2014 ሜይ 7, ረቡዕ

"የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ፍቅር በአባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ አንደበት"



“የእመቤታችን ምስጋናዋ እንደ ሰማይ ኮከብ እንደ ባሕር አሸዋ በዝቶልኝ እንደ ልብስ ለብሼው ተጐናጽፌው እንደ ምግብ ተመግቤው ጠግቤው እያሉ ሲመኙ ከነበሩትና የእመቤታችን ጣዕመ ፍቅሯ ከበዛላቸው ሊቃውንት ውስጥ አንደኛው ኢትዮጵያዊዉ ሊቅ አባ ጊዮርጊስ ሲኾን ስለፍቅሯ አርጋኖን፣ ኈኅተ ብርሃን፣ መዐዛ ቅዳሴ፣ እንዚራ ስብሐት፣ ሕይወታ ለማርያም የሚሉ መጻሕፍትን ጽፎላታል፡፡ ስለ ፍቅሯ ታላቅነት ከገለጸው ውስጥ ጥቂቶቹ
1. “ፍቅርኪ ምዉቅ ኤጴሞሰ ልብሱ ለዕሩቅ ኢይትከደኖ እደ ንፉቅ ኢይትረከብ በወርቅ እንበለ ዳእሙ በጽድቅ”
(ለተራቈተው የትከሻው ልብሱ የሚኾን ሙቀት ያለው ፍቅርሽ፤ የመናፍቅ እጅ አይጐናጸፈውም በጽድቅ ካልኾነ በቀር በወርቅ አይገኝም)
ሊቁ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ እንደጠቀሰው የእግዚአብሔር ጸጋ የእናቱ በረከት በሃይማኖት እንጂ በወርቅ በብር በጥርጣሬ መንፈስ የሚገኝ ከዚኽ የምናረጋግጠው በዝቶ የሚሰጠው እነቅዱስ ኤፍሬም፣ እነአባ ሕርያቆስ፣ እነቅዱስ ያሬድ እንደ ምግብ ተመግበው የጠገቡት እንደ ልብስ ለብስ ለብሰው የተጐናጸፉት የቅድስት ድንግል ማርያም ፍቅር እንደ ሲሞን ያሉ ተጠራጣሪዎች ፈጽመው የማያገኙት እንደኾነ አስረድቷል፡፡
2. “ፍቅርኪ ባዝግና ለዘየዐንቆ በትሕትና ኢይረክቦ እደ ሙስና ወልድኪ ጥዒና ዘያወረዝዎ ለርሥእና”
(በትሕትና ለሚያስረው ሰው ፍቅርሽ ዝርግፍ ወርቅ ነው፤ የጥፋት እጅም አያገኘውም፤ ልጅሽም እርግናን የሚያስጐለምሰው ጤንነት ነው)
3. “ፍቅርኪ ሰንፔር ለዘይርሕቆ ይስሕቦ መንገለ አሚን ያቀርቦ መኑ ከማኪ ምክንያተ ድኂን ዘተውሕቦ”
(ማዕድናትን የመሳብ ባሕርይ ያለው ሰንፔር ፍቅርሽ የሚርቀውን ይስበዋል፤ ወደ ሃይማኖትም ያቀርበዋል፤ የድኅነት ምክንያት የተሰጠው እንዳንቺ ያለ ማነው?)
ሊቁ የጠቀሰው የሰንፔር ደንጊያ በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ ለ12 ጊዜያት ሲጠቀስ ይኽ የከበረ ደንጊያ በእጅጉ ብሩህ ሲኾን የራቀውን ኹሉ እንደ ማግኔት ስቦ የማቅረብ ኀይል አለው፤ በተመሳሳይ መልኩ በቅድስት ድንግል ማርያም ጣዕመ ፍቅር እንደ በላዔ ሰብእ ያሉ ወደ ሃይማኖት ተስበው በምልጃዋ በልጇ ቸርነት ድነዋልና ይኽነን ተናገረ፡፡
በቅዱሳት መጻሕፍት የተራቀቀው ይኽ ታላቅ ሊቅ በዚኽ ክፍል ላይ ጠቅልሎ ባንድ ማዕድን በሰንፔር ብቻ መስሎ የተናገረውን ክብሯን በሰኞ የአርጋኖን ምስጋናው ላይ በብዙዎች የከበሩ ማዕድናት በመመሰል ሲተነትነው
“ኦ እግዝእትየ ቅድስት ድንግል ማርያም ዘበዕብራይስጢ ማሪሃም (ሚርያም)፤ ወካዕበ መሠጠኒ ኅሊናየ ከመ አስተማስለኪ በአእባን ክቡራት…” (በዕብራይስጥ ማሪሃም (ሚርያም) በመባል የተመረጥሽ ድንግል እመቤቴ ማርያም ሆይ ዳግመኛ በከበሩ ደንጊያዎች እመስልሽ ዘንድ ልቡናዬን አነሣሣኝ፤ መረግድ በሚባል ዕንቊን አመሳስዬ እጠራሻለኊ፤ ሕብራቸውም በተራራ ላይ ካለ በረድ በሚነጣ በሄጶዴጤንና በጶዴር መስዬ እጠራሻለኊ ይኸውም ለንጽሕናሽ የሚገባ ምሳሌ ነው፡፡
የጳዝዮን ደንጊያ አንቺ ነሽ፤ የሰንፔር የሶምና የክርስቲሎቤ ደንጊያ አንቺ ነሽ ይኸውም አርአያና አምሳል ዐይንን ለሚያስደስት ብርሃናዊ ደም ግባትሽ ነው፡፡ አሜቴስጢኖስ የሚባል የማዕድን ዐይነት ደንጊያ አንቺ ነሽ፡፡ ኢያሰጲድ ሰርዲኖ ከሚባሉ ማዕድናት የተሠሩ ደንጊያ አንቺ ነሽ ይኽም አርአያና ምሳሌ ክፋት ነቀፋ ለሚያገኘው ቅድስና ጌጥ ነው፡፡ ርኲሰትን ከሚያነጻ እለመቅሊጦስ ከሚባል ማዕድን የተገኘ ደንጊያ አንቺ ነሽ የዓለሙ ኀጢአት ባንቺ ምክንያተ ድኂንነት ነጽቷልና፤ የበደሉ ዝገትም ባንቺ ምክንያተ ድኂንነት ታድሷልና፡፡
ሲጮኽ ለሚያዳምጠው የሚያስደስት የደወል ደንጊያ የቤተ መቅደስ ምርዋ አንቺ ነሽ በሕማም ጭንቀት ጊዜም ቢደውሉት ልትወልድ የምታምጥ ሴት ልቡና ይመሠጣል እስከምትወልድበትም ጊዜ ድረስ የመውለድ ሕማም አይሰማትም፤ እንዲኹም ሰማዕታት የቅድስናሽን ጣዕመ ዜና የልጅሽንም ለቤዛ ዓለም የመስቀሉን አሳዛኝ ዜና በመስማት በሰማዕትነት የሚያገኛቸውን መከራ አያውቋትም፤ የምስክርነታቸው ዋጋ የኾነውን የጽድቅ አክሊል እስከሚቀዳጁበት ድረስ፡፡ አንጥረኞች ብረቶችን የሚያቀልጡበት ብርቱ የአድማስ ደንጊያ አንቺ ነሽ፤ በወሊድ ያልተለወጠ የማኅተመ ድንግልናሽ ኀይል እንደ አድማስ ደንጊያ ጽኑ ነውና) በማለት በእጅጉ አስደናቂ የኾነ ትምህርትን የእመቤታችን ጣዕመ ውዳሴዋ የበዛለት ይኽ ሊቅ አስተምሯል፡፡
4. “ፍቅርኪ ሰከለ በልበ ጠቢባን ዘበቈለ እምአፈ ነኪር ሰሰለ መኑ ዘተሀጒለ በጸሎትኪ ዘተወከለ”
(በብልኆች ልብ የበቀለ ፍቅርሽ አፈራ ከእምነት ከተለየ ሰው አንደበትም ራቀ፤ በጸሎትሽ ከታመነ ሰው የጠፋ ማነው?)
5. “ፍቅርኪ መጽሐፍ ዘኢያነብቦ ቈላፍ ዘይሜንነኪ በጸሪፍ ኢይጸድቅ በአፍ ወያንኅሎ ነደ ሰይፍ”
(ፍቅርሽ ያልተገዘረ ሰው የማያነብበው መጽሐፍ ነው፤ በመንቀፍ የሚንቅሽ ሰውም በአንደበት አይጸድቅም፤ የሰይፍ እሳትም ያፈርሰዋል?)
6. “ፍቅርኪ ኀየለ ከመ ዘዐቢይ ፈለግ መሊኦ እስከ ድንጋግ በጊዜ ጽምዑ ኢይሰትዮ ጸዋግ”
(ፍቅርሽ እስከ ከንፈሩ መልቶ እንደሚፈስስ የታላቅ ወንዝ ፈሳሽ በረታ፤ ክፉ ሰውም በጥማቱ ጊዜ አይጠጣውም)
7. “ሐሊበ ፍቅርኪ እግዝእትየ በዝቀ ኅሊናየ ተቶስሐ እምገይበ ከናፍር ዘተቀድሐ ለብእሲ ኀጥእ ዘይመይጦ በንስሓ”
(እመቤቴ ሆይ በደለኛውን ሰው ወደ ንሥሓ የሚመልሰው ከከንፈሮች ማሰሮ የተቀዳ የፍቅርሽ ወተት በዐሳቤ ማድጋ ተጨመረ)
ይኽ ከቊ140-143 የቅድስት ድንግል ማርያም ፍቅሯ ጣዕመ ፍቅሯ የበዛለት ሊቁ አባ ጊዮርጊስ በጠቢባን ልብ ውስጥ ስለሚያፈራው ከመናፍቃን ልቡና ስለተለየው፤ በቅዱሳን ልቡና የታተመውና የተጻፈው የልቡናቸውን የክፋት ሸለፈት ባልተቈረጡት ዘንድ ግን ፈጽሞ ስለራቀው፤ በፍጹማኑ ልቡና ግን እንደ ታላቅ ወንዝ ውሃ ማዕበል በመላ ሰውነታቸው ተሰራጭቶ እንደ ውሃ የሚጐነጩትና የሚረኩበት ፍቅሯ በክፉዎች ዘንድ ግን ፈጽሞ የማይታሰብ እንደኾነ እንደ ወርቅ አንከብሎ እንደ ሸማ ጠቅልሎ ከገለጸ በኋላ “እመቤቴ ሆይ በደለኛውን ሰው ወደ ንሥሓ የሚመልሰው ከከንፈሮች ማሰሮ የተቀዳ የፍቅርሽ ወተት በዐሳቤ ማድጋ ተጨመረ” በማለት በርሱ ኅሊና ውስጥ የበዛ ፍቅሯን በጥልቀት ገልጾታል፡፡ ይኸውም በአባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ መጽሐፈ ገድል ላይ እንደምናነብበው ይኽ ሊቅ ከዕለታት ባንዳቸው በእመቤታችን ሥዕል ሥር ወድቆ በሚጸልይበት ጊዜ ከእመቤታችን ሥዕል ተአምራታዊ ወተት ሲንጠባጠብ አይቶ ያንንም በቀመሰው ጊዜ ልቡ ብሩህ ኾኖለት “ኆኅተ ብርሃን” የሚል አስደናቂ የነገረ ማርያምን መጽሐፍ ጽፎላታል፡፡
ይኽ ልዩ ፍቅሯ በልቡናቸው በዝቶ እንዲያድር እንደ አባ ጊዮርጊስ የተመኙ ብዙዎች ቅዱሳን አሉ ለምሳሌ ሊቁ ቅዱስ ኤፍሬም ሸክላ ሠርቶ ከሚያገኘው ገቢ ላይ ለዕለት ጒርሡ ብቻ እያስቀረ የቅድስት ድንግል ማርያም ፍቅሯ ይጸናበት ነበርና በርሷ ስም ይመጸውት ነበር፤ እመቤታችንንም በእጅጉ ከመውደዱ የተነሣ ከሉቃስ ወንጌል “ወበሳድስን፣ ጸሎተ ማርያም” አውጥቶ በዕድሜዋ ልክ 64 64 ጊዜ እየጸለየ “የእመቤታችን ምስጋናዋ እንደ ሰማይ ኮከብ እንደ ባሕር አሸዋ በዝቶልኝ እንደ ልብስ ለብሼው ተጐናጽፌው እንደ ምግብ ተመግቤው ጠግቤው እያለ ሲመኝ ይኽነን ተምኔቱን አይታ ወደ ልጇ አሳስባ እልፍ ከአራት ሺሕ ድርሰት በመድረስ “አኀዝ እግዚኦ መዋግደ ጸጋከ” (አቤቱ የጸጋኽን ማዕበል ሞገድ ግታልኝ) አስኪል ደርሷል፡፡
በተመሳሳይ መልኩ ልክ እንደ ቅዱስ ኤፍሬም “የእመቤታችን ምስጋናዋ እንደ ሰማይ ኮከብ እንደ ባሕር አሸዋ በዝቶልኝ እንደ ልብስ ለብሼው ተጐናጽፌው እንደ ምግብ ተመግቤው ጠግቤው” እያለ ይመኝ ለነበረው ለትሑቱ ለአባ ሕርያቆስም ፍቅሯን አብዝታለት ቅዳሴ ማርያሟን እንዲደርስ ባርካዋለችና ሊቁ ከዚኽ ኹሉ በመነሣት የጣዕመ ፍቅሯን ታላቅነት በዚኽ ክፍል ላይ አስፍቶ ጻፈ፡፡
ስለዚኽ ልዩ ፍቅሯ ዳግመኛ በሰኞ የአርጋኖን መጽሐፉ ላይ “ወዘንተ ኲሎ አእሚርየ ኀሠሥኩ ኪያኪ ለረዲኦትየ ወተፈሣሕኩ በፍርቃንኪ ወበፍርቃነ ኢየሱስ ክርስቶስ ወልድኪ…” (ይኽነንም ኹሉ ዐውቄ ለርዳታዬ አንቺን ፈለግኊ፤ በአንቺና በልጅሽ በኢሱ ክርስቶስ ምስጋና ፈጽሜ ደስ ተሰኘኊ፤ ፍቅርሽም በሰውነቴ አዳራሽነት ፈጽሞ ተዘረጋ እጅግም ከፍ ከፍ አለ በዛም፤ እንደ ወንዝ ፈሳሽም መላኝ፤ በክረምት ወራት እንደ ግዮን ወንዝ፤ በአዝመራ ወራት እንደ ጤግሮስ ፈሳሽ፤ በእሸት ወራት እንደ ኤፍራጥስ ወንዝ፤ በእንጭጭ በጨርቋ ጊዜ እንደ ኤፌሶን ፈሳሽ፤ ጉምም በምድር ላይ እንዲጐተት ደመናም በአየር ላይ እንዲረብ ፍቅርሽ በእኔ ዘንድ ኾነ አንቺም በተድላዬ ጊዜ ሽልማት ኾንሽኝ፤ በደስታዬ ጊዜ ክብ ዘውዴ ኀቲም ቀለበቴ ነሽ፤ በሐሳቤም ኹሉ አንቺን አደንቃለኊ እንዲኽም እላለኊ፤ እግዚአብሔር የሰው ልጅ ለምትኾን ለድንግል ማርያም ምን ያኽል ጸጋና ክብርን ሰጣት) በማለት አመስግኗታል፡፡
ለአባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ ጣዕመ ፍቅሯን ያበዛችለት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ለእኛም ፍቅሯን እንደ ሰማይ ኮከብ እንደ ባሕር አሸዋ ታብዛልን አሜን፡፡
ከመጋቤ ሐዲስ ሮዳስ ታደሰ

                                   በአውሮጳ   የካህናት አንድነት ማኅበር ሊቋቋም መሆኑ ታወቀ በ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከመላዋ አውሮጳ   የተውጣጡ ካህናት፡” የ...