2014 ኖቬምበር 24, ሰኞ

ጾም - ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዳስተማረው (ክፍል አራት)

(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ሰኞ ኅዳር 15 ቀን፣ 2007 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!

 ውድ የመቅረዝ ወዳጆች! እንዴት ዋላችኁ? እንዴት አረፈዳችኁ? እንኳን ለጾመ ነቢያት በሰላምና በጤና አደረሳችኁ፡፡ ዛሬም አባታችን ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እጅግ ጣፋጭ የኾነ ስብከቱን ቀጥሏል፡፡ የዛሬውን ስብከት የተረጐምንላችኁ የኦሪት ዘፍጥረትን እየተረጐመ ባስተማረው የአራተኛው ቀን ስብከቱ ነው፡፡ ምእመናኑ ወደ ጉባኤው መምጣታቸውን ቀጥለዋል፡፡ በየቀኑ ያስቀድሳሉ፤ በየቀኑ ይቈርባሉ፡፡ ቅዳሴውን ካስቀደሱና ከቅዱስ ቁርባኑ ከተሳተፉ በኋላም ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በሚያስተምራቸው ትምህርት ነፍሳቸውን መግበው ይሔዳሉ፡፡ ይኽን በየቀኑ እያየ አባታችን ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በጣም ይደሰታል፡፡ የምእመናኑ ትጋት እያየ ርሱም ማስተማሩን ቀጥሏል፡፡ በተለይ በሦስተኛው ቀን ዶፍ ዝናብ እየዘነበባቸው እንኳን ምእመናኑ አለመበተናቸውን አይቶ ቅዱሱን እጅግ በጣም አስደስቶታል፡፡ በመኾኑም በዛሬው ስብከቱ ይኽን የምእመናኑን ትጋት አይቶ ያስተማረው ትምህርት ነው፡፡ ምንም እንኳን ከዛሬ 1600 ዓመታት የተሰበከ ስብከት ቢኾንም ዛሬም አዲስ ነው፤ አይጠገብም፤ ነፍስን ይመልሳል፡፡ እስኪ እኔ ነገር ከማስረዝምባችኁ ከራሱ ከሊቁ አብረን እንማር፡፡ የነቢያትን፣ የሐዋርያትን፣ የሊቃውንትን ጉባኤ የባረከ አምላክ የእኛንም ይባርክልን፡፡ በያለንበት ኾነንም ቃሉን እንድንማር ልቡናችንን ይክፈትልን፡፡ አሜን!!!

እጅግ የምወዳችኁ የእግዚአብሔር ቤተ ሰቦች! በታላቅ ትጋትና ጉጉት ኾናችኁ በየቀኑ ወደ ቤተ ክርስቲያን መምጣታችኁ እያየኹ ነፍሴ ደስ ተሰኘች፤ ዕለት ዕለትም አምላኬን ስለ እናንተ አመሰግነዋለኹ፡፡ ረሃብ የጤነኝነት ስሜት ነው፤ ቃለ እግዚአብሔርን ለመማር መጓጓትም በመንፈሳዊ ሕይወት ጤነኛ መኾናችንን የሚያመለክት ነው፡፡ ክብር ምስጋና ለስም አጠራሩ ይኹንና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተራራው ስብከቱ፡- “ጽድቅን የሚራቡና የሚጠሙ ብፁዓን ናቸው፤ ይጠግባሉና” /ማቴ.5፡6/ ያለውም ይኽን የሚያስረዳ ነው፡፡
 እንዴት አድርጌ እንደማመሰግናችኁ አላውቅም፡፡ ምክንያቱም ጽድቅን ከመራባችኁና ከመጠማታችኁ የተነሣ ብፁዓን ኾናችኁ ሳለ አኹንም ይኽን ማድረጋችኁን አላቆማችኁምና፡፡ ልጆቼ! አባታችን እግዚአብሔር እንዴት እንደሚወደን እያያችኁ ነውን? ከእኛ የሚመጣ ትንሽ መነሣሣት ካለ እግዚአብሔር ከእኛ መነሣሣት በላይ በኾነ በረከት ነው የሚባርከን፡፡ እኛ ትንሽ ፈቃደኞች ስንኾን ርሱ ግን ከእኛ በላይ ብዙ ጸጋና በረከት ይሰጠናል፡፡

እኔም ይኽን እየተመለከትኩ እናንተን ለማስተማር እጓጓለኹ፡፡ በመንፈሳዊ ሕይወታችን ለውጥ እንድናመጣ በጣም እጥራለኹ፡፡ ማስተማሬንም እቀጥላለኹ፡፡ እናንተ በመንፈሳዊ ሕይወታችኁ እንድትበረቱ ማንኛውንም ዓይነት መሥዋዕት እከፍላለኹ፡፡ ምክንያቱም እዚኽ ብቻ እንድታቆሙ አልፈልግምና፡፡ ከዚኽም በበለጠ ወደ መንፈሳዊ ከፍታ እንድትወጡ እፈልጋለኹ፡፡ ከዚኽ በበለጠ በምትውሉበት የሥራ ቦታ፣ በምትውሉበት የትምህርት ቦታ አስተማሪዎች እንድትኾኑ እፈልጋለኹ፡፡ ቆማችኁ በማስተማር ሳይኾን መልካም ሥራችኁን አይተው ብዙዎች እንዲማሩ እፈልጋለኹና ትጋቴን ከወትሮው ይልቅ እጨምራለኹ፡፡ ድካሜ በከንቱ እንዳልቀረ እያየኹ ነውና ከዚኽ የበለጠ ማስተማር እንዳለብኝ ይሰማኛል፡፡
 ከምንም በላይ ደስ ያለኝ ደግሞ የዘራነውን ዘር ቀን በቀን እየጐመራ ነው እየሔደ ያለው፡፡ በወንጌል ላይ እንደተጠቀሰው ዓይነት እንቅፋት አላጋጠመንም፡፡ እንደምታስታውሱት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዘሩ ምሳሌ ባስተማረው ትምህርት ከተዘራው ዘር አንድ አራተኛው ብቻ ጥሩ ፍሬ ሲያፈራ ሦስት አራተኛው ግን እንደተጠበቀው አልኾነም፡፡ በመንገድ ዳር ላይ የወደቀው ዘር ወፎች መጥተው በልተዉታል፡፡ ብዙ መሬት በሌለበት በጭንጫ ላይ የወደቀው ፀሐይ ሲወጣ ጠውልጎ ወዲያው ደርቋል፡፡ በእሾኽ መካከል የወደቀውም እሾኹ አንቆታል፡፡ በመልካም መሬት ላይ የወደቀው ግን መቶ፣ ስድሳ፣ ሠላሳ ፍሬ አፈራ /ማቴ.13፡3-8/፡፡
 እኔም ትምህርቴ በመንገድ ዳር፣ ወይም በጭንጫ፣ ወይም በእሾኽ መካከል እንዳልወደቀ እየተመለከትኩ ነውና ትጋቴ እንዲጨምር አደረጋችኁኝ፡፡ መልካም እርሻ ኾናችኋልና በትጋት እንዳስተምራችኁ አድርጋችኁኛል፡፡

 እጅግ የምወዳችኁ ልጆቼ! ይኽን ኹሉ የምላችኁ ግን በውዳሴ ከንቱ ላመሰግናችኁ ፈልጌ አይደለም፡፡ ይኽን ኹሉ እንድል ያደረገኝ አንድ ነገር ስለተመለከትኩኝ ነው፡፡ ትናንት በዘነበው ኃይለኛ ዝናብ እንኳን አልተበተናችኁም፡፡ ዝናቡ እየዘነበባችኁም ቢኾን ቃሉን ለመማር ቁጭ ብላችኁ ነበር፡፡ ይኽ ለእኔ ትልቅ መልእክት አለው፡፡ እግዚአብሔር በእኔ በባርያው አድሮ የሚያስተምረውን ትምህርት በሙሉ ልባችኁ ኾናችኁ እየተቀበላችኁ እንደኾነ አሳይቶኛል፡፡ እንድተጋ አድርጋችኁኛል የምለውም ስለዚኹ ነው፡፡

 ቃለ እግዚአብሔርን በማስተዋል የሚያደምጥ ሰው ቃሉ ከልቡናው ትከሻ አይወርድም፡፡ ዘወትር ያስታውሰዋል፡፡ ደግሞም ፈቃደኛ ለኾነ ልብ ማስተማር እንዴት ደስ ይላል መሰላችኁ፡፡ መጽሐፍስ “ፈቃደኛ ለኾነ ልብ የሚያስተምር ሰው ብፁዕ ነው” ብሎ የለ /ሲራክ 25፡9/፡፡ ከጾም ውጤቶች አንዱ ይሔ ነው፡፡ ገና ይኽን ስንዠምር ጾም የነፍስ የሥጋ ቁስልን ትፈውሳለች ያልኳችኁ ይኸው ነበር፡፡ ወዮ! ገና ከአኹኑ ይኸን ያኽል ለውጥ ካየን፥ በሚቀጥሉት ቀናት ትምህርቱን የበለጠ ስንማርና የጾም ወራቱ ሲቀጥልማ እንዴት እንኾን ይኾን? ስለዚኽ የምወዳችኁ ልጆቼ! ቅዱስ ጳውሎስ እንዳለ፡- “በፍርሐትና በመንቀጥቀጥ የራሳችኁን መዳን ፈጽሙ” ብዬ እለምናችኋለኹ /ፊልጵ.2፡12/፡፡ ጠላት ዲያብሎስን በምንም መልኩ ለስንፍና አንጋብዘው፡፡ ከዚኽ የበለጠ እንትጋ እንጂ ከእንግዲኽ ወዲኽ ወደኋላ መመለስ አያስፈልገንም፡፡ ዲያብሎስ አኹን ያፈራነውን ፍሬ እያየ መበሳጨቱ አይቀርም፡፡ ይኽን የያዝነውን ፍሬ ለማስጣልም እንደሚያገሣ አንበሳ ኾኖ በዙርያችን እንደሚዞር በፍጹም መርሳት የለብንም /1ኛ ጴጥ.5፡8/፡፡ ነገር ግን ጠንቃቃዎችና በእግዚአብሔር ቸርነት የምንደገፍ ከኾነ ዲያብሎስ ምንም ሊያደርገን አይችልም፡፡ ችግር የሚኾነው እኛው ወደኋላ ማየት ስንዠምር ነው፡፡

 አያችኁ ልጆቼ! ለመንፈሳዊ ሕይወታችን ደንታ ቢስ ካልኾንን የምንለብሰው ጸጋ መንፈስ ቅዱስ እንዲኽ ብርቱ የኾነ የጦር ዕቃ ነው የሚያለብሰን፡፡ ስለዚኽ ኹለንተናችንን (ንግግራችንን፣ አለባበሳችንን፣ አሰማማችንን፣ ማንኛውንም አካሔዳችንን) በእግዚአብሔር ዕቃ ጦር ማለትም በእግዚአብሔር ቃል የምናለብሰው ከኾነ ዲያብሎስ የሚወረውረው ጦር እኛን ሊጐዳን አይችልም፡፡ እንደዉም ተመልሶ ርሱን ነው የሚጐዳው፡፡ 
እጅግ የምወዳችኁ ልጆቼ! ብቻ እኛ ፈቃደኞች እንኹን እንጂ፣ ብቻ እኛ በጾም በጸሎት ቃለ እግዚአብሔርንም በማድመጥ እንበርታ እንጂ የእግዚአብሔር ቸርነት እኛን ከብረት በላይ ጠንካራ ነው የሚያደርገን፡፡ አኹን ከእኛ መካከል አንድን ብረት በቦክስ ቢመታ ማን ነው የሚጐዳው? ብረቱ ወይስ እጃችን? ብረቱ ምንም አይኾንም፤ እጃችን ግን በእጅጉ ይጐዳል፡፡ የፈለገ ያኽል ጠንካሮች ብንኾንም ብረትን ማቁሰል አንችልም፡፡ ርሱ ነው የሚያቆስለን፡፡ በእግራችን ይኽን ብረት ብንመታው እኛው ደም በደም ኾነን እንቆስላለን እንጂ ብረቱ ምንም አይኾንም፡፡ ልክ እንደዚኹ እኛም በጾም፣ በጸሎት፣ በስግደት፣ ከቅዱስ ሥጋውና ከክቡር ደሙ በመቀበል፣ በመልካም ምግባር ኹለንተናችንን የምንከላከል ከኾነ፥ ዲያብሎስ እኛን ለመጉዳት የሚወረውረው ጦር መልሶ የሚጐዳው ራሱ ዲያብሎስን ነው፡፡ የእግዚአብሔር ቸርነት ከእኛ ጋር ስለሚኾን ጠላት እግዚአብሔርን አልፎ ሊያጠቃን አይችልም፡፡ ጸጋ መንፈስ ቅዱስ ከእኛ ጋር ስለሚኾን ዲያብሎስን ልምሾና ምንም ዓቅም የሌለው ነው የሚያደርገው፡፡

 ስለዚኽ እጅግ የምወዳችኁ ልጆቼ! መንፈሳዊ ትጥቅን እንታጠቅ፡፡ ሳንታጠቅ ከጠላት ዲያብሎስ ጋር አንታገል፡፡ ትርፉ መቁሰል አልፎም መሞት ብቻ ነውና፡፡ ስለዚኽ መንፈሳዊውን ትጥቅ ለመታጠቅ የምናደርገው ትጋት ጨምረን እንቀጥልበት ብዬ እለምናችኋለኹ፡፡ የትም ብንሔድ ይኽን መንፈሳዊ ትጥቃችንን ትተን መሔድ የለብንም፡፡ ወደ ቤተ ክርስቲያን ብንመጣ፣ ወደ ሥራ ቦታ ብንሔድ፣ ወደ ትምህርት ቤት ብንሔድ፣ ወደ ቤታችን ብንሔድ፣ ብንነቃ፣ ብንተኛ ያለዚኽ ትጥቅ መንቀሳቀስ የለብንም፡፡ ትጥቃችንን ይዘን የትም ብንሔድ ጠላት ያጠቃናል ብለን አንሰጋም፡፡ ደግሞም ይኽን ተሸክሞ ለመዞር (ክላሽ፣ መትረየስ፣ ሽጉጥ እንሚባሉት) እንደ ምድራዊ ትጥቆች አይከብድ፡፡ እንደዉም የበለጠ ብሩሃን (ብርሃን የተሞላን) ያደርገናል፡፡ ይኽን ብርሃን እያየም ጠላት ዲያብሎስ ሊያጠቃን አይችልም፡፡ ከእኛ ጋር ያለውን ብርሃን ለማየት ዓይኑ አይችልምና፡፡ እንዲኽ ከኾነም ደጋግሜ እንደነገርኳችኁ በጾም የሚገኘውን የነፍስ የሥጋ ቁስላችንን እናክማለን፡፡

 ወስብሐት ለእግዚአብሔር!!!

ጾም - ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዳስተማረው (ክፍል ሦስት)



(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ቅዳሜ ኅዳር 13 ቀን፣ 2007 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
ውድ የመቅረዝ ወዳጆች እንዴት ናችኁ? ዛሬም ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ስብከቱን ቀጥሏል፡፡ ባለፈው ትምህርቱ ሊቁ ብዙ ነገር አስተምሮናል፡፡ በጾም ወደ እግዚአብሔር የበለጠ እንደምንቀርብ፣ ምሥጢራተ እግዚአብሔርን ለማወቅና ለመረዳት ልቡናችን ብሩህ እንደሚኾን፤ ከዚኽ በተጨማሪ በጾም አዳም ከመደበሉ በፊት በገነት የነበረውን ሕይወት እንደምንለማመደው አስተምሮናል፡፡ ምክንያቱም አዳም ከመበደሉ በፊት የእንስሳት ተዋጽኦዎችን አይበላም ነበር፤ ይኽን መብላት የዠመረው ከበደለ በኋላ ነው፡፡ ሥጋውን የሚያስወፍሩና ነገረ እግዚአብሔርን ከማሰብ የሚያርቁ ተግባራትን አይፈጽምም ነበር፡፡ እኛም በመጾማችን ሥጋችንን እየቀጣን ሳይኾን በገነት የነበረውን አዳምን መስለን የበለጠ ወደ እግዚአብሔር የምንቀርብበት መንፈሳዊ መንገድ እንደኾነ አስተምሮናል፡፡ ዛሬስ ምን ብሎ ነፍሳችንን ይመግባት ይኾን? የሊድያን ልቡና የከፈተ አምላክ የእኛንም ይክፈትልን አሜን!!!

ዛሬ ብሩህ የኾነ ፊታችኁን እያየኹ እጅግ በጣም ደስ ብሎኛል፡፡ ደስታዬ ግን ልጆች ከወላጆቻቸው ጋር ሲጫወቱ እንደሚያመጡት ዓይነት ደስታ አይደለም፡፡ የእኔ ደስታ ከዚኽ የተለየ ነው፡፡ ምክንያቱም ቃለ እግዚአብሔር የተራበችውን ነፍሳችኁን ለመመገብ እንዴት ተጠራርታችኁ እንደመጣችኁ፣ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “ሰው ከእግዚአብሔር አፍ በሚወጣ ቃል ኹሉ እንጂ በእንጀራ ብቻ አይኖርም” ብሎ የተናገረውን ቃሉን በተግባር ለመፈጸም /ማቴ.4፡4/ ይኽንን በዓል ለማክበርም እንዴት ጓጕታችኁ እንደመጣችኁ ዐይቼ ደስታዬ ልዩ ነው፡፡
 ስለዚኽ ኑ እንደ ገበሬዎች እንኹን ብዬ እለምናችኋለኹ፡፡ ገበሬዎች እርሻቸው እንደለሰለሰ፣ ምንም ዓይነት አረምም እንደሌለ ሲያረጋግጡ እኽል ይዘሩበታል፡፡ እኛም ኑ እንደገበሬዎቹ እንኹን፡፡ በእግዚአብሔር ቸርነት የልቡናችን እርሻ ከለሰለሰ፣ በዚኹ በልቡናችን እርሻ የሚዘራውን ቃለ እግዚአብሔር የሚያንቁትን እንደነ ስልቹነትና ግዴለሽነት የመሰሉ አረሞች ከተነቀሉልን፣ ልቡናችን ሰማያዊ ምሥጢራትን ለመመርመር ብሩህ ከኾነልን፣ ከምድራዊ ነገር ይልቅ ሰማያዊ ነገርን ማስቀደም ከዠመርን ከዛሬ ዠምረን ጠለቅ ባለ መልኩ መማማር እንዠምራለን፡፡ ልቡናችን እንዲኽ በቃለ እግዚአብሔር ከለሰለሰ በኋላ ቃሉን የበለጠ ብንዘራበት ፍሬ ማፍራት የሚችል ይኾናልና፡፡ ጾሙም እየገባ ስለኾነ ስለ ምድራዊ መብልና መጠጥ ማሰብ ስለቀነስን ቃሉን ለማድመጥ ምቹ ነው፡፡ አብዝቶ የበላና የጠጣ ሰው ቃሉን ተማር ብንለው እንዴት ሊሰማን ይችላል? ስለበላው ምግብና ስለጠጣው መጠጥ የሚያስብና ሥጋው ወፍሮ የሚያስቸግረው ሰው እንባችን እንደ (አባይ) ወንዝ እየፈሰሰ ብንነግረውም ደንታ አይሰጠውም፡፡
ስለዚኽ አኹን ቃሉን ለመማር ምቹ ጊዜ ነው፡፡ በቤታችን ውስጥ አንድን ነገር ለቤተሰባችን ማሳመን የምንፈልግ ከኾነ ከቤት ሠራተኛዋ ዠምሮ ኹሉም ሰው ሰላማዊና ለማድመጥ ዝግጁ የኾነበትን ሰዓት መምረጥ አለብን፡፡ ጾም ደግሞ የነፍስ ዕረፍትን የምትሰጥ፣ ሽማግሌዎችን ደስ የምታሰኝ፣ ለወጣቶች ቀና መንገድን የምታስተምር፣ ሰውን ኹሉ ጠንቃቃና አርቆ አሳቢ የምታደርግ፣ በየትኛውም ዕድሜ የሚገኘውን ሰው የምታስጌጥ፣ ኹሉንንም እንደ ዕንቁ ፈርጥ የምታሳምር ናት፡፡ ስለዚኽ ከዛሬ ዠምሮ በከተማችን ምንም ዓይነት ሁካታ አይኑር፤ ዳንኬራ ቤቶች የሚሔድ አይገኝ፤ በመንፈሳዊ ሕይወቱ ቸልተኛ ሰው አይገኝ፤ እኅቶች አለባበሳቸውን ያስተካክሉ፡፡ ኹሉም ሰው ክርስቲያን ክርስቲያን ይሽተት፡፡ ከትናንትናው ጉባኤ በኋላ ዛሬ ላይ ሳያችኁ ይኽን እመለከታለኹ፡፡ በዚኽም ጾም ምን ያኽል ኃይል እንዳላት አስተዋልኩኝ፡፡ ጾም የሰዎችን አስተሳሰብ እንዴት እንደምትቀይር፣ የገዢዎች ብቻ ሳይኾን የተገዢዎችም፣ የአሠሪዎችም የሠራተኞችም፣ የወንዶችም የሴቶችም፣ የሀብታሙም የድኻውም፣ በአጠቃላይ የሰውን ልቡና እንዴት የማንጻት ኃይል እንዳላት ተገነዘብኩኝ፡፡ ገዢውም ተገዢውም ሲጾም ራሱን ዝቅ ማድረግ ይለማመዳል፡፡ ጾም ድኻውም ሀብታሙም እኩል የምታደርግ መሣሪያ ናት፡፡ በሚጾም ልቡና እኔ እበልጥ እኔ እበልጥ ምንም ዓይነት ቦታ የለውም፡፡
 በዚኽ ጉባኤ ላይ የታደማችኁ እጅግ የምወዳችኁ ምእመናን ሆይ! ጾም ለየትኛውም ዓይነት መንፈሳዊና ሥጋዊ በሽታ እንዴት ዓይነት ፍቱን መድኃኒት እንደኾነ ተገነዘባችኁን? ይኽን ከእናንተ እየተመለከትኩ ትጋቴ ከትናንቱ ይልቅ ዛሬ እጅግ ጨመረ፤ በመኾኑም ልቤ እናንተን ለማስተማር ተነሣሣ፡፡ እግዚአብሔር በእኔ በባርያው አድሮ የሚዘራው ቃል በጭንጫ ላይ ሳይኾን በመልካም እርሻ እየበቀለ እንደኾነ ዐየኹ፡፡ በአጭር ጊዜም ፍሬውን ማየት ችያለኹ፡፡
ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ከዚኽ በኋላ እዚያ ለታደሙት ምእመናን በኦሪት ዘልደት (ዘፍጥረት) ምዕራፍ አንድ ቁጥር አንድ እስከ ኹለት ያለውን ኃይለ ቃል ነው የሚተረጕምላቸው፡፡ በነገራችን ላይ በጥንታዊቷ ቤተ ክርስቲያን ሥርዓት በዐቢይ ጾም በብዛት የሚተረጐመው መጽሐፍ ኦሪት ዘፍጥረት ነው፡፡ ከስሙ መረዳት እንደምንችለው መጽሐፉ ስለ ብዙ ልደታት የሚናገር ነው፡፡ የሰማይና የምድር ልደት፣ የሰው ልጅ ልደት፣ የሰንበት ልደት፣ የጋብቻ ልደት፣ የኃጢአት ልደት፣ የመሥዋዕት (የድኅነት) ልደት /3፡15/፣ የትንቢት ልደት /3፡15/፣ የሰው ሥልጣን ልደት /9፡1-6/፣ የሀገራት ልደት /11/፣ የእግዚአብሔር ሕዝቦች ልደት /12፡1-3/፡፡ በዚያን ጊዜ ወደ ክርስትና ይመጡ የነበሩት አዳዲስ አማንያንም በፋሲካ ነበር የሚጠመቁት፤ ማለትም ዳግም የሚወለዱት፡፡ ይኸውም ሐዋርያው ጳውሎስ ጥምቀት ማለት ከክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ የምንተባበርበት ዳግም አዲስ ልደትም የምናገኝበት እንደኾነ ያስተማረውን ትምህርት በተግባር ለመፈጸም ነው /ሮሜ.6፡4-6/፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅም የኦሪት ዘፍጥረትን በዚኽ ጊዜ የሚተረጕምላቸው ስለዚኹ ነው፡፡ በዚኽ ዕለት ካስተማረው ትምህርት የሚከተሉት ዋና ዋና ነጥቦች እናገኛለን፡-
·        እግዚአብሔር ከመዠመሪያ አንሥቶ ለሰው የተናገረው በሰውኛ ቋንቋ እንደኾነ፤
·        ሰው ቢበድልም እንኳ ፍቅሩ አላስችል ብሎት ፍቅራችንን እናድሰው እያለ ከነ አዳም፣ ከነ ቃየን፣ ከነ ኖኅ፣ ከነ አብርሃም (በተለይ ከአብርሃም ጋር በቤቱ እንግዳ ኾኖ በመግባት) ዝቅ ብሎ እንደተጨዋወተ፤
·        ከእስትንፋስ ይልቅ ለሰው ልጆች ቅርብ ኾኖ ሳለ ሰዎች አላስተውል ቢሉት የበለጠ እንዲያውቁት ፈልጐ በሙሴ በኩል ደብዳቤ እንደላከላቸው፤
·        ሙሴም የተቀበለውን ደብዳቤ ለሕዝቡ በየጊዜው ያነብላቸው (ይነግራቸው) እንደነበረ፤
·        ሙሴ የሰማይና የምድር ፈጣሪ እግዚአብሔር መኾኑን እንደነገራቸው፤ እኛም ይኽን አሜን ብለን ልንቀበል እንደሚገባን፤
·        የእግዚአብሔር አሠራር ከሰው አሠራር ልዩ እንደኾነ፡፡ ለምሳሌ ሰው አንድን ቤት ሲሠራ ከመሠረት እንደሚዠምር ቀጥሎም ጣርያና ግድግዳ እንደሚሠራ፤ እግዚአብሔር ግን ከሰማይ ማለትም ከጣርያው ዠምሮ ቀጥሎም ምድርን ማለትም መሠረቱን እንደፈጠረ፤
·        ሰው ከምድር አፈር ተፈጥሮ ሳለ አፈሩ እንዴት ብሎ ነርቭ፣ አጥንት፣ የደም ቧንቧ፣ ጡንቻ፣ ፀጉር፣ ምላስ፣ ሳንባ፣ ልብ እንደኾነ ስናስብ ልቡናችን ተደንቆ ተደንቆ ዝም ብለን እግዚአብሔርን ማድነቅ ብቻ ሊኾን እንደሚገባና ይኽን ላደረገ ጌታ ምስጋና ብቻ ማቅረብ እንደሚገባን፤
 ይኽንና ይኽን የመሰለ ጣፋጭ ትምህርት ካስተማራቸው በኋላ ሊቁ የሚከተለውን ይነግራቸዋል፡-
እጅግ የምወዳችኁና እዚኽ ጉባኤ ላይ የታደማችኁ ቃሉንም ያዳመጣችኁ ምእመናን ሆይ! አኹን ለጊዜው የትርጓሜው ትምህርታችን ገታ እናድርግና አንድ ነገር ታደርጉ ዘንድ እለምናችኋለኹ፡፡ ወደየቤታችን ስንሔድ ቃሉን ለመተግበር እንጣጣር፡፡ ቃሉን በልቡናችን ጽላት እንቅረጸውና ዘወትር እንደ እንጀራ እንመገበው፡፡ አባቶች ለቤተሰቦቻችኁ ዛሬ የተማርነውን ትምህርት ድገሙላቸው፡፡ እኛቶችም ይኽን ከባሎቻቸው ያድምጡ፡፡ ልጆች ከእናቶቻቸው ይኽን ያድምጡ፡፡ ልጆች ብቻ አይደለም፤ ከቤት ውስጥ ያሉት እንስሳትም ይኽን ያድምጡ፡፡ ይኽን ያደረግን እንደኾነ፣ በዚኽ ጉባኤ የተማርነውን ትምህርት ከቤታችን ሔደን በተግባር የምንኖረውና ቃሉን ደጋግመን የምንበላው ከኾነ ቤታችን ቤተ ክርስቲያን ትኾናለች፡፡ ዲያብሎስም ወደ ቤታችን መግባት አይቻለውም፡፡ የነፍሳችን ጠላት የኾነው ርኵስ መንፈስ ተኖ ይጠፋል፡፡ በርሱ ፈንታም ወደቤታችን መንፈስ ቅዱስ ሰተት ብሎ ይገባል፡፡ ሰላምና ፍቅር፣ አንድነትና መስማማት ወደ ቤታችን ከነጓዛቸው ሰተት ብለው ይገባሉ፡፡ ይኽን ያደረጋችኁ እንደኾነ እኛንም የበለጠ ታተጉናላችኁ፡፡ የቃሉን ምሥጢር የበለጠ እንድናስተምራችኁ ታበረቱናለችኁ፡፡ ገበሬ የዘራውን እኽል ፍሬ ሲያፈራለት አይቶ እጅግ ደስ እንደሚሰኝ ኹሉ እኛም ደስ እንሰኛለን፡፡ ተደጋግፈንም ክርስቲያን ክርስቲያን የምንሸት እንኾናለን፡፡
ስለዚኽ ደጋግሜ እንደነገርኳችኁ በመንፈሳዊ ሕይወታችን የትም ብንኾን ቸልተኞችና ደንታ ቢሶች ልንኾን አይገባንም፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ሲናገር እንዲኽ ይላል፡- “መልካሙን ሥራችኁን አይተው በሰማያት ያለውን አባታችኁን እንዲያከብሩ ብርሃናችኁ እንዲኹ በሰው ፊት ይብራ” /ማቴ.5፡16/፡፡ የተማርነውን ትምህርት በተግባር የምንፈጽም ከኾነ በዚኽ ጉባኤ የተማርነው ትምህርት ግቡን መትቷል ማለት ነው፤ ፍሬ አፍርተናል ማለት ነው፤ በእውነት ክርስቶስን መስለነዋል ማለት ነው፡፡ ዳግመኛም ቅዱስ ያዕቆብ እንደነገረን እምነት ያለ ሥራ የሞተ ነው፤ ሥራም ያለ እምነት እንደዚኹ የሞተ ነው /ያዕ.2፡26/፡፡ የፈለገ ያኽል በእምነታችን ምንም እንከን የሌለን ብንኾን፣ ነገር ግን በተግባራዊ ሕይወታችን ሰነፎችና በኀጢአት ሕይወት የምንኖር ከኾነ ስሕተት የሌለው እምነታችን ምንም አይጠቅመንም፡፡ ልክ እንደዚኹ እውነተኛ እምነት ውስጥ ሳንኖር የፈለገ ያኽል መከራ ብንቀበልም፣ የምድር መልአክ ብንመስልም አይጠቅመንም፡፡ ስለዚኽ በየጊዜው የምንማረው ትምህርት ጊዜአዊ ስሜታችንን የሚያረካ ሳይኾን ሕይወታችንን የሚቀይረው ሊኾን ይገባል፡፡ ጌታችን ሲናገር፡- “ይኽን ቃሌን ሰምቶ የሚያደርገው ኹሉ ቤቱን በዓለት ላይ የሠራ ልባም ሰውን ይመስላል” ብሏል /ማቴ.7፡24/፡፡ ይኽ ሰው ልባም የተባለው ቃሉን ስለሰማ ብቻ አይደለም፤ ቃሉን ሰምቶ እንደ ዓቅሙ ለመተግበር ስለሚጣጣር እንጂ፡፡ ቃሉን ሰምቶ ለጊዜው የሚደሰትና “አቤት የዛሬው ጉባኤ ሲያስደስት” ብሎ የማይተገብር ሰው ግን ሰነፍ ሰው ነው፡፡ ይኽ ሰነፍ ሰውም ቤቱን በአሸዋ እንደሠራ ሰው ነው፡፡ ቤቱን በአሸዋ የሠራ ሰው ነፋስ ወይም ጐርፍ ሲመጣ ይፈርሳል፡፡ ፈተና ባጋጠመው ሰዓት ዐለት በተባለው ክርስቶስ ስላልቆመ ይሸነፋል፡፡ ልባም ሰው ግን በእነዚኽ ፈተናዎች የበለጠ ይፈካል፡፡ ክርስቶስን እየመሰለ ይሔዳል፡፡ ልባሙ ሰው ፈተና ባጋጠመው መጠን ከክርስቶስ ጋር ስለሚኾን መልካም ሥራው የበለጠ እየታየ ይሔዳል፡፡ ሰነፍና ለመንፈሳዊ ሕይወቱ ደንታ የሌለው ክርስቲያን ግን የፈለገ ያኽል እዚኽ ጉባኤ መጥቶ ቁጭ ብሎ ቢማርም ፈተና ባጋጠመው ጊዜ በቀላሉ ይወድቃል፡፡ ፈተናው ከብዶት ሳይኾን እርሱ ሰነፍ ስለኾነ (ክርስቶስ አብሮት ስለሌለ)፡፡
ስለዚኽ የጦር ዕቃችንን እናንሣ፡፡ የአንድ ሳምንት ጿሚዎች ሳንኾን ዘወትር ብርቱዎች እንኹን፡፡ ይኽን ያደረግን እንደኾነ በፈተና እንጸናለን፡፡ ትዕግሥተኞች እንኾናለን፡፡ በመንግሥተ ሰማያት ከምናገኘው ደስታ ጋር ስናነጻጽረው የአኹኑ ሕይወታችን ፈተና ምንም እንዳልኾነ እናውቃለን፡፡ አኹን ትዕግሥተኞችና በፈተና የምንጸና ከኾነ 30፣ 60፣ 100 ያማረ ፍሬ ማፍራት እንችላለን፡፡ ቸርና ሰው ወዳጅ እግዚአብሔር በፈተና እንድንጸና ይርዳን፡፡ የይምሰል ሳይኾን የእውነትና እግዚአብሔር የሚወደው የጾም ወራት ያድርግልን፡፡ ዳግም በመጣ ጊዜ የሕይወት ቃል እንዲያሰማን ፈቃዱ ይኹን፡፡ ምስጋና፣ ክብር፣ አኰቴት ለአብ፣ ለወልድ ለመንፈስ ቅዱስ ዛሬም ዘወትርም እስከ ዘለዓለሙ ድረስ ይኹን፡፡ አሜን!!!

ጾም - ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዳስተማረው (ክፍል ኹለት)



(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ሐሙስ ኅዳር 11 ቀን፣ 2007 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
ውድ የመቅረዝ አንባብያን፡፡ በትናንቱ ጕባኤ ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ብዙ ነገር አሳስቦን ነበር፡፡ ጉባኤውን ለመታደም ወደ ቤተ ክርስቲያን ዓውደ ምሕረት ከመጣን አይቀር ከነበሽታችን ልንመለስ እንደማይገባ ይልቁንም መንፈሳዊ መድኃኒትን ውጠን ልንመለስ እንደሚገባን፣ የነፍስና የሥጋ መድኃኒት ከምትኾን ከጾም ጋር አብረው የማይሔዱ ነገሮች ምን ምን እንደኾኑ፣ ከእንግዲኽ ወዲኽ ቤተ ክርስቲያን ቀኖና አውጥታ ጾም ነው ስላለችን ብቻ ሳይኾን በዓላማ ልንጾም እንደሚገባና ሌላ ብዙ ነፍስን የሚያለመልሙ ትምህርቶችን አስተምሮን ነበር፡፡ ምንም እንኳን የዛሬው ትምህርት ለእኛ ኹለተኛ ጕባኤ ቢኾንም ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ግን ከትናንቱ ጋር በአንድ ቀን ጕባኤ ያስተማረው ነው፡፡ የመዠመሪያው ቀን ስብከቱም ዛሬ ላይ እንጨርሳለን፡፡ በነገራችን ላይ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ቁመቱ አጭር ስለነበረ ምእመናኑ ባዘጋጁለት መድረክ ላይ ወጥቶ ነበር የሚያስተምረው፡፡ ዛሬ በየዓውደ ምሕረቱ የምንመለከተው አትሮንስም ከዚያን ጊዜ ዠምሮ አገልገሎት ላይ የዋለ ነው፡፡ መልካም ጕባኤ እንዲኾንልን በመመኘት ፊታችንና መላ ሰውነታችንን ሦስት ጊዜ በማማተብ ትምህርቱን በትጋት ኾነን እንድንማር በድጋሜ ጋበዝናችኁ፡፡
 

   በመንፈሳዊ ሕይወት ቸልተኛ መኾንና ለራስ ሕይወት ግድ አለመስጠት የብዙ ኃጢአቶች ምክንያት እንዲኹም ነጸብራቅ ነው፡፡ ልክ እንደዚኹ ጾምም የብዙ በረከት ምክንያት እንዲኹም ነጸብራቅ ነው፡፡ እንደምታስታውሱት አዳም በገነት በነበረ ጊዜ ለመንፈሳዊ ሕይወቱ ቸልተኛና ግድ የሌለው እንዳይኾን ብሎ ልዑል እግዚአብሔር አንድ ትእዛዝ ሰጥቶት ነበር፡፡ እንዲኽ በማለት፡- “ከገነት ዛፍ ኹሉ ትብላለኅ፤ ነገር ግን መልካሙንና ክፉን ከሚያስታውቀው ዛፍ አትብላ” /ዘፍ.2፡16-17/፡፡ እዚህ ጋር “ብላ፤ አትብላ” የሚለው የሚለው ትእዛዝ በምሳሌ ስለ ጾም ጥቅም የሚያስረዳ ነው፡፡  የሰው ልጅ ግን ይህቺን አንዲት ትእዛዝ ለመጠበቅ አልታዘዝ አለ፤ ትዕግሥት አጣ፤ ሞትንም በራሱ ላይ አመጣ፡፡ የሰው ልጆች ጠላትና ክፉ መንፈስ የኾነው ዲያብሎስም እንደምታስታውሱት አዳም በገነት የአታክልት ስፍራ ደስ ብሎት እንደ ሰማያውያን መላዕክት ኾኖ እየኖረ ስለነበረ ቀናበት፡፡ አምላክ ትኾናለህ ብሎም አታለለውና የነበረውን ቅድስና እንኳን አሳጣው፡፡ አያችኁ ልጆቼ! ያለንን ቅዱስ ነገር በአግባቡ ሳንይዝ ይልቁንም ሌላ ከዚኽ የበለጠ ነገር መመኘት መዘዙ ብዙ ነው፡፡ ጠቢቡ ሰው “በዲያብሎስ ቅንኣት ምክንያት ሞት ወደ ዓለም ገባ” ያለንም እኮ ስለዚኹ ምክንያት ነው /ጥበብ 2፡24/፡፡ እንግዲኽ ሞት ወደ ሰው ልጆች እንዴት በስንፍና እንደመጣ እያስተዋላችኁ ነው ልጆቼ? በኋላ ዘመን መጽሐፍ ቅዱስ ሲጻፍም በመንፈሳዊ ሕይወት መድከምን እንዴት እንደሚነቅፍ እንመልከት፡- “ሕዝቡም ሊበሉና ሊጠጡ ተቀመጡ፤ ሊዘፍኑም ተነሡ” /ዘጸ.32፡6/፤ “ወፈረ፤ ደነደነ፤ ሰባ፤ የፈጠረውንም እግዚአብሔርን ተወ፤ የመድኃኒቱንም አምላክ ናቀ” /ዘዳ.32፡15/፡፡ የሰዶም ኗሪዎችም የዲን እሳት ዘንቦባቸው የጠፉት ለመንፈሳዊ ሕይወታቸው እጅግ ቸልተኞች ስለነበሩና ለመብልና ለመጠጥ ሰፊ ቦታን ስለ ሰጡ ነው፡፡ ነቢዩ ሕዝቅኤል ስለዚኹ ጉዳይ ሲነግረን እንዲኽ ብሏል፡- “የሰዶም ኃጢአት ይኽ ነበረ፤ ትዕቢት እንጀራን መጥገብ መዝለልና ሥራ መፍታት” /ሕዝ.16፡49/፡፡ በአጭር አነጋገር አብዝቶ መብላትና መጠጣት፣ ጾምን ችላ ማለት የብዙ ኃጢአቶች ምክንያት ነው፡፡
 እንግዲኽ ራስን አለመግዛት እንዴት አደገኛ እንደኾነ አያችኁ? አኹን ደግሞ ጾም እንዴት በረከትን እንደሚያመጣ እንመልከት፡፡ ሙሴ 40 ቀን ስለጾመ የእግዚአብሔር ሕግ የተጻፈበትን ጽላት ተቀበለ /ዘጸ.24፡18/፡፡ ከተራራው ሲወርድ ግን የሕዝቡን ኃጢአት ተመለከተና ኃጢአተኛ ሕዝብ የእግዚአብሔርን ሕግ መቀበል አይችልም ሲል ብስንት መለማመጥ የተቀበለውን ጽላት ወርውሮ ሰበረው፡፡ ይኽ ታላቅ ነቢይ በተሰበረው ፋንታ ሌላ ጽላት ለመቀበል 40 ቀናት ነው የጾመው /ዘጸ.34፡28/፡፡ ታላቁ ነቢይ ኤልያስም ልክ እንደ ሙሴ 40 ቀንና 40 ሌሊት ጾሟል፡፡ እንዲኽ በመጾሙም በእሳት ሠረገላ ተነጥቆ ወደ ሰማይ ተወሰደ፤ እስከ አኹን ድረስም አልሞተም፡፡ እጅግ አስደናቂ የኾነው ሰው ነቢዩ ዳንኤልም እጅግ ብዙ ቀናትን ይጾም ስለነበረ ተንኰለኞች ወደ አንበሳ ጕድጓድ እንኳን ቢጥሉት አንበሶች ሊበሉት አልቻሉም፡፡ አንበሶቹ ለነቢዩ ዳንኤል እንደ በጐች ነበሩ፡፡ አንበሶቹ በግ የኾኑት ግን ተፈጥሯቸው ተለውጦ በግ በመኾን ሳይኾን ዳንኤልን ሳይበሉት ከነተናጣቂ ተፈጥሯቸው ሳሉ ነው፡፡ የነነዌ ሰዎች የእግዚአብሔርን ቁጣ ያስቀሩት በመጾማቸው ነው፡፡ እንደዉም በነነዌ የጾሙት ሰዎች ብቻ አልነበሩም፤ እንስሳቱም ጭምር እንጂ፡፡ በዚኽም ምክንያት እግዚአብሔር ሊያደርገው ከተናገረው ክፉ ነገር ተጸጽቶ አላደረገውም /ዮናስ 3፡10/፡፡ ከብሉይና ከሐዲስ ኪዳን እንዲኽ በመጾማቸው የተጠቀሙ ብዙ ሰዎችን መጥቀስ እንችላለን፡፡ ነገር ግን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያደረገው ነገር ኹላችንንም የሚያስተምር ነውና እሱን ብንመለከት፡፡ ኹላችኁም እንደምታውቁት አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ 40 ቀንና 40 ሌሊት ጾሟል /ማቴ.4/፡፡ ሲጾምም ዲያብሎስን ድል አድርጎ አሳይቶናል፡፡ ጌታችን ይኽን ያደረገበት ምክንያት ዲያብሎስን ለማሸነፍ እኛም የጾምን ትጥቅ መታጠቅ እንዳለብን ሲያስተምረን ነው፡፡
እዚኽ ጋር ምናልባት ከእናንተ መካከል፡- “አባታችን! ቅድም እንደነገርከን እነ ሙሴ፣ እነ ኤልያስ 40 ቀንና 40 ሌሊት ጾመዋል፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ልክ እንደ ሙሴና እንደ ኤልያስ አንዲት ቀን እንኳን ሳይጨምር መጾሙ ለምንድነው?” ብሎ የሚጠይቅ ሊኖር ይችላል፡፡ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ይኽን ያደረገው ያለ ምክንያት አይደለም፡፡ ጌታችን እንዲኽ የጾመው እኛን በጣም ስለሚወደን ነው፡፡ ምክንያቱም ሲዠምርም የእኛን ሥጋ ሳይዋሐድ መምጣት ይችል ነበር፡፡ ነገር ግን በጣም ስለሚወደን ሥጋችንን ተዋሐደ፤ ከእኛ ከሰዎች ያልራቀ መኾኑን ሲያስረዳንም ጾመ፡፡
 እንግዲኽ ከላይ ለማየት እንደቻልነው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ሌሎችም ቅዱሳንም በመጾማቸው ምክንያት ዲያብሎስን አሸንፈውታል፡፡ በተለይ ቅዱሳኑ በመጾማቸው ምክንያት ለሥጋቸውም ለነፍሳቸውም ብዙ ጥቅምን አግኝተዉበታል፡፡
 ስለዚኽ እጅግ የምወዳችኁ ልጆቼ! የጾም ጥቅም እንዴት ትልቅ እንደኾነ እየተማርንና እየተመለከትን ሳለ የጾም ወራት ሲቃረብ ደስ ብሎን ልንቀበለውና ንቁዎች ኾነን እጅግ ብዙ ጥቅምን ልናገኝበት ይገባናል ብዬ እማልዳችኋለኹ፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “የውጭው ሰውነታችን ቢጠፋ እንኳን የውስጡ ሰውነታችን ዕለት ዕለት ይታደሳል” ብሎ እንዳስተማረን /2ኛ ቆሮ.4፡16/ ጾም ሲገባ እጅግ ደስ ሊለን ይገባል፡፡ ከዚኽ የሐዋርያው ቃል እንደምንረዳው ጾም ማለት ነፍሳችን የበለጠ የምትወፍርበት መንገድ ነው ማለት ነው፡፡ እንጀራ ሥጋችን እንዲወፍር እንደሚያደርገው ኹሉ ጾም ደግሞ ነፍሳችን እንድትወፍር ያደርጋታል፡፡ ጾምን የምታዘወትር ነፍስ ከእግዚአብሔር ጋር ያላት ቀረቤታ እጅግ ስለሚጨምር ገና በዚኽ ምድር ሳለች ቅድስና በቅድስና እየጨመረች፣ ምሥጢራተ እግዚአብሔርን እያስተዋለች፣ የመንግሥተ ሰማያትን ጣዕም እየቀመሰች ትሔዳለች፡፡ እጅግ ብዙ ጭነትን የተሸከመች መርከብ ባሕሩንና ወጀቡን ማለፍ እንደሚያቅታት ኹሉ መብልና መጠጥ የሚያበዛ ሰውም የዚኽን ዓለም ወጀብ ማለፍ አይችልም፡፡ ቀለል ያለና ተመጣጣኝ የኾነ ጭነትን የያዘች መርከብ ግን ብዙ ችግር ሳይገጥማት የታሰበላት ቦታ በታሰበላት ጊዜ  ትደርሳለች፡፡ መብልና መጠጥን ሳያበዛ ጾም የሚወድ ክርስቲያንም ንቃተ ኅሊናው ብሩህ ነው፡፡ በዚኽ ምድር በሚያጋጥሙት ችግሮችም በቀላሉ እጅ አይሰጥም፡፡ ዛሬ ላይ በዚኽ ምድር የሚያጋጥሙት ጊዜያዊ ችግሮች እንደ ጥላና ሕልም እንደሚያልፉ ይገነዘባል፡፡ እንዲኽ እንዳናስብና በዚኽ ምድር በሚያጋጥሙን ጥቃቅን ችግሮች እንድንጨናነቅ የሚያደርጉን በመንፈሳዊ ሕይወታችን እጅግ ቸልተኞች ስንኾን ነው፡፡ ምክንያቱም የዘወትር ሐሳባችን መብልና መጠጥ ላይ ከኾነ በመንፈሳዊ ሕይወታችን ደካሞች ነው የምንኾነው፡፡ ሥጋችን ይወፍራል፡፡ የማሰብና የማመዛዘን ዓቅማችን ይቀንሳል፡፡ ለነፍሳችን ምንም በማይጠቅም እንተ ፈንቶ ነገርም ተጠምደን እንውላለን፡፡  
 ስለዚኽ እጅግ የምወዳችኁ ምእመናን ሆይ! በጊዜያዊ ነገር ብቻ እየተጠመድን በመንፈሳዊ ሕይወታችን ቸልተኞች አንኹን ብዬ እለምናችኋለኹ፡፡ በመንፈሳዊ ሕይወታችን ቸልተኞች ስንኾን የምንጐዳው በሚመጣው ዓለም ብቻ አይደለም፡፡ በዚኽ ምድር ሳለንም በመብልና በመጠጥ ብዛት ምክንያት የሚመጡ ብዙ በሽታዎች ተጠቂዎች ነው የምንኾነው፡፡ እኛ በሐዲስ ኪዳን ያለን ክርስቲያኖች ነን፡፡ በዚያ በጨለማው የብሉይ ኪዳን የነበሩ ሰዎች እንኳን በመንፈሳዊ ሕይወታቸው ቸልተኞች እንዳይኾኑ ይልቁንም ጾምን እንዲያዘወትሩ ይነገራቸው ነበርና እባካችኁ ቸልተኞች አንኹን ብዬ እለምናችኋለኹ፡፡ እስኪ አምላካችን እግዚአብሔር ምን እንደሚለን እናድምጥ፡- “ክፉውን ቀን ከእናንተ ለምታርቁ፣ የግፍንም ወንበር ለምታቀርቡ፣ ከዝሆን ጥርስ በተሠራ አልጋ ላይ ለምትተኙ፣ በምንጣፋችኁም ላይ ተደላድላችኁ ለምትቀመጡ፣ ከበጐችም መንጋ ጠቦትን ከጋጥም ውስጥ ጥጃን ለምትበሉ፣ በመሰንቆም ድምፅ ለምትንጫጩ፣ እንደ ዳዊትም የዜማን ዕቃ ለምታዘጋጁ፣ በፋጋ የወይን ጠጅ ለምትጠጡ፣ እጅግ ባማረ ሽቱም ለምትቀቡ፣ ስለዮሴፍ መከራ ግን ለማታዝኑ ለእናንተ ወዮላችኁ” /አሞጽ.6፡3-6/፡፡ ልጆቼ! እግዚአብሔር በነቢዩ አሞጽ አድሮ እስራኤላውያንን እንዴት አድርጐ እንደወቀሳቸው፣ መብልንና መጠጥን ሲያበዙ እንዴት አድርጐ እንደገሠፃቸው አያችኁን? እንደዉም በደንብ አስተውላችኁት ከኾነ አብዝተው መብላታቸውንና መጠጣታቸውን ብቻ አይደለም የወቀሳቸው፡፡ ጨምሮም እነዚኽ ሰዎች ከዚኽ በላይ ደስታ እንደሌላቸው፥ ደስታቸው ግን እንደ ጧት ጤዛ ብዙ እንደማይቆይ ነግሯቸዋል፡፡
 አኹን በዚኽ ምድር ላይ የምንመለከታቸው ነገሮች ልክ እንደዚኽ የሚጠፉ ናቸው፡፡ ክብርም በሉት፣ ሥልጣንም በሉት፣ ሀብትና ንብረትም በሉት፣ የምናገኛቸው መልካም አጋጣሚዎችም በሉት፣ ኹሉም ጠፊዎች ናቸው፡፡ ከእነዚኽ አንዱ ስንኳ ዘለዓለማዊ የለም፡፡ ኹሉም እንደ ወራጅ ውኃ የሚያልፉ ናቸው፡፡ የሙጥኝ ብለን ልንይዛቸው ብንሞክር እንኳን ብዙ ልናቆያቸው አንችልም፡፡ የምንቀረው ባዶአችን ነው፡፡ መንፈሳዊ ነገሮቻችን ግን የእነዚኽ ተቃራኒ ናቸው፡፡ እንደ ጽኑ ዐለት አይንቀሳቀሱም፤ ትተዉን አይሔዱም፡፡ በጊዜ ብዛት አይበላሹም (Expire date የላቸውም)፡፡ እስኪ አኹን ልጠይቃችኁ ልጆቼ! የማይጠፋውን ሀብት በሚጠፋው ሀብት የምንቀይረው እንዴት ብንደነዝዝ ነው? ዘለዓለማዊውን ደስታችን በዘለዓለማዊ ለቅሶ፣ ዘለዓለማዊውን ሕይወት በጊዜያዊ ሕይወት፣ ዘለዓለማዊውን ሀብታችን በሚጠፋ ሀብት መቀየራችን ምን ዓይነት ስንፍና ቢይዘን ነው?
 ስለዚኽ በዚኽ ጕባኤ የታደማችኁ ኹላችኁም ምእመናን ሆይ! እለምናችኋለኹ፡፡ ለመንፈሳዊ ሕይወታችን ተገቢውን ትኵረት እንስጠው፡፡ ለምድራዊ ነገር ፈጣን ኾነን ሳለ ለመንፈሳዊ ሕይወታችን ሰነፎች አንኹን፡፡ በመንፈሳዊ ሕይወታችን ጠንካሮች እንድንኾን የምታደርገንን ጾምንም እንውደዳት፡፡ ከርሷ ጋር ያሉት ሌሎች በጐ ምግባራትንም (ጸሎት፣ ስግደት፣ ምጽዋት፣ ወዘተ) እንውደዳቸው፡፡ ከዛሬ በኋላ አዲስ የአኗኗር ስልትን (Renewed Life style) እንዠምር፡፡ በየቀኑ መልካም ምግባራትን መሥራት የሚያስደስተን እንኹን፡፡ በዚኽ በምንቀበለው ጾም ብዙ መንፈሳዊ ተግባራትን እናድርግና ራሳችንን በሰማያዊ ክብር እናስጊጥ፡፡ እንዲኽ የምናደርግ ከኾነ ጾሙ ሲፈታ ወደ ቅዱስ ሥጋውና ወደ ክቡር ደሙ ሳናፍር መቅረብ ይቻለናል፡፡ በልቡናችን ውስጥ የነበረውን ቆሻሻ ኹሉ ስለምናስወግድ ንጹሓን ኾነን ከዚያ ሰማያዊ ማዕድ ተሳታፊዎች መኾን እንችላለን፡፡ ከዚያም በጐ ምግባራችን የማይጠፋና ኃይልን ስለሚያገኝ በመጨረሻው ቀን ኑ እናንተ የአባቴ ብሩካን የሚለውን የሕይወት ቃል መስማት እንችላለን፡፡ የእግዚአብሔር ጸጋ ስለማይለየን ሕይወታችን በጸሎትና በምልጃ የተሞላ ይኾናል፡፡ እግዚአብሔርን ደስ አሰኝተን መኖር ይቻለናል፡፡ ይኽን እንድናደርግ ሰውን በመውደዱ ሰው የኾነው ክርስቶስ ይርዳን፡፡ አሜን!!!

ጾም - ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዳስተማረው (ክፍል አንድ)



(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ረቡዕ ኅዳር 10 ቀን፣ 2007 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
 ይኽን ጽሑፍ ወደ አማርኛ የመለስነው ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ የኦሪት ዘልደትን መጽሐፍ ከተረጐመበት ከመዠመሪያው ድርሳኑ ላይ ነው፡፡ ስብከቱ ረዘም ስለሚልም አንዱን ድርሳን በክፍል በክፍል አድርገን አቅርበነዋል፡፡ ሊቁ ይኽን ስብከት የሰበከው ዐቢይ ጾም ሊገባ ጥቂት ቀናት ሲቀሩት እንደኾነ ከስብከቱ መረዳት እንችላለን፡፡ ምንም እንኳን ከፊታችን የምንቀበለው ጾም ጾመ ነቢያት ቢኾንም የጾም ዓላማው አንድ ነውና ለዚኽም ጊዜ ይስማማል በማለት አኹን ልናቀርበው ወደናል፡፡ በመኾኑም ልክ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በሚያስተምርበት ዓውደ ምሕረት እንዳለን ኾነን በማሰብ ፊታችንና መላ ሰውነታችንን በትእምርተ መስቀል ሦስት ጊዜ በማማተብ ቃሉን በትሕትና እንድንማር እንጋብዛችኋለን፡፡ መልካም ጉባኤ!!! 

ቤተ ክርስቲያን እንደዚኽ በልጆቿ ደምቃ ሳይ፥ እናንተም ጕባኤውን ለመታደም ደስ ብሏችኁ ስትመጡ ዐይታ ነፍሴ ሐሴት አደረገች፤ ደስም ተሰኘች፡፡ ጕባኤውን ለመታደም መጥታችኁ ፊታችኁ እንደምን በደስታ እንደተመላ ዐይቼ ጠቢቡ ሰው “ደስ ያለው ልብ ፊትን ያበራል” እንዳለው ልቤ በደስታ ፍንክንክ አለብኝ /ምሳ.15፡13/፡፡ ቀጣዩ ወራት የቁስለ ነፍሳችንን መድኃኒት የምናገኝበት ወርሓ ጾም ነውና ይኽን የምስራች እነግራችኍ ዘንድ ዛሬ ጧት ከወትሮው በተለየ ትጋት ነው የተነሣኹት፡፡ ደግ አባት ነውና ባለፉት ወራት የሠራነውን ኃጢአት ሥርየት እናገኝበት ዘንድ ሽቶ አምላካችን ፈውሰ ሥጋ ፈውሰ ነፍስ የሚኾን ቅዱስ ጾምን አዘጋጅቶልናል፡፡
ስለዚኽ ከእኛ መካከል አንድ ስንኳ ተስፋ የሚቈርጥ፣ በድብርትም የሚያዝ ከቶ አይገኝ፡፡ ይልቁንም ደስ የምንሰኝበትን፣ የሕመማችንን ፈውስ የምናገኝበትን መድኃኒት እረኛችን እግዚአብሔር አዘጋጅቶልናልና ወርሓ ጾም በመምጣቱ ደስ ልንሰኝ ይገባል፡፡ አሕዛብ ይኽን ወራት ደስ ተሰኝተን መቀበላችንን አይተው ይፈሩ፡፡ በእኛና በእነርሱ መካከል ሰፊ ልዩነት እንዳለ አይተውም ይማሩ፡፡ በዓላቶቻቸው በዘፈንና በስካር፣ ይኽም በመሰለ ሌላ ርኵስ ግብር የተሞሉ ናቸውና፡፡
 ምእመናን ከዚኽ አሕዛባዊ ግብር ተለይተን በዓል ልናደርግ ይገባናል፡፡ በምግባር በትሩፋት ልናጌጥ ልናሸበርቅ ይገባናል፡፡ እውነተኛ ጾም ማለት ሰዎች የሚድኑበት፣ ሰላምና አንድነት የሚያገኙበት፣ ክፉ ግብርን ቈርጠው የሚጥሉበት፣ አርምሞን ገንዘብ የሚያደርጉበት፣ በመብልና በመጠጥ ከመንጋጋት የሚላቀቁበት ነው፡፡ በዚኽ በወርሓ ጾም ዕረፍተ ሥጋ ወነፍስ እንዲኹም አርምሞ፣ የነፍስ ወሥጋ ፍቅርና ደስታ፣ ራስን መግዛት፣ እንዲኹም ሌሎች እዚኽ መዘርዘር የማንችላቸው ብዙ የብዙ ብዙ ምግባር ትሩፋቶችን ገንዘብ የምናደርግበት ነው፡፡
 እንኪያስ እጅግ የምወዳችኁ ምእመናን ሆይ! አንዳች የሚረባንን ነገር ይዘንም ወደ ቤታችን እንመለስ ዘንድ ቃላችንን በታላቅ ትጋትና ጉጉት ኾናችኁ ተቀበሉት ብዬ እማልዳችኋለኹ፡፡  ኹላችንም ወደዚኽ ጉባኤ የመጣነው ሌላ ነገር ሽተን አይደለምና፡፡ ወሬ ለማውራት፣ የተባለውን ነገር ምንም ሳንሰማ ለማጨብጨብ፣ ከዚያም ምንም የሚረባ ነገርን ሳንይዝ ወደ ቤታችን ለመመለስ ወደዚኽ ጉባኤ አልመጣንምና ቃላችንን በማስተዋል ትከታተሉት ዘንድ እማልዳችኋለኹ፡፡ እግዚአብሔር በእኔ በባርያው አድሮ ለነፍሳችን ድኅነት የሚጠቅም ነገር ይናገራል፡፡ ስለዚኽ እጅግ ብዙ የሚጠቅም ነገር ሰንቀን ወደ ቤታችን እንመለስ ዘንድ እማልዳችኋለኹ፡፡ ምክንያቱም ቤተ ክርስቲያን ማለት ሐኪም ቤት ናት፡፡ ወደርሷ የሚመጡትም ተገቢውን መድኃኒት አግኝተው መሔድ አለባቸው፡፡ ቃሉን ብቻ አድምጠን ነገር ግን በሕይወታችን አንዳች ተግባራዊ የኾነ ለውጥ ከሌለን ወደ ጉባኤ መምጣታችን፣ ቃለ እግዚአብሔር መማራችን አንዳች ረብሕ የለውም፡፡ ብጹዕ ሐዋርያ ጳውሎስ እንዲኽ እንዳለ፡- “በእግዚአብሔር ፊት ሕግን የሚያደርጉት ይጸድቃሉ እንጂ ሕግን የሚሰሙ ጻድቃን አይደሉምና” /ሮሜ.2፡13/፡፡ ክብር ምስጋና ለስም አጠራሩ ይኹንና አምላካችን ክርስቶስም፡- “በሰማያት ያለውን የአባቴን ፈቃድ የሚያደርግ እንጂ ጌታ ሆይ ጌታ ሆይ የሚለኝ ኹሉ መንግሥተ ሰማያት የሚገባ አይደለም” /ማቴ.7፡21/፡፡ ስለዚኽ እጅግ የምወዳችኁ ምእመናን ሆይ! ቃሉን በመስማታችን ብቻ አንዳች የምንጠቀመው ነገር ስለሌለ የሰማነውን የምናደርግ እንጂ የምንሰማ ብቻ አንኹን፡፡ እንዲኽ ከኾነም (ሰምተን የምንፈጽም ከኾነ) እምነታችን ሕይወት ያለው እምነት ይኾናል፡፡
 ስለዚኽ እግዚአብሔር ስለ ጾም የሚያስተምረንን ትምህርት ለማዳመጥ እዝነ ልቡናችንን እንክፈት፡፡ ጾም ሙሽሪትን ትመስላለች፡፡ ሙሽሪትን በሠርግ አዳራሽ ኾነው የሚቀበሏት ሰዎች ቤቱን ያስጌጡታል፤ ይሸልሙታል፡፡ ወደ ሠርጉ አዳራሽ የሚገባውን ሰው የሠርግ ልብስ ለብሶ እንደኾነ፣ የቆሸሸ እንዳልኾነ አይተው ያስገቡታል፡፡ እኛም እንዲኽ ልንኾን ይገባናል ብዬ እነግራችኋለኹ፡፡ ልቡናችንን በማንጻት፣ ልል ዘሊል ከመኾን በመራቅ፣ የክፋት እርሾን በማስወገድ፣ ከጾም ጋር አብረው የሚመጡትን የሚያጅቧትን መልካም ምግባራትንም ለመቀበል የልቡናችንን ውሳጤ በመክፈት የምግባር እናት፣ የማስተዋል እንዲኹሉም ለሌሎች ምግባራት ኹሉ ንግሥት የምትኾን ጾምን ልንቀበላት ይገባናል ብዬ እነግራችኋለኹ፡፡ ይኽን ያደረግን እንደኾነ ታላቅ ሐሴት እናደርጋለን፤ ርሷም ቁስለ ነፍሳችንን ትፈውስልናለች፡፡ በሌላ አገላለጽ ብነግራችኁ ሐኪሞች በአንድ ታማሚ ሰውነት ውስጥ ያለውን ቆሻሻ፣ መርዘኛ ፈሳሽን ማስገድ ሲፈልጉ መዠመሪያ የሚያደርጉት ነገር ቢኖር ታማሚው ምግብ ከመውሰድ እንዲቈጠብ ነው፡፡ ታማሚው ለጊዜው ምግብን ከመብላት ካልተከለከለ ሓኪሞቹ የሚሰጡት መድኃኒት እንደተፈለገው ውጤት አይሰጥም፡፡ እኛም ቁስለ ነፍስ ቁስለ ሥጋ የምትፈውሰውን ጾም ስንቀበላት ከዚኽ በላይ ልንኾን ይገባናል ብዬ እነግራችኋለኹ፡፡ ድኅነተ ሥጋ ድኅነተ ነፍስን የምንሻ ከኾነ ልቡናችንን ንጹሕና ንቁ በማድረግ ልንወስዳት ይገባናል፡፡ እንዲኽ ካልኾነ ግን ከጥቅሟ ይልቅ ጉዳቷ ያመዝናል፡፡
 ዛሬ የምነግራችኁ ነገረ ለአንዳንዶቻችኁ እንዲኹ ተራ የልበ ወለድ ንግግር እንደሚኾንባችኁ አውቃለኹ፡፡ እኔ ግን በዓላማ (ድኅነተ ሥጋ ድኅነተ ነፍስን ለማግኘት) የምንጾም እንኹን እንጂ እንዲኹ የልማድ ባርያ አንኹን ብዬ እማልዳችኋለኹ፡፡ እስኪ ንገሩኝ! በየቀኑ ሆዳሞችና ሰካራሞች በመኾናችን የምናገኘው ጥቅም ምንድነው? አንዳች የምናገኘው ጥቅም የለም፡፡ ይልቁንም የከፋ ጉዳትን በራሳችን ላይ የምናመጣ ነን ብዬ እነግራችኋለኹ፡፡ ከልክ በላይ ጠጥተን ስንሰክር የማስተዋል ልቡናችን ይጠፋል፤ የጾም ጥቅሟም አብሮ ይጠፋል፡፡ እስኪ ንገሩኝ! እስከ እኩለ ሌሊት ድረስ ብዙ መጠጥን ከሚጠጡ ሰዎች በላይ የሚያንገሸግሽ ምን አለ? ወይንን በመጠጣት በየመሸታ ቤቱ አድረው ፀሐይ ከምትወጣባቸው ሰዎች በላይ የሚያሳዝን ማን አለ? እነዚኽ በመጠጥ ብዛት የሚሰክሩ ሰዎች ከሚያገኙት ሰው ጋር ይጋጫሉ፤ ጠጪው ሰካራሙ ተብለው በማኅበረ ሰብኡ ይታወቃሉ፤ ቤታቸው የተናቀ ነው፤ የሚናገሩት ነገር ቁምነገር ስለሌለው ሕፃን ዐዋቂው ይሳለቅባቸዋል፡፡ ከዚኽም በላይ በጣም የሚያሳዝነው ነገር ደግሞ የእግዚአብሔር ቃል እንደሚል “ሰካሮች የእግዚአብሔርን መንግሥት አይወርሱም” /1ኛ ቆሮ.6፡10/፡፡ ወዮ! … ወዮ! … ወዮ! … እንደ ጧት ጤዛ ለሚጠፋ ርካታ የዘለዓለምን መንግሥት ማጣት እንደምን ያለ ጉስቁልና ነው?
 እዚኽ ጉባኤ የተሰበሰብን ምእመናን በእንደዚኽ ዓይነት ስንፍና ከመያዝ እግዚአብሔር ይጠብቀን! እያንዳንዷን ቀን በትዕግሥትና ራስን በመግዛት ኾነን በዙርያችን ከሚያንዣብበው የዲያብሎስ ወጀብም ተጠብቀን ወደ ነፍሳችን ወደብ ይኸውም ወደ እውነተኛ ጾም ከርሷ የሚገኘውን ድኅነተ ሥጋ ድኅነተ ነፍስም እናገኝ ዘንድ እግዚአብሔር ይርዳን፡፡

                                   በአውሮጳ   የካህናት አንድነት ማኅበር ሊቋቋም መሆኑ ታወቀ በ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከመላዋ አውሮጳ   የተውጣጡ ካህናት፡” የ...