆን ስለነገሠ ፈተናውን መቋቋም አልቻሉምና ነው፡፡ ስለዚህ አስማንድዮስ ከዛ ይልቅ ግብረ ሰዶምን እያበረታታ በአንዳንድ ሀገሮች እንደሚታየው ወንድ ከወንድ፣ ሴት ከሴት ጋር እያቆራኘ በቤተ ክርስቲያኖቻቸው” ጋብቻ እስከ መፈጸም አድርሷቸዋል፡፡ ስለዚህም ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ይላል፣” ስለዚህ እርስ በርሳቸው ሥጋቸውን ሊያዋርዱ እግዚአብሔር በልባቸው ፍትወት ወደ ርኵሰት አሳልፎ ሰጣቸው፤ ይህም የእግዚአብሔርን እውነት በውሸት ስለ ለወጡ በፈጣሪም ፈንታ የተፈጠረውን ስላመለኩና ስላገለገሉ ነው፤ እርሱም ለዘላለም የተባረከ ነው፤ አሜን። ስለዚህ እግዚአብሔር ለሚያስነውር ምኞት አሳልፎ ሰጣቸው፤ ሴቶቻቸውም ለባሕርያቸው የሚገባውን ሥራ ለባሕርያቸው በማይገባው ለወጡ፤ እንዲሁም ወንዶች ደግሞ ለባሕርያቸው የሚገባውን ሴቶችን መገናኘት ትተው እርስ በርሳቸው በፍትወታቸው ተቃጠሉ፤ ወንዶችም በወንዶች ነውር አድርገው በስሕተታቸው የሚገባውን ብድራት በራሳቸው ተቀበሉ። እግዚአብሔርን ለማወቅ ባልወደዱት መጠን እግዚአብሔር የማይገባውን ያደርጉ ዘንድ ለማይረባ አእምሮ አሳልፎ ሰጣቸው፤ ዓመፃ ሁሉ፥ ግፍ፥ መመኘት፥ ክፋት ሞላባቸው፤ ቅናትን፥ ነፍስ መግደልን፥ ክርክርን፥ ተንኰልን፥ ክፉ ጠባይን ተሞሉ፤ የሚያሾከሹኩ፥ ሐሜተኞች፥ አምላክን የሚጠሉ፥ የሚያንገላቱ፥ ትዕቢተኞች፥ ትምክህተኞች፥ ክፋትን የሚፈላለጉ፥ ለወላጆቻቸው የማይታዘዙ፥ የማያስተውሉ፥ ውል የሚያፈርሱ፥ ፍቅር የሌላቸው፥ ምሕረት ያጡ ናቸው፤ እንደነዚህ ለሚያደርጉት ሞት ይገባቸዋል የሚለውን የእግዚአብሔርን ሕግ እያወቁ እነዚህን ከሚያደርጉ ጋር ይስማማሉ እንጂ አድራጊዎች ብቻ አይደሉም።” /ሮሜ.1፥24-ፍጻሜ

4.    መንፈሳዊ ባህል፣  የክህነት ክብር፣ ሰብአዊ ክብርና የእድሜ፣ የቅደም ተከተል ትስስርና  ክብር እንዲጠፋ የሚሠሩ፣ በሚለው ዙሪያ ስንመለከት በቀላሉ ቅዱስ ጳውሎስ በመልእክቱ ያለውን ማየት እጅግ ጠቃሚ ነው፡፡ነገር ግን በመጨረሻው ቀን የሚያስጨንቅ ዘመን እንዲመጣ ይህን እወቅ። ሰዎች ራሳቸውን የሚወዱ ይሆናሉና፥ ገንዘብን የሚወዱ፥ ትምክህተኞች፥ ትዕቢተኞች፥ ተሳዳቢዎች፥ ለወላጆቻቸው የማይታዘዙ፥ የማያመሰግኑ፥ ቅድስና የሌላቸው፥ ፍቅር የሌላቸው፥ ዕርቅን የማይሰሙ፥ ሐሜተኞች፥ ራሳቸውን የማይገዙ፥ ጨካኞች፥ መልካም የሆነውን የማይወዱ፥ ከዳተኞች፥ ችኩሎች፥ በትዕቢት የተነፉ፥ ከእግዚአብሔር ይልቅ ተድላን የሚወዱ ይሆናሉ፤ የአምልኮት መልክ አላቸው ኃይሉን ግን ክደዋል፤ እነዚህ ደግሞ ራቅ። ወደ ቤቶች ሾልከው እየገቡ፥ ኃጢአታቸው የተከመረባቸውን በልዩ ልዩ ምኞትንም የሚወሰዱትን ሁል ጊዜም እየተማሩ እውነትን ወደ ማወቅ ሊደርሱ ከቶ የማይችሉትን ሞኞችን ሴቶች የሚማርኩ፥ ከእነዚህ ዘንድ ናቸውና። ኢያኔስና ኢያንበሬስም ሙሴን እንደተቃወሙት፥ እንዲሁ እነዚህ ደግሞ አእምሮአቸው የጠፋባቸው ስለ እምነትም የተጣሉ ሰዎች ሆነው፥ እውነትን ይቃወማሉ። ዳሩ ግን የእነዚያ ሞኝነት ደግሞ ግልጥ እንደሆነ፥ ሞኝነታቸው ለሁሉ ይገለጣልና ከፊት ይልቅ አይቀናላቸውም።” / 2ጢሞ. 3፥1.7/ በማለት በመጨረሻው ዘመን የሚነሡ ሰዎችን ፀባይን ይነግረናል፡፡ ይህንን ትምህርተ ጥቅስ ለማገናዘብ  እግዚአብሔርን የማያምነውን ህዝብ ትተን፣ አሁን በዓለም ሁሉ ካለው የቤተ ክርስቲያንዋ አማኞች ብቻ አንጻር በመጠኑ እንይ ደግሞ፤

ሀ. መንፈሳዊ ባህል ማፍረስን ስንመለከት፣ የሁሉንም ባይሆን፣ የአንዳንዶቹ አማኞች ሰዎች ጸባይ ቅ. ጳውሎስ ”ከእግዚአብሔር ይልቅ ተድላን የሚወዱ ይሆናሉ፤ የአምልኮት መልክ አላቸው ኃይሉን ግን ክደዋል” የሚያሰኝ ሕይወት የያዙ እንደሆነ ያስረግጥልናል፡፡ እንደ አማኝ ቤተ ክርስቲያን የሚገኙ፣ ነገር ግን መንፈሳዊ አምልኮ የማይፈጽሙና የራሳቸውን አሳብ ቤተ ክርስቲያን ላይ ሊጭኑ የሚፈልጉትን ነው ’የአምልኮት መልክ አላቸው ኃይሉን ግን ክደዋል’ ያላቸው፡፡ የእግዚአብሔር ቤት መታዘዝ፣ መከባበርና ሰላም የነገሠበት መሆን ነው ያለበት፡፡ ነገር ግን በአንዳንድ ቦታ እንደሚስተዋለው በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ብዙዎቹ በመንፈሳዊው ባህል የጠነከሩ እንዳሉ ሁሉ አንዳንዶቹ ሥራ ፈቶች ሆነው ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ፖለቲካ፣ዘረኝነት፣አሉባልታ፣ ወዘተ በማምጣት ቤተ ክርስቲያንን ሲያውኩአት ይታያል፡፡ ቅ. ሉቃስ በተመሳሳይ አይሁድ ቀንተው በቤተ ክርስቲያን ላይ ያደረጉትን ”አንዳንዶቹ ተረድተው ከሚያመልኩም ከግሪክ ሰዎች ብዙ ከከበሩትም ሴቶች ጥቂቶች ያይደሉ፥ ከጳውሎስና ከሲላስ ጋር ተባበሩ።  አይሁድ ግን ቀንተው ከሥራ ፈቶች ክፉ ሰዎችን አመጡ ሕዝብንም ሰብስበው ከተማውን አወኩ፥” /የሐዋ. ሥራ 17፣ 5/ በማለት እንደገለጸው ያሉ ናቸው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም ”ወደ ቤቶች ሾልከው እየገቡ፥ ኃጢአታቸው የተከመረባቸውን በልዩ ልዩ ምኞትንም የሚወሰዱትን ሁልጊዜም እየተማሩ እውነትን ወደ ማወቅ ሊደርሱ ከቶ የማይችሉትን ሞኞችን ሴቶች የሚማርኩ፥ ከእነዚህ ዘንድ ናቸውና።” ይላቸዋል፡፡

ለ. የክህነት ክብርን ማፍረስ በተመለከተ፣ ቅ. ጳውሎስ ”ኢያኔስና ኢያንበሬስም ሙሴን እንደ ተቃወሙት፥ እንዲሁ እነዚህ ደግሞ አእምሮአቸው የጠፋባቸው ስለ እምነትም የተጣሉ ሰዎች ሆነው፥ እውነትን ይቃወማሉ። ዳሩ ግን የእነዚያ ሞኝነት ደግሞ ግልጥ እንደ ሆነ፥ ሞኝነታቸው ለሁሉ ይገለጣልና ከፊት ይልቅ አይቀናላቸውም።” እንዳለው ሁሉ ካህናት ነን ከሚሉት ጀምሮ እስከ ምእመናን ድረስ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሐዋርያት ሰጥቷቸው በአንብሮተ እድ እየተሾሙ ሲወርድ መጥቶ ለኛ የደረሰውን ታላቁን የድኅነት መፈጸሚያ ክህነት እንደ ኢያኔስና ኢያንበሬስ ዛሬ በብዙዎች ተንቆና ተዋርዶ ይገኛል፡፡ ለምሳሌ ከሚፈጸሙ ስህተቶች ጥቂቶቹን ቀጥለን እንመለከት፣

  • ቅዱስ ማቴዎስ ”በዚያን ዘመን ብዙዎች ይሰናከላሉ፣ እርስ በርሳቸውም አሳልፈው ይሰጣጣሉ፣ እርስ በርሳቸው ይጣላሉ” /ማቴ. 24፣10/ እንዳለው ሁሉ፤ለዘመናት በአንድነት የኖረችውን ቤተክርስቲያን ”ከዓመጻም ብዛት የተነሣ የብዙዎች ፍቅር ትቀዘቅዛለች” እንዲል፣ በዚህ ዘመን በድፍረት አስተዳደሩዋን በመከፋፈል ”ኢያኔስና ኢያንበሬስም ሙሴን እንደ ተቃወሙት” እንዲሁ አሳድጋ፣ አስተምራ፣ ክህነት የሰጠቻቸውን እናታቸውን ቤተ ክርስቲያን እስከ ማውገዝ የድፍረት ኀጢአት የተደረሰበት ዘመን ነው፡፡በመወጋገዙ ሂደት ያለው ጉዳትን ማን አስተዋለው? እግዚአብሔር ይማረን እንጂ እንደ ሰውኛው ከሆነ፣ በጭካኔ፣ ውስጥ ያለው ውጪውን፣ ውጭ ያለው ደጋግሞ ውስጥ ያለውን አውግዞትአንዲት ነፍስ ወደ እግዚአብሔር እንዳትደርስ ተቆላልፎ ቁጭ ብሏል፡፡ ነገር ግን ኢያኔስና ኢያንበሬስ ሙሴን ቢቃወሙትም ሙሴ ክህነቱ ከእግዚአብሔር በመሆኑ የእግዚአብሔር ክብር በርሱ ላይ ተገልጦ እግዚአብሔርን የተቃወሙት በደላቸው እንደ ተገለጠ ሁሉ፣ ዘለዓለማዊዋ ቤተ ክርስቲያን ክህነታዊ ክብርዋ በእግዚአብሔር ዘንድ ክቡር ነው፡፡  ”ሁሉ ለንጹሖች ንጹሕ ነው፤ ለርኵሳንና ለማያምኑ ግን ንጹሕ የሆነ ምንም የለም፥ ነገር ግን አእምሮአቸውም ሕሊናቸውም ረክሶአል።  እግዚአብሔርን እንዲያውቁ በግልጥ ይናገራሉ፥ ዳሩ ግን የሚያስጸይፉና የማይታዘዙ ለበጎ ሥራም ሁሉ የማይበቁ ስለ ሆኑ፥ በሥራቸው ይክዱታል።” / ቲቶ. 1፥15/ እንዳለ፡፡
  • ” ሰለስቱ ምእት በኒቂያ ጉባኤ ’ያለ ኢጲስ ቆጶስ ፈቃድ ቤተ ክርስቲያንን የመሠረተ ከክህነቱ ይሻር’ብለው ደንግገዋል፡፡ ነገር ግን በተለይ በውጭ አገር እየተለመደ የመጣው ጉዳይ የትኛውንም ኤጲስቆጶስ ሳያስፈቅድ አንድ ካህን፣ ከዚያም አልፎ በሚገርም ሁኔታ ዲያቆን ወይም ምእመን ከፈለገ ቦርድ አቋቋምኩ እያለ ቤተ ክርስቲያን አስተምራ አጥምቃ ያሳደገችውን ምእመን ከሥርዓተ ቤተክርስቲያን በማውጣት እንደ ማንኛውም ድርጅት ቤተ ክርስቲያን ከፈትኩ የሚባልበት የድፍረት ኀጢአት በጠራራ ፀሐይ ከሚፈጸምበት ዘመን ደርሰናል፡፡ በተጨማሪም በዚህ ዓይነት ለተቋቋሙ ሁሉ የሚገለገሉበት ታቦት ከየት መጣ? ሜሮን ከየት ተገኘ? የሚሉ ጥያቄዎች ምላሽ የላቸውም፡፡ ”ብዙዎች ይስታሉ” እንደተባለ በድፈረትና በስሕተት መሠረት ላይ የስሕተትና የድፍረትን ግድግዳ ማቆም፣ የስሕተትና የድፍረት ጣሪያንም ማዋቀር እንደ ሕጋዊ ሥራ ከተቆጠረ ሰነባበተ፡፡
  • የጥፋት ርኩሰት በተቀደሰው ስፍራ ቆሞ ስታዩ አንባቢው ያስተውል” /ማቴ 24፣15/ በየአጥቢያው የሚሰማውን ክፉ ወሬ ስናስተውል የዚህ ትንቢት ተፈጻሚነት እንዳገኘ ያረጋግጥልናል፡፡ የተሐድሶ ሴራ፣ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሚፈጠሩት ጭቅጭቆች፣ በመነኮሳትና በካህናት የሚነሱ ሐሜቶች፣ ሙሰኝነት፣ዘረኝነት ምን ይነግሩናል?በውጭ አገር በየቦታው አቋቋምን የሚሉት ሰበካ ጉባኤ ሳይሆን ራስ ገዝ የቦርዶቹ አስተዳደር ግፍ ደግሞ በሚገርም ሁኔታ የሚያገለግለው ካህንን የሚያዩት እንደ እግዚአብሔር ካህን ሳይሆን ከአንድ ቅጥር ሠራተኛቸው በታች ነው፡፡ ስለ አስተዳደሩ እንዲያውቅ አይፈልጉም፣ እነሱ ያዘዙትን ብቻ ይሰብካል/ ይናገራል፣ ካህኑም ሲፈልጉ የሚያኖሩት ሲፈልጉ የሚያባርሩት ሆኗል፡፡ ይህን አሠራር ለዘመናት ቤተ ክርስቲያን ከኖረችበት አንጻር ስናየው እጅግ የራቀና አስጸያፊ የሚባል ነው፡፡ ጌታችን ቤተ ክርስቲያንን የመሠረተው በሥልጣነ ክህነት እንድትተዳደር ሲሆን ይህኛው በተቃራኒ የቆመ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ምእመኑን አስተምራ አጥምቃ አሳድጋ እንደገና በተንኮለኞች ሤራ ልጆቹዋን ቀስጠው በስዋ ላይ እንዲያምጹ ማድረግ የጥፋት ርኩሰት መሆኑን ስንቱ ተረድቶት ይሆን?፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ”ማንም ልዩ ትምህርት የሚያስተምር ከጌታችንም ከኢየሱስ ክርስቶስ በሆነው ጤናማ ቃልና እግዚአብሔርን ለመምሰል በሚስማማ ትምህርት የማይጠጋ ቢሆን፥ በትዕቢት ተነፍቶአል አንዳችም አያውቅም፥ ነገር ግን ምርመራን በቃልም መዋጋትን እንደ በሽተኛ ይናፍቃል፤ ከእነዚህም ቅንዓትና ክርክር ስድብም ክፉ አሳብም እርስ በርስ መናደድም ይወጣሉ፥ አእምሮአቸውም በጠፋባቸው እውነትንም በተቀሙ፥ እግዚአብሔርን መምሰል ማትረፊያ የሚሆን በመሰላቸው ሰዎች ይገኛሉ። እንደነዚህ ካሉት ራቅ።” /1 ጢሞ.6፥3-5/ እንዳለ፡፡

ሐ. ሰብአዊ ክብርና የዕድሜ፣ የቅደም ተከተል ትስስርና  ክብር እንዲጠፋ የሚሠሩ ለሚለው ሌላ ብዙ ከማለት ይልቅ ቅዱስ ጳውሎስ በመልእክቱ ”ሰዎች ራሳቸውን የሚወዱ ይሆናሉና፥ ገንዘብን የሚወዱ፥ ትምክህተኞች፥ ትዕቢተኞች፥ ተሳዳቢዎች፥ ለወላጆቻቸው የማይታዘዙ፥ የማያመሰግኑ፥ ቅድስና የሌላቸው፥ ፍቅር የሌላቸው፥ ዕርቅን የማይሰሙ፥ ሐሜተኞች፥ ራሳቸውን የማይገዙ፥ ጨካኞች፥ መልካም የሆነውን የማይወዱ፥  ከዳተኞች፥ ችኩሎች፥ በትዕቢት የተነፉ” በማለት የዘረዘረው ለርእሰ ጉዳዩ ተስማሚና በቂ ነው፡፡/1ጢሞ.3፥1-3/

ባጠቃላይም የምጽአት ምልክቶች የሚያሳዩት ሁኔታዎች ከመንፈሳዊው እስከ ዓለማዊው፣ ከተማረው እስከ መሀይሙ፣ ከትልቅ እስከ ትንሽ፣ ያላገባው፣ ያገባው፣ መነኩሴው ሳይቀር ሁሉም ሁሉም ባንድ ላይ ከቅድስና ርቀት፣ ከጥፋት ርኩሰት፣ ከመከራ ሕይወት፣ ተቋደሽ መሆናቸውን ነው የሚያሳየው፡፡ ነገር ግን ቅዱሳት መጻሕፍት ተባብረው እንደመሰከሩልን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ድንገት ይመጣል አይዘገይም፡፡ ቅዱስ ዳዊት ”ከክብሩ ውበት ከጽዮን እግዚአብሔር ግልጥ ሆኖ ይመጣል።  አምላካችን ይመጣል ዝምም አይልም፤ እሳት በፊቱ ይቃጠላል፥ በዙሪያውም ብዙ ዐውሎ አለ።” /መዝ.49፥2-3/ ብሎ እንደተናገረው፡፡ ከላይ እንደተዘረዘረው የሰው ልጆች ሁለ ጊዜ ከመንፈሳውያን እስከ ዓለማውያን ድረስ በተጠመዱበት የዓለማዊ ሥራ እንደ ተወጠሩ ነው ያሉት፡፡ ከዚህም በኋላ የበለጠ በሥጋ ሥራ እየተወጠሩ ይሄዳሉ እንጂ መንፈሳዊ ወደ ሆነው የተጋድሎ ሕይወት የሚያዘነብል ይኖራል ለማለት ያስቸግራል፡፡ እንዲያውም በዐመጽ እየበረታ እስከ መቅደስ ድፍረቱን ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ይገልጸዋል፤”ማንም በማናቸውም መንገድ አያስታችሁ፤ ክህደቱ አስቀድሞ ሳይመጣና የዓመፅ ሰው እርሱም የጥፋት ልጅ ሳይገለጥ፥ አይደርስምና። እኔ እግዚአብሔር ነኝ ብሎ አዋጅ እየነገረ በእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ እስኪቀመጥ ድረስ፥ አምላክ ከተባለው ሁሉ፥ ሰዎችም ከሚያመልኩት ሁሉ በላይ ራሱን ከፍ ከፍ የሚያደርገው ተቃዋሚ እርሱ ነው።” /2ተሰ.2፥3-4/ ይለናል፡፡ ነገር ግን ክርስቲያኖች ነን የምንል ሁሉ የጥፋት ትንቢቱ እኛ ላይ እንዳይፈጸም አሁኑኑ ሳናመነታ ንስሐ መግባትና በትንቢት ከተገለጡት ርኩሰቶች ጨክነን መራቅ ይገባናል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር አሜን፡፡

ተዘጋጅታችሁ ኑሩ ማቴ 24፤44


አትምኢሜይል
መጋቢት 4 ቀን 2007 ዓ.ም.
በዲ/ን ተመስገን ዘገየ
ይህ ቃል ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በደብረ ዘይት ለደቀመዛሙርቱ ስለ ዳግመኛ ምጽአቱና ስለ ዓለም ፍጻሜ ምልክቶች ሲጠይቁት የተናገረው ኃይለ ቃል ነው፡፡ “ወእንዘ ይነብር እግዚእነ ውስተ ደብረ ዘይት ቀርቡ ኀቤሁ አርዳኢሁ፣ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በደብረ ዘይት ተቀምጦ ሳለ ደቀ መዛሙርቱ ለብቻቸው ወደ እሱ ቀረቡና እንዲህ አሉት፤ ንግረነ ማእዜ ይከውን ዝንቱ ወምንትኑ ተአምሪሁ ለምጽአትከ፣ ንገረን ይህ መቼ ይሆናል? የዓለም ፍጻሜ ምልክቱስ ምንድን ነው?” አሉት፡፡


ደብረ ዘይት ከኢየሩሳሌም በስተምሥራቅ የቄድሮንን ሸለቆ ተሻግሮ የሚገኝ ታላቅ ተራራ ነው፡፡ 800 ሜትር ያህል ከባሕር ጠለል በላይ ከፍታ አለው፡፡ ቤተፋጌና ቢታንያም ከግርጌው የሚገኙ መንደሮች ናቸው፡፡ ደብረ ዘይት ስያሜውም የተሰጠው በላዩ ከሚበቅሉት (ተራራውን ከሸፈኑት) የወይራ ዛፎች የተነሳ ነው፡፡ ደብረ ዘይት ማለት የወይራ ዛፍ የመላበት (በብዛት የሚገኝበት) ተራራ ማለት ነውና፡፡
የደብረ ዘይት ተራራ ብዙ ታሪካዊ ክስተቶችን ያስተናገደ ተራራ ነው፡፡ በብሉይ ኪዳን ዘመንም ዳዊት ከአቤሴሎም በሸሸ ጊዜ ወደ ደብረ ዘይት ዐቀበት እንደወጣ በ2ኛ. ሳሙ. 15፤30 “ዳዊትም ወደ ደብረ ዘይት ዐቀበት ወጣ” ይላል፡፡ ይህ ተራራ በሕዝቅኤል ትንቢት ስብሐተ እግዚአብሔር እንደሚያርፍበት ተነግሮአል፡፡ የእግዚአብሔር ክብርም ከከተማይቱ መካከል ተነሥቶ በከተማይቱ ምሥራቅ በኩል በአለው ተራራ ላይ ቆመ፡፡ ት.ሕ11.23
ዘሩባቤል ከሠራው ቤተ መቅደስ ዐደባባይ ደብረ ዘይት 75 ሜትር ገደማ ከፍ ብሎ ይገኛል፡፡ ቤተ ፋጌና ቢታንያም የሚበሉት ታሪካውያን ቦታዎች ከደብረ ዘይት ግርጌ ይገኛሉ፡፡ 
ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሆሳዕና ዕለት ከደብረ ዘይት ወደ ኢየሩሳሌም እንደገባ በማርቆስ ወንጌል ምዕራፍ 11.1 ላይ “ወአልጺቆሙ ኢየሩሳሌም ኀበ ቤተ ፋጌ ወቢታንያ በኀበ በደብረ ዘይት ፈነወ ክልኤተ እምአርዳኢሁ ፤ወደ ኢየሩሳሌም ከደብረ ዘይት አጠገብ ወደ አሉት ወደ ቤተ ፋጌና ወደ ቢታንያ በቀረቡ ጊዜ ከደቀ መዘሙርቱ ሁለቱን ላከ” ይላል፡፡ አይሁድም ጌታን የያዙት በደብረ ዘይት ተራራ ግርጌ በምትገኘው ጌቴሴማኒ ነው፡፡
አንቢቦሙ ወሰቢሖሙ ወጽኡ ወሖሩ ውስተ ደብረ ዘይት ወእምዝ ይቤሎሙ እግዚእ ኢየሱስ ኵልክሙ ትክሕዱኒ በዛቲ ሌሊት፣ መዝሙርም ከዘመሩ በኋላ ወደ ደብረ ዘይት ወጡ በዚያን ጊዜ ኢየሱስ በዚች ሌሊት ሁላችሁ በእኔ ትሰናከላላችሁ” አላቸው፡፡ ማቴ. 26.30
ጌታችንም ሲያስተምር ውሎ ማታ ሔዶ የሚያድረው በደብረ ዘይት ተራራ ውስጥ ባለችው ኤሌዎን ዋሻ ውስጥ ነበር፡፡ በዕለተ ሆሳዕናም ከኢየሩሳሌም ሲወጡ የገባውም ወደ ደብረ ዘይት ነው፡፡ ማር 11.1 በዚህ ዓለም የፈጸመውን አገልግሎት ካጠናቀቀ በኋላ ወደ ሰማይ ያረገውም በደብረ ዘይት ተራራ ነው፡፡ ወደፊትም ዓለምን ለማሳለፍ ይመጣል ተብሎ የተነገረው ትንቢት ላይ መገለጫው ደብረ ዘይት እንደሆነች ተገልጿል፡፡ እነሆ እግዚአብሔር ቀን ይመጣል ብዝበዛሽንም በውስጥ ይከፍላሉ፡፡ አሕዛብም ሁሉ ኢየሩሳሌምን ይወጉአት ዘንድ እሰበስባለሁ ከተማይቱም ትያዛለች ት. ዘካርያስ 14.1
ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነገረ ምጽአቱ (ዳግም ምጽአቱ በደብረ ዘይት ተራራ) ላይ በሰፊው አስተምሯል፡፡ በቤተ መቅደስ ትይዩ በደብረ ዘይት ተቀምጦ ሳለ ጴጥሮስና ያዕቆብ ዮሐንስና እንድርያስም ለብቻ ጠየቁት፡፡ እንዲህም አሉት ንገረን ይህ መቼ ይሆናል (ማር 13.3፣ማቴ 24.1-51) ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አቡነ ዘበሰማያት የሚለውን ጸሎት ያስተማረውም በደብረ ዘይት ተራራ ነው፡፡ ከ62 ሀገሮች በላይ ልሳን(ቋንቋ) በሞዛይክ ተጽፎ ይገኛል፡፡ ከእነዚህም መካከል አንዱ ግእዝ ነው፡፡ በመሆኑም 5ኛው የዐቢይ ጾም ሰንበት የክርስቶስ ነገረ ምጽአት የሚዘመርበት፤ የሚሰበክበት ዕለት ስለሆነ በደብረ ዘይት ተሰይሟል፡፡ ሰያሚውም ሊቁ ቅዱስ ያሬድ ነው፡፡ በዕለቱ የሚነበበው የወንጌል ክፍልም ማቴ 24.1-36 ነው፡፡
 ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከመቅደስ ወጥቶ ወደ ደብረ ዘይት በሄደበት ሰዓት ደቀ መዛሙርቱ አጠገቡ ቀርበው ዘሩባቤል ያሳነፀውን የመቅደስ ግንቦች እያሳዩት ቀረቡ፡፡ “አማን እብለክሙ ኢይትኀደግ ዝየ እብን ዲበ እብን ዘኢይትነሠት፣ እውነት እላችኋለሁ ድንጋይ በድንጋይ ላይ ሳይፈርስ በዚህ አይቀርም” አላቸው፡፡ ከዚህ በኋላ የኢየሩሳሌምን መፍረስና ዳግም መምጣትን አስፍቶ አምልቶ ከነምልክቱ ለደቀ መዛሙርቱ አስተማራቸው፡፡ ለአሕዛብም ምስክር እንዲሆንባቸው በሰማያዊ ንጉሥ ፊት ያለ ምክንያት ለፍርድ እንዲቆሙ የእግዚአብሔር ሕገ መንግሥት ወንጌል በአሕዛብ ቤት ሳይቀር ለሁሉም ይሰበካል፡፡ በዚህ ጊዜ መጨረሻው እየቀረበ ይመጣል” (ማቴ.24.14) በማለት በስፋት አስተምሮአቸዋል፡፡ እምበለስ አእምሩ አምሳሊሁ፣ ነገሩን በበለስ እወቁ፡፡ የበለስ ቅጠል መለምለም ማለት የጠፋችው የእስራኤል መንግሥት መመሥረት የመድኀኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ መምጣት 11ኛ ምልክት ነው፡፡ ማቴ 24.32
ከዚህ በኋላ በማናውቀው ጊዜና ሰዓት እግዚአብሔር ወልድ በግርማ መለኮት በክበበ ትስብእት (በአካላዊ መጠን) ከቅዱሳን መላእክት ጋር በደመና ይመጣል፡፡ “ናሁ ይመጽእ በደመና ሰማይ ወትሬእዮ ኩላ ዐይን ወእልክቱሂ እለ ወግእዎ ይበክዩ በእንቲአሁ ኩሎሙ አሕዛበ ምድር እወ አማን፣ እነሆ በሰማይ ደመና ይመጣል ዐይን ሁሉ ታየዋለች የወጉትም ሁሉ ያለቅሳሉ የምድር ወገኖች ሁሉ የኀዘን ድምፅ ያሰማሉ፡፡ አሕዛብ ሁሉ ስለ እርሱ ያለቅሳሉ፡፡” (ራእይ 1.7)
ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ዳግም ምጽአቱ በተናገረበት አንቀጹ ቅዱሳን ሐዋርያትን ካስጠነቀቀበት ዐቢይ ኃይለ ቃል መካከል ስለ ሐሰተኞች መምህራን መምጣት ነበር፡፡ “እስመ ብዙኃን ይመጽኡ በስምየ እንዘ ይብሉ አነ ውእቱ ክርስቶስ ወያስሕትዎሙ ለብዙኃን” የሚያስታችሁ እንዳይኖር ተጠንቀቁ፡፡ ብዙዎች እኔ ክርስቶስ ነኝ እያሉ በስሜ ይመጣሉና ብዙዎችንም ያስታሉ በማለት (በማቴ 24.5) አስጠንቅቋል፡፡ ክርስቲያኖች አሁንም በ21ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የበግ ለምድ ለብሰው ከሚመጡባችሁ በውስጣቸው ግን ነጣቂ ተኩላዎች ከሆኑት ከሐሰተኞች መምህራን ተጠበቁ፡፡ ከእሾህ ወይን ከኩርንችትስ በለስ ይለቀማል? በማለት እውነተኛ የወንጌል መምህራንን በመምሰል ብዙዎችን እንደሚያሳስቱ ጌታችን አስተምሮናል (ማቴ 7.15 ) ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም በሮሜ 16.17 “ነገር ግን ወንድሞቼ ሆይ! እናንተ የተማራችሁትን ትምህርት የሚቃወሙትን መለያየትና ማሰናከያ የሚያደርጉትን ሰዎች እንድትመለከቱ እለምንቹሃለሁ፡፡ ከእነርሱ ዘንድ ፈቀቅ በሉ እንዲህ ያሉት ለገዛ ሆዳቸው እንጂ ለጌታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ አይገዙምና በመልካምና በሚያቆላምጥ ንግግር ተንኰል የሌለባቸውን ሰዎች ልብ ያታልላሉና” ይላል፡፡
የእስክንድርያው ሊቀ ጳጳስ ቅዱስ ቄርሎስ እንደተናገረ “እኛስ ያለማወላወል የደጋግ አባቶችን ሃይማኖት እንይዛለን” (ሃይማኖተ አበው ) ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ የመጀመሪያውን እምነታችን እስከ መጨረሻው አጽንተን ብንጠብቅ የክርስቶስ ተከፋዮች ሆነናልና፡፡ (ዕብ 3.14) ይላል፡፡ ስለዚህ በጊዜው ያለ ጊዜውም መጽናት ይገባል (2ኛ ጢሞ4.2)
የዓለም መጨረሻውና የኢየሱስ ክርስቶስ መምጫ ምልክቶች በማቴ 24.1 በስፋት ተዘርዝረዋል፡፡

ለመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሁለት ታላላቅ ምጽአቶች እንዳሉት ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ሲያስረዳ “….በዓለም ፍጻሜ ራሱን በመሥዋት ኃጢአት ሊሽር አንድ ጊዜ ተገልጧል… አንድ ጊዜ ከተሰዋ በኋላ ያድናቸውም ዘንድ ለሚጠባበቁት ሁለተኛ ጊዜ ያለ ኃጢአት ይታዩላቸዋል” (ዕብ 9.26-28 ) በማለት ተናግሮአል፡፡

የመጀመሪያው ምጽአቱ ሥጋ በመልበስ ለሰው መሥዋዕት ሁኖ ሊያድን ለካሳ በፍጹም ትህትና የእኛን ውርደት ተቀብሎ በበረት በመወለድ በሥጋ ማርያም መጣ፡፡ በሚሞት በሚሰደድ በሚዳከም ፤በሚበረታ፤ በሚራብ፤ በሚጠማ ፤ በሚዝል በሚወድቅ በሕርየ ሰብእ (የሰው ባሕርይ) እንደ አንድ ኃጥእ ሞት፣ እስኪፈረድበት ድረስ ራሱን ዝቅ አድርጐ መጣ፡፡

ወንጌለ መንግሥቱን ሊሰብክልን ከሞት ወደ ሕይወት ሊያሸጋግረን በሥጋ ማርያም መጣ፡፡ ከአይሁድ ስድብን ታገሠ ኃጥአንን በሽተኞችን ሊያድን በምድር ላይ ተመላለሰ፡፡ ስለ እኛ ተገረፈ፣ ተሰቀለ፣ ሞተ ያውም መራራ ለሆነ የመሰቀል ሞት ታዘዘ፡፡ ሞቶ በሦስተኛው ቀን ተነሳ ወደ ሰማይም በዐርባኛው ቀን አረገ በየማነ አብ ተቀመጠ፡፡ ይህ ነው የመጀመሪያው ምጽአቱ መከራን ለመቀበል እኛን ለማዳንና ለሰው ልጆች ያለውን ፍቅር ለመግለጥ ነው፡፡

ዳግማዊ ምጽአቱ፡- በግርማ መለኮት በክበበ ትስብእት በፍጹም ጌትነት በኃጥአን (የመጀመሪያ ምጽአቱን) ባልተቀበሉት ላይ ሊፈርድ ዐይን ሁሉ እየተመለከተው በገሃድ ይመጣል፡፡ “እግዚአብሔርስ ገሀደ ይመጽእ ወአምላክነሂ ኢያረምም እሳት ይነድድ ቅድሜሁ፣ እግዚአብሔር ግልጥ ሁኖ ይመጣል ዝምም አይልም እሳት በፊቱ ይነዳል (መዝ 50.3)
መጥቶም ዝም አይልም (ኤሌ ለክሙ ጸሐፍት ወፈሪሳውያን መደልዋን፤ ግብዞች ጸሐፍት ፈሪሳውያን ወዮላቸሁ) እያለ ይወቅሳል ወንጌልንም ያስተምራል፡፡ ጻድቃንን “እናንተ የአባቴ ብሩካን ወደ እኔ ኑ ብሎ ይጠራል ኃጥአንንም እናንተ ርጉማን ሐሩ እምኔየ፤ ከእኔ ወግዱ” ብሎ ያሰናብታቸዋል፡፡ በፊቱ እሳት ይነዳል ማለት ጻድቃን የሚድኑበት ሕይወት ኃጥአን የሚጠፉበት መዓት በባሕርዩ አለ ማለት ነው፡፡ ክርስቲያኖች ሆይ! የመድኀኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ሁለተኛ መገለጥ ለእኛስ ለምን ይሆን? ለዘለዓለማዊ ሕይወት ወይስ ለዘለዓለም ሞት?
ጌታችን በደብረ ዘይት ያስተማራቸው ትምህርቶች በመሠረታዊነት በ3 ከፍለን ልናያቸው እንችላለን፡፡
1. ምልክት፡- በዚያ ዘመን እንዲህ ይሆናል እያለ በፍጻሜ ዘመን የሚከሰቱትን ድርጊቶች፡፡
2. ትእዛዝ፡- በዚያ ዘመን ከጥፋት እንድን ዘንድ የሰጠን አምላካዊ ትእዛዝ ነው፡፡ በይሁዳ ያሉ ወደ ተራራዎች ይሽሹ እያለ ፡፡

3. ማስጠንቀቂያ በፍጻሜ ዘመን እንዲህ ሁናችሁ የተገኛችሁ “ወዬላችሁ” እያለ የተናገራቸው ናቸው፡፡ ለዚህም ምሳሌ “ለእርጉዞችና ለሚያጠቡ ወዮላቸው” የሚለው እርጉዝ ማለት የኃጢአት ዐሳብ የጸነሱት ሲሆኑ የሚያጠቡ ያላቸው ኃጢአትን ጸንሰው በንግግር የወለዱትን ነው” 
በይሁዳ ያሉት ወደ ተራሮች ይሽሹ (ማቴ 24.16) በዚህ ቃል መሠረት በይሁዳ በዓለም ያሉ ወደ ተራራ ይሽሹ ተብሏል፡፡ በሃይማኖት ጸንተው ምግባር ትሩፋት እየሠሩ የሚኖሩ ክርስቲያኖች ወደ ተራራ ይሽሹ ነው፡፡ 
ለመሆኑ ተራራ ምንድን ነው?
1. ተራራ የተባለው ረድኤተ እግዚአብሔር ነው፡፡ “ተራሮች በኢየሩሳሌም ዙሪያ እንደሆኑ ከዛሬ ጀምሮ ለዘለዓለም እግዚአብሔር በሕዝቡ ዙሪያ ነው “መዝ. 124.2 ይላል፡፡ በዚህ ቃል የእግዚአብሔር ረድኤት በተራራ ተመስሎ ቀርቧል፡፡ ምክንያቱም ተራራ እንደሚከልል እግዚአብሔርም በረድኤቱ ይከልላልና፡፡ ስለዚህ ወደ ተራራ ሽሹ ማለት ረድኤተ እግዚአብሔርን ተስፋ አድርጉ ማለት ነው፡፡

2. ተራራ የተባለችው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ናት፡፡
3. ድንግል ማርያም የጽዮን ተራራ ትባላለች “አንሰ ተሠየምኩ ንጉሠ በላዕሌሆሙ፣ በጽዮን በደብረ መቅደሱ ፤እኔ ግን በእነርሱ ላይ ንጉሥ ሆኜ ተሾምሁ በተቀደሰው ተራራ ላይ በጽዮን ላይ ” መዝ.2.6 ስለዚህ ትውልድ ድንግል ማርያምን ዓምባ መጠጊያ ያደርግ ማለት ነው፡፡
4. ተራራ የተባሉት ቅዱሳን አባቶቻችን ናቸው፡፡ መዝ.86.1 መሠረታቲሃ ውስተ አድባር ቅዱሳን ፤መሠረቶቿ በቅዱሱ ተራሮች ናቸው” ስለዚህ ወደ ተራራ ሽሹ ማለት ወደ ቅዱሳን አባቶቻችን ቅረቡ በአማላጅነት ሥልጣናቸው አምናችሁ ተማጸኗቸው ሲል ነው፡፡

በሰገነት ያለውም በቤቱ ያለውን ሊወስድ አይውረድ ይላል (ማቴ 24.17) ሰገነት ከፍ ያለ ቦታ ነው፡፡ በዚህ ቃል በሠገነት የተመሠለ በምግባር በሃይማኖት የበረታ የወጣትነት ዘመን አልፎ ከማዕከላዊነት የደረሰ ማለት ሲሆን፤ በዝቅታ የተመሠለ ደግሞ በኃጢአት ምክንያት የሚመጣ የነፍስ ተዋርዶ ነው፡፡ 
ዴማስና ይሁዳ በሰገነት ነበሩ በኋላ ግን በዝቅታ ሥፍራ ተገኙ፡፡ መዋል በማይገባቸው ቦታ ውለው ተገኙ፡፡ በክርስትና ከፍ ከፍ ብለው በመንፈሳዊነት መጽናት አቃታቸው፡፡ እኛስ ከየትኛው ስፍራ እንሆን?
በእርሻም ያለ ልብሱን ይወስድ ዘንድ ወደ ኋላ አይመለስ (ማቴ24.18) በእርሻ የተመሰለ የመነነ ወይም በምንኩስና ሕይወት ያለ ማለት ነው፡፡ በእርሻ ያለ አይመለስ ማለት በምነና በምንኩስና ያለ ይህንን ሕይወት የጀመረ አይመለስ፡፡ ስለዚህ ስደታችሁ በክረምት ወይም በሰንበት እንዳይሆን ተግታችሁ ጸልዩ አለ (ማቴ 24 .20) ክረምት የፍሬ የአጨዳ ሳይሆን የሥራ የመዝሪያ ወቅት ነው፡፡ ሰንበትም የዕረፍት ቀን ናት፤ በሠንበት ሥጋዊ ሥራ አይሠራም፡፡ አንድም በክረምት ቅጠል ካልሆነ ፍሬ አይገኝም እናንተም ሃይማኖት ይዛችሁ ምግባር ከሌላችሁ ዋጋ የላችሁም ማለቱ ነው፡፡
ሽሽት የተባለ ዕለተ ምጽአት ሲሆን በሽሽት የተመሰለው ሞት ድንገት እንደሚመጣ ዕለተ ምጽአትም በድንገት ስለሚሆን ነው፡፡ ትርጉሙ ንስሓችሁን ሳትጨርሱ የንስሐ ፍሬ ሳታፈሩ በድንገት ዕለተ ምጽአት እንዳይደርስባችሁ ጸልዩ የሚል ይሆናል፡፡ ክርስቲያን በዚህ ዓለም ሲኖር “ድልዋኒክሙንበሩ፤ ተዘጋጅታችሁ ኑሩ” ማቴ 24:24 በተባለው አማናዊ ቃል መሠረት ራሱን በንስሓ አዘጋጅቶ የጌታውን መምጣት ሊጠብቅ ይገባዋል፡፡ 

2015 ማርች 11, ረቡዕ

እረፍቱ ለአቡነ ገ/መንፈስ ቅዱስ


Written By Hulubante Abebe 

 የእግዚአብሔር ዓይኖች ወደ ጻድቃን ጆሮቹም ወደ ጩኸታቸው ናቸውና። መታሰቢያቸውን ከምድር ያጠፋ ዘንድ የእግዚአብሔር ፊት ክፉን በሚያደርጉ ላይ ነው። ጻድቃን ጮኹ፥ እግዚአብሔርም ሰማቸው ከመከራቸውም ሁሉ አዳናቸው።” 
                                 
 መዝ ፴፫፡፲፭-፲፯ 
መጋቢት 5 በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስትያን አማኞች ዘንድ የፃድቁ አቡነ ገ/መንፈስ ቅዱስ ዓመታዊ ክብረ በዓል በደመቀ ሁኔታ ተከብሮ ይውላል 
በዚህ እለት እምናከብረው የእረፍት መታሰቢያቸውን ሲሆን ከገድላቸውም እንዲህ ተፅፎ እናገኘዋለን 
ፃድቁ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ የተወለዱት ግብፅ ንሂሳ በምትባል ቦታ ከአባታቸው ስምዖን ከእናታው አቅሌስያ ነው። በአጠቃላይ የኖሩበት ዕድሜ 562 አመት ሲሆን 300 ዓመቱን በግብጽ 262 ቱን በኢትዮጵያ 100 ዓመት በዝቋላ በተጋድሎ ያሳለፉ ታላቅ አባት ናቸውኢትዮጵም የአስራት ሐገራቸው ሆና በቃልኪዳን ተሰጣቸዋለች  እናታቸው ሳትታቀፋቸው ወተት ሳይጠጡ በመንፈስ ቅዱስ አድገው በ፫ ዓመታቸው ቅዱስ ገብርኤል መጥቶ እስከ ሰባቱ ሰማያት አውጥቶ ወደ እግዚአብሔር አቀረበው፤ ባረከውም፤ ድንግል ማርያም ጻድቃን ሰማዕታት ወዳሉበት ተወስዶ ተባርኮ በጌታችን ቃል ተቀብሎ ወደ አባ ዘመደ ብርሃን ወዳሉበት አውርዶ በዚያም አድጎ መንፈሳዊ ሥራን በአጭር ጊዜ በማጠናቀቅ ተጋድሎውን ጀምሯል። በበረሃ ሲኖሩ 60 አንበሳና ነብር የተሰጣቸው ሲሆን አንበሳ እና ነምሮቹም የሚበሉትም የቅዱሱን እግር ያረፈበትን ቦታ በመላስ ነው። የአባታችን ገድል እንደሚያስረዳው እንደ ሰው ልብስ ለብሰው ሳይሆን ልብሳቸው በጸጋ የተሰጣቸው ጠጉር ነበር እሱም ልክ እንደ ልብስ ያገለግላቸው ነበር
 ከሚያስገርመው ገድላቸው ውስጥ አባታችንን ለመጠየቅ የመጡት አባ ሳሙኤል ዘዋልድባ ከሁለት ጓደኞቻቸው ጋር መጥተው እንግዶቹን አንበሶቹ በልተው አባታችን አቡነ ገ/መንፈስ ቅዱስም በመንፈስ መምጣታቸውን አውቆ ሲነግሯቸው ለምን ያልተፈቀደላችሁን በላችሁ ብለው የበሉትን አንበሶች የበላችሁትን አንድም ሳታስቀሩ ትፉ ብሏቸው ወደ እግዚአብሔር ጸልየው በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ተነሱ ባሉ ጊዜ የተበሉት ነፍስ ዘርተው እነ አባ ሳሙኤል ዘዋልድባም በሰላም ወደ ባእታቸው በአባታችን በአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ጸሎት በሠላም ገብተዋል።
መጋቢት 5 በገድለ አቡነ ገ/መንፈስ ቅዱስ
ዕለቱ ቅዳሜ ለእሁድ አጥቢያ ሰዓቱ ከሌሊቱ ስድስት ሰዓት ሆኗል፤ አሁንም ህማሙን እየታገለ እያላበው በድካም ለፍጥረቱ ሁሉ ይለምናል፤ “አቤቱ ህዝብህን አድን ርስትህን ኢትዮጰያንም ባርክ” ይላል። ህመም የጀመረው መጋቢት 3 ዓርብ ቀን ነው፤መታመሙን የሰሙ እንደርሱ ቅዱሳን የሆኑት ዘርአ ቡሩክ፤ ፍሬ ቅዱስ፤ያዕቆብ፤ብንያምና ዮሴፍ እንዲሁም በወቅቱ የኢትዮጰያ ንጉስ የነበረው እንድርያስ ሊጠይቁት ተሰብስበዋል ወደ አጠገቡ መድረስ ግን አልተቻላቸውም አባታችን ገብረመንፈስ ቅዱስ የሚጋርደው እንጨት ዛፍ በሌለበት በርሃ እንደ አንበሳ ተኝቶ አዩት በላዩ ያረፈው የእግዚያብሔር ጸጋ ከፊቱ የሚወጣው ብርሃን ቀይ መልኩ ረዥም የራስ ጠጉሩ እንደ ነጭ ሐር የሚሆን ጽሕሙ አስደነቃቸው። ከሌሊቱ ሰባት ሰዓት ሲሆን ከሰማይ ታላቅ ነጎድጓድ ድምጽ ተሰማ ጌታችን መላአክትን አስከትሎ ወደ አባታችን ወረደ፤ ከሰማይ ወደ ምድር ህብሩ አምሳያው ልዩ ልዩ የሆነ እንደ ጸሐይና እንደ ጨረቃ የሚያበራ እንደ ወንጪፍ ድንጋይ ይወረወር ነበር ከዚያ የነበሩ ሁሉ ፈሩ ወደ ኃላም ሸሹ ምድር ራደች ተራሮች ኮረብቶች ተናወጡ ብርቱ ጩኸት
ንውጽውጽታ ሆነ። “ወዳጄ ገብረመንፈስ ቅዱስ ሰላም ላንተ ይሁን” እነሆ የማይታበል ቃል ኪዳን እገባልኃለው ስምህን የጠራ መታሰቢያህን ያደረገውን፤ እጣን ቋጥሮ ግብር ሰፍሮ መባ ይዞ ቤትህ የመጣውን እምርልኃለው አንተ ከገባህበት ገነት መንግስተ ሰማያት አገባዋለሁ አለው፤ አባታችንም “አቤቱ ጌታ ሆይ የኢትዮጰያን ህዝብ ማርልኝ” አለው፤ እነሆ ምሬልኃለው አስራት በኩራት አድርጌም ሰጥቼሃለው፤ ከመጋቢት አምስት ቀን ጀምሮ ዝክርህን ያድርጉ በአማላጅነትህም ይማጸኑ አለው። ከዚህ በኃላ ሰባቱ ሊቃነ መላእክት የአባታችንን ነፍስ ሊቀበሉ ወረዱ በታላቅ ምስጋናም ወደ ሰማይ አሳረጉት ስጋውንም ይዘውት ሄዱ የት እንደተቀበረ ግን እስካሁን አይታወቅም አንዳንዱ በእየሩሳሌም ነው ይላሉ፤ ሌላው በምድረ ከብድ ነው ይላል ግን እስካሁን ልክ እንደ ሊቀ ነብያት ሙሴ ስጋ የት እንደተቀበረ አይታወቅም። ገድሉ ትሩፋቱ ከሰማይ ከዋክብት ከምድር አሸዋ ይበዛል ኢትዮጰያን አብዝቶ ይወዳታል፤ ምድራዊ ምግብ አልተመገበም የእናቱን ጡት እንኳን አልጠባም፤ ልብስ፤ መጠለያ አልፈለገም፤ የክረምት ቁር የበጋ ሐሩር እየተፈራረቀበት በተጋድሎ 562 ዓመት ኖረ፤ በዛሬዋ ቀን ሩጫውን ጨረሰ። ለእግዚያብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም ከአባታችን በረከት ያሳትፈን።
የአባቶችን የቅዱሳንን ታሪክ እንድናውቅ ከሚፈለግባቸው ምክንያቶች ውስጥ አንዱ ከነርሱ ገድል ተምረን እኛም ወደአምላክ መንገድ እንድንቀርብብበት ነውና አምላከ ገ/መንፈስ ቅዱስ መንገዱን ያብራልን ። ገድሉንም ሰሚወች ብቻ ሳንሆን እምንማርበት ያድርግልን ።
መጋቢት 5 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
1.አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ጻድቅ /አባ ገብረ ሕይወት/                                     2.ቅዱስ አባ ሰረባሞን /በምድረ ግብፅ ምንኩስናን ካስፋፉ ታላላቅ ቅዱሳን አንዱ/                 3.አባ ግርማኖስ ጻድቅ /ሶርያዊ/                                                         4.ቅድስት አውዶክስያ ሰማዕት /ከከፋ የኃጢአት ሕይወት ተመልሳ ለቅድስና የበቃች እናት/ 
5.ቅዱሳን ስምዖንና ሚስቱ አቅሌስያ /የአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ወላጆች/

                       ወስብሐት ለእግዚአብሔር

                                   በአውሮጳ   የካህናት አንድነት ማኅበር ሊቋቋም መሆኑ ታወቀ በ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከመላዋ አውሮጳ   የተውጣጡ ካህናት፡” የ...