2015 ኖቬምበር 2, ሰኞ

ከቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ


አትም ኢሜይል
ጥቅምት 22 ቀን 2008 ዓ.ም
06tikm sinodosየኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ከጥቅምት 11-22 ቀን 2008 ዓ.ም ሲያካሔድ የቆየውን መደበኛ ስብሰባ በዛሬው ዕለት አጠናቋል፡፡

ከቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠውን መግለጫ እንደሚከተለው አቅርበነዋል፡፡
01tikm sinod
02tikm sinod
03tikm sinod
04tikm sinod
05tikm sinodos

ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ: በአ/አበባ ሀ/ስብከት በቅዱስ ሲኖዶስ የተመደበቡትን ሓላፊነት እንዳይወጡ መደረጋቸውን ተናገሩ፤“ሥልጣንን አላግባብ በመጠቀም ዐቢይ የሕግ ግድፈት ተፈጽሟል


?
ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ፡-
  • ከቅዱስ ፓትርያርኩም ኾነ ከጠቅላይ ጽ/ቤቱ ጋር በመልካም የሥራ ግንኙነት ላይ ነበርኩ
  • የአ/አበባ ሀ/ስብከትን ኹለት ሥራ አስኪያጆች የመለመለውና ያቀረበው አካል አይታወቅም
  • ሒሳቡን እንዲያንቀሳቅሱ ሌላ ፈራሚ ሊቀ ጳጳስ የተመደቡበት ኹኔታ አሳዛኝ ክሥተት ነው
  • በረዳት ሊቀ ጳጳስነት የመደበኝ ምልዓተ ጉባኤው፣ ለቤተ ክርስቲያን የሚበጅ መፍትሔ ይስጠኝ
በምልአተ ጉባኤው ስብሰባ፡-
  • ልዩ ደንብና መመሪያ ባልወጣበት የፓትርያርኩ ልዩ ሀ/ስብከት መኾኑ ክፍተት ፈጥሯል
  • የፓትርያርኩ፣ የረዳት ሊቀ ጳጳሱና የሥራ አስኪያጁ ተግባርና ሓላፊነት መታወቅ አለበት
  • በሚሻሻለው ቃለ ዐዋዲ የሦስቱ ሓላፊዎች ሥልጣንና ተግባር ተካቶ እንዲቀርብ ተወስኗል
  • ፓትርያርኩ ያለረዳት ሊቀ ጳጳሱ ምርጫ ሥራ አስኪያጆችን በመሾም የሕግ ግድፈትና ጣልቃ ገብነት የፈጸሙበትን አካሔድ በመደገፍ “ሕመም ቢኖርብኝም የሥራ ፍላጎት አለኝ” በሚል በአዲስ አበባ ለመመደብ የጠየቁት ሊቀ ጳጳስ ክፉኛ ትዝብት ላይ ወድቀዋል
*            *            *
ጥቅምት 15 ቀን 2008 ዓ.ም.
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን
ለቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ
አዲስ አበባ
ጉዳዩ፡- በቅዱስ ሲኖዶስ በተሰጠኝ የሥራ ሓላፊነት ላይ ከሕገ ቤተ ክርስቲያኑና ከቃለ ዐዋዲው ውጭ በደል በመፈጸሙ፤ የተፈጸመውን የሥራና የሕግ ግድፈት በቅዱስ ሲኖዶሱ ለማሳረምና ትክክለኛ ፍትሕ እንዲሰጠኝ የቀረበ አቤቱታ ነው
ብፁዕ ወቅዱስ አባታችን፤ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት አባቶቼ፤ እንደሚታወቀው ኹሉ በጥቅምት 2007 ዓ.ም. በመንፈስ ቅዱስ መሪነት እና የበላይነት በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ለአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በቤተ ክርስቲያኗ ሕግ መሠረት የቅዱስ ፓትርያርኩ ረዳት ሊቀ ጳጳስ በመኾን መመደቤ ይታወቃል፡፡
እኔም በዚህ በመንፈስ ቅዱስ በሚመራው ታላቅ ጉባኤ እና በአባቶቼ የተሰጠኝን ሓላፊነትና አደራ ከተመደብኩበት ጊዜ አንሥቶ አቅሜ በፈቀደ መልኩ ያለውን ነባራዊ ኹኔታ በማገናዘብ ከቅዱስ ፓትርያርኩ ጋር በመመካከር የጠቅላይ ቤተ ክህነቱንም የሥራና የደረጃ መዋቅርን በመጠበቅ እያገለገልኩ እገኝ ነበር፤ ለዚህም እንደ ማሳያ፡-
ሀ/በሀገረ ስብከቱ የባለጉዳዮች መስተንግዶ ሥርዐት ዘመናዊና ቀልጣፋ እንዲሁም ተጠያቂነት ያለው እንዲኾን በማድረግ የተለያዩ አደረጃጀቶችን ሊጠቅም በሚችል መልኩ በማውጣት፤
ለ/የንብረትና የገንዘብ አጠባበቅ ኹኔታ በመረጃ የተደራጀ እና ዘመናዊ አሠራር እንዲኖረው በማድረግ፤
ሐ/በመንግሥት በኩል ቤተ ክርስቲያኗ ያላትን መብትና ጥቅም በመገንዘብ ከቀረጥ ነጻ በኾነ መንገድ ለቅዱስ ፓትርያርኩ እና ለሀገረ ስብከቱ የትራንስፖርት መገልገያ የሚውሉ መኪናዎች እንዲገቡ ጥረት በማድረግ፤
መ/ሀገረ ስብከቱ የሚያከናውናቸው ሥራዎች በአጠቃላይ በተጠና ዕቅድ እንዲሠራ፤ የየክፍሎቹ ሓላፊዎች በሚለካና ሊደረስበት በሚችል መልኩ ዕቅድ እንዲዘጋጅና የቀረበው ዕቅድም በአስተዳደር ጉባኤው ተገምግሞ ሥራ ላይ እንዲውል መመሪያ በመስጠት ስንሠራ ቆይተናል፡፡
ከላይ ለማሳያነት የጠቀስኋቸው ተግባራት ብዙ ጠለቅ ያለ የአፈጻጸም ሒደቶች ቢኖሯቸውም አቅም በፈቀደ መልኩ ስንቀሳቀስ ቆይቼ ነበር፡፡
ኾኖም ከቅዱስ ፓትርያርኩም ኾነ ከጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ጋር በመልካም የሥራ ግንኙነት፣ በቤተ ክርስቲያኗ ሕግና መመሪያ መሠረት አባቶቼ የሰጣችኹኝን የሥራ ሓላፊነት በመወጣት ላይ ነበርኩ፡፡
ይኹንና ዐቢይ የሕግ ግድፈት በመፈጸሙ ምክንያትና ሥልጣንን አለአግባብ በመጠቀም ጣልቃ ገብነት ሥራዬን በሓላፊነት እንዳላከናውን ተደርጌአለኹ፡፡ ከዕንቅፋቶቹና ከተፈጸሙት የሕግ ስሕተቶችም መካከል፤
1/ በጥቅምት ወር 2007 ዓ.ም. በቅዱስ ሲኖዶስ ጸድቆ በወጣው ሕገ ቤተ ክርስቲያን አንቀጽ 50፣ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ሀገረ ስብከት ነው፤ ካለ በኋላ በንኡስ ቁጥር ሦስት፣ ሀገረ ስብከቱ የሚገኘው የሀገሪቱ ርእሰ ከተማ ላይ እንደ መኾኑ መጠን ከሌሎች አህጉረ ስብከት የሚለይባቸው ልዩ ኹኔታዎች ስላሉ እኒኽን ኹኔታዎች ከግምት ያስገባ ለየት ያለ አደረጃጀት በቃለ ዐዋዲው እንዲኖረው እንደሚደረግ ይገልጻል፡፡
በዚህ መሠረት ልዩ መመሪያ ባልወጣበት ኹኔታ አንቀጹን በሌላ መንገድ በመተርጎምና ምክንያቱን በግልጽ ባላወቅሁት መንገድ ሕገ ቤተ ክርስቲያን አንቀጽ 53 ንኡስ ቁጥር 8ን በመተላለፍ፤
1.1) ሊቀ ጳጳሱ ለሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ መልምለው ለቅዱስ ፓትርያርኩ ሳያቀርቡና በሕጉም መሠረት የጋራ ስምምነት ሳይኖረን፤
1.2) በመቀጠልም በሕጉ መሠረት የረዳት ሊቀ ጳጳሱንና የቅዱስ ፓትርያርኩን ይኹንታ መሠረት አድርጎ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ማጽደቅ ሲገባው ይህ መሠረታዊ ሒደት ባልተፈጸመበት ኹኔታ፤
1.3) መልማዩና አቅራቢው በውል ማን እንደኾነ ባልታወቀበትና ሕግ በማይፈቅደው መልኩ በፓትርያርኩ ቀጥተኛ የሹመት ደብዳቤ ሥራ አስኪያጅ እና ምክትል ሥራ አስኪያጅ ለሀገረ ስብከቱ በመመደቡ ምክንያት ሀገረ ስብከቱ ከፍተኛ ቀውስ ውስጥ ገባ፡፡
2. እኒህን ዋነኛ የሕግ ግድፈቶች በመዘርዘር ጉዳዩ በቅዱስ ፓትርያርኩ እንዲታረም በመጀመሪያ በ11/07/2007 ዓ/ም በመቀጠልም በ16/07/2007 ዓ/ም በተጻፈ ደብዳቤ ጠይቄ ነበር፤ ነገር ግን ምላሽ አልተሰጠኝም፡፡ በተጨማሪም ጉዳዩ በቋሚ ሲኖዶስ ትኩረት ተሰጥቶት እንዲታረም በ17/7/2007 ዓ/ም አቅርቤ ነበር፡፡
3. ያለሊቀ ጳጳሱ አቅራቢነትና መልማይነት፣ ያለጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ጽ/ቤት ዕውቅናና አጽዳቂነት ከሕግ ውጭ በቀጥታ በቅዱስ ፓትርያርኩ ለሀገረ ስብከቱ የተሾሙት ሥራ አስኪያጅ፣ የቃለ ዐዋዲውን አንቀጽ 45 ንኡስ ቁጥር 7ን በመተላለፍ፣ አሳማኝ እና ምክንያታዊ ባልኾነ መንገድ በሀገረ ስብከቱ በክፍል ዋና ሓላፊነት ተመድበው የሚሠሩትን ሠራተኞች በ30/08/2007 ዓ/ም ያለሀገረ ስብከቱ ረዳት ሊቀ ጳጳስ ዕውቅናና ፈቃድ የተወሰኑትን ከደረጃ ዝቅ በማድረግ፣ የቀሩትንም እዚያው ባለው የሥራ ክፍል አዘዋወሩ፡፡
ከዋና ክፍል ሓላፊዎቹ በቀረበልኝ አቤቱታ፤ ሕጉን የጣሰና ምክንያቱ በትክክል ያልታወቀ ዝውውርና ከደረጃም ዝቅ ማድረግ በመኾኑ በተጨማሪም ሠራተኞች በተሰማሩበት የሥራ መስክ ላይ ተረጋግቶ የመሥራት መብትን የሚያሳጣ በመኾኑ ባለኝ ሥልጣንና ሓላፊነት መሠረት በ30/08/2007 ዓ/ም ዝውውሩንና ከደረጃ ዝቅ ማድረጉን አገድኩ፡፡ ይህም በሕጉ መሠረት ተጢኖ መታየትና መገምገም ሲኖርበት የቃለ ዐዋዲውን አንቀጽ 60 ቁጥር 2 ፊደል (ሰ)እና(ሸ) ያለአግባብ በመጥቀስና በመጠቀም በ4/9/2007 ዓ/ም በቅዱስ ፓትርያርኩ በተፈረመ ደብዳቤ እኔ ያስተላለፍኩት ሕጋዊ እግድ ያለአግባብ ተሻረ፡፡
4. ይህ በእንዲህ እንዳለ በ24/09/2007 ዓ/ም ከቅዱስ ፓትርያርኩ በተጻፈ ደብዳቤ በሥራ ገበታዬ ተገኝቼ ሥራዬን እንድቀጥል ደብዳቤ ደረሰኝ፡፡ እኔም በ25/09/2007 ዓ/ም ለደብዳቤው፣ በቅን ልቡና ሥራዬን እየሠራሁ መኾኑን፤ የሠራተኞችን ደመወዝ፣ የሚታወቁና አይቀሬ የኾኑትን የሀገረ ስብከቱን ዕለታዊ የሥራ ማስኬጃ ወጪዎችንም እየፈረምኩ ሥራዎች እየተከናወኑ እንደኾነ በመግለጽ ሥራዬን እንደምሠራ አሳወቅሁ፤ ነገር ግን ባልተለመደ አኳኋን ገንዘብን በሚመለከት ሌላ ሊቀ ጳጰስ እንደተመደበ ሰማኹ፤ ይህ አሳዛኝ ክሥተት ነው፡፡
ስለዚህም በረዳት ሊቀ ጳጳስነት መመደቤን በመወሰን ሥልጣኑንና ሓላፊነቱን የሰጠኝ ይህ ምልዓተ ጉባኤ እንደ መኾኑ፣ ለቤተ ክርስቲያናችን በሚበጅ አካሔድ መፍትሔ ይስጠኝ ዘንድ እጠይቃለኹ፡፡
እግዚአብሔር ኢትዮጵያን ይባርክ

                                   በአውሮጳ   የካህናት አንድነት ማኅበር ሊቋቋም መሆኑ ታወቀ በ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከመላዋ አውሮጳ   የተውጣጡ ካህናት፡” የ...