2014 ኦክቶበር 13, ሰኞ

‹ቀራንዮ፣ መድኃኔዓለም፣ ካህናቱ›

                                                                                  
ቅዱስ ጳውሎስ ተከስሶ በቂሣርያው ገዥ በፊስጦስ ፊት በቀረበ ጊዜ አይሁድ ለብቻቸው ቀርበው በቅዱስ ጳውሎስ ላይ ይፈርድበት ዘንድ ጎትጉተውት፣ እነርሱ ማስረጃ ያሉትንም አቅርበውለት፣ ሕጋቸውንም ጠቅሰው ማሳመኛ አቅርበውለት ነበር፡፡ አሕዛባዊው ገዥ ፊስጦስ ግን እግዚአብሔርን እናውቃለንም፣ እንፈራለንም ከሚሉት አይሁድ ተሽሎ ያሉትን ከማድረግ ራሱን ከለከለ፡፡
ከጥቂት ቀናት በኋላ ንጉሥ አግሪጳና በርኒቄ ወደ እርሱ በመጡ ጊዜ ጉዳዩን አቀረበላቸው፡፡ ፊስጦስ አይሁድ ያቀረቡትን ስሞታ፣ ውትወታና ክስ ተቀብሎ በቅዱስ ጳውሎስ ላይ ያልፈረደበትን ምክንያት ለአግሪጳ ሲገልጥለት ‹‹ተከሳሹ በከሳሾቹ ፊት ለፊት ሳይቆም፣ ለተከሰሰበትም መልስ ይሰጥ ዘንድ ፈንታ ሳያገኝ፣ ማንንም ቢሆን አሳልፎ መስጠት የሮማውያን ሥርዓት አይደለም›› ብሎ መሆኑን ነግሮታል (የሐዋ.25÷16)፡፡
ይህ በሮማውያን ዘመን እጅግ የታወቀውን ራስን በእኩል ደረጃ የመከላከል መብት በተመለከተ ሮማዊው ታሪክ ጸሐፊ አፒያን (95-165ዓም) በጻፈው Civil War በተሰኘው መጽሐፉ (3:54) ላይ ‹‹የምክር ቤት አባሎች፣ ሕጉ የተከሰሰ ሰው የተከሰሰበትን ሰምቶ በእርሱ ላይ ከመፈረዱ በፊት መልስ የመስጠት መብት አለው ይላል›› ሲል አሥፍሮት ነበር፡፡ ፊሊክስ የጠቀሰው ይኼንን ነው፡፡ አበው በትርጓሜያቸው ‹አሕዛብ ፍርድ ይጠነቅቃሉ›› ሲሉ የመሰከሩት እንዲህ ያለው የሮማውያንን ሕግ ነው፡፡ ለዚህ ጥንቁቅ የፍርድ ሥርዓትም ሲሉ አያሌ የሮማውያንን የፍተሕና የፍርድ ሐሳቦች በቤተ ክርስቲያን የፍትሕ ሥርዓት ውስጥ (በቀኖና) እንዲገቡና እንዲሠራባቸው አድርገዋል፡፡


ይህንን የምትተረጉምና የምታስተምርን ቤተ ክርስቲያን እንወክላለን የሚሉ ሰዎች ናቸው ሰሞኑን ተሰብስበው ተከሳሹ በሌለበት ፍርድ ሲሰጡ ያየናቸው፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን ተሳሳተ ተብሎ እንኳን ቢሆን ቤተ ክርስቲያኒቱ ለአርዮስና ለንስጥሮስ፣ ለመቅዶንዮስና ለሰባልዮስ የሰጠችውን መብት ቤተ ክህነቱ ለማኅበረ ቅዱሳን ሊነፍገው አይገባም ነበር፡፡ በቀደዱላቸው ቦይ መንጎድ፣ ተጠልቷል ብለው በሚያስቡት ላይ መፍረድ ሃይማኖታቸው የሆነ፤ ፓትርያርኩን ምን ያስደስታቸዋል እንጂ የትኛው እውነት ነው ለሚለው የማይጨነቁ ሰዎች የክስ መዓታቸውን ሲያዘንቡ ማኅበሩ መልስ እንዲሰጥ ዕድል ሊሰጠው ይገባ ነበር፡፡ ነገር ግን ሰዎቹ ለበዓሉ የሚስማማውን ቀለም ትተው ለባለ ሥልጣኑ የሚስማማውን ቀለም መረጡ፡፡ ሊቁ ክፍለ ዮሐንስ ‹ካህን ከመሆን እረኛ መሆን ይሻላል› እንዳለው ከቤተ ክህነት ፊልክስ ተሽሏል፡፡
ፊሊክስ ለቅዱስ ጳውሎስ፣ ሠለስቱ ምእት ለአርዮስ፣ ማኅበረ ኤፌሶን ለንስጥሮስ የሰጡትን ዕድል ቤተ ክህነቱ ለማኅበረ ቅዱሳን ለመስጠት ፈቃደኛ አልሆነም፡፡ ለምን?
ሰዎቹ እውነቱን ለመጋፈጥ ዐቅም አንሷቸዋል ማለት ነው፡፡ የሚሉት ነገር የሆኑ አካላትን ስለማስደሰቱ እንጂ እውነት ስለመሆኑ ርግጠኞች አይደሉም፡፡ ስለዚህም ተከራካሪያቸውን ለመስማትና የእነርሱ ‹እውነት› ሲሞገት ለማየት ዐቅም ያንሳቸዋል፡፡ ወይም ደግሞ
ከክርክሩ በፊት ውሳኔውን ወስነው ጨርሰዋል፡፡ ፓትርያርክ አቡነ ቴዎፍሎስን ለደርግ አሳልፈው የሰጡት የቤተ ክህነት ሰዎች እንዲህ ነበር ያደረጉት፡፡ ፓትርያርኩን አሳልፈው ሰጥተዋል፡፡ ውሳኔውን ወስነዋል፡፡ ነገር ግን ለውሳኔው ምክንያት መፈለግ ነበረባቸው፡፡ ስለዚህም አቡነ ቴዎፍሎስ ሠሩ ያሏቸውን ጥፋቶች ለብቻቸው ተሰብስበው፣ ‹በደላቸውን› ዘርዝረው፣ እርሳቸው መልስ ሊሰጡ በማይችሉበት ሁኔታ ለደርግ አስተላለፉ፡፡ እነዚህ ሰዎች ለብቻቸው መሰብሰብ የፈለጉት፣ የፓትርያርኩንም መልስ የመስጠት መብት የነፈጉበት አንዱ ምክንያት ፓትርያርኩ በሚሰጡት መልስና በሚያቀርቡት ማስረጃ እውነታቸው ነፋስ ያየው ገለባ እንዳይሆንባቸው ነው፡፡ ወይም
እነዚህ ሰዎች የራሳቸውን ሥራ አይደለም እየሠሩ ያሉት፡፡ ቤተ ክርስቲያኒቱን ሲበጠብጡ የኖሩት ካህናተ ደብተራ (ከቤተ ክህነት ደመወዝ እየወሰዱ ለቤተ መንግሥት ሲሠሩ የኖሩ ካህናት ነን ባዮች) ዋናው መለያቸው የሚሠሩት የራሳቸውን ሥራ አለመሆኑ ነው፡፡ የመለካዊነት ጠባይ ስላላቸው ሌሎች ተናገሩ የሚሏቸውን ይናገራሉ፣ ፈጽሙልን የሚሏቸውን ይፈጽማሉ፤ አውግዙልን የሚሏቸውን ያወግዛሉ፤ አጽድቁልን የሚሏቸውንም ያጸድቃሉ፡፡ የሚሠሩት ሥራ የላኳቸውን ሰዎች ማርካቱን እንጂ የሚያስከትለውን ነገርና የሚያስከፍለውን ዋጋ አያውቁትም፡፡ እነዚህ ነበሩ አባ በጸሎተ ሚካኤልን ያሰደዱት፣ እነዚህ ነበሩ አባ ፊልጶስን ያንከራተቱት፣ እነዚህ ነበሩ እጨጌ ዕንባቆምን ለልብነ ድንግል ከስሰው ምንም ባላጠፋው ጥፋት ‹ጉንጽ› በተባለው ዓለም በቃኝ እስር ቤት ያሳሠሩት፤ በኋላም ለሀገሪቱ ጥፋትን ያመጡት፡፡ ጥይት የመታው ሰው ተናድዶ ‹‹ምነው እንዲህ ታበላሸኝ›› ቢለው ‹‹እባክህ እኔ አይደለሁም፣ እኔ ተተኮስኩ እንጂ ተኳሹ ሌላ ነው፤ እኔ መልክተኛ ነኝ›› አለው፡፡ ‹‹ተኳሹ የት አለ?›› ቢለው ‹‹እርሱማ አይታይም ተደብቆ ነው የሚተኩሰው፤ እርሱ ስለሚደበቅኮ ነው እኔ የመጣሁት›› አለው ይባላል፡፡
ወይም እነዚህ ሰዎች ስንፍናቸውን የሚያሳይባቸውን፣ ድካማቸውን የሚገልጥባቸውን፣ ሊያጠፉት ወድደዋል፡፡ ሰውዬው ዶሮውን በጦም አርዶ ለምን አረድከው ቢባል ‹‹እሱ ነው ጠዋት እየተነሣ መንጋቱን የሚያሳብቅብኝ፣ አርፌ እንዳልተኛበት፡፡እርሱ ባይጮህ ኖሮ መንጋቱን ማን ያውቅ ነበር? ተኛህ ብሎስ ማን ይከሰኝ ነበር›› አለ አሉ፡፡ ከመንቃት ይልቅ ማንቂያውን ማጥፋት፡፡ የ13ኛው መክዘ የደቡብ ሐዋርያ አቡነ አኖሬዎስ ታላቁ በካህናተ ደብተራ ተከስሶ ወደ ንጉሥ ሰይፈ አርእድ የቀረበበት ክስ አስቂኝ ነበር፡፡ ‹‹ከንጉሡ የሚበልጥ ቤተ ክርስቲያን ሠርቷል›› ነበር የተባለው፡፡ ጉዳዩን ሊያጣራ የሄደው የጉዳም አለቃ ያገኘው ቤተ ክርስቲያን ግን እንደተባለው አልነበረም፡፡ ነገር ግን ከክሱ ንጹሕ መሆኑ ቅጣቱን አላስቀረለትም፡፡ ከገዳሙ ወጥቶ በወለቃ በረሃ እንዲከራተት ሆኗል፡፡ ምናለ ከንጉሡ የሚበልጥ ቤተ ክርስቲያን ቢሠራ? የሚያስመሰግነው እንጂ የሚያስነቅፈው አልነበረም፡፡ ለካህናተ ደብተራ ግን ይኼ ስንፍናቸውን ይገልጠዋል፣ እንደ አውራ ዶሮውም መተኛታቸውን ያሳይባቸዋል፡፡
ቅዱስ ሲኖዶሱ አሁን መስቀለኛ መንገድ ላይ ቆሟል፡፡ የሚቀርቡት ክሶች ለምን ቀረቡ ማለት አይቻልም፡፡ ነገር ግን በአይሁድ አደባባይ ፍርድ ሲጓደል፣ እንደ ጲላጦስ ሚስት የሚያስጠነቅቅ ያስፈልጋል፡፡ ገለልተኛ አካል አቋቁሞ የተባሉትን ያጣራ፡፡ ራሱ የማኅበሩ አመራር ለተከሰሰበት መልስ ይስጥ፡፡ አሕዛባዊው ፊሊክስ ለቅዱስ ጳውሎስ የሰጠውን መብት ሲኖዶሱ ለማኅበሩ መስጠት አለበት፡፡ ተጣርቶ በተገኘው ማስረጃና ምስክር መሠረት ውሳኔ ይሰጥ፡፡ ጥፋተኛው ይታረም፤ እውነተኛው ይገለጥ፡፡
በዐፄ ኃይለ ሥላሴ ዘመን ቀራንዮ መድኃኔዓለም አለቅነት ተሾመው የሄዱትን አባት ካህናቱ አስቸገሯቸው፡፡ ለጥቂት ጊዜ የተላኩበትን ሊሠሩ ሞከሩ ግን አልሆነም፡፡ በመጨረሻም ለንጉሡ እንዲቀይሯቸው አመለከቱ፡፡ ንጉሡም ምነው ምን ገጠመህ? ቢሏቸው ‹‹ካህናቱም ካህናቱ፣ ቀራንዮም ቀራንዮ፣ መድኃኔዓለምም መድኃኔዓለም›› አሉ ይባላል፡፡ ሰቃይ ተሰቃይና የመስቀያ ቦታ አንድ ሲገናኙ ያ ነው ክፉ ዘመን፡፡
ማኅበሩን እንደ ተቋም፣ እንደ ጽ/ቤትና እንደ ድርጅት ማፍረስ ቀላል ነው፤ እንደ አስተሳሰብ፣ እንደ አመለካከት፣ እንደ የአገልግሎት መሥመርና አተያይ ግን ማፍረስ አይቻልም፡፡ ዛሬ ማኅበሩን በማፍረስ የሚጀመረው አጥር ንቅነቃ ግን መጨረሻው ሲኖዶሱን በማደንበሽ እንዳይጠናቀቅ ያሰጋል፡፡ ባለቤቱን ካልናቁ ነውና፡፡ 

2014 ኦክቶበር 10, ዓርብ

ማኅሌተ ጽጌ (Part One

 
 
ማኅሌተ ጽጌ፤ ምንጩ ትርጉሙ መልእክቱ 
           ይህ ድርሰት በማንኛውም ጊዜ የሚጸለይ ቢሆንም በተለየ ሁኔታ በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የሚውለው ከመስከረም 26 እስከ ኅዳር 5 ቀን ድረስ ባለው የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም የስደት ዘመን ነው፡፡ በዚህ ወቅት በየሳምንቱ እሑድ ሌሊት በሙሉ የእመቤታችንን ከልጇ ጋር ወደ ግብፅ መሰደድና መንከራተት እያሰቡ የሚደረስ ምሥጋናና ጸሎት ነው፡፡
             በሀገራችን የመስከረምና የጥቅምት ወራት የአበባ ወራት /ዘመነ ጽጌ/ ናቸው፡፡ ይህም ወቅት ተራሮች በአበባ የሚያጌጡበትና ለዓይን ማራኪ የሚሆኑበት ጊዜ ነው፡፡ በዚህም ዘመን ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ «ስለ ልብስስ ስለምን ትጨነቃላችሁ) የሜዳ አበቦች እንዴት እንዲያድጉ ልብ አድርጋችሁ ተመልከቱ፡፡ አይደክሙም፣ አይፈትሉም፤ ነገር ግን እላችኋለሁ ሰሎሞንስ ስንኳ በክብሩ ሁሉ ከእነዚህ እንደ አንዱ አልለበሰም፡፡ እግዚአብሔርን ዛሬ ያለውን ነገም ወደ እቶን የሚጣለውን የሜዳን ሣር እንዲህ የሚያለብሰው ከሆነ እናንተ እምነት የጐደላችሁ እናንተንማ ይልቁን እንዴት እንግዲህ ምን እንበላለን ምንስ እንጠጣለን) ምንስ እንለብሳለን) ብላችሁ አትጨነቁ ...» /ማቴ.5÷28-33/ በማለት የተናገረውን ቃል በማሰብ መጨነቅ የሚገባን መንግሥተ ሰማያት ለመግባት እንጂ በዚህ ዓለም ስላለው ነገር እንዳልሆነ ተራሮችን በአበባ ያለበሰ አምላክ በአርአያውና በአምሳሉ የፈጠረንን እኛን ለኑሮ የሚያስፈልገንን ምግብና ልብስ እንደማይነሳን እያሰብን የምንዘክርበት ወቅት ነው፡፡
                እንዲሁም ክቡር ዳዊት «ተዘከር እግዚኦ ከመ መሬት ንሕነ ወሰብእሰ ከመ ሳዕር መዋዕሊሁ ወከመ ጽጌ ገዳም ከማሁ ይፈሪ፤ አቤቱ እኛ አፈር እንደሆን አስብ ሰውስ ዘመኑ እንደሣር ነው እንደ ዱር አበባ እንዲሁ ያብባል ነፋስ በነፈሰበት ጊዜ ያልፋልና» /መዝ.12÷14-16/ በማለት እንደ ተናገረው የሰው ሕይወት በሣር ይመሰላል፡፡ ሣር አድጐ አብቦ ከዚያ በኋላ ይደርቅና በነፋስ አማካኝነት የረገፈው ሣር እየተነሣ የነበረበት ቦታ ስንኳ እስከማይታወቅ ድረስ ይሆናል፡፡ ሰውም ከአደገ በኋላ በሕማም ፀሐይነት ይደርቅና በሞት ነፋስነት ይወሰዳል፡፡ ከዚያ በኋላ ወደ መቃብር ሲወርድ የነበረበት ቦታ ይዘነጋል፡፡ ስለዚህ ዘመነ ጽጌ ሰው ዘመኑ እንደ አበባ በቶሎ የሚረግፍ መሆኑን በማሰብ ይህ ዘመን ሳያልፍ መልካም ሥራ ለመሥራት ትንሣኤ ኅሊና የሚነሣበት ጊዜ ነው፡፡ ቅዱስ ያሬድ ለዘመነ ጽጌ የሠራው ድጓም ይህንኑ የሰውን ዘመን አጭርነት የሕይወቱን ኢምንትነት በዚህ ሕላዌ የተፈጠረ ሰው በዚህ ዓለም ክፉ ሥራ መሥራት እንደሌለበት ሁልጊዜ በተዘክሮተ ሞት እንዲኖር የሚያስረዳ ነው፡፡
                     በዘመነ ጽጌ ቅዱስ ያሬድ ከደረሰው ድጓ በተጨማሪ ከላይ እንደተጠቀሰው 14ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የተነሣ አባ ጽጌ ድንግል ከዚሁ ዘመን ጋር የተያያዘ ድርሰት ደርሷል፡፡ ይህ ድርሰት በግጥም መልክ የተደረሰ በአብዛኛው አምስት ስንኞች ያሉት ሲሆን ብዛቱም 15 ያክል ነው፡፡ ይህም ድርሰት «ማኅሌተ ጽጌ» በመባል የሚታወቀው ነው፡፡ ፍሬ ከአበባ አበባም ከፍሬ እንደሚገኘው ሁሉ ማኅሌተ ጽጌም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምንና ልጇን መድኃኒታችንና አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስን በአበባና በፍሬ እየመሰለ የሚያስረዳ ድርሰት ነው፡፡ እርሷን በአበባ ሲመስል ልጇን በፍሬ እርሷን በፍሬ ሲመስል ደግሞ ልጇን በአበባ እየመሰለ ይናገራል፡፡ ነቢዩ ኢሳይያስ «ትወጽእ በትር እምሥርወ እሴይ ወየዓርግ ጽጌ እምጉንዱ፤ ከእሴይ ግንድ በትር ይወጣል፤ ከሥሩም ቁጥቋጦ ያፈራል»  /ኢሳ.11÷1/ ብሎ ከእሴይ ዘር የምትገኘውን እመቤታችንን በበትር ከርሷ የሚገኘውን ክርስቶስን ደግሞ በጽጌ መስሎ ትንቢቱን ተናግሯል፡፡ አባ ጽጌ ድንግልም ድርሰቱን በዚሁ አንጻር በመቀመር እያንዳንዱን መልክዕ እመቤታችንንና ልጇን አስተባብሮ በጽጌና በፍሬ በመመሰል የእግዚአብሔርን ድንቅ ሥራ በምሥጢር በታሪክ፣ በጸሎትና በመሳሰለው መልክ ድንቅ በሆነና በተዋበ ሁኔታ አዋሕዶ ደርሶታል፡፡
                                                                                                                  
                     እመቤታችን ጣዕሟንና ፍቅሯን እንዲሁም ምስጋናዋን ሲናፍቁ የነበሩትን ቅዱስ ኤፍሬምንና አባ ሕርያቆስን ውዳሴዋንና ቅዳሴዋን እንደገለጸችላቸው ለፍቅሯ ሲሳሳ ለነበረው ለአባ ጽጌ ድንግል ደግሞ ይህንን ማኅሌተ ጽጌን እንዲደርስ አድርጋዋለች፡፡ ከላይ እንደተገለጸው ማኅሌተ ጽጌ በመልክዕ አደራረስ ሥርዓት የተደረሰ ሲሆን ይህንንም ለመመልከት እንዲያመች በሚከተሉት ክፍሎች ከፋፍሎ ማቅረብ ይቻላል፡፡
1. ጸሎት
            በዚህ አገባብ ጸሎት ስንል በተለየ ሁኔታ ጸሎትነቱ የጐላውን ለማየት እንጂ ድርሰቱ በሙሉ ጸሎት ነው፡፡ ሌሎቹንም እንዲሁ ታሪክ፣ ተግሳጽ፣ ምሥጢር ተብለው መከፈላቸው በበዛውና በጐላው ለመግለጽ ነው እንጂ ሁሉም በሁሉ አለ፡፡ በጸሎትነታቸው ጐልተው ከሚታዩት ውስጥ የተወሰኑትን እንመለከታለን፡፡
1.1.  አንብርኒ ማርያም ውስተ ልብኪ ከመ ሕልቀት፣
ወከመ ማዕተብ ፁርኒ በመዝራዕትኪ ልዕልት፣
በእንተ ርስሐትየሰ ኢትመንንኒ ንግሥት፣
እስመ ወሀብኩ ንብረትየ ለፍቅርኪ ሞት፣
ዘአሰገርዎሙ ለሰማዕት በጽጌሁ ሕይወት፡፡
              ጠቢቡ ሰሎሞን «የምእመናንንና የክርስቶስን ነገር በምሥጢር በተናገረበት በመኃልይ መጽሐፉ «እንደ ማኅተም በልብህ እንደ ማኅተም በክንድህ አኑረኝ» /መኃ.9÷6/ ይላል፡፡ ይኸውም የምእመናንንና የክርስቶስን አንድነት የሚገልጽ ነው፡፡ «አንብርኒ ማርያም ውስተ ልብኪ ከመ ሕልቀት፤ ወከመ ማዕተብ ፁርኒ በመዝራዕትኪ ልዕልት» ማለቱ እመቤታችንን እንደ


ማኅተም በልብሽ አኑሪኝ በማለት በእናትነትሽ፣ በአማላጅነትሽ አትርሽኝ ካለ በኋላ «በእንተ ርስሐትየሰ ኢትመንኒ ንግሥት» ይላል፡፡ ይኸም ማለት አትርሽኝ በልብሽ አኑሪኝ ብዬ የምለምንሽ አንቺ እንዳትረሽኝ የሚያደርግ መልካም ሥራ ኖሮኝ አይደለም፡፡ ስለዚህ በሰውነቴ ክፋት ምክንያት በኃጢ አቴና በወራዳነቴ ምክንያት እኔን ከማሰብ ከልቡናሽ አታውጪኝ በማለት እመቤታችን በርኅሩኅ ልቧ «መሐር ወልድየ ወተዘከር ኪዳንየ» እያለች እንድታዘክረን የሚያሳስብ ጸሎት ነው፡፡
ሶበ አተቦ ለማይ በቅዳሴኪ እንዘ ይጼሊ፣
ረሰዮ ኅብስተ ጽጌ ሃይማኖት ሳሙኤል ዘሐቅለ ዋሊ፣
ምሕረተ ወፍትሐ ለተአምርኪ አኀሊ፣
ሥረዪ ኃጢአትየ ወእጸብየ አቅልሊ፣
እስመ ኩሎ ገቢረ ማርያም ትክሊ፡፡
            አባ ሳሙኤል ዘዋልድባ ቅዳሴ ማርያምን እየደገሙ ውኃው በተአምራት ኅብስት ይሆንላቸው ነበር፡፡ ይህን ተአምር ከአደነቀ በኋላ «ማርያም ሆይ ሁሉን ማድረግ ትችያለሽና ኃጢአቴን አስተስርይልኝ» ይላል፡፡ ጌታችን «እውነት እላችኋለሁ የሰናፍጭ ቅንጣት የሚያህል እምነት ቢኖራችሁ ይህን ተራራ ከዚህ ወደዚያ እለፍ ብትሉት ያልፋል፤ የሚሳናችሁም ነገር የለም» /ማቴ.17÷1/ በማለት ላመነ የሚሣነው ነገር እንደሌለ ተናግሯል፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም መልአኩ «ትጸንሻለሽ፣ ትወልጃለሽ ...» ብሎ ባበሠራት ጊዜ ይህ እንደምን ይሆንልኛልብላ ስትጠይቅ «ለእግዚአብሔር የሚሳነው ነገር የለም» ሲላት በፍጹም እምነት ይኩነኒ በከመ ትቤለኒ እንደቃልህ ይሁልኝ» በማለት የተቀበለች ናት፡፡ ይህንንም ቅድስት ኤልሳቤጥ መንፈስ ቅዱስን ተመልታ «ከጌታ የተነገረላት ቃል ይፈጸማልና የታመነች ብፅዕት ናት» /ሉቃ.1÷453 ብላ መስክራለች፡፡ ላመኑ ሁሉ የሚቻል ከሆነ እመቤታችን ግን ቅዱሳን ሁሉ የሚማጸኑትን አምላክ በሥጋ ወልዳ ያስገኘች ስለሆነች ለእርሷ የሚሳናት ነገር የለም፡፡ ስለዚህም ነው ላንቺ የሚሳንሽ ነገር የለምና ኃጢአቴን አስተስርዪልኝ፣ የከበደኝን ሁሉ አቅልይልኝ በማለት የለመነው፡፡

                                   በአውሮጳ   የካህናት አንድነት ማኅበር ሊቋቋም መሆኑ ታወቀ በ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከመላዋ አውሮጳ   የተውጣጡ ካህናት፡” የ...