2015 ጁን 12, ዓርብ

የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ለወንጌል የሰጠቺው ትኩረት፡- በ14ኛው መክዘ ወንጌል መነሻነት ሲዳሰስ


የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ወንጌል ወደ ግእዝ ቋንቋ መተርጎም የጀመረው በአባ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን ዘመን፣ የተጠናቀቀው ደግሞ በተሰዓቱ ቅዱሳን መሆኑን ይገልጣሉ[1]፡፡ እስካሁን በተደረጉት ጥናቶች የተገኘው ጥንታዊው የብራና የግእዝ መጽሐፍም የአባ ገሪማ ወንጌል ነው[2]፡፡ ይኼ ከ4-7 መክዘ ባለው ዘመን ውስጥ የተጻፈውና በአድዋ እንዳ አባ አባ ገሪማ ገዳም የሚገኘው ወንጌል ቤተ ክርስቲያኒቱ ወንጌልን ለመተርጎምና ለማስተማር የሰጠቺውን ጥንታዊ ትኩረት አመልካች ነው፡፡ በ6ኛው መከዘ የተነሣው ቅዱስ ያሬድ የደረሰው ድጓ ብሉይ ኪዳንን ከሐዲስ ኪዳን አስተባብሮ የያዘና ጥንታውያን የክርስቲያን ሊቃውንት (ቄርሎስ፣ አትናቴዎስ፣ ባስልዮስ፣ ዮሐንስ አፈወርቅ፣ ጎርጎርዮስ ዘእንዚናንዙና ዘኑሲስ) የተረጎሙትን ትርጓሜ በውስጡ ይዞ መገኘቱ መጽሐፍ ቅዱሱ ብቻ ሳይሆን ትርጓሜዎቹም በአኩስም የክርስትና ዘመን በሊቃውንቱ እና በሕዝቡ ዘንድ የታወቁና የተሰበኩ እንደነበር ያሳየናል፡፡ 
የእንዳ አባ ገሪማ ወንጌል

ክርስትና ብሔራዊ ሃይማኖት እንዲሆን ያደረጉትና የመጀመሪያዎቹ ኢትዮጵያውያን ክርስቲያን ነገሥታት የሆኑት ኢዛናና ሳይዛና ክርስትና ሲነሡ ‹አብርሃ እና አጽብሐ› ተብለው መጠራታቸው ወንጌልን ኢትዮጵያውያን የተቀበሉት ‹ብርሃናችን፣ ንጋታችን› ነው ብለው መሆኑን ይጠቁማል፡፡ የመጀመሪያውን ጳጳስ ፍሬምናጦስን የሰየሙበት ‹ከሣቴ ብርሃን› የሚለው ስያሜም የወንጌል መሰበክ እንደ ብርሃን መገለጥ ተደርጎ መወሰዱን ያመለክታል፡፡ ‹እኔ የዓለም ብርሃን ነኝ[3]› የሚለውን ቃል ያላወቀ ሕዝብ መቼም  ይህንን ስያሜ አይሰጥም፡፡ ይኼ ስያሜ ከወንጌል ሰባኪነት ጋር የተያያዘ በመሆኑ በዲማና አካባቢዋ ወንጌልን በብርቱ የሰበከው በኪሞስ ‹ተከሥተ ብርሃን› ›ብርሃን ተገለጠ› ተብሎ መጠራቱን ገድለ አቡነ ፊልጶስ ይነግረናል[4]፡፡
  የኢትዮጵያ ነገሥታት በሳንቲሞቻቸው ላይ የመስቀልን ምልክት ካደረጉ የመጀመሪያዎቹ የዓለም ነገሥታት መካከል ናቸው[5]፡፡ በአኩስም በተገኙት ሳንቲሞች በሳንቲሞቻቸው ላይ የመስቀልን ምልክት ያደረጉ ከ17 በላይ የአኩስም ነገሥታት ተገኝተዋል[6]፡፡ ይኼም ክርስትና በኢትዮጵያውያን ውስጥ ቦታ አግኝቶ የዕለት ተዕለት ሕይወት የሆነው ተሰብኮ ሳይውል ሳያድር መሆኑን አመልካች ነው፡፡ እነዚህ ነገሥታት በሳንቲሞቻቸው ላይ ከመስቀል ምልክት በተጨማሪ ስመ እግዚአብሔርን ጽፈዋል፡፡ 
                                                                   የአኩስም ዘመን ሳንቲሞች [7]
የወንጌሉን ሐሳቦች የሚገልጡ ‹ሰላምና ደስታ ለሕዝቡ ይሁን፣ ምሕረትና ሰላም፣ በእግዚአብሔር ጸጋ፣ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን፣ በክርስቶስ ድል የሚያደርግ› የሚሉትን ቃላትም አስጽፈውም ተገኝተዋል[8]፡፡ ምሕረት፣ ሰላም፣ ምስጋና፣ ጸጋ የሚሉት በአብዛኛው በቅዱስ ጳውሎስ መልእክታት ላይ የምናገኛቸው የሐዲስ ኪዳን ትምህርቶች በሳንቲሞቹ ላይ መጻፋቸው የወንጌሉን ስብከትና የስብከቱን ውጤት ያሳያል፡፡ ድል አድራጊነትን ለክርስቶስ መስጠታቸውም ኢየሱስ ክርስቶስን ማወቅና በሕይወት ውስጥ ቦታ መስጠት ከክርስትና መሰበክ ጀምሮ በሀገሪቱ የነበረ እንጂ የ20ኛው መክዘ ግኝት አለመሆኑን ያሳያል፡፡ 
ኢዛና በሦስት ቋንቋዎች ባስጻፈው የድንጋይ ላይ ጽሑፍ ኢየሱስ ክርስቶስን ‹የሰማይ ጌታ› ብሎ ጠርቶ ድሉ በእርሱ ርዳታ መገኘቱን ይገልጥልናል[9]፡፡ ኢዛና በሌላኛው የድንጋይ ላይ ጽሑፉም ‹በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ› ሲል በሥላሴ ላይ ያለውን እምነት ገልጧል[10]፡፡ ይህም አሚነ ሥላሴ በኢትዮጵያውያን ዘንድ የነበረውን ቦታ ይነግረናል[11]፡፡
በዛግዌ ዘመን ወርቃማ ጊዜ ላይ የምናገኘው ቅዱስ ላሊበላ በላስታ ሮሐ የሰማያዊቱንና ምድራዊቱን ኢየሩሳሌም ምሳሌ ሠርቷል፡፡ ይህም ቅዱስ ጳውሎስ በገላትያ መልእክቱ ኢየሩሳሌም ሰማያዊትና ኢየሩሳሌም ምድራዊት በማለት የከፈለው ትምህርት መሠረት ያደረገ መሆኑን አመላካች ነው[12]፡፡ ከሠራቸው ውቅር አብያተ ክርስቲያናት መካከል ‹ቤተ መድኃኔዓለም›፣ ‹ቤተ ዐማኑኤል›፣ ‹ቤተ መስቀል› የወንጌሉ ትምህርት ከሰዎች ኑሮ አልፎ ሥነ ሕንጻ ሲሆን ያሳዩናል፡፡ አንድን ነገር ዐውቆ፣ ያወቀውን አምኖ፣ ያመነውም ተረድቶ፣ በዓይነ ኅሊናም ስሎ ወደ ኪነ ሕንጻ ለመለወጥ ለነገሩ በአእምሮ ውስጥ ጥልቅ ቦታ መስጠትን ይጠይቃል፡፡ የገላትያ ሰዎች ይህንን ሥዕል አጥፍተው ነው በቅዱስ ጳውሎስ የተወቀሱት[13]፡፡ የልደት በዓል በላሊበላ ከጥንት ጀምሮ ያለውን ቦታ ስናይ እነዚህን ሰዎች ክርስቶስን አያውቁትም ብሎ ከመናገር በፊት ዘጠና ዘጠኝ ጊዜ ማሰብ እንደሚገባ ሕያው ምስክር ነው፡፡ 
ኢትዮጵያዊው ሐዋርያ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ከ700 ዓመታት በፊት በደቡብ ኢትዮጵያ ባደረጉት ስብከት ስመ ክርስቶስን ጠርተው ያስተምሩ፣ ሕዝቡም ክርስቶስን አንዲያውቅ ይሰብኩ እንደነበር የሚያስረዳን በገድላቸው ላይ በተጻፈው የደቡብ ስብከታቸው ውስጥ ከ52 ጊዜ በላይ ስመ ክርስቶስን ጠርተው ሲያስተምሩ ማንበባችን ብቻ ሳይሆን በዳሞት መጀመሪያ የተከሉት ቤተ ክርስቲያን በኢየሱስ ስም መሆኑንም ስናይ ነው፡፡ ወደ ሰሜን ለበለጠ ትምህርትና ተጋድሎ በሄዱ ጊዜ ለዐሥር ዓመት ያገለገሉበት ገዳም ሐይቅን የመሠረቱት አባት ‹ኢየሱስ ሞዓ› ተብለው መጠራታቸው የሚነግረንም ነገር አለ፡፡ ከሐይቅ በፊት ቢያንስ 200 ዓመት ቀድሞ የተሠራው ጥንታዊው የአካባቢው ቤተ ክርስቲያንም ‹እግዚአብሔር አብ› መባሉ የምሥጢረ ሥላሴው ትምህርት ሳይቋረጥ የቀጠለ መሆኑን ያሳያል፡፡  
የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ለመጀመሪያ ጊዜ የተጠቀመቺባቸው ሁለቱ ቅዳሴያት ‹ቅዳሴ እግዚእ› እና ‹ቅዳሴ ሐዋርያት› ናቸው[14]፡፡ ይህም ለጌታችን ትምህርትና ለሐዋርያት ስብከት የተሰጠውን ቦታ የሚያሳይ ነው፡፡ ምናልባትም ከውጭ የተተረጎሙት ቅዳሴያት እነዚህ ሁለቱ ብቻ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡
በአኩስም ዘመን ከተተረጎሙት የሃይማኖት መጻሕፍት መካከል አንዱ ነገረ ክርስቶስን የሚተነትነው ‹መጽሐፈ ቄርሎስ› መሆኑ፣ ኢትዮጵያውያን ከውጭ ተርጉመው ከተጠቀሙባቸው የሊቃውንት ጸሎቶች መካከል አንዱ የሆነው የአባ ኤፍሬም ውዳሴ ማርያም ከጠቅላላው ይዘት 63 በመቶው ኢየሱስ ክርስቶስን በተመለከተ ቤተ ክርስቲያን የምታምነውን እምነት መያዙ የሚነግረን ብዙ ነገር አለ፡፡
ከአኩስም ዘመን ጀምሮ ነገራተ ሕዝብ የሚመዘገቡት በወርቅ ወንጌል ነው፡፡ ራሱ ወንጌሉም ‹ወንጌል ዘወርቅ› ተብሎ መጠራቱ የወንጌሉን ቦታ ይገልጣል፡፡ በእንዳ አባ ገሪማ ወንጌል[15]፣ በደብረ ሊባኖስ ዘሺምዛና ወንጌል[16]፣ በጉንዳ ጉንዶ ወንጌል፣ በሐይቅ እስጢፋኖስ ወንጌል[17]፣ በክብራን ወንጌልና በደብረ ሊባኖስ ወንጌል የምናገኛቸው መረጃዎችም ይህንን ያስረግጡልናል፡፡
የክብራን ገብርኤል ወንጌል( British, Ms. 481)
ከክርስትና መግባት ጀምሮ ኢትዮጵያውያን የተጠቀሙበት የዘመን መቁጠሪያ አራቱን ዓመታት በአራቱ ወንጌላውያን ስም መጥራቱና የዐቢይ ጾም ስምንቱ እሑዶች ጌታችን በወንጌል ላይ በሠራቸው ሥራዎች መሠረት መሰየማቸው ወንጌልና የወንጌል ትምህርት ከጥንት ጀምሮ በኢትዮጵያ የያዘውን ጽኑ መሠረት አመልካች ነው፡፡ 
እነዚህ ሁሉ ነገሮች  ወንጌል፣ የወንጌል ትምህርትና የወንጌል መሠረት የሆነው ክርስቶስ በኢትዮጵያውያን ጠቅላላ ሕይወት ውስጥ ከሥጋና ደም ጋር የተዋሐዱ እንጂ እንደ እንግዳ ደራሽ እንደ ውኃ ፈሳሽ አለመሆናቸውን ያጠይቁልናል፡፡
ኢትዮጵያውያን ወንጌሉን በሚገባ አስጽፈውታል፣ ተርጉመውታል፣ ሥለውታል፣ አዚመውታል፣ ኪነ ሕንጻ አድርገውታል፣ ተጠርተውበታል፣ ከዚህም አልፈው መሥዋዕት ሆነውለታል፡፡ ወንጌል በኢትዮጵያ ውስጥ የነበረውን የዕውቀትና የክብር ቦታ ከሚያሳዩን ማስረጃዎች አንዱ ዘመናትን ተሻግረው እኛ እጅ የደረሱት የወንጌል ቅጅዎች ናቸው፡፡ እነዚህ ቅጅዎች በሚገባ የተጻፉ፣ በሐረግ ያሸበረቁ፣ በሥዕል የተገለጡ፣ ትንታኔ የተሰጠባቸው፣ ቀመር የተዘጋጀላቸው፣ ማውጫና ማብራሪያ የተሰጣቸው፣ ወንጌሎቹ በወንጌላውያኑ የተጻፉበትን ቦታና ዘመን የሚያመለክቱ ናቸው፡፡ በዚህ ጽሑፍ በ14ኛው መክዘ የመጀመሪያዎቹ ዓመታት የተጻፈውን የግእዝ ወንጌል መሠረት አድርገን ነገሩን እንዳስሳለን፡፡
አርባዕቱ ወንጌል ዘደብረ ጊዮርጊስ
መጽሐፉ የሚገኘው በዋልተርስ የሥነ ጥበብ ሙዝየም በቁጥር W 836 ተመዝግቦ ነው፡፡ በብዙ ገጾቹ ላይ ውኃ ፈስሶበት ለማንበብ ያስቸግራል፡፡ በአንድ ወቅት በትግራይ ደብረ መዐር የሚገኘው የቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ንብረት የነበረው ይኼ ወንጌል 516 የብራና ቅጠሎች ያሉት ነው፡፡ ወንጌሉ በ1973 እኤአ የሮበርትና ናንሲ ኑተር ገንዘብ ሆነ፡፡ በ1996እኤአ ደግሞ የአልተን ደብሊው ጆንስ ፋውንዴሽን ገዝቶ በሙዝየሙ አስቀመጠው፡፡ ወንጌሉን የጻፈው መጥሬ ክርስቶስ የተባለ ጸሐፊ ሲሆን አባ አርከ ሥሉስ በ18ኛው መክዘ ማርያም ጽኩዕ ለሚባል ደብር እንደሰጡት በማቴዎስ ሥዕል ሥር በጻፉት መግለጫ ይናገራል፡፡ ከዚያ በኋላ እንዴት የደብረ መዐር ጊዮርጊስ ንብረት እንደሆነ እንዴትም ከሀገር እንደወጣ አላወቅኩም፡፡
   
የወንጌሉ መግቢያ
                                                                 
መልእክተ አውሳብዮስ
አውሳብዮስ የታወቀውን የቤተ ክርስቲያን ታሪክ መጽሐፍ Ecclesiastical History የጻፈ አባት ነው፡፡ በዚህ ወንጌል ላይ አውሳብዮስ ቀርጲያኖስ ለተባለ ሰው አርባዕቱ ወንጌልን በተመለከተ የጻፈው ደብዳቤ ይገኛል፡፡ በደብዳቤው ላይ እንደተገለጠው አሞንስ አሌክሳንድራዊ የሠራውን የወንጌላት ቀመር ሰድዶለታል፡፡ አውሳብዮስም ለቀርጲያኖስ በዚህ ደብዳቤ ይገልጥለታል፡፡

የአውሳብዮስ ደብዳቤ
                                                                        

(1)አራቱ ወንጌላውያን የሚተባበሩበትን፣
(2)ማቴዎስ፣ ማርቆስና ሉቃስ የሚተባበሩበትን፣
(3)ማቴዎስ ሉቃስ ዮሐንስ የሚተባበሩበትን፣
(4)ማቴዎስ ማርቆስ ዮሐንስ የሚተባበሩበትን፣
 (5)ማቴዎስና ሉቃስ የሚተባበሩበትን፣
(6)ማቴዎስና ማርቆስ የሚተባበሩበትን፣
(7)ማቴዎስና ዮሐንስ የሚተባበሩበትን፣
(8)ሉቃስና ማርቆስ የሚተባበሩበትን
(9) ሉቃስና ዮሐንስ የሚተባበሩበትን
(10) አራቱንም በየራሳቸው ያላቸውን
ሠለስቱ ወንጌላት(ማቴዎስ፣ ማርቆስ፣ ሉቃስ) የሚተባበሩበት

ይኼ ቀመር ከጥንት ጀምሮ የቅዱሳት መጻሕፍት ጥናት በቤተ ክርስቲያናችን ይሰጥ እንደነበረ ያመለክታል፡፡ አራቱን ወንጌላውያን በየራሳቸው በትርጓሜ ከማጥናት ባለፈ አራቱ የሚገናኙበትንና የሚለያዩበትን እየተነተኑ በቀመር ማጥናቱ ለምን ተለዩ? የሚል ጥያቄ በአጥኝዎቹ ዘንድ ተነሥቶ እንደነበረ ያሳያል፡፡ ጥያቄውን ለመመለስ ሊቃውንቱ የደከሙትን ድካምም በየትርጓሜው ውስጥ የምናየው ነው፡፡ ‹ማቴዎስ እንዲህ አለ፤ ማርቆስም እንዲህ ብሏል፣ ሉቃስም እንዲህ ይላል፣ እንደምን ነው ቢሉ› የሚለው ዓይነት፡፡
ይህ ቀመር በመልእክተ አውሳብዮስ እንደተገለጠው የሚለያዩበትንና የሚገናኙበትን ለማጥናት ብቻ ሳይሆን አንዱን የወንጌል ታሪክ በተመለከተ በአራቱም ወንጌላውያን ያለውን ሐሳብ ለማየት የሚያገለግል፣ ከዚህም በላይ የወንጌሉን ልዩ ልዩ ክፍሎች በየታሪካቸው ዘውግ ለማጥናትና በቃል ለመያዝም የሚያስችል ነው፡፡
አርእስት
በአራቱም ወንጌሎች ላይ በየአንዳንዱ ምእራፍ ምን ምን ይዘት እንዳለ የሚያሳይ ርእስ አላቸው ፡፡ ርእሱ የሚጻፈው በላይኛው የብራናው ኅዳግ ላይ ሲሆን በርእሱ የተገለጠው የመጽሐፉ ክፍል የሚጀምርበት ቦታ ልዩ ምልክት በቀይ ቀለም ተደርጎበታል፡፡ ምልክቱ በሥዕሉ ላይ እንደምናየው ከላይ ቀለበት ያለው ወራጅ መሥመር ይደረግና መሐል ወገቡ ላይ የX ምልክት ይደረጋል፡፡ ይህም ወንጌሉን በጉዳይ በጉዳይ ከፋፍሎ የመማርና የማስተማር ባሕል እንደነበረ ያሳያል፡፡
  የአርእስት አሰጣጥ
   እንስሳት
በወንጌሉ ውስጥ የወንጌሉን ሐሳብ የሚገልጡ የእንስሳት ሥዕሎች አሉ፡፡ የመጀመሪያዋ ፒኮክ ወፍ ናት፡፡ የፒኮክ ወፍ በጥንት ክርስቲያኖች ዘንድ ትንሣኤ ሙታንን የምታመለክት ነበረች፡፡ ሌላዋ ደግሞ ጳልቃን ወይም ፔሊካን ተብላ የምትጠራው ስትሆን እርሷም ዛሬም ድረስ በትርጓሜያችን እንደሚነገረው የትንሣኤ ሙታን ምሳሌ ናት፡፡ ሌላም አንድ ወፍ አለች፡፡ ማን እንደሆነችና ትርጉሟንም ለማወቅ አልቻልኩም፡፡ ሌላዋ ሰጎን ናት፡፡ ሰጎን የክርስቲያኖችና የመንፈስ ቅዱስን ግንኙነት ለማሳየት የምትመሰል ወፍ ናት፡፡ ከወፎች በተለየ የምናገኘው እንስሳ በግ ነው፡፤ እርሱም የታረደው የክርስቶስ ምሳሌ ነው[18]፡፡
በመጽሐፉ ውስጥ ካሉት ወፎች(ፒኮክ)
                                                 
     ሰጎን

                                                                           
ምልክቶች
ከላይ ካየነው የ‹ቶ›[19] መሰል ምልክት በተጨማሪ ትምህርቱን፣ ተግሣጹን፣ ተአምሩን ለማመልከት ልዩ ልዩ ምልክቶችን ማድረጉን አውሳብዮስ ይገልጣል፡፡ በመጽሐፉም ውስጥ ያንን በመከተል በግራና በቀኝ በሚገኙ ኅዳጎች ላይ ምልክቶች ይገኛሉ፡፡ ከዚህም በተጨማሪ በአውሳብዮስ ቀመር ላይ ለእያንዳንዱ ቀመር የተሰጠው ቁጥር በወንጌሉ ውስጥም  በሚገኙበት በሚገኙበት ቦታ በቀይ ቀለም ቁጥሩ በግእዝ ተጽፏል፡፤ ይህም የወንጌላቱን ጥናት የሚያቀል ነው፡፡
  
አዲሱ ርእስ የሚጀምርበት የ‹ቶ› መሰል ምልክት
                                                  
    ሥዕል
በያንዳንዱ ወንጌላዊ መግቢያ ላይ የወንጌላዊው ሥዕል አለ፡፡
ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃስ
                                                                   

የማቴዎስ ወንጌል ከመጀመሩ በፊት ደግሞ የጌታችንን ሥነ ስቅለት(በጉ ከመስቀሉ በላይ ይታያል)[20] የሚያሳይ ጥንታዊ ሥዕል፣
 
   የሥነ ስቅለቱ ሥዕል፣ ክርስቶስ በበግ መስለውት
                                                     

 የጌታችንን ትንሣኤ የሚያሳይ ሥዕል(በሁለት ሴቶች መካከል ሆኖ)፣
የጌታ ትንሣ፣ ቅዱሳት አንስት ግራና ቀኝ
የጌታችን ዕርገትና በዙፋኑ ላይ መቀመጥን የሚያሳዩ ሥዕሎች አሉ፡፡ 
 ጌታችን ዐርጎ በዙፋኑ ሲቀመጥ
ከዚህም በተጨማሪ ጸሐፊው የአርባዕቱን ወንጌል ኅብረት በዲያግራም ገልጦታል፡፡ 
 
 የአርባዕቱ ወንጌልን አንድነት ለመግለጥ የተሳለ ዲያግራም
የመጻሕፍቱ ክፍሎች ማውጫ
ከማርቆስ ወንጌል ጀምሮ የመጻፍቱን ልዩ ልዩ አርዕስት ለማውጣት የሚያስችል ማውጫ ተዘጋጅቶላቸዋል፡፡ ማውጫዎቹ የመጽሐፉን ገጽ የሚጠቀሙ ሳይሆኑ ጉዳዩንና ቅደም ተከተሉን ብቻ የሚያሳዩ ናቸው፡፡
የማቴዎስ ወንጌል ማውጫ

መሥፈርና መቁጠር
ወንጌሉ የእያንዳንዱን ወንጌላውያን አርእስተ ነገር ቆጥሮና ሠፍሮ ያስቀምጣል፡፡ በዚህ መሠረት
ጠቅላላ የወንጌላውያኑ አርእስተ ነገር 218 ሲሆን
ማቴዎስ 68
ማርቆስ 48
ሉቃስ 83
ዮሐንስ 19
እንዳላቸው ያትታል፡፡ ጠቅላላ ቃሎቻቸውም 90 ሺ 700 (፺፻፯፻) መሆናቸውን ይናገራል፡፡ ይህም ነገር የወንጌሉ ጥናት ከ600 ዓመታት በፊት የደረሰበትን ደረጃ የሚገልጥ ነው፡፡
 
የማርቆስ ወንጌልን የአርእስት ቁጥር የሚያሳይ መረጃ
ማጠቃለያ
ከላይ ያየናቸውን ነጥቦች ስንመረምራቸው የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ለወንጌለ ክርስቶስ ትምህርትና ጥናት የነበራትን ዋጋ፣ ከዚህም በላይ ለወንጌሉ ጌታ ለኢየሱስ ክርስቶስ ያላትንም ቦታ የሚያሳይ ታሪካዊ መረጃ ነው፡፡ ወንጌሉን ይህንን ያህል ሠፍሮና ቀጥሮ፣ ተንትኖና አፍታቶ ለማወቅ የተፈለገውም የሚያስገኘው ምድራዊ ጥቅም ኑሮ አልነበረም፡፡ ክርስቶስን ዐውቆ በክርስቶስ መንገድ ለመኖር ስለተፈለገ እንጂ፡፡ ቤተ ክርስቲያኒቱ ያፈራቻቸው ቅዱሳንም ይህንን በመሰለው የወንጌል ትምህርት ታንጸውና በስለው የወጡ እንደነበሩ የ13ኛው መክዘን የሐይቅ እስጢፋኖስ ወንጌል ከአቡነ ተክለ ሃይማኖት ታሪክ ጋር፣ የደብረ መጣዕን ወንጌል ከአባ ሊባኖስ ታሪክ ጋር፣ የክብራንን ወንጌል ከአባ ዘዮሐንስ ታሪክ ጋር፣ አያይዞ ማሰብ ይቻላል፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ ይህቺን ቤተ ክርስቲያን ወንጌል አልሰበከችም፣ ክርስቶስንም አታውቀውም ብሎ እንደመናገር ያለ ከባድ ኃጢአት ሊኖር አይችልም፡፡

2015 ጁን 9, ማክሰኞ

ጾምና የዩኒቨርሲቲዎቻችን አስተዳደር


የሰኔ ጾም መግባትን ተከትሎ በአንዳንድ ዩኒቨርሲቲዎች ውስጥ የምግብ ክርክሮች መፈጠራቸውን የሚያሳዩ መረጃዎች እየወጡ ነው፡፡ ‹የጾም ምግብ ምግብ ይሠራልን› ብለው በሚጠይቁ ተማሪዎችና ‹ያቀረብንላችሁን ብቻ ብሉ› በሚሉ የዩኒቨርሲቲ አስተዳደሮች መካከል ነው ክርክሩ፡፡
የዩኒቨርሲቲ አስተዳደሮች ይህንን የተማሪዎችን ጥያቄ ላለመቀበል የሚያቀርቧቸው መከራከሪያዎች ከሦስት የዘለሉ አይደሉም፡፡ የመጀመሪያው ሃይማኖታዊ አክራሪነትን ከመዋጋት ጋር የተያያዘ ነው፡፡ የአንድ ሰው መጾምና መጸለይ የአክራሪነት መመዘኛዎች መሆናቸውን የሚያሳይ ምንም ዓይነት መዝገበ ቃላት ሊቀርብ ባይችልም፡፡ መንግሥት መመሪያ ሰጠን እንዳይሉም መንግሥት በተለያዩ ቦታዎች አክራሪነትን ለመተርጎም የሚያዘጋጃቸው መዛግብት ጾምን የአክራሪነት መግለጫ አድርገው ያቀረቡበት ጊዜ የለም፡፡ አክራሪነት፣ ሽብርተኛነት፣ ጽንፈኛነት የሚሉት ጽንሰ ሐሳቦች በጥንቃቄና ገደብ ባለው ሁኔታ የማይተረጎሙ ከሆነ ለመለጠጥና የተፈለገውን ሁሉ ለማካተት ምቹዎች ናቸው፡፡ እነዚህ ሐሳቦች ለተቋማትና ባለ ሥልጣናት ግላዊ ትርጎማ የተመቹ በመሆናቸው በማሳያዎች፣ በመግለጫዎችና ገደብ ባለው ሁኔታ መተርጎምን የሚጠይቁ ናቸው፡፡

በወጣቶች በተለይም በዩኒቨርሲቲዎች ውስጥ የእምነት አክራሪነት እንዳይፈጠር ከተፈለገ የእምነት አክራሪነትን ከዩኒቨርሲቲዎች ነባራዊ ሁኔታ አንጻር ሁሉንም ሊያግባባ በሚችል ሁኔታ መተርጎምንና ግልጽ የሆኑ ማሳያዎችን ማስቀመጥን ይጠይቃል፡፡ በተለይ ደግሞ እንደ ኢትዮጵያ ባሉ ሃይማኖት ከባሕል፣ ሥነ ልቡና፣ አመለካከትና አነዋወር ጋር በእጅጉ ድርና ማግ በሆነባቸው ሀገሮች የምዕራባውያንን ወይም የሩቅ ምሥራቆችን አስተሳሰብ ይዞ መጥቶ አክራሪነትን መበየን እንጀራን ምግብ ነው ለማለት በፓስታ መመዘኛ እንደመመዘን ያለ ነው፡፡
ለምሳሌ በአንዳንድ ዩኒቨርሲቲዎች ሂጃብ መልበስ ወይም ነጠላ ማድረግ የአክራሪነት መገለጫ ተደርጎ ሲወሰድ ይታያል፡፡ እነዚህ ሁለቱም መሠረታቸው እምነት ቢሆንም በሂደት ግን የሕዝቦች ባሕል ሆነዋል፡፡ አንድ ሰው በዩኒቨርሲቲ ውስጥ ነጠላ ወይም ሂጃብ ሲለብስ እየገለጠ ያለው ሃይማኖቱን ነው ወይስ ባሕሉን? የሚለውን ለመወሰን እጅግ አስቸጋሪ ነው፡፡ እንዲያውም በአንድ ኮሌጅ ውስጥ የኮሌጅ ጥበቃዎች ወደ ግቢው የሚገቡ ተማሪዎችን እያዩ ‹‹አንቺ መስቀለኛ አጣፍተሻልና አስተካክዪ›› እስከማለት የደረሱበትም ቦታ አለ፡፡ ለመሆኑ የአንድን ሰው አለባበስ ሃይማኖታዊ ነው ወይም ባሕላዊ ነው ብሎ የሚወስነው የግቢው ጥበቃ ነውን? በምን ሥልጣን? በየትኛውስ የዕውቀት መጠን? ለምሳሌ አንዲት ልጅ መስቀል የተጠለፈበት የሐበሻ ቀሚስ ለብሳ ወደ ኮሌጅ ግቢ ለመግባት አትችልም ማለት ነው? መስቀል የተነቀሰቺ ልጅስ?
‹የአበራሽን ጠባሳ ያየ በእሳት አይጫወትም› እንዲሉ ሶርያና ኢራቅን፣ አፍጋኒስታንንና ሊቢያን ያየ ዩኒቨርሲቲ፣ ነጠላ መልበስንና ሂጃብ ማድረግን አክራሪነት ነው ብሎ ለመጨዋት መነሣት አልነበረበትም፡፡ የጾምም ጉዳይ እንዲሁ ነው፡፡ አንድ ሰው ሲጾም ይበልጥ ወደ አርምሞ፣ ይበልጥ ወደ ጽሙና ይገባል፡፡ ከብዙ ነገሮች ይቆጠብ ዘንድ ራሱን ይገዛል፤ አካላዊ ድካምን ተቀብሎ መንፈሳዊ ጥንካሬን ያገኛል፡፡ ጾም የልቡና ትንሣኤን የሚያመጣ ነው፡፡ እንዲያውም ጾም የአክራሪነት ተቃራኒ ነው፡፡ ራስን ለመቅጣት የሚጾም ሰው ዮሌሎችን ጥፋት ለማሰብ ዕድሉ አነስተኛ ነው፡፡ ይልቅስ አክራሪነትን ለመዋጋት ጾምን ማበረታታት አንዱ መፍትሔ ነው፡፡
ሌላው የዩኒቨርሲቲ አስተዳደሮች የሚያነሡት ሐሳብ ሴኩላሪዝምን ነው፡፡ ትምህርት ቤቶች የእምነት ማስፋፊያዎች አይደሉም፡፡ ትምህርት ዓለማዊ(ሴኩላር) ነው፡፡ ስለዚህ ሃይማኖታዊ የሆነውን የጾም ጉዳይ አናስተናግድም ነው፡፡ ትክክል ነው ትምህርት ቤቶች መርሐቸው ዓለማዊነት(ሴኩላሪዝም) ነው፡፡ ትምህርት ቤቶች ሴኩላሪዝምን ይከተላሉ ማለት ግን ሃይማኖት በትምህርት ቤቶች ቦታ የለውም ማለት አይደለም፡፡ በአውሮፓና በአሜሪካ ዩኒቨርሲቲዎች ሴኩላሪዝምን የተከተለ የትምህር መርሕ አላቸው፡፡ በግቢያቸው ውስጥ ግን ለተማሪዎቹ የማምለኪያ ቦታ ይፈቅዳሉ፡፡
በአሁኑ ዘመን የዓለም መንግሥታት ሴኩላሪዝምን በተመለከተ ሁለት ዓይነት አቅጣጫዎችን ይከተላሉ፡፡ የመጀመሪያው Assertive secularism ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ passive secularism ነው፡፡ አሰርቲቭ ሴኩላሪዝም ሃይማኖታዊ ሥነ ሥርዓቶችን፣ መገለጫዎችንና ምስሎችን በአደባባይ መጠቀምን፣ ማሳየትንና መግለጥን ይከለክላል፡፡ እምነት ከግላዊ ክበብ ውጭ በይፋ ሕዝባዊ መድረክ እንዳይተገበርም  በጥብቅ ይከታተላል፡፡ ለዚህ የሚጠቀሰው የፈረንሳይና የቱርክ ሴኩላሪዝም ነው፡፡ ፈረንሳይ እኤአ በ2003 ባወጣችው ሕግ በትምህርት ቦታዎች ሂጃብ፣ የአይሁድን ኪፓ፣ ትልልቅ መስቀሎችንና ሌሎች የእምነት ይፋዊ መገለጫዎችን ማድረግን ከልክላ ነበር[1]፡፡ ፓሲቭ ሴኩላሪዝም የሚባለው ደግሞ መንግሥት ምንም ዓይነት የክልከላም ሆነ የፈቃድ ሕግ ሳያወጣ ሰዎች በራሳቸው ፍላጎት ብቻ እምነታቸውን እንዲገልጡ ለራሳቸው ነገሩን መተው ነው፡፡ የአሜሪካ መንግሥት ሴኩላሪዝም ይህንን የሚመስል ነው[2]፡፡
ምንም እንኳን በሴኩላሪዝም ሐሳባቸው ቢለያዩም ሦስቱም መንግሥታት ሴኩላር መንግሥታት ናቸው፡፡ ያም ማለት የሕግና የመንግሥት ሥርዓታቸው ከሃይማኖታዊ ተጽዕኖ ውጭ ነው፤ ከዚህም በተጨማሪ አንድን የተለየ ሃይማኖትን ወይም ደግሞ ፀረ እምነትነተን (Atheism) ኦፊሴላዊ አድርገው አልተቀበሉም፡፡ ብዙ ሊቃውንት ደግሞ ሴኩላር መንግሥትን በሁለት ነገሮች ይበይኑታል፡፡ የመጀመሪያው የመንግሥትና ሃይማኖት መለያየት ሲሆኑ ሁለተኛው ደግሞ የእምነት ነጻነት ነው[3]፡፡ በብዙ ሴኩላር መንግሥታት የመንግሥትና እምነት መለያየት በሕገ መንግሥት የተገለጠ አይደለም፤ ትግበራውን በአጽንዖት የመከታተል ሁኔታም የለም(It is not a practical issue)፡፡ በተቃራኒው የእምነት ነጻነትን በተመለከተ ግን በሕገ መንግሥት ግልጽ በሆነ ሁኔታ የሚቀመጥ ተግባዊነቱንም በአጽዖት የሚከታተሉት ነው፡፡ ይህም የሚያሳየው ከመንግሥትና እምነት መለያየት ይልቅ የእምነት ነጻነት መከበር ዋነኛው የሕዝቦች ጥያቄ መሆኑን ነው፡፡ የሦስቱም መንግሥታት ልዩነት የመጣው ይህንን የእምነት ነጻነት የመተርጎም ላይ ነው፡፡
 የኢትዮጵያ መንግሥት ብሎም የትምህርት ተቋማት የትኛውን ዓይነት የሴኩላሪዝም መንገድ እንደሚከተሉ ግልጽ አይደለም፡፡ አሰርቲቭ ሴኩላሪዝምን ነው እንዳንል መንግሥት ራሱ የእምነት በዓላትን በብሔራዊ ቴሌቭዥን ሲያስተላልፍ ይታያል፤ በፓርላማውም የእምነት መገለጫ ልብሶችን የለበሱ ተወካዮች ይታያሉ፡፡ ፓሲቭ ሴኩላሪዝምን ነው እንዳይባልም በትምህርት ቤቶች ውስጥ የሚፈጸሙ ክልከላዎች አሉ፡፡ የአሰርቲቭ ሴኩላሪዝም ዋናው ዓላማ እምነትን ከሕዝባዊ መድረክ(public sphere) ለማውጣት ይሁነኝ ብሎ መሥራት (comprehensive doctrine) ሲሆን የፓሲቭ ሴኩላሪዝም ሚና ግን መንግሥት በልዩ ልዩ እምነቶች ውስጥ ያለውን የገለልተኛነት ሚና አጽንቶ መጠበቅ ነው፡፡
እንደ ኢትዮጵያ ባሉ ብዙ እምነቶች፣ ባሕሎችና ልማዶች ባሉባት ሀገር፤ ሃይማኖት ትምህርት ብቻ ሳይሆን ባሕል፣ የቀን አቆጣጠር፣ አለባበስ፣ የአስተሳሰብ ቅኝትና የአነዋወር መንገድ በሆነባት ሀገር፤ በባሕልና እምነት መካከል የተቆረጠ መሥመር ለማስመር በሚያስቸግር ማኅበረሰብ ውስጥ፤ መንግሥትም ሆነ የትምህርት ተቋማት ቢከተሉት የሚመከረው ፓሲቭ ሴኩላሪዝምን ነው፡፡ አንደኛው በእምነቱ ምክንያት በሌላው ላይ ተጽዕኖ የማያደርግ ከሆነ፣ መንግሥታዊ ሥራን፣ ሕጋዊ ሂደትንና የመማር ማስተማር ሂደቱን ትርጉም ባለው መጠን እስካላወከ ድረስ፣ ተቋማቱም ይሁነኝ ተብሎ ለሚደረግ የእምነት ማስፋፋት ሥራ[4] መድረክ እስካልሆኑ ድረስ ፓሲቭ ሴኩላሪዝም ለኢትዮጵያ ተመራጭ ነው፡፡
ጾምን ከዚህ አንጻር የተመለከትነው እንደሆነ በምንም መልኩ ይሁነኝ ተብሎ በኮሌጅ ውስጥ የሚደረግ የሃይማኖት ማስፋፋት እንቅስቃሴ አይደለም፡፡ ሰዎች ተሰብስበው ሊማሩና ሊጸልዩ ይችሉ ይሆናል፡፡ ተሰብስቦ መጾም ግን አይቻልም፡፡ ጾም ግላዊ ስለሆነ፡፡ በተመሳሳይ የጾም ወቅት የሚሳተፉ ሰዎች ግን ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ በሙስሊምና ክርስቲያን ተማሪዎች ዘንድ በኮሌጆች የሚታየውም ይኼው ነው፡፡ በአንድ ተመሳሳይ የጾም ወቅት የሚደረግ ሱታፌ፡፡ በርግጥ ይሄ የጾ ሐሳብ  እምነትን ግላዊ ብቻ ለማድረግ ከሚያስበው አመለካከት ይለያል፡፡ ምዕራባውያን ‹እምነት ግላዊ ብቻ ነው› ብለው የሚቀበሉት ሐሳብ በፕሮቴስታንት የእምነት አስተምህሮ ላይ የተመሠረተ ነው፡፡ እምነት ግላዊ ምርጫ አለው፡፡ በግላዊ ወሳኔም የሚከተሉት ነው፡፡ ነገር ግን ይህንን ግላዊ ምርጫና ውሳኔ በኅብረት መግለጥና መሳተፍ የሚጠይቅበት ጊዜ ግን አለ፡፡ በኦርቶዶክስ፣ በካቶሊክ፣ በእስልምናና በይሁዲ እምነቶች ዘንድ ግላዊ የሆኑ የእምነት ሕይወቶችና ሕዝባዊ(ማኅበራዊ) የሆኑ የእምነት ሕይወቶችም አሉ፡፡ የረመዳን ጾምና የሑዳዴ ጾም የዚህ ማኅበራዊ የእምነት ክበብ መገለጫዎች ናቸው፡፡
ትምህርት ቤቶች የጋራ ሱታፌን የሚጠይቁትን ማኅበራዊ የእምነት ክዋኔዎችን መከልከል የለባቸውም፡፡ ምናልባት የጋራ ክዋኔ(Public demonstration) የሚጠይቁ ማኅበራዊ ክዋኔዎች ላይ እንደየሁኔታው ተዐቅቦ ሊያደርጉ ይችሉ ይሆናል፡፡[5] ጾም ግን የጋራ ሱታፌን እንጅ ክዋኔን አይጠይቅም፡፡ የጋራ ሱታፌውም የሚመጣው በተመሳሳይ ወቅት በተመሳሳይ ሥርዓት ስለሚጾም ነው፡፡
ሃይማኖታዊ እሴቶችን በተመለከተ የክልከላን አሠራር ከመከተል የገለልተኛነትን አሠራር መከተሉ የሚጠቅመው ሃይማኖታዊ እሴቶች ዛሬ ዛሬ በኮሌጅ ተማሪዎች ዘንድ በአደገኛነት እየመጡ ያሉትን የአደንዛዥ ዕጽ ተጠቃሚነት፣ ሥርዓት አልበኝነት፣ የትምህርት ግዴለሽነት፣ በጊዜያዊ ጥቅሞችና ደስታዎች ዘላቂ መሥመርን መሳት፣ የጠባብነትና የጎጠኝነት አስተሳሰቦችንና ድርጊቶችን ለመከላከል የላቀ ሚና ስለሚኖራቸው ጭምር ነው፡፡ የትምህርት ተቋማት በኢትዮጵያ ማኅበረሰብ ውስጥ አፈጻጸሙ ውስብስብ ከሚሆነው አሰርቲቭ ሴኩላሪዝም ይልቅ ፓሲቭ ሴኩላሪዝምን ቢከተሉ ሃይማኖት በማኅበረሰቡ ውስጥ አዎንታዊ ሚና እንዲጫወት መንገዱን ያመቻቻሉ፡፡ የነገው ትውልድም ብዙኅነትን በአዎንታዊ መልክ ለምዶትና ገንዘብ አድርጎት ከዩኒቨርሲቲ እንዲወጣ ያደርጉታል፡፡ እንዲያውም ዩኒቨርሲቲዎች እንደሌሎች የመንግሥት ተቋማት የሃይማኖትን ጉዳይ በ‹የለሁበትም› መንገድ ከማስተናገድ ይልቅ ምሁራዊ ውይይት እንዲደረግበት መንገድ ቢከፍቱ አንዱ ስለሌላው በጎውን የማወቅና ልዩነቱን ተቀብሎ በሰላም ለመኖር እንዲችል ያደርጉ ነበር፡፡ ሰው በጠባዩ የማያውቀውን ነገር ይፈራዋል፣ ይሠጋዋልም፡፡ የእምነት ጉዳዮችን በምሁራዊ መንገድ በማየት መተዋወቁ ቢፈጠር ፍርሃትና ሥጋቱን ለማስወገድ በተቻለ ነበር፡፤ የትምህርት ተቋማት ሴኩላር መሆንም ለዚህ ነበር ዋናው ጥቅሙ፡፡ ጾም ለመከልከል አልነበረም፡፡  
     ሌላው የዩኒቨርሲቲ አስተዳደሮች የሚያነሡት መከራከሪያ ‹‹የተለያዩ ቡድኖችን ፍላጎት በአነስተኛ የኢኮኖሚ ዐቅም ውስጥ ማሟላት ስለማንችል በዩኒቨርሲቲው ዐቅም ላይ የተመሠረተ አንድ ወጥ መርሐ ግብር ብቻ ነው የምንከተለው›› የሚል ነው፡፡ በርግጥ ዩኒቨርሲቲዎች እንደ አውሮፓና አሜሪካ ዩኒቨርሲቲዎች ለእምነቶቹ ሁሉ የማምለኪያ ቦታ ለመስጠት የሚያስችል ዐቅም ላይኖራቸው ይችላል፡፡ ነገር ግን የጾም ምግብ ለማዘጋጀት የሚያስችል አቅም አላቸው፡፡ በሁለት ምክንያት፡፡ የመጀመሪያው የኦርቶዶክስም ሆኑ የሙስሊም የጾም ወቅቶች ጊዜያቸው የታወቀ ነው፡፡ ለጋራ አስተዳደር አስቸጋሪ አይደሉም፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ የጾም ምግብን ማዘጋጀት ለአንድ ዩኒቨርሲቲ ከፍስክ ምግብ ይልቅ ርካሽ ነው፡፡ ይህም የዩኒቨርሲቲውን በጀት የሚያቃውስ ሳይሆን በተዘዋዋሪ መንገድ የሚደጉም ነው፡፡ የተማሪዎቹ ጥያቄ ከምንበላው ምግብ የሥጋ፣ የቅቤ፣ የወተትና የዕንቁላል ነገር ተቀንሶ አትክልትና ሽሮ ይሰጠን ነው፡፡ የዩኒቨርሲቲው ክርክር ደግሞ በጾም ሥጋ ካልበላችሁ የሚል ነው፡፡     
በዚህ ሰሞን ያለው ሁኔታ እንኳን ብንመለከት አንድ ኮሌጅ ሦስት የምግብ መርሐ ግብር ብቻ ይጠበቅበታል፡፡ ለሙስሊም ተማሪዎች የማፍጠሪያ ምግብ ማዘጋጀት(ያም ቢሆን ቀድሞ የሚሰጣቸውን የቁርስና የምሳ ነገር ትቶ እራት ላይ ማቅረብ እንጂ አዲስ ነገር አልጠየቁትም)፣ ለኦርቶዶክስ ተማሪዎች የጾም ምግብ ማዘጋጀት፣ ለሌሎች ተማሪዎች በዩኒቨርሲቲው መርሐ ግብር መሠረት ማዘጋጀት፡፡ ዩኒቨርሲቲው ተጨማሪ ሠራተኞችንና ቁሳቁሶችን ለማቅረብ በጀት የለኝም ካለ እንኳን ተማሪዎች ሲጾሙ በተውት በጀት መጠቀም ይችላል፡፡ ቅንነቱ ካለ፡፡ ለዚያውስ ቢሆን ‹ለስሟ መጠሪያ ቁና ሰፋቺ› ሆኖ ነው እንጂ ኮሌጅ ውስጥ ስንት ቀን ሥጋ ተበልቶ ነው?
በአሁኑ ዘመን ሥጋን የማይመገቡ ማኅበረሰቦች በዓለም ላይ እየተፈጠሩ ነው፡፡ በብዙ ቦታዎችም ለእነርሱ የሚሆኑ ምግቦች ይዘጋጃሉ፡፡ ታላላቅ ሆቴሎች፣ የግብዣ ቦታዎች፣ መንግሥታዊ ሥነ ሥርዓቶች፣ በዓሎች፣ የአውሮፕላን ጉዞዎች፣ ወዘተ ሥጋ ለማይመገቡ ሰዎች የተለየ ምግብ ማዘጋጀታቸውን በይፋና በኩራት ይገልጡታል፡፡ ጉዳዩንም ከመብትና ለተጠቃሚ የተመቸ ከባቢ ከመፍጠር አንጻር ያዩታል፡፡ ዩኒቨርሲቲዎቻችንም እነዚህ ሥጋ የማይበሉ ማኅበረሰቦች ቢፈጠሩባቸው ሥጋ የመብላት ግዴታ አለብህ ሊሉ ነው? ብዙዎቹ የዩኒቨርሲቲ አስተዳደር ሹመኞች ለትምህርት ወይም ለሥልጠና አለበለዚያም ለልምድ ልውውጥ ወደ ውጭ ዩኒቨርሲቲዎች ሄደው ነበር፡፡ የተማሪዎችን ፍላጎቶች እንዴት ከትምህርት ቤት ፖሊሲ ጋር በተጣጣመና ማንንም በማይጎረብጥ መልኩ እንደሚያስተናግዱት አላዩምን? 
መካነ አእምሮ የሆነው ዩኒቨርሲቲ ጾምን የመሰሉ ሃይማኖታዊ እሴቶችን ከእምነት ነጻነትና ተገቢውን አገልግሎት ከማግኘት መብት አንጻር እጅግ በሠለጠነ መንገድ ተርጉሞ በቀላሉ ችግሩን መፍታት ካቃተው ‹መካነ አእምሮ› ከሚለው ቃል ውስጥ ‹ካ› እንዲጠብቅ ያደርገዋል፡፡ 
Posted by ዳንኤል ክብረት

2015 ጁን 1, ሰኞ

፬ኛው የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ጠቅላላ ጉባኤ የጋራ አቋም መግለጫ


eotc ssd pouring out to patriarch palace00
በሐዋርያዊት፣ ጥንታዊት እና ብሔራዊት ቤተ ክርስቲያናችን ህልውና እና ዕድገት ፊት ከተጋረጡትና አፋጣኝ እልባት ከሚሹት የዘመናችን የውስጥ ችግሮች እና የውጭ ተግዳሮቶች ውስጥ ሙስና እና ኑፋቄ ቀዳሚዎቹ ናቸው፡፡ አንዱ የሌላው መተላለፊያ፣ መንሥኤ እና
ውጤት እየኾኑ ለቤተ ክርስቲያን ተቋማዊ ለውጥ የተደረጉ ጥረቶችን ሲያመክኑ፤ የመዋቅር እና የአደረጃጀት አቅሟን ሲያዳክሙ ቆይተዋል፡፡
በአዲስ አበባ ሰንበት ት/ቤቶች አንድነት የሚያዝያ ፳፯ ቀን ፳፻፯ ዓ.ም. መግለጫ እንደተመለከተው፣ በቅዱስ ሲኖዶስ ተወግዘው ከተለዩ በኋላ በቅጥር ወደ አስተዳደራዊ እና የአገልግሎት መዋቅሯ የገቡ የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ መናፍቃን መኖራቸው ሙስና እና ኑፋቄ የተሳሰሩ እና የሚመጋገቡ ለመኾናቸው ግልጽ አስረጅ ነው፡፡
ከግንቦት ፳፩ – ፳፫ ቀን ፳፻፯ ዓ.ም. በጠቅላይ ቤተ ክህነት የመሰብሰቢያ አዳራሽ ሲካሔድ ቆይቶ ለጽርሐ መንበረ ፓትርያርኩ አርዕድ አንቀጥቅጥ በኾኑ፤ መልካም አስተዳደር እና ፍትሐዊ ፍርድ በሚጠይቁ መዝሙሮች ትላንት ማምሻውን የተጠናቀቀው ፬ኛው ዓመታዊ ሀገር አቀፍ የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ጠቅላላ ጉባኤ፣ በጋራ አቋም መግለጫዎቹ በቀጥታ ይኹን በአማራጭ ያረጋገጠውም ይህንኑ እውነታ ነው፡፡
*       *       *
eotc ssd 4th gen assembly participants
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት

ብፁዕ አቡነ ሉቃስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ እና የሰቲት ሑመራ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ
ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ እና የወላይታ ኮንታ እና ዳውሮ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ
ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ የበላይ ሓላፊ ሊቀ ጳጳስ፣ በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የፓትርያርኩ እንደራሴ ሊቀ ጳጳስ፣ የጉራጌ ስልጤ ከምባታ እና ሐዲያ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ
ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት
የጠቅላይ ቤተ ክህነት የመምሪያ ሓላፊዎች
ከተለያዩ አካላት ጥሪ የተደረገላችኹ የክብር እንግዶች፤
እኛ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ጠቅላላ ጉባኤያትን ወክለን በ፬ኛው የሀገር አቀፍ የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት አጠቃላይ ጉባኤ ላይ የተሳተፍን የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ጠቅላላ ጉባኤ አባላት ከግንቦት ፳፩ – ፳፫ ቀን ፳፻፯ ዓ.ም. ላለፉት ሦስት ቀናት÷ የማደራጃ መምሪያው ዓመታዊ የአገልግሎት ዘገባ፤ ከ37 አህጉረ ስብከት የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት እና የሰንበት ት/ቤቶች ዋና ክፍሎች ሪፖርቶች፤ የሰንበት ት/ቤቶች አባላት በኾኑ ባለሞያዎች በቀረቡ ጥናታዊ ጽሑፎች ላይ ሰፊ ውይይት አድርገናል፡፡
በመምሪያው ዘገባም ኾነ ከ37 አህጉረ ስብከት የመጡ ተወካዮች ያቀረቡት ሪፖርት ሰንበት ት/ቤቶች እጅግ በርካታ ተግባራት እያከናወኑና የቤተ ክርስቲያንን ተልእኮ ለማፋጠን እየተጉ መኾኑን አስገንዝቧል፡፡ ኾኖም ግን በየአህጉረ ስብከቱ የሚታዩ፡-
  • የመናፍቃን እና የአፅራረ ቤተ ክርስቲያን ተጽዕኖ
  • በየአጥቢያ ቤተ ክርስቲያን እየደረሱ ያሉ የአስተዳደር በደሎች
  • የበጀት እና የመምህራን እጥረት፣ የአዳራሽ እጥረት፤
  • የአንዳንድ አህጉረ ስብከት ስፋት ለትራንስፖርት አመቺ አለመኾን፤
አገልግሎቱን እየተገዳደሩ ያሉ ዋና ዋና ችግሮች ኾነው ተዘግበዋል፡፡
‹‹የሰው ኃይል አያያዝ በሰንበት ት/ቤት›› በሚለው ጥናታዊ ጽሑፍ መነሻነት በተደረገው ውይይትም ለቤተ ክርስቲያን ኹለንተናዊ ዕድገት ወሳኝ የኾነው የሰው ኃይል መኾኑን በማመን የቤተ ክርስቲያን አካላት በሙሉ በተለይም ሰንበት ት/ቤቶች ትኩረት ሰጥተን ልንሠራበት እንደሚገባ ተገንዝበናል፡፡ በማያያዝም ‹‹የኢኮኖሚ ግንባታ ለቤተ ክርስቲያን›› በሚለውም ጥናት፣ የኢኮኖሚ አቅም ማነስ÷ የመጠቀምን፣ የመደመጥን፣ የመወሰንን፣ የመተግበርን አቅም ያሳጣል፤ በሌላ በኩል እምነትን ይፈትናል፤ ሥጋዊውን ጥቅም ለማሳካት ሲባል ከቤተ ክርስቲያን መለየትን ያመጣል፤ ብዙ ተባዙ ምድርንም ምሏት ያለውን የእግዚአብሔር ቃል ያስጥሳል፤ ወጣቱንም ለስደት እና ለመከራ እየዳረገ ይገኛል፤ የቤተ ክርስቲያን ተልእኮም እንዳይፋጠን ያደርጋል፡፡
ስለዚኽ ቤተ ክርስቲያን ያላትን ሀብት በአግባቡ በመጠቀም ኢኮኖሚያዊ አቅሟን ልታጠናክር፤ ተሰሚነቷን ልታስከበር ይገባታል፤ ሰንበት ት/ቤቶችም የኢኮኖሚ አቅማቸውን ለማጠናከር የሚያስችሉ ተግባራት ሊሠሩ፤ የቤተ ክርስቲያን መምሪያዎችም ሊያግዟቸው እንደሚገባ ውይይቱ ትኩረት ሰጥቶበታል፡፡
በመጨረሻም በሪፖርቱም ኾነ በጥናታዊ ጽሑፎች የተጠቀሱትን ዋና ዋና ችግሮች በመለየት በተደረገ የቡድን ውይይት ሰንበት ት/ቤት በቀጣይነት በጋራ የምንሠራቸውን እና የምንስማማባቸውን የአቋም መግለጫዎች አውጥተናል፡፡
  1. የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ከ2006 – 2010 ዓ.ም. የታቀደውን የአምስት ዓመት መሪ ዕቅድ በቀሩት ጊዜያት ለመፈጸም እና ለማስፈጸም ቃል እንገባለን፤
  2. የሰንበት ት/ቤቶች አጠቃላይ መሪ ዕቅድ የኹሉም የአጥቢያ ሰበካ መንፈሳውን ጉባኤያት ዕቅድ አካል እንዲኾን እና የጠቅላይ ቤተ ክህነት መምሪያዎችም ኹሉ መሪ ዕቅዱን ከዕቅዳቸው ጋራ በማገናዘብ እንዲያካትቱ ይደረግ ዘንድ እንጠይቃለን፤
  3. መልክአ ምድርን መሠረት ያደረገ የሰንበት ት/ቤቶች ትስስር በማጠናከር ሰንበት ት/ቤቶች ባልተቋቋሙባቸው አጥቢያዎች እንዲቋቋሙ፣ በተቋቋሙባቸው ደግሞ የተጠናከረ አገልግሎት እንዲሰጥባቸው ለማድረግ እንሠራለን፤
  4. የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ኑፋቄ ችግሮችን ለማጋለጥ ያስችል ዘንድ ከሀገር አቀፍ የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ጀምሮ እስከ አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ት/ቤት የሚደርስ መረጃ የማሰባሰብ ሥርዐት በመዘርጋት የመረጃ ማሰባሰቡን አጠናክረን እንሠራለን፤
  5. በአኹኑ ሰዓት በቤተ ክርስቲያን ተልእኮ አፈጻጸም ላይ ተጽዕኖ እየፈጠረ ያለው የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ መናፍቃንን እንቅሰቃሴ ለማስቆም ከቅዱስ ሲኖዶስ ጀምሮ በየደረጃው ያሉ የቤተ ክርስቲያን አካላት አፋጣኝ ርምጃ እንዲወስዱ እንጠይቃለን፤
  6. ቀደም ሲል በአዲስ አበባ ሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ስለ ፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ መናፍቃን የቀረበው ማስረጃ ውሳኔ እንዲሰጠው፤ ውሳኔውም ተግባራዊ ይኾን ዘንድ ከቅዱስ ሲኖዶስ ጀምሮ ያሉ የቤተ ክርስቲያን አካላት አስፈላጊውን ርምጃ እንዲወስዱ እንጠይቃለን፤
  7. በአኹኑ ጊዜ አንዳንድ የቤተ ክርስቲያን ሓላፊዎች በሰንበት ት/ቤት ወጣቶች እና አባላት ላይ በተሳሳተ አመክንዮ እያደረሱት ያለው እስር፣ እንግልት እና ወከባ እንዲቆምልን በአጽንዖት እንጠይቃለን፤
  8. ከዚኽ ጋር ተያይዞ የመንግሥት የፍትሕ አካላትም ከአጥፊዎች ጋር በመተባበር የሰንበት ት/ቤት አባላትን ከማሰር እና ከማንገላታት እንዲታቀቡ ይደረግ ዘንድ እንጠይቃለን፤
  9. በቃለ ዐዋዲው እና በ1986 ዓ.ም. ሕገ ደንቡ ላይ የተጠቀሰው የሰንበት ት/ቤቶች የዕድሜ ገደብ እንዲነሣልን በድጋሜ እንጠይቃለን፤
  10. ከሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ አንሥቶ እስከ አጥቢያ ሰንበት ት/ቤቶች የሚደርስ የፋይናንስ ትስስር እና አያያዝ ሥርዐት በመምሪያው በኩል ተጠንቶ እንዲጸድቅልን እንጠይቃለን፤
  11. የቤተ ክርስቲያንን ሀብት እና ንብረት ለግል ጥቅማቸው በማዋል የቤተ ክርስቲያንን አቅም የሚያዳክሙ አማሳኞች ማስረጃ ተጠናቅሮ በአገሪቱ ሕግ መሠረት እንዲጠየቁልን እንጠይቃለን፤
  12. የቤተ ክርስቲያን የፋይናንስ አሠራር ማእከላዊ እንዲኾን እና በባለሞያዎች የሚታገዝ የክትትል እና የቁጥጥር ሥርዐት እንዲኖረው እንጠይቃለን፤
  13. በዘመናችን ሚዲያ በወጣቱ እና በሕፃናት አስተዳደግ ላይ ከፍተኛ ተጽዕኖ እየፈጠረ ስለሚገኝ የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ በስፋት ለምእመናን ለማዳረስ እንዲቻል በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሚመራ እና የሚተዳደር፤ ቤተ ክርስቲያኒቷንም የሚወክል የቴሌቪዥን መርሐ ግብር እንዲጀመር በአጽንዖት እንጠይቃለን፤
  14. በአኹኑ ሰዓት በቤተ ክርስቲያን ስም ቤተ ክርስቲያንን የማይወክል ትምህርት እና መልእክት የሚያስተላልፉ የቴሌቪዥን መርሐ ግብሮች በተቻለ ፍጥነት እንዲዘጉ አልያም በቤተ ክርስቲያን ስም ከመጠራት እና ከመጠቀም እንዲከለከሉ እንጠይቃለን፤
  15. ለጠቅላላ ጉባኤው ተወካዮቻቸውን ያልላኩ አህጉረ ስብከት ተለይተው በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ የማያዳግም ርምጃ እንዲወሰድባቸው እንጠይቃለን፤
  16. በቤተ ክርስቲያናችን መንፈሳዊ እና ልማታዊ ጉዳዮች ከአባቶቻችን ጋር በመኾን ያለንን አቅም አሟጠን በመጠቀም ለቤተ ክርስቲያን ዕድገት እና ልዕልና የበኩላችንን ድርሻ እንወጣለን፤
  17. የቤተ ክርስቲያናችንን ኹለንተናዊ ችግር ለመፍታት ከመንፈሳዊ ኰሌጅ ምሩቃን(ቴዎሎጅያን) ጋር ተባብረን የምንሠራ መኾናችንን እንገልጻለን፤
  18. የአዲስ አበባ ሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ያቀረበው ጥያቄ የኹላችንም አቋም ስለኾነ አፋጣኝ መልስ እንዲሰጠው እንጠይቃለን፡፡
 ግንቦት ፳፫ ቀን ፳፻፯ ዓ.ም.

2015 ሜይ 30, ቅዳሜ

4ኛው ሀገር አቀፍ የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ጠቅላላ ጉባኤ ተጀመረ


አትም ኢሜይል
ግንቦት 22 ቀን 2007 ዓ.ም.
በእንዳለ ደምስስ
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስ002sundayቲያን መንበረ ፓትርያርክ የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃና መምሪያ የሀገር አቀፍ የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ጠቅላላ ጉባኤ ግንቦት 21 ቀን 2007 ዓ.ም በጠቅላይ ቤተ ክህነት ስብከተ ወንጌል አዳራሽ ተጀመረ፡፡

በጠቅላላ ጉባኤው ላይ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት እና የቅዱስ ፓትርያርኩ ረዳት፤ የከንባታ ሀዲያ የስልጤ ጉራጌ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤ የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ የበላይ ሓላፊ ጉባኤውን በጸሎት ከፍተዋል፡፡

ብፁዕነታቸው ባስተላለፉት መልእክት ከዚህ በፊት ሰንበት ት/ቤቶች ተጣምረው የጋራ ሥራ መሥራት ባለመቻላቸው በተናጠል ዕቅዶችን በማውጣትና የአፈጻጸም ስልቶች በመንደፍ ይጓዙ እንደነበር ገልጸው፤ የተናጠል ጉዞውም ውጤታማ ባለመሆኑ ከሰ/ት/ቤቶች ወጣት ምሁራን ጋር በመነጋገርና በመገምገም የአገር አቀፍ የሰ/ት/ቤቶች አንድነት በማቋቋም ለቅዱስ ሲኖዶስ በማቅረብ፤ ቅዱስ ሲኖዶስም የቀረበው ጥያቄ ለቤተ ክርስቲያን ያለውን ጥቅም በማረጋገጥ ደንብ ወጥቶ መጽደቁን ጠቅሰዋል፡፡

የሰ/ት/ቤትን ጥቅም ባልተረዱ በአንዳንድ ግለሰቦች ዘንድ የሰ/ት/ቤት ተማሪዎች መባል እንደ ነቀፋ ይቆጠር የነበረውን ስም ማስቀረት የሚቻለው በሥራ መሆኑን የጠቀሱት ብፁዕነታቸው የወጣቱን አእምሮ ለሃይማኖታዊ ልማት በማነሳሳት ረገድ የአንድነቱ መቋቋም ጉልህ ሚና መጫወቱን ገልጸዋል፡፡ አባላቱም የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ጥቅም በማስቀደም ከቡድናዊና ጐሣዊ አስተሳሰብ በመራቅ የቤተ ክርስቲያንን ችግሮች ለመቅረፍ እንዲተጉ አሳስበዋል፡፡

001sunday003sunday
የሰ/ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ዋና ሓላፊ መምህር ዕንቁባሕርይ ተከስተ ባቀረቡት ሪፖርትም በአገሪቱ ውስጥ በሚገኙ 37,332 አብያተ ክርስቲያናት ውስጥ ከ20,000,000 በላይ ወጣቶች እንዳሉ የሚገመት ሲሆን፤ እሰካሁን በ8,610 አብያተ ክርስቲያናት በሥርዓት ተመዝግበው አገልግሎት በማግኘት ላይ ያሉ ወጣቶች 2,701,253 ብቻ መሆናቸውን ጥናቶች እንደሚያመለክቱ ገልጸው ይህንንም መሠረት በማድረግ ገና ብዙ መሥራት እንደሚገባ አስታውቀዋል፡፡

በ2007 ዓ.ም. የተከናወኑ ዋና ዋና ሥራዎችንም በተመለከተ መምህር እንቁባሕርይ ለጉባኤው አቅርበዋል፡፡ በዚህም መሠረት ሀገር አቀፍ አደረጃጀት በመላው ሀገሪቱ አደራጅቷል፤ ያልተቋቋመባቸውም ቦታዎች ለማቋቋም ጥረት እየተደረገ እንደሚገኝ፤ የ2007 ዓ.ም. እና የ2008 ዓ.ም. ዝርዝር የአፈጻጸም መርሐ ግብር በማውጣት በመላው ሀገሪቱ ተግባራዊ መደረጉ፤ ከ2005 እስከ 2010 የአምስት ዓመት መሪ ዕቅድ በሀገር አቀፍ ደረጃ ተግባራዊ እየተደረገ መሆኑ፤ በማደራጃ መምሪያው ድረ ገጽ በመላው ዓለም ለሚገኙ ምእመናን እያሰተማረ መሆኑ፤ የሰንበት ትምህርት ቤቶች አደረጃጀትን እስከ ወረዳ ድረስ በማውረድ እየተንቀሳቀሰ እንደሚገኝ፤ የተለያዩ ስልጠናዎችንና ጉባኤያትን እንዲሁም ስብሰባዎች ማድረጉ፤ የፋይናንስ አሠራር ረቂቅ ተዘጋጅቶ በውይይጥ ላይ እንደሚገኝ በሪፖርታቸው ውስጥ ተካትተዋል፡፡

ያጋጠሙ ችግሮችን በመተመለከተም የበጀት እጥረት፤ ብቁ የሰው ኃይል አለመመደብ፤ የመልካም አስተዳደር እና የፍትሕ እጦት የፈጠረው ችግር፤ ወጣቶች በየቦታው እየተንገላቱና እየታሰሩ መሆናቸው፤ ሕጋዊ የወጣት ሰንበት ትምህርት ቤት እያለ ከመዋቅር ውጭ የደብር አለቃና ጸሐፊ በተጓዳኝ የጽዋ ማኅበራትን እያደራጁባቸው እንደሚገኙ፤ የማኅበራት ወሰን የለሽ እንቅስቃሴና ጣልቃ ገብነት ሓላፊው እንደ ችግር ካነሷቸው መካከል ይገኙባቸዋል፡፡

ችግሮቹን ለመፍታት የተወሰዱ የመፍትሔ አቅጣጫዎች በተመለከተም ግልጽ የሆነ የወጣቶች ራዕይና ስትራቴጂ ማስቀመጥ፤ከሀገር አቀፍ ጠቅላላ የሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት እስከ አጥቢያ ሰንበት ትምህርት ቤቶች ድረስ ማጠናከር፤ የሁሉም ሰንበት ትምህርት ቤቶች አሠራር እንቅስቃሴ በማእከል ደረጃ መቆጣጠርና መከታተል እንዲቻል የሀሳብ ልውውጥና ስልት መንደፍ፤ የትምህርትና የመዝሙርን ወጥነት ለማረጋገጥ ጥረት እየተደረገ እንደሚገኝ እንደመፍትሔ ጠቁመዋል፡፡

የኢትዮጵያ የሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት ምክትል ሓላፊ ወ/ሮ ማርታ ኃ/ማርያም ባቀረቡት ሪፖርት የአንድነቱ ሥራ አመራር ኮሚቴ ከተመረጠ ሁለት ዓመታት ቢያስቆጥርም የአመራር አባላቱ ከተለያዩ አህጉረ ስብከት የተመረጡ በመሆናቸው ተሰባስቦ ወጥ የሆነ አገልግሎት ለመፈጸም እንደተቸገሩ ገልጸው፤ በዚህ ዓመት ግን የተለያዩ ኮሚቴዎችን በማዋቀር እንቅስቃሴ መጀመራቸውን አብራርተዋል፡፡

ሰንበት ትምህርት ቤቶች እያጋጠሟቸው ከሚገኙ ችግሮች መካከል ሲገልጹ የተዘጋጀ ሥርዓተ ትምህርት በየደረጃው ያለመኖር፤ የመመህራን ችግር፤ የፋይናንስ እጥረት፤ ከውስጥ ሆነው ቤተ ክርስቲንን የሚያጠቁ የአጽራረ ቤተ ክርስቲያን እንቅስቃሴ እንዲሁም የአስተዳደር ችግሮች ዋና ዋናዎቹ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡

በዚህም መሠረት በተነሱትና ሌሎችም ችግሮችና መፍትሄዎቻቸው ላይ ጠቅላላ ጉባኤው ተወያይቶ ለቅዱስ ሲኖዶስ እንዲቀርብ ጠይቀዋል፡፡

ቀጥሎም የሀገረ ስብከታቸውን ሰንበት ትምህርት ቤቶች  አንድነት ወክለው በመጡ የሰንበት ትምህርት ቤት አመራር አባላት የ2007 ዓ.ም. ሪፖርታቸውን በቅደም ተከተል አቅርበዋል፡፡

መምህር በለጠ ብርሃኑ የሰው ኃል አያያዝ በሰንበት ትምህርት ቤት በሚል ጥናታዊ ጽሑፍ አቅርበው ውይይት ተደርጎበታል፡፡

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃና መምሪያ የሀገር አቀፍ የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ጠቅላላ ጉባኤ እስከ ግንቦት 23 ቀን 2007 ዓ.ም ድረስ ለሦስት ተከታታ ቀናት ሲካሔድ ይቆያል፡፡

2015 ሜይ 26, ማክሰኞ

ሰበር-ዜና የታላቁ ደብረ ሊባኖስ ገዳም የድጓው ሊቅ አለቃ መርዓዊ /የኔታ መኮንን አረፉ

                                                                                                         ዜና ዕረፍቱ ለአለቃ መርዓዊ ሣህለ ሚካኤል ማኅቶታ ለደብረ ሊባኖስ ፈረየ ዓምአተ ወአመከአበ ቦ ዘ፷ ወቦ ዘ፴ ዘራዒሁሰ እንድርያስ ውእቱ ወፍሬሁኒ ጳጳሳት ወሊቃውንት እሙንቱ ::
   ታላቁ ሊቅ አለቃ መርዓዊ ሣህለ ሚካኤል የቤተ መንግሥት ቁም ጸሐፊና የደብረ ሊባኖስ ገዳም የሃይማኖተ አበው ትክለኛ ከሆኑት አባታቸው አለቃ ሣህለ ሚካኤልና ከእናታቸው ወ/ሮ እቱነሽ ጌታሁን በደብረ ሊባኖስ አካባቢ ልዩ ስሙ ፍኖተ ጽድቅ /ዋሻ ገደል/ ታሕሳስ 13ቀን 1915 ዓ.ም ተወለዱ
  እድሜያቸው ለትምህርት እንደደረሰ የአባታቸው ርስት ከሚገኝበት ልዩ ስ ጠሬ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ከአባ ወልደ ማርያም ንባብና የቅዳሴ ትምህርታቸውን ተከታትለዋል በ1928 ዓ.ም ጣሊያን ኢትዮጲያን በወረረበት ወቅት ከተክለ ሃይማኖት ልጆች ጋር በመሆን ገና በልጅነት ዕድሜያቸው በግዳጅ ታስረው ወደ ሞቃዲሾ ተግዘዋል ከዚያም ፋሺሽት ጣሊያን ድል ተነሥቶ ኢትዮጲያን ለቆ ከወጣ በኋላ በ1933 ዓ.ም  ከሞቃዲሾ ወደ ትውልድ ቦታቸው ወደ ደብረ ሊባኖስ ገዳም ተመልሰው በጠላት ምክንያት ለተቋረጠው ትምህርታቸው መንፈሳዊ ቅንዓትና ልዩ ፍላጎት ስለነበራቸው
 አንደኛ ከሁለቱ መምህራኖች ከአለቃ ተገኝና ከየኔታ ንጉሤ የዜማ ትምህርታቸውን ተከታትለዋል::
   ሁለተኛ በ1936 ዓ.ም በሥሬ መድሐኔዓለም ዝነኛና ታዋቂ ከሆኑት ከታላቁ ሊቅ አለቃ ጥበቡ ገሜ ዘንድ ቅኔን ከነ አገባቡ ቀጽለዋል
   ሶስተኛ በ1937 ዓ.ም ወደ ጎንደር በመሄድ በእስቴ ወረዳ ልዩ ስሙ መካነ ኢየሱስ ከሚባለው ደብር ከመምህር ጥበቡ ድጓና ጾመ ድጓን ለሁለተኛ ጊዜ ተምረዋል እንዲሁም በዚሁ ደብር ከላይ በተጠቀሱት መምህር ዝማሬና መዋስዕትን በሚገባ ተምረዋል ::
አራተኛ በ1940 ዓ.ም በዚያው በጎንደር ቆላማ አካባቢ ወደ ሆነው ወደ መልዛ በመውረድ የተማሩትን እያስተማሩ ለድጓና ጾመ ድጓ ጽሑፍ የሚሆናቸውን ብርሃና በማውጣት ቆይተዋል::
  አምስተኛ በ1945 ዓ.ም የድጓ ማስመስከሪያ ወደ ሆነው ወደ ቤተልሔም ገብተው ለሶስት ዓመታት ድጓና ጾመ ድጓውን ጽፈውና አስመስክረው በመምህርነት ተመርቀዋል
 ስድስተኛ ወደ ጎንደር ከተማ በመሄድ ደብረ ኃይል ወደብረ ጥበብ በዓታ ለማርያም የአቋቋም ምስክር ከሆኑት ከአለቃ ክፍሌ ዘንድ አቋቋም በሚገባ ተምረዋል የአቋቋም ትምህርታቸውን ካጠናቀቁ በኋላ የትምህርት ቤት ጓደኛቸውና የመንፈስ ቅዱስ ወንድማቸው ከሆኑት ከርዕሰ ደብር መዝገቡ ኃብተ ገብርኤል ጋር በመሆን ለትምህርት ከሄዱበት ከጎንደር ክፍለ ሀገር ለቀው በአውሮፕላን የኢትዮጲያ መናገሻ ከተማ ወደ ሆነችው ወደ አዲስ አበባ ከተማ መጥተው በደብረ ሰላም ቅዱስ እስጢፋኖስ ቤተ ክርስቲያን በድጓ መምህርነት እያስተማሩ ሳለ በወቅቱ የኢትዮጲያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ፖትርያርክ በሆኑት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ባስልዮስ መልካም ፈቃድ ለድጓ መምህርነት ተመርጠው የትውልድ ቦታቸው ወደ ሆነው ወደ ታላቁ ገዳም ወደ ደብረ ሊባኖስ በ1949 ዓ.ም ተመድበው የማስተማር ሥራቸውን ጀምረዋል::
    አለቃ መርዓዊ ሣህለ ሚካኤል ከመምህርነት ሥራቸው በተጨማሪ ባላቸው ጊዜ የሐዲስ መምህር ከሆኑት ከመምህር ፍስሐ ኪዳንና ትምህርተ ኅቡዓት አንድምታ ትርጓሜን ቀጽለዋል በመቀጠልም ከየኔታ አንድርጌ ውዳሴ ምርያምና ቅዳሴ ማርያም አንድምታ ትርጓሜን አሂደዋል::
         አለቃ መርዓ ሣህለ ሚካኤል ዘነሣዕክሙ በፀጋ  በፀጋ ሀቡ የሚለውን አምላካዊ ቃል አብነት በማድረግ ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይሉ ያለዋጋ ከመላው ኢትዮጲያ የሚመጡ ደቀ መዛሙርትን በዕውቀት በመቅረጽ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳትን አያሌ ሊቃውንትን ለቤተ ክርስቲያኒቱ አፍርተዋል::
   አለቃ መርዓዊ ሣህለ ሚካኤልን ከመምህራን ልዩ የሚያደርጋቸው ለተማሪዎቻቸው ከዜማ ትምህርት በተጨማሪ ፍትሐ ነገሥት መጽሐ መነኮሳት የዓለም ታሪክን በማገናዘብ የዓለም ታሪክን በማስነበብ አዕምሮአቸው እንዲበለጽግ በማድረግ እጅግ የላቀ ተሰጥኦ ነበራቸው
  እንዲሁም በአካባቢው ያሉ ወንዶችና ሴቶች ህፃናትን ወደ ገዳሙ የሚመጡ መናንያንን ሴት መነኮሳትን የግዕዝ ንባብና ሥነ ጽሑፍ እንዲያውቁ በማድረግ ትውልድ የሚያኮራ ታላቅ ሥራ ሠርተዋል::
ታላቁ ሊቅ አለቃ መርዓዊ ሣህለ ሚካኤል በልዩነት ከተሰጣቸው የመንፈስ ቅዱስ ሐብት የሚያስደንቀወ የዜማ ትምህርት ለመማር ከሳቸው ዘንድ የሚመጡ ደቀ መዛሙርት ሁሉ በአዕምሮ የበለፀጉ ማስተዋልና በዕውቀት እጅግ የተካኑ መሆናቸው የእሳቸውን የመንፈስ ቅዱስ ልዩ ስጦታ መሆኑን ይገልጻል
     ሥልጣነ ክህነትን በተመለከተ አለቃ መርዓዊ ሣህለ ሚካኤል የዲቁና ማዕረግን ከብፁዕ አቡነ ማቴዎስ ግብጻዊ የቅድስና ማዕረግን ከብፁዕ አቡነ ሣዊሮስ ኢትዮጲያዊ ተቀብለዋል::ሥርዓተ ምንኩስናም በዚሁ ታላቅ ገዳም ፈጽመዋል::
      አለቃ መርዓዊ ሣህለ ሚካኤል በታላቁ ገዳም በደብረ ሊባኖስ በዕልቅና ከ1977 ዓ.ም እስከ ዕለተ ዕረፍታቸው ሊቃውንቱን በቅንነትና በመንፈሳዊነት ሲመሩ ቆይተዋል::
   አለቃ መርዓዊ ሣህለ ሚካኤል በክብር ላይ ክብር በትሩፋት ላይ ትሩፋት ለመጨመር ወደ ቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም በመሄድ ታሪካዊ ቦታዎችን ጎብኝተዋል::
አለቃ መርዓዊ ሣህለ ሚካኤል እንደ ኢዮብ በትዕግሥት እንደ አብርሃም በልግስና እንደ አባታቸው አቡነ ተክለ ሃይማኖት በተጋድሎና በትሩፋት በንጽሕና በቅድስና ምትክ የሌላቸውና አባታቸው ቅዱስ ያሬድ ዘኮኖ ልቡ ሠረገላ ለጸሎት ብፁዕ ውእቱ ያለው ቃል የተፈጸመላቸው የምንመካባቸው አባታችን ነበሩ ምንም እንኳን ለደቀ መዛሙርቶቻቸው ብርሃን ለዚህ ታላቅ ገዳም ዓምድ ቢሆኑም ለሰው ልጆች ሁሉ የማይቀር የሞት ፅዋ ለሳቸውም የማይቀር በመሆኑ እንደ ቅዱስ ጳውሎስ አንሰ በድርየኒ ፈጸምኩ ወሃይማኖትየኒ ሰለጥኩ እንከሰ ጽኑሕ ሊተ አክሊል ዘየአስየኒ መኮንነ ጽድቅ ብለው ለ60 ዘመናት እስትንፋሳቸው እስከ ተቋረጠችበት ዕለት ድረስ ከደቀ መዛርቶቻቸውና ከወንበራቸው ሳይለዩ ግንቦት7 ቀን 2007 ዓ.ም በተወለዱ በ92 ዓመታቸው ከዚህ ዓለም በሞተ ሥጋ ተለይተው የቀብራቸው ሥነ ሥርዓትም ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት አበው መነኮሳት ሊቃውንት ደቀ መዛሙርቶቻቸውና ወዳጅ ዘመዶቻቸው በተገኙበት ግንቦት 8 ቀን 2007 ዓ.ም በታላቁ ደብረ ሊባኖስ በክብር ተፈጽሟል::
    ለደቀ መዛሙርቶቻቸውና ወዳጅ ዘመዶቻቸው መፅናናትን እየተመኘን ለሁላችንም በረከታቸውና ረድኤታቸው አይለየን በማለት እንሰናበታቸዋለን::




2015 ሜይ 15, ዓርብ

ሰበር-ዜና የታላቁ ደብረ ሊባኖስ ገዳም የድጓው ሊቅ አለቃ መርዓዊ /የኔታ መኮንን አረፉ



ነገ ወደ መንገድ እሄዳለሁ ውዳሴ ማርያም እንዳታስታጉሉ፡፡

የኔታ መርዊ ሐሙስ ማታ ተማዎቻቸውን ካስተማሩ በኋላ  ከተናገሩት 

         
                                                                     
ደብረ ሊባኖስ ገዳም ሲነሳ አብረው የሚታወሱ ለረጅም ዘመናት ድጓ በማስተማር በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንን የፈሩ በምናኔያቸው ፤በማስተማር ብቃታቸው፡ በመኅሌት ቁመት ድካም የማያውቃቸው አለቃ መርዓዊ ዛሬ ግንቦት 7 /2007 ዓ.ም ማረፋችው ተሰማ፡፤ ይህ ዜና እንደተሰማ በተለይ በ አዲስ አበባ አድባራትና ገዳማት በማገልገል ላዪ የሚገኙ ሊቃውንት ልጆቻቸው ዛሬ ከሰዓት በኋላ ወደ ደብረ ሊባኖስ ገዳም ኢየተመሙ ይገኛሉ፡፡አለቃ መርዓዊ ከገዳሙ ህልውና ቀጥሎ በስስት ዓይን የሚታዩ ትሁት ፤መናኝ፤ ፤ ማኅሌታዊ፤ መምህር ነበሩ ፡፡
ማሳሰቢ
ይህን አሳዛኘ ዜና የሰማሁት  ለአገልግሎት ኮቦልቻ  እንደደረስኩ ነውና  ሙሉ ዝርዝር መረጃዎችን አጠናክረን እናደርሳለን፡፡
የሊቁ አባታችንን ነፍስ ከቅዱሳን ሊቃውንት አጠገብ ያኑርልን፡፡

                                   በአውሮጳ   የካህናት አንድነት ማኅበር ሊቋቋም መሆኑ ታወቀ በ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከመላዋ አውሮጳ   የተውጣጡ ካህናት፡” የ...