የደብረ ሊባኖስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት አንድነት ገዳም ገዳማዊ
ሥርዓቱ እንደተጠበቀ ቢሆንም የጎርፍ አደጋ፤ የብዝኅ ሕይወት መመናመን፤ የሕገ ወጥ የመሬት ወረራና ሌሎችም ችግሮች
እየተፈታተኑት ይገኛል፡፡ ይህንን ችግር ለመቅረፍና ዘላቂ መፍትሔ ለማምጣት በገዳሙና በማኅበረ ቅዱሳን ባለሙያዎች
ፕሮጀክቶች ተቀርጸው ወደ ሥራ ተገብቷ
ፕሮጀክቶቹንም በተያዘላቸው እቅድ መሠረት ለማስፈጸም በጠቅላይ
ቤተ ክህነት ስብከተ ወንጌል አዳራሽ ሠኔ 8 ቀን 2006 ዓ.ም. የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ ግብር ላይ ፕሮጀክቶቹንና
ገዳሙን አስመልክቶ የተዘጋጀ መጽሔት ለምእመናን ተሰራጭቷል፡፡ ከመጽሔቱ ያገኘናቸውን ጥቂት መረጃዎች እናካፍላችሁ፡
ገዳሙ በጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት በ1296 ዓ.ም. የተቆረቆረ ሲሆን፤ 710 ዓመታትን አስቆጥሯል፡፡ በገዳሙ አስተዳደር ሥር ከአቡነ ተክለ ሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን በተጨማሪ የቅዱስ አማኑኤል እና የቅዱስ ፊልጶስ አብያተ ክርስቲያናት ይገኛሉ፡፡
በገዳሙ ውስጥ የሚጎበኙ የተለያዩ የነገሥታት ሥጦታዎች፤ ቅዱሳት መጻሕፍት፤ ንዋየ ቅድሳት፤ የቅዱሳን አጽም፤ ፈውስ የሚገኝባቸው የጸበል ቦታዎችም ይገኛሉ፡፡
የደብረ ሊባኖስ ገዳም አምስቱ ስያሜዎችን ስንመለከት፡-
ምድረ ግራሪያ፡-
ግራሪያ የሚለውን ስያሜ የሰጠችው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ናት፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከልጇ ከወዳጇ ከጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ወደ ምድረ ግብጽ ስትሰደድ በኢትዮጵያ ውስጥ ከቆየችባቸው ቦታዎች አንዱ ይህ ቅዱስ ቦታ ነው፡፡ ለአንድ ሳምንት ቆይታ አድርጋ የቦታውን ስም ምድረ ግራሪያ ስትል ሰይማዋለች፡፡ ግራሪያ ማለት ኩሉ ይገርር ሎቱ፤ ሁሉ ይገዛላታል ማለት ነው፡፡ አንድም ግራር በቁሙ ለሁሉ ጥላ፤ መሰብሰቢያ እንደሆነ ደብረ ሊባኖስም የሁሉ ጥላ መሰብሰቢያ ነውና ምድረ ግራሪያ ተብሏል፡፡