2014 ሴፕቴምበር 6, ቅዳሜ

ጳጉሜን - አምስት፣ ስድስት፣ ሰባት

የመግቢያ ማስታወሻ
በጽሑፉ ውስጥ በግእዝ ቁጥሮች በቅንፍ ውስጥ የተጻፉት ሐሳቡን እንዲወክሉ ብቻ ነው፡፡ በኋላ (ቁጥር ፭ ተመልከት ቢል ያንን ሐሳብ መልሶ ለማየት እንዲረዳ ነው፡፡
የኢትዮጵያን የዘመን አቆጣጠር ለየት ከሚያደርጉት ነገሮች አንዱ ጳጉሜ የምትባል አሥራ ሦስተኛ ወር ስላለችን ነው፡፡ የቤት ኪራይና የወር ደመወዝ የማንከፍልባትና የማንቀበልባት፤ መብራትና ውኃ ግን ከነሐሴ ወር ጋር ጨምረው የሚያስከፍሉባት፤ ሲሻት አምስት፣ ሲያስፈልጋት ስድስት፣ ስትፈልግ ደግሞ ሰባት የምትሆን ወር ናት፡፡ እንዲያውም ከአሥራ ሁለቱ የኢትዮጵያ ወሮች ጳጉሜ በብዙ መንገድ የተለየች ናት፡፡
በአንድ በኩል በጣም ትንሿ ወር ናት፡፡ ሲቀጥልም ወርኃዊ በዓላት የማይውሉባት ወር ናት፡፡ እንዲያም ሲል ደግሞ ከሌሎች ወሮች በተለየ የቀኖቿ መጠን የሚቀያየሩ ብቸኛ ወር ናት፡፡ ከሌሎች የኢትዮጵያ ወሮች በተለየም ስሟ ኢትዮጵያዊ ያልሆነ ወር ናት፡፡ በሁለት ዘመናት መካከልም እንደ መሸጋገሪያ የምትታይ ወርም ናት፡፡  


ጳጉሜ ማለት በግሪክ ‹ጭማሪ› ማለት ሲሆን ዓመቱን በሠላሳ ቀናት ስንከፍለው የሚተርፉትን ዕለታት ሰብስበው የሰየሟት ተጨማሪ ወር ናት፡፡ ወይም በየዕለቱ በፀሐይና በጨረቃ አቆጣጠር መካከል የሚፈጠረውን ልዩነት ሰብስበው ያከማቹባት ወር ትባላለች፡፡ ዓመቱ በዐውደ ፀሐይ ሲለካ 365 ቀናት ከ15 ኬክሮስ 6 ካልዒት ሲሆን በጨረቃ ሲለካ ደግሞ 354 ቀናት ከ22 ኬክሮስ፣ 1 ካልዒት፣ 36 ሣልሲት፣ 52 ራብዒት፣ 48 ኀምሲት ነው፡፡ (60 ኬክሮስ አንድ ቀን ነው)በሁለቱ መካከል(በፀሐይና በጨረቃ) በዓመት ውስጥ ያለው ልዩነት 11 ቀናት ከ7 ኬክሮስ ይሆናል፡፡ [በነገራችን ላይ በዘመን አቆጣጠራችን ውስጥ ከዕለት በታች የምንቆጥርባቸው ስድስት መለኪያዎች አሉ፡፡ ኬክሮስ፣ ካልዒት፣ ሣልሲት፣ ራብዒት፣ ኀምሲትና ሳድሲት፡፡ 60 ሳድሲት አንድ ኀምሲት፣ 60 ኀምሲት አንድ ራብዒት፣ 60 ራብዒት አንድ ሣልሲት፣ 60 ሳልሲት አንድ ካልዒት፣ 60 ካልዒት ደግሞ 1 ኬክሮስ ይሆናል፡፡ 60 ኬክሮስ ደግሞ 1 ዕለት፡፡ 1 ኬክሮስ 24 ደቂቃ ነው]
ጳጉሜን ለማግኘት የሚጠቅመን የየዕለቱን ልዩነታቸውን መመልከቱ ነው፡፡ በየዕለቱ በጨረቃና በፀሐይ መካከል 1 ኬክሮስ 52 ካልዒት(60 ካልዒት አንድ ኬክሮስ ነው)፣ ከ 31 ሣልሲት(60 ሣልሲት አንድ ካልዒት ነው) ይሆናል፡፡[ይህም ማለት 5 ሰዓት ከ48 ደቂቃ ከ46 ካልዒት(ሴኮንድ?)] ይህ ልዩነት በአንድ ወር ምን እንደሚደርስ ለማወቅ በ30 እናባዛው፡፡ 30 ኬክሮስ፣ 1560 ካልዒት፣ ከ930 ሣልሲት ይሆናል፡፡ የዓመቱን ለማግኘት ደግሞ በ12 እናባዛው፡፡ 360 ኬክሮስ(፩)፣ 18720 ካልዒት(፪)፣ 11160 ሣልሲት(፫) ይመጣል፡፡
ቀደም ብለን 60 ኬክሮስ አንድ ዕለት ይሆናል ባልነው መሠረት 360 ኬክሮስ ለ60 ሲካፈል 6 ዕለታትን ይሰጠናል(፩)፡፡ 18720 ካልዒትን(፪) በስድሳ በማካፈል 312 ኬክሮስን እናገኛለን፡፡ ያም ማለት ትርፉን 12 ኬክሮስ ትተን 300ውን ኬክሮስ ለ60 በማካፈል 5 ዕለት እናገኛለን፡፡ ይኼም ማለት 5 ዕለት ከ12 ኬክሮስ(፬) ይሆናል፡፡ 11160 ሣልሲትን(፫)ለ60 ብናካፍለው 186 ካልዒት ወይም ደግሞ 3 ኬክሮስና 6 ካልዒት(፭) ይሆናል ማለት ነው፡፡
ከላይ ኬክሮስን በዓመቱ ቀናት አባዝተን ያገኘነው(፩) 6 ዕለት አለ፡፡ ይኼ ዕለት ሕጸጽ ይባላል፡፡ ፀሐይና ጨረቃን እኩል መስከረም አንድ ላይ ዓመቱን ብናስጀምራቸው ፀሐይ የወሯ መጠን ምንጊዜም ሠላሳ ሲሆን ጨረቃ ግን በአንደኛው ወር 29 በሌላኛው ወር ግን 30 ስለምትሆን ዓመቱ እኩል አያልቅም የጨረቃ ዓመት ነሐሴ 24 ቀን ያልቃል፡፡ ይህም ማለት ጨረቃ በሁለት ወር አንድ ጉድለት ታመጣለች፡፡ ያንን ነው ሊቃውንቱ ሕጸጽ(ጉድለት) ያሉት፡፡ በዚህም መሠረት ከላይ ኬክሮሱን(፩) በዓመቱ ቀናት አባዝተን ያገኘነውን 6 ዕለት ለጨረቃ ሕጸጽ ስንሰጠው የመስከረም/ ጥቅምት (1)፣ የጥቅምት/ ኅዳር(2)፣ የጥር/ የካቲት(3)፣ የመጋቢት/ ሚያዝያ(4)፣ የግንቦት/ ሰኔ (5)፣ የሐምሌ ነሐሴ (6) ሆነው ተካፍለው ያልቃሉ፡፡
በሌላም በኩል ደግሞ በጨረቃና በፀሐይ ዑደት መካከል በዓመት ያለው ልዩነት 11 ቀናት ከ15 ኬክሮስ ከ6 ካልዒት) ይሆናል፡፡ ስድስቱን ዕለታት ጨረቃ ለምታጎልበት (ሕጸጽ) ብንሰጠው ቀሪ 5 ዕለት ይኖረናል፡፡ ጳጉሜ ማለት እነዚህ 5 ቀናት ናቸው፡፡ አሁን የአሥራ አንዱን ዕለታት ከፈጸምን ሽርፍራፊዎቹን (15 ኬክሮስና 6 ካልዒት) እንይ፡፡
ከላይ እንዳየነው በፀሐይና ጨረቃ ዓመታት መካከል የተፈጠሩትን 11 ቀናት ስድስቱ ለሕጸጽ ማሟያ ሲገቡ የቀሩት 5 ዕለታት ናቸው ጳጉሜ የምትባለውን ወር በመሠረታዊነት የፈጠሯት፡፡ በጎርጎርዮሳውያኑ አቆጣጠር እነዚህ 5 ተጨማሪ ዕለታት በጃንዋሪ፣ ማርች፣ ሜይ፣ ጁላይና ኦገስት ላይ ስለተጨመሩ እነዚህ ወራት 31 ለመሆን ተገድደዋል፡፡ (ይህንን የከፈለው በ46 ቅልክ የነበረው ዩልየስ ቄሣር ነው፡፡ ለአራቱ ወሮች 30 ቀን፣ ለአንዱ 28/29 (በየአራት ዓመቱ)፣ ለቀሩት ሰባት ወሮች ደግሞ 31 ሰጥቷቸዋል፤ ለአምስቱ ወሮች 31 ያደረጋቸው ከጳጉሜ ወስዶ ሲሆን ለሁለቱ ወሮች አንዳንድ ቀን የጨመረላቸው ከፌቡርዋሪ 2 ቀናት ወስዶና ወሩን 28 አድርጎ ነው)፡፡
ከእንግዲህ የሚቀሩን ከላይ የየዕለቱን ልዩነት ለዓመት ስናባዛ (ቁጥር ፪ና ፫ ተመልከት) የቀሩን 15 ኬክሮስና 6 ካልዒት ናቸው፡፡ ሁለቱን  ከላይ ያየናቸውን (፬ና፭) ስንደምራቸው (12 ኬክሮስ + 3 ኬክሮስ ከ6 ካልዒት) 15 ኬክሮስ ከ 6 ካልዒት ይመጣሉ፡፡
ቀደም ብለን አንድ ዕለት 60 ኬክሮስ ነው ብለናል፡፡ ስለዚህም አንድ ዕለት (60 ኬክሮስ) ለማግኘት ከላይ ያገኘነውን 15 ኬክሮስ በ 4 ማባዛት አለብን፡፡ በአራት ዓመት አንዴ ጳጉሜ 6 የምትሆነው እነዚህ በየዓመቱ የተጠራቀሙት 15 ኬክሮሶች አንድ ላይ መጥተው በአራት ዓመት አንድ ጊዜ አንድ ዕለት ስለሚሆኑ ነው፡፡ እርሷም ሠግር(leap year) ትባላለች፡፡ ጎርጎርዮሳውያኑ ይህቺን ሠግር በፌቡርዋሪ ወር ላይ ጨምረው ወሩን በየአራት ዓመቱ አንድ ጊዜ 29 ቀን ያደርጉታል፡፡
15ቱ ኬክሮስ በአራት ዓመት ተደምረው አንድ ዕለት መጡና በአራት ዓመት አንዴ ጳጉሜን ስድስት አደረጓት፡፡ የቀረችው 6 ካልዒትስ (ቁጥር ፭) የት ትግባ?
ካልዒት አንዲት ዕለት ትሆን ዘንድ 3600 ካልዒት ያስፈልጋሉ፡፡ ይህንን ያህል ካልዒት ለማግኘት 600 ዓመታት ያስፈልጉናል፡፡ ለዚህ ነው ጳጉሜ በየስድስት መቶ ዓመታት ሰባት የምትሆነው፡፡ እስካን የጠየቅኳቸው የባሕረ ሐሳብና የታሪክ ሊቃውንት በታሪካችን ውስጥ ጳጉሜን 7 የሆነችበትን ዘመን እንደማያውቁ ነግረውኛል፡፡ ሒሳቡ ሲሰላ በየ 600 ዓመቱ ሰባት ትሆናለች ቢባልም አስቦ በስድስት መቶኛው ዓመት ሰባት የሚያደርጋት እንደሌለ ይናገራሉ፡፡ በፈረንጆቹ ብሂል ‹ፌብሩዋሪ 30› ማለት የመሆን ዕድል ያለው ነገር ግን ሆኖሞ የማያውቅ ሊሆንም የማይችል(possible but never happen)› ተደርጎ እንደተወሰደው ሁሉ ምናልባት በኛም ጳጉሜን 7 ማለት እንደዚያው ይሆን ይሆናል፡፡
በነገራችን ላይ ጳጉሜን 5 ቀን በቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ዘንድ ‹ዕለተ ምሪያ› ወይም የተመረጠች ቀን ትባላለች፡፡ የጌታችን ልደት ለመጠበቅ ሊቃውንቱ ሲያሰሉባት የቆየችው ዕለት በመሆኗ ነው ይህንን ስያሜ ያገኘችው፡፡ የጌታችንን ልደት ቀን የምትወስነው ጳጉሜ 5 ቀን ናት፡፡ ልደት የሚውለው ጳጉሜ 5 በዋለበት ቀን ነው፡፡ ለምሳሌ ዘንድሮ ጳጉሜን 5 ቀን ረቡዕ ነው የምትውለው፤ ስለዚህም በ2007 ዓም ልደት የሚውለው ረቡዕ ነው፡፡ በየአራት ዓመቱ አንድ ጊዜ ጳጉሜን 6 ስትሆን ልደት በ28 የሚከበረው ዕለተ ምሪያን ስለማይለቅ ነው፡፡ ስድስተኛዋ ቀን ልደትን በአንድ ቀን ስታዘልለው እኛ በ28 እናከብረዋለን፡፡ ልደት ጳጉሜ 5 ቀንን(ዕለተ ምሪያን) ስለማይለቅ፡፡ ታድያ ምነው እነ ጥምቀትና ግዝረት አይለወጡም? ቢሉ፡፡ ሊቃውንቱ የሚሰጡት መልስ ‹ትውልድ ሱባኤ እየቆጠረ በተስፋ የጠበቃት ዕለተ ልደትን ስለሆነ ነው፤ ሌሎቹ የመጡት በልደቱ ምክንያት ነው›› የሚል ነው፡፡
በጎርጎርዮሳውያንም ቢሆን በአራት ዓመት አንዴ ልደት ዝቅ ትላለች፡፡ የእነርሱ የማይታወቀን ጭማሪዋ ፌብርዋሪ ላይ ስለሆነች ነው፡፡ ያ ደግሞ አዲሱን ዓመት ካከበሩ በኋላ ስለሚመጣ ነው፡፡ የእኛ ግን የምትወድቀው ጳጉሜን መጨረሻ ላይ በመሆኗ ከአዲስ ዓመት በፊት ስለምትጨመር ጎልቶ ይታወቃል፡፡
እንግዲህ ጳጉሜ የምትባለው አስገራሚ ትንሷ ወራችን እንዲህ በስሌት የተሞላች፣ አምስት ሆና ቆይታ በየአራት ዓመቱ አንዴ ስድስት፣ በየስድስት መቶ ዓመቱ ደግሞ ሰባት የምትሆን ናት፡፡ ታላላቆቹ ወሮች ምንም ሳይፈጥሩ የልደትን ቀን የምትወስን፣ የዓመቱን ሠግር የምታመጣ፣ ታሪከኛ ወር ናት፡፡ ትንሽ ትልቅ ማለት እንዲህ ነው፡፡

አዲሱ ዓመት - ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዳስተማረው (ክፍል ፫)



(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ጳጉሜ ፩ ቀን፣ ፳፻፮ ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
የቀጠለ…                       
 ለእግዚአብሔር ክብር ብሎ ሰውን መውቀስም አለ፡፡ ከእናንተ መካከል፡- “እንዴት ብሎ? ርግጥ ነው ብዙውን ጊዜ ሠራተኞቻችንን እንወቅሳለን፡፡ ለእግዚአብሔር ክብር ብሎ መውቀስስ እንደምን ያለ ነው?” አዎ! የሚሰክር ወይም የሚሰርቅ ሠራተኛ ወይም ጓደኛ ብናይ ወይም ከዘመዳችን አንዱ ወደ ተውኔት ቤት፣ ወይም ለነፍሱ ምንም ረብሕ ወደማያገኝበት ሥፍራ ሲሮጥ፣ በከንቱ ሲምል፣ የሐሰት ምስክርነትን ሲሰጥ፣ ወይም ሲዋሽ፣ ወይም ሲቈጣ ብናየው ዠርባችንን ብንሰጠውና ብንገሥፀው ወቀሳችን ለእግዚአብሔር ክብር የተደረገ ነው ይባላል፡፡

 ዳግመኛም አንድ ሰው ቢበድለን፣ ርሱ ራሱ የሠራውንም ጥፋት በእኛ ቢያመካኝ ስለ እግዚአብሔር ብለን ይቅር ልንለው ይገባል፡፡ ብዙዎቻችን ግን ለጓደኞቻችን፣ ለሠራተኞቻችን የዚኽ ተቃራኒውን ነው የምናደርገው፡፡ ጓደኞቻችን ወይም ሠራተኞቻችን ቢበድሉን እናንባርቃለን፤ ይቅርታ የሌለው ፍርድም እንፈርድባቸዋለን፡፡ እኛው ራሳችን እግዚአብሔርን በገቢር ስንሰድብ አንድም ስናሰድብ ወይም ነፍሳችንን ስንጐዳ ግን እንደበደልን አይሰማንም፡፡ ይኽ ግን በአዲሱ ዓመት ልናስተካክለው የሚገባ ነገር ነው፡፡ ዕለት ዕለትም ልንለማመደው ይገባል፡፡  
 የበደሉንን ሰዎችስ ወዳጅ ማድረግ ይገባልን? አዎ! ለእግዚአብሔር ክብር ሲባል የበደሉንን ሰዎች ወዳጅ ማድረግ ይገባናል፡፡ ለእግዚአብሔር ክብር ሲባል ሰውን ጠላት ማድረግስ? አዎ! ይቻላል፡፡ ለመኾኑ ስለ እግዚአብሔር ክብር ብሎ ሰውን ወዳጅና ጠላት ማድረግ ሲባል ምን ማለት ነው? ሰውን ወዳጅ ማድረግ ሲባል ያንን ሰው ከገንዘባችን፣ ከማዕዳችን እንዲካፈል በእኛም እንዲደገፍ ማድረግ ማለት አይደለም፡፡ አንድን ሰው እውነተኛ ወዳጅ ኾንነው አንድም አደረግነው የሚባለው ነፍሱን እንዳይጐዳ ብንገሥፀውና ብንመክረው፣ ቢበድል (በበደሉ የሚጐዳው ርሱ ራሱ ነውና) እንደ ጠላት ሳይኾን እንደ ወዳጅ ቀረብ ብለን የሚረባውን ብንነግረው፣ ከወደቀበት የኀጢአት አረንቋ እንዲነሣ ብናደርግ ለዚኽም ዘወትር በጸሎት ብንረዳውና ወደ እግዚአብሔር እንዲቀርብ ብናደርግ ነው፡፡ ስለ እግዚአብሔር ክብር ብሎ ሰውን ጠላት ማድረግም ይፈቀዳል፡፡ ይኽን ከዚኽ በፊት ያላከናወንነው ከኾነም ከአኹኑ አዲሱ ዓመት መዠመር እንችላለን፤ ለእግዚአብሔር ክብር ብለን ሰውን ጠላት ማድረግ፡፡ ለምሳሌ አንድ ጋጠ ወጥ፣ ክፋትን የተመላ፣ ንግግሩ (ትምህርቱ) ኹሉ በምንፍቅና መርዝ የተለወሰ፣ ዘወትር ነፍሳችንን የሚያውካትና የሚጐዳት ሰው ካለ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “ቀኝ ዓይንኅም ብታሰናክልኽ አውጥተኽ ከአንተ ጣላት” እንዳለ /ማቴ.5፡29/ እነዚኽን ሰዎች መራቅ ጠላትም ማድረግ ይፈቀዳል፡፡ እነዚኽ ሰዎች ቀኝ ዓይን ተብለው መጠቀሳቸውም ምንም እንኳን እንደ ዓይናችን የምናያቸው ወዳጆቻችን ቢኾኑም ነፍሳችንን የሚጐዷት ከኾነ ከእኛ ዘንድ ልናርቃቸው ይገባል፡፡
 ንግግራችንም ዝምታችንም ለእግዚአብሔር ክብር ልናደርገው ይገባል፡፡ ስለ እግዚአብሔር ብሎ መናገር ሲባል ምን ማለት ነው? ለምሳሌ ከአንድ ጓደኛችን ጋር ቁጭ ብለን ስንጨዋወት “ማን ሥልጣን ላይ ወጣ፣ ማን ወረደ፣ ማን አለፈ፣ ማን ምን ክብር አገኘ” እያልን ከምንጨዋወት ይልቅ ስለ ነገረ ሃይማኖት፣ ስለ ገሃነመ እሳት፣ ስለ መንግሥተ ሰማያት ብንጨዋወት መናገሩ ጥቅምን ይሰጣል፡፡ ነፍሳችንን በማይጠቅማት ነገር አላስጨነቅናትምና፡፡ ይኽን ዓይነት ኅብረት ባንተወዉም አንጐዳንም፡፡ በኋለኛው ቀን ላይ ይኽ ኹሉ ማድረጋችን አንዳች ጥቅም ይሰጠናልና፡፡ ስለዚኽ ለነፍሳችን አንዳች የሚጠቅም ነገር በሌለው ስብስብ መካከል መቀመጡና ማውራቱ ለእኛ ጉዳት እንጂ ረብሕ የለውም፡፡ የዚኽ ስብስብ መንፈስ ለውጦ ስለ ነገረ እግዚአብሔር ማውራቱም ስለ እግዚአብሔር ክብር አደረግነው ይባላል፡፡ ዝምታችንም ለእግዚአብሔር ክብር መኾን ይገቧል፡፡ ምንም ሳንበድለው ክፉ ለሚያደርግብን ሰው፣ ሳንወቅሰውና ሳናንጐራጉርበት በትዕግሥት ዝም ብንል ዝምታችን ለእግዚአብሔር ክብር የተደረገ ነው ይባላል፡፡
ማመስገንና መገሠፅ፣ ወይም ከቤት ውስጥ መኾንና አለመኾን ወይም መናገርና አርምሞ ብቻ አይደለም፤ ኀዘናችንም ደስታችንም ስለ እግዚአብሔር ክብር ሊኾን ይገባል፡፡ አንድ ወንድማችን ኀጢአት እየሠራ ብናየው ወይም እኛው ራሳችን በበደል ስንወድቅ ብናለቅስና ብናዝን ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እንዳለ “እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ የኾነ ኀዘን ጸጸት የሌለበትን፣ ወደ መዳንም የሚያደርሰውን ንስሐ ያደርጋልና” /2ኛ ቆሮ.7፡10/ ኀዘናችን ለእግዚአብሔር ክብር የተደረገ ነው ይባላል፡፡ አንድ ወንድማችን መልካም ነገርን ስላገኘ ልክ ለእኛ እንደተደረገ አድርገን እግዚአብሔርን ብናመሰግንም ደስታችን ለእግዚአብሔር ክብር የተደረገ ነው ይባላል፡፡ ከዚኽ ደስታም እጅግ ብዙ ጥቅምን እናገኝበታለን፤ እንኪያስ ይኽን በአዲሱ ዓመት እንለማመደዋ!!!
 በወንድሙ ደስታ መደሰት ሲገባው ወንድሙ ስለ ተጠቀመ ብቻ በቅናት ከሚቃጠል ሰው በላይ አሳዛኝ ሰው ማን አለ? እስኪ ንገሩኝ! በወንድሙ ደስታ በማዘኑ የእግዚአብሔርን ፍርድ በራሱ ላይ በመጨመር በነፍስ በሥጋ ከሚጐዳ ቅናተኛ ሰው በላይ የሚያሳዝን ፍጥረት ማን አለ? ወንድማችን ስለ ተጠቀመ ብናመሰግን ወይም ብንደሰት፣ ወንድማችን ስለ ተጐዳም ብናዝን እና ብናለቅስ ይኽንንም ለእግዚአብሔር ክብር ብለን ብናደርገው አንጠቀምምን?
  ፀጉርን ከማሳጠር በላይ ምን ትንሽ ነገር አለ? ነገር ግን ይኽም ለእግዚአብሔር ክብር ማድረግ ይቻላል፡፡ ለምሳሌ ሴቶች በፀጉራቸው ምክንያት ወንዶች የሚሰነካከሉ ከኾነና ይኽንን ዐውቀው ባይቈርጡትም ወንዶቹ በማይሰናከሉበት መንገድ ቢሸላለሙት፣ ደካማ ወንድሞቻቸው በማይሰናከሉበት መንገድ ራሳቸውን ቢያጌጡ ይኽን ለእግዚአብሔር ክብር አድርገዉታልና ሹመት ሽልማታቸው የበዛ ነው፡፡ የክፉ ምኞት ፍላጻን ለእግዚአብሔር ክብር ሲባል አስቀርተዉታልና ዋጋቸው በሰማያት ዘንድ ታላቅ ነው፡፡ ስለ እግዚአብሔር ክብር ብሎ አንዲት ኩባያ ውኃን የሰጠ ሰው ርስት መንግሥተ ሰማያትን የሚያገኝ ከኾነ፥ የምናደረግው ኹሉ ለእግዚአብሔር ክብር ብለን የምናከናውነው ከኾነማ ሹመት ሽልማታችን እንደምን አይበዛ?
  ስለ እግዚአብሔር ክብር ብሎ መሔድም አለመሔድም አለ፡፡ ምን ማለት ነው? ወደ ክፋት የማንሔድ ከኾነ፣ የቆነጃጅትን ውበት በማድነቅ ስም ልቡናችን በምኞት መንፈስ የማንጠመድ ከኾነ፣ አንዲት ቆንጆ ልጅ በፊታችን ብናይና እንደምታሰናክለን ተረድተን ዓይናችንን ከርሷ ዞር የምናደርግ ከኾነ ውበትን ለእግዚአብሔር ክብር አዋልነው ይባላል፡፡
 አለባበሳችንም ቢኾን ለእግዚአብሔር ክብር ልናደርገው ይገባናል፡፡ እጂግ ውድ የኾኑ አልባሳትን ባንለብስ፣ ሰውነታችንን እጂግ ሳናራቁት፣ በአጭሩ ሰውን የማያሰናክል አለባበስን ብንከተል አለባበሳችን ስለ እግዚአብሔር ክብር አደረግነው ይባላል (በነገራችን ላይ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በአጸደ ሥጋ በዚኽ ዘመን ቢኖርና ከቅርብ ጊዜ ወዲኽ የምናየውን የእኅቶቻችንን አለባበስ ቢያይ ምን ብሎ ሊገሥፅ እንደሚችል አስቡት፡፡ ምክንያቱም እኅቶቻችን በስመ ዘመናዊነት የሚለብሱት እጅግ በጣም አጭር ቀሚስ ወይም ሱሪ የብዙ ደካማ ወንዶችን ልብ በዝሙት ይፈታተናልና)፡፡
 የምጫማው ጫማ እንኳን ለእግዚአብሔር ክብር ልናደርገው ይገባል፡፡ አንዳንድ ሰዎች ለሚያደርጉት ጫማ ከዓቅም በላይ ሲጨናነቁ አያለኹ፡፡ ፊታቸውን በተለያየ መንገድ ለማሸብረቅ የሚወዱትን ያኽል ስለ ጫማቸው ውበት እጂግ የሚጨነቁ ሰዎችን አያለኹ፡፡ ምንም እንኳን ይኽ እንደ ትንሽ ነገር አድርገን ብናስበውም ዘወትር በወንዶችም በሴቶችም የምናየው ነገር ነው፡፡ ስለዚኽ ጫማችን እንኳን ሳይቀር ለእግዚአብሔር ክብር ልናደርገው ይገባናል ማለት ነው፡፡ በአካሔዳችንም፣ በአለባበሳችንም፣ እግዚአብሔርን ደስ ማሰኘት እንደሚቻል ሲናገር ጠቢቡ ምን እንደሚለን እስኪ እናድምጠው፡- “ከአለባበሱና ከአካሔዱ ከአሳሳቁም የተነሣ የሰው ጠባዩ ይታወቃል” /ሲራክ 19፡27/፡፡ ስለዚኽ በአዲሱ ዓመት ብቻ ሳይኾን በየዕለቱ የምናደርገው ኹሉ ለእግዚአብሔር ክብር የምናደርገው ከኾነ አሕዛቡም፣ መናፍቁም፣ ፈላስፋውም አስቦበት ሳይኾን እንዲኹ በእኛ ይደነቃል፡፡
 ትዳራችን እንኳን ለእግዚአብሔር ክብር ልናደርገው ይገባናል፡፡ መኝታችን (በትዳር ውስጥ የሚደረገው ሩካቤ) ንጹሕ ማድረግ፣ ትዳርን ለብር ወይም ሌላ ምድራዊ ነገርን ለማግኘት ሳይኾን ነፍሳችንን ለማዳን፣ እግዚአብሔርን ለማግኘት የሚደረግ ከኾነ ለእግዚአብሔር ክብር አደረግነው ይባላል፡፡ የትዳር አጋራችንን ከዘለዓለማዊ ሕይወት አንጻር እንጂ ከውበት፣ ከሃብት፣ ወይም ከሌላ ጊዜአዊ ጥቅም አንጻር የማንመለከት ከኾነ ትዳራችን ለእግዚአብሔር ክብር የተደረገ ነው ይባላል፡፡ በአዲሱ ዓመት ይኽን ልንለማመድ ይገባናል፡፡
 ይቀጥላል…

አዲሱ ዓመት - ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዳስተማረው (ክፍል ፪

)




(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ነሐሴ ፳፯ ቀን፣ ፳፻፮ ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
የቀጠለ…

 ከገቢረ ኀጢአት ሳይወጡ አዲስ ዓመት ሲመጣ መደሰት፣ ብዙ መብልና መጠጥ ማዘጋጀት፣ አዲስ ልብስም መልበስ ጥቅም የለውም፡፡ ነፍሳችን በኀጢአት እየተጨነቀች፣ ነፍሳችን ተርባና ተጠምታ ሳለ፣ የተዳደፈ የኀጢአት ልብስም ተጆቡና ሳለ አዲስ ዓመት ማክበር ለእኛ ምን ጥቅም ይሰጠናል? እንዲኽ ከገቢረ ኀጢአት ሳይወጡ አዲስ ዓመትን ማክበር ማለት ለእኔ እንደ ልጆች የዕቃ ዕቃ ጨዋታ ነው፡፡

 ክርስቶስ ከዚኹ ሥራ አውጥቶናል፡፡ ከሕፃንነት አዕምሮ ወደ ማወቅ አሸጋግሮናል፡፡ ከምድራውያን ለይቶ ከሰማያውያን ጋር ደባልቆናል፡፡ ስለዚኽ “መልካሙን ሥራችኁን ዐይተው በሰማያት ያለውን አባታችኁን እንዲያከብሩ ብርሃናችኁ እንዲኹ በሰው ፊት ይብራ” እንደተባለ አፍአዊ ሳይኾን መንፈሳዊውን ብርሃን ልናበራ ይገባናል /ማቴ.5፡16/፤ በአዲሱ ዓመት፡፡ ይኽም ብርሃን ተስፋ መንግሥተ ሰማያትን የሚያስገኝ ነው፡፡
 ወዳጄ ሆይ! ቤቱ ቆሽሾ ሳለ ውጫዊ በሩን ብቻ ለማሽቀርቀር ለምን ትጨነቃለኽ? ነፍስኅ በኀጢአት ተዳድፋ ሳለ ሥጋኽን ብቻ ለማስደሰት ለምን ትሮጣለኽ? አስቀድመኽ ቤቱን (ነፍስኽን) ለማስዋብ አትሽቀዳደምምን? አስቀድመኽ ለነፍስኽ የምታስብ ከኾነ ከሰው እጅ ሳይኾን ከክርስቶስ እጅ ሹመት ሽልማት ትቀበላለኽ፡፡ ኹል ጊዜ “የማደርገው ነገር እግዚአብሔር ይከብርበታልን?” ብለኽ አስብ እንጂ እንዲኹ በዘልማድ የምትመላለስ አትኹን ብዬ እመክርኻለኁ፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ሲመክረን፡- “እንግዲኽ የምትበሉ ወይም የምትጠጡ ብትኾኑ ወይም ማናቸውም ነገር ብታደርጉ ኹሉን ለእግዚአብሔር ክብር አድርጉት” ያለንም ስለዚኹ ነውና በአዲሱ ዓመት በድርጊቶቻችን ኹሉ እግዚአብሔርን ለማክበር እንዘጋጅ /1ኛ ቆሮ.10፡31/፤ አዲስ ዓመት ማክበር ማለት ይኼ ነውና፡፡
 ለመኾኑ ለእግዚአብሔር ክብር ሲባል መብላት ወይም መጠጣት ማለት ምንድነው? ድኻውን ወደ ቤታችን ስንጠራው፤ በማዕዳችንም ክርስቶስ አብሮ ሲኖር ለእግዚአብሔር ክብር በላን ወይም ጠጣን ይባላል፡፡
 ሐዋርያው የመከረን ግን በመብላችን ወይም በመጠጣችን ብቻ እግዚአብሔርን እንድናከብረው አይደለም፡፡ ጨምሮም “ማናቸውም ነገር ብታደርጉ ለእግዚአብሔር ክብር አድርጉት” አለን እንጂ፡፡ ስለዚኽ ወደ ሸንጐም ብንሔድ፤ ወደ ቤተ ክርስቲያንም ብንሔድ ለእግዚአብሔር ክብር ልናደርገው ይገባናል፡፡ እነዚኽን ለእግዚአብሔር ክብር ማድረግ የምንችለውስ እንዴት አድርገን ነው? ወደ ቤተ ክርስቲያን፣ ወደ ሥርዓተ ቅዳሴው፣ ወደ ጉባኤው፣ ወደ ሌላውም አግልግሎት ስንሔድ አካሔዳችን እግዚአብሔር የሚከብርበት መኾን አለበት፡፡ እግዚአብሔር የማይከብርባቸው ብዙ ምልልሶች አሉና በአዲሱ ዓመት ወደ ቤተ ክርስቲያን መመላለሳችን ለእግዚአብሔር ክብር መኾን አለበት፡፡
 ከቤት ቁጭ ማለትን የምንመርጥ ከኾነም ለእግዚአብሔር ክብር ልናደርገው ይገባናል፡፡ “ምን ማለት ነው?” ልትል ትችላለኅ፡፡ ከቤት ወጥተን ክፋት ወደ መላበት ሥፍራ፣ ክርክርና ክስ ወደ ሰፈነበት ሸንጐ፣ ዘፈን ስካርና ገቢረ ኀጢአት ወደሚደገስበት ነፍስንም ወደሚያውክ ስፍራ ከመሔድ ተቈጥበን ከቤት ቁጭ ብንል ለእግዚአብሔር ክብር አደረግነው ይባላል፡፡ ስለዚኽ ከቤት ውስጥ ቁጭ ማለትም ወደ ቤተ እግዚአብሔር መሔድም እኩል ለእግዚአብሔር ክብር ማድረግ ይቻለናል ማለት ነው፡፡
 በአዲሱ ዓመት ብናመሰግንም ብንገሥፅም ለእግዚአብሔር ክብር መኾን አለበት፡፡ “ለእግዚአብሔር ክብር ሲባል ማመስገንና መገሠፅ ሲባልስ ምን ማለት ነው?” ብሎ የሚጠይቅ ሰው ሊኖር ይችላል፡፡ እንበልና በመሥሪያ ቤታችን ቁጭ ብለናል፡፡ እጂግ ክፋትን የተመሉ ሰዎችም በፊታችን ይመላለሳሉ፡፡ እነዚኽ ሰዎች በውስጣቸው በትዕቢት፣ በቁጣ፣ እንዲኹም ይኽን በመሳሰሉ ጥገኛ ተሐዋስያን የተመሉ ናቸው፡፡ ነገር ግን እጂግ ውድ የኾኑ አልባሳትን ለብሰዋል፡፡ አከባቢውን የሚለውጡ ውድ የኾኑ ሽቶዎችን ተቀብተዋል፡፡ ይኽን እያየን ሳለ አንድ ሰው መጥቶ፡- “እንዴት የታደለ ሰው እንደኾነ ዐየኸውን? ደስ አይልም?” ሊለን ይችላል፡፡ እንዲኽ የሚላችኁን ሰው ገሥፁት፤ ምክሩት፤ ወይም ዝም በሉት፡፡ ቢቻላችኁ እዘኑለት (አልቁስለት)፡፡ ተግሣፅን ለእግዚአብሔር ክብር ማድረግ ማለትም ይኼ ነው፡፡
 ተግሣፅ ሲባል ሰዎች ከነበሩበት የተሳሳተ አመለካከት ወጥተው ወደ ቀና አስተሳሰብ እንዲመጡ ማድረግ ነው፡፡ ከእንግዲኽ ወዲኽ ክፋትን ሳይኾን ምግባር ትሩፋትን እንዲያደንቁና እነርሱም ራሳቸው ለዚያ የተዘጋጁ እንዲኾኑ ማድረግ ነው፤ ተግሣፅ፡፡
 ከላይ እንደነገርኳችኁ “እንዴት የታደለ ሰው እንደኾነ ዐየኸውን? ደስ አይልም?” ለሚላችኁ ሰው እንዲኽ በሉት፡- “ወዳጄ! ይኽ ሰው ንዑድ ክቡር ነው የምትለኝ ስለምንድነው? እጂግ ግሩምና ድንቅ የኾነች ሠረገላ (በዚኹ በ21ኛው መ/ክ/ዘ. የግል አውሮፕላን ወይም ሃመር መኪና ልንለው እንችላለን!) ስላለው ወይም ብዙ ሠራተኞችን (ብዙ ኩባንያዎችን ልንለው እንችላለን!) ስለሚያስተዳድር፣ እጂግ ውድ ውድ የኾኑ ፋሽን ልብሶችን ስለሚለብስ፣ በየዕለቱም የተለያዩ የመጠጥ ዓይነቶችን ስለሚጠጣና ቅንጡ የኾነ ሕይወትን ስለሚመራ ነውን? እውነት እውነት እልኻለኁ! ለዚኽ ሰውዬስ የዕድሜ ዘመን ዕንባ ያስፈልገዋል ብዬ እነግርኻለኁ፡፡ አንተ ርሱን የምታደንቀው አፍአዊ ነገሩን ብቻ በማየት ነው፡፡ አንተ ርሱን የምታደንቀው ግሩምና ድንቅ የኾነችውን ሠረገላው፣ ወይም ወርቃማው መጋለቢያውን፣ ወይም ልብሱን ዐይተኽ ነው፡፡ ይኽ ግን ለእኔ ምንም ነው፡፡ እስኪ ንገረኝ! ከዚኽ ሰው በላይ ጐስቋላ ሰው ማን አለ? ሠለገላው፣ መጋለቢያው፣ ልብሱ፣ እና ሌላው ሃብቱ እየተደነቀለት ሳለ ርሱ ግን ምንም ሳይመሰገን ቢሞት ከርሱ የባሰ ጐስቋላ ሰው ማን አለ ትለኛለኽ? ከዚኽ ዓለም ወደዚያኛው ዓለም ይዞት የሚሔድ ብዕል (ሃብት) ከሌለው ከዚኽ ሰው በላይ ድኻ ማን አለ? ከአፍአ ሲታይ እጂግ የሚያምርበት ከውስጡ ግን የተለሰነ መቃብር ከኾነው ከዚኽ ሰውዬ በላይ ጐስቋላ ሰው ማን አለ? የእኛ የክርስቲያኖች ትክክለኛ ሃብት ጌጣ ጌጥ፣ ወይም ሠራተኞቻችን ወይም ልብሳችን ወይም ሠረገላዎቻችን አይደሉም፡፡ የእኛ ትክክለኛ ሃብት ምግባር ትሩፋታችን ነው፡፡ የእኛ ሃብት በእግዚአብሔር ማመናችንና መታመናችን ነው፡፡”
 ዳግመኛም እጅግ ድኻ፣ በጓደኞቹ ዘንድ ዕድሜውን በሙሉ እንደ ፋራና ያልዘመነ ሰው የሚቈጠር፥ ግን ደግሞ በምግባር በትሩፋት ያጌጠ ሰውን ብታዩ ይኽ ሰው ንዑድ ክቡር ሰው ነው ብዬ እነግራችኋለኹ፡፡ ምንም በዚኽ ምድር ላይ ያፈራውና ያጠራቀመው ሃብት ባይኖሮውም በሰማያት ዘንድ ድልብ ሃብት አለውና ይኽ ሰው በእውነት ንዑድ ክቡር ነው ብዬ እነግራችኋለኹ፡፡
 ይኽን አመለካከት ስለያዛችኁ ብቻ ጓደኞቻችኁ፡- “ኧረ በሥሉስ ቅዱስ! ይኽ ሰውማ እጅግ የተረገመ ሰው ነው!” ቢልዋችኁ፥ “እንደዉም እንደዚኽ ሰው ንዑድ ክቡር የለም፡፡ ወዳጅነቱ ከኃላፊውና ጠፊው ሃብትና ንብረት ሳይኾን ከእግዚአብሔር ጋር ነውና ንዑድ ክቡር ነው፡፡ ዕድሜውን በሙሉ ሲያከማች የነበረው እንደ እኛ አፍአዊውን ሳይኾን ብልና ዝገት የማያገኘውን ብዕል ነበርና ንዑድ ክቡር ነው፡፡ የዚኹ ሰው ሀብቱ በትዕቢት፣ በቁጣ፣ በዘፈን፣ በስካርና በገቢረ ኀጢአት ያልቆሸሸ ንጽሐ ልቡናው ነውና ንዑድ ክቡር ነው፡፡ እስኪ ንገረኝ! ይኽ ሰው ግሩምና ድንቅ የኾነች ሠረገላ፣ በወርቅ የተሽቆጠቆጠ መጋለቢያ፣ ውድ ውድ የኾኑ አልባሳት ስለሌለው የተጐዳ ይመስልኻልን? ርስት መንግሥተ ሰማያትን ከማግኘት በላይ ሌላ ምን ሃብት አለ ብለኽ ልትነግረኝ ትችላለኽ?” ብላችኁ መልሱላቸው፡፡
 እግዚአብሔር የሚወዳችኁ እናንተም የምትወዱት ሆይ! በአዲሱ ዓመት ብቻ ሳይኾን ዘወትር እንዲኽ እግዚአብሔርን በሚያስከብር መንገድ የምንገሥፅ፣ ወይም የምናመሰግን ከኾነ ሹመት ሽልማታችን ብዙ ነው፡፡
 ልጆቼ! ይኽን ኹሉ የምነግራችኁ እንዲኹ ስሜታችኁን ለማርካት አይደለም፡፡ ይልቁንም በአዲሱ ዓመት ብቻ ሳይኾን በየዕለቱ አስተሳሰባችንን እንዲኽ የምናስተካልለው ከኾነና እኛም እንደዚኹ በምግባር በትሩፋት ለማጌጥ የምንሽቀዳደም ከኾነ ሹመት ሽልማታችን ብዙ የብዙም ብዙ መኾኑን ለማስረዳት ነው፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ክቡር ዳዊት ስለዚኹ ጕዳይ ምን እንደሚል እስኪ አብረን እናድምጠው፡- “በአንደበቱ የማይሸነግል፣ በባልንጀራው ላይ ክፋትን የማያደርግ፣ ሰርቆ ቀምቶ እናት አባቱን የማያሰድብ፣ እኩይ ምግባር በፊቱ የተናቀለት፣ እግዚአብሔርንም የሚፈሩትን የሚያከብር፣ ለባልንጀራው ምሎ የማይከዳ፣ ገንዘቡን በአራጣ የማያበድር፣ ከድኻው መማለጃን የማይቀበል፣ እንዲኽ የሚያደርግ ሰው በመከራ ሥጋ መከራ ነፍስ ለዘለዓለም አይታወክም” /መዝ.15፡3-5/፡፡ ይኽም ማለት ክፋትን በመጸየፍ በጐውንም በማመስገን እግዚአብሔርን የሚያከብር ሰው ነፍሱ ለዘለዓለም አትታወክም ማለት ነው፡፡ ዳግመኛም ይኼ ክቡር ዳዊት በሌላ ሥፍራ እንዲኽ አለ፡- “አቤቱ ባለሟሎችኅ በእኔ ዘንድ እንደምን እጅግ ንዑዳን ክቡራን ናቸው! አስቀድመው ከነበሩት ባለሟሎችኅ ይልቅም እኒኽ ፈጽመው ጸኑ!” /መዝ.139፡17/፡፡
 እግዚአብሔር ያከበረውን ግን አትገሥፁ፡፡ ምክንያቱም እግዚአብሔር በጽድቅ በቅድስና ሕያዋን የኾኑትን ያከብራልና፡፡ በሰው ዓይን እዚኽ ግቡ የማይባሉ ድኾች ቢኾኑም በእግዚአብሔር ዘንድ ንዑዳን ክቡራን ናቸውን እነዚኽን አትገሥፁ፡፡ እግዚአብሔር ያላከበረውን ግን ገሥፁት፡፡ ምንም ያኽል በወርቅ ላይ ቆሞ በወርቅ ላይ ቢተኛም ምግባር ትሩፋትን ሳይይዝ በገቢረ ኀጢአት የፀናውን፣ በሚቀጥለው ዓመትም ይኽን ለማድረግ የሚያቅደውን ሰው ገሥፁት፡፡ በአጭር ቃል ስታመሰግኑም ስትገሥፁም ለእግዚአብሔር ክብር አድርጉት፡፡ አዲስ ዓመትን ማክበር ማለት እንደዚኽ በኹለንተናችን አዲስ ሰው ኾኖ በመዘጋጀት ነውና፡፡
ይቀጥላል…

አዲሱ ዓመት - ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዳስተማረው (ክፍል ፩)



(መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ነሐሴ ፳፬ ቀን፣ ፳፻፮ ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
 የምወዳችኁ ልጆቼ! አዲሱ ዓመት የደስታ የሰላምና የጤና እንዲኾንላችኁ ትሻላችሁን? እንኪያስ ገና ከዥመሩ በስካር፣ በዘፈን፣ በገቢረ ኀጢአት ለማሳለፍ አታቅዱ፡፡ የአዲሱ ዓመት የመዠመሪያውን ዕለት ብቻ ሳይኾን እያንዳንዱን ቀን በገቢረ ኀጢአት አትዠምሩት፡፡ እግዚአብሔርን ደስ የሚያሰኝ ሥራ፣ ምግባር ትሩፋት በመሥራት አሐዱ በሉ እንጂ፡፡ ዕለታት ክፉዎች ወይም ጥሩዎች የሚኾኑት በተፈጥሮአቸው እንደዚያ ኾነው አይደለም፡፡ ዕለቱን ክፉ ወይም ደግ እንዲኾን የምናደርገው እኛው ነን፡፡ የአምናው ማግሰኞ ከዘንድሮ ማግሰኞ የተለየ አይደለም፡፡ የተለየ የሚያደርገው የእኛ ብርታት ወይም ስንፍና ብቻ ነው፡፡
የጽድቅን ሥራ የምንሠራበት ከኾነ አዲሱ ቀን ብቻ ሳይኾን አዲሱ ዓመት ለእኛ መልካም ነው፡፡ ኀጢአት የምንሠራበት ከኾነ ግን ቀኑ ብቻ ሳይኾን አዲሱ ዓመትም ክፉና መከራ የመላበት ይኾንብናል፡፡ አዲሱን ዓመት በበጐ ሥራ የምንዠምረው ከኾነ በዓመቱ በምናደርገው ማንኛውም ክንውን ላይ በጐ ተጽዕኖ ያሳድርብናል፡፡ በትግሃ ሌሊት፣ በቀዊም፣ በጾም በጸሎት እንድንበረታ ስንቅ ይኾነናል፡፡ በስካር፣ በዘፈን፣ በኀዘን የምንዠምረው ከኾነ ግን ዓመቱ ሙሉ እንዲኽ የተጐሳቈለ ዓመትን እናሳልፋለን፡፡ ሕይወታችንን በከንቱ እንገፋለን፡፡ ዲያብሎስም ይኽን ጥንቅቅ አድረጐ ስለሚያውቅ ዓመቱን በገቢረ ኀጢአት እንድንዠምረው እየቀሰቀሰ ነው፡፡ ፈቃዳችንን አጥፍቶ፣ ዓይነ ልቡናችንን አሳውሮ በዘፈን፣ በስካር፣ በዋይታ እንድንዠምረው በተለያየ መንገድ እየለፈፈ ነው፡፡
 ሰነፍ ሰው “ቀኑ ክፉ ወይም መልካም የሚኾነው በእኔ ምክንያት አይደለም” ብሎ ያምናል፡፡ እንዲኽ በማመኑም ክፉ ነው ብሎ በሚያስበው ቀን ገቢረ ጽድቅ መሥራት እንደሚቻል አያስብም፡፡ ቢያደርግም ትርጕም እንደሌለው አድርጐ ይቈጥሯል፡፡ የጽድቅ ሥራ ለመሥራት በተመቻቸለት ቀንም ልል ዘሊል ከመኾኑ የተነሣ ምግባር ትሩፋት ለመሥራት አይሽቀዳደምም፡፡ ስንፍናው ምን ዓይነት ጉዳት እንደሚያመጣበት አይረዳም፡፡ ድኅነቱን ሳይፈጽም ዕድሜውን ኹሉ በከንቱ ይገፋል፡፡ እንዲኽ ያለ የሥጋም የነፍስም ጕዳት እንደሚያገኘው ዲያብሎስ ዓይነ ልቡናውን ስለሚያሳውርበት ከአጋንንት ወጥመድ ለመሸሽ ዓቅምን ያጣል፡፡
 ዲያብሎስም ዕለት ዕለት ይኽን እንዳንገነዘብ በተለያየ ማጥመጃ መንገዶች እኛን ለመጣል ይሯሯጣል፡፡ አንዱ መንገድም ስለ ክርስትና ሕይወታችን ግድ እንዳይኖረን ማድረግ ነው፡፡ በዚኽም ክርስቲያናዊ ተፈጥሮአችንን ያሳጣናል፡፡ የእግዚአብሔርን ሥራ በገቢር እንድንሰድብ ያደርገናል፡፡ ነፍሳችንን በቆሸሸ ስፍራ ተወሽቃ እንድትቀር ያደርጋታል፡፡
 የምወዳችኁ ልጆቼ! እኛ ግን ይኽን ልናውቅ ልንረዳ ይገባናል፡፡ በዓለም ላይ ከኀጢአት በቀር ክፉ ነገር እንደሌለ ልናውቅ ልንረዳ ይገባናል፡፡ ከምግባር ከትሩፋት በቀርም መልካም ነገር እንደሌለ ልናውቅ ልንረዳ ይገባናል፡፡ በዚኽም ዘወትር እግዚአብሔርን ደስ አሰኝተን ልንኖር እንዲገባን ማወቅ መረዳት ይገባናል፡፡ መጠጥ ደስታን አያመጣም፤ ደስታን የሚያመጣው ጸሎት ነው፡፡ ደስታን የምናገነኘው ቃለ እግዚአብሔርን ከመስማት እንጂ ከስካር አይደለም፡፡ ስካር የነፍስ መታወክን ያመጣል፤ ቃሉን መስማት ግን ተመስጦን ያመጣል፡፡ ስካር ሁካታን ያመጣል፤ ቃሉን መስማት ግን ሁካታን ያርቃል፡፡ ስካር ዓይነ ልቡና እንዲጨልም ያደርጋል፤ ቃለ እግዚአብሔር ግን የጨለመው ዓይነ ልቡናችን ብሩህ እንዲኾን ያደርጋል፡፡ ስካር የኀጢአት ጓዝ ይዞ ይመጣል፤ ቃለ እግዚአብሔር ግን አዲስ የሚመጡትን ብቻ ሳይኾን የነበሩትንም ያስወግዳል፡፡
 ልጆቼ! የዚኽን ዓለም ደስታ ንቆ ሰማያዊ ደስታን እንደመሻት ያለ ጥበብ ምንም የለም ብዬ እነግራችኋለኹ፡፡ ይኽን ገንዘብ የምናደርግ ከኾነ፣ ለሰማያዊ ሕይታችን ቅድሚያን የምንሰጥ ከኾነ የዚኽ ዓለም ዝባዝንኬ ቢቀርም አይከፋንም፡፡ አንድ ሰው ባለጸጋ ስለኾነ ቅናት አይይዘንም፡፡ ምንም ምድራዊ ሀብት ባይኖረንም ድኾች እንደኾንን አናስብም፡፡ ባለ ጸጋውን ክርስቶስ የያዘ ሰውስ እንዴት ድኻ ይባላል? በዓመት አንድ ጊዜ ብቻ ሳይኾን በየዕለቱ በዓል ማድረግ ማለትም ይኸው ነው፡፡
 እግዚአብሔር የሚወዳችኁ አንድም እግዚአብሔርን የምትወዱት ሆይ! አንድ ክርስቲያን በዓልን ሲያከብር ሳምንትን ወይም ወርን ወይም ዓመትን ጠብቆ መኾን የለበትም፡፡ ከክርስቲያናዊ ተፈጥሮው ጋር እንደሚስማማ አድርጐ ዕለት ዕለት በዓል ሊያደርግ ይገቧል እንጂ፡፡ ከክርስቲያናዊ ተፈጥሮው ጋር የሚስማማ በዓል ማለትስ ምን ማለት ነው? ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ምን እንደሚለን አብረን እናድምጠው፡- “በቅንነትና በእውነት ቂጣ በዓልን እናድርግ እንጂ በአሮጌ እርሾ በክፋትና በግፍ እርሾም አይደለም” /1ኛ ቆሮ.5፡8/፡፡ ንጽሐ ልቡናን ገንዘብ ያደረገ ሰው ዕለት ዕለት በዓልን ያከብራል፡፡ ተስፋ መንግሥተ ሰማያት የተጠበቀለት ነው፡፡ ከሰማያዊው ማዕድና መጠጥ ተካፍሎ ሐሴት ያደርጋል፡፡ በዚኽ ምድር ላይ የሚደረጉ ጊዜያዊ ክንውኖች ስለቀረበት የኾነ ነገር እንደቀረበት አያስብም፤ ርሱ ያገኘው ከዚኽ በእጅጉ የሚልቅ ነውና፡፡ ነፍሱን ከሚያቆሽሹ ገቢረ ኀጢአቶች ራሱን ይጠብቃል፡፡
  በገቢረ ኀጢአት ተሰማርተን ሳለ ሺሕ ጊዜ በዓላትን ብናከብር ግን እንዳከበርን ልንቈጥረው አይገባንም፡፡ ያከበርነው የበዓል ቀን (በዓል ማለት ደስታ ማለት ነው) ሳይኾን የኀዘን ቀን ነውና፡፡ ነፍሴ በኀጢአት ቀንበር ተይዛ በድቅድቅ ጨለማ ውስጥ ሳለች የደስታን ቀን ባከብር ለእኔ ምን ጥቅም ያመጣልኛል?
 እግዚአብሔር የሚወዳችኁ እናንተም የምትወዱት ልጆቼ! አዲሱ ዓመት የእውነት አዲስ ዓመት እንዲኾንላችኁ ካሻችኁ ነፍሳችኁን ከኀጢአት ቀንበር አላቋት እንጂ ድጋሜ በኀጢአት ሸክም አትጫኗት፡፡ አሮጌው ዓመት እንዳለቀ ስታዩ እግዚአብሔርን አመስግኑት፡፡ ወደሌላ ዘመን አሸጋግሯቸዋልና እግዚአብሔርን አመስግኑት፡፡ ልቡናችኁንም ውቀሱት፡፡ በዕሜአችኁ ስንት ጊዜ እያለፈ እንደኾነ እያሰባችኁም ራሳችኁን እንዲኽ ብላችኁ ጠይቁት፡- “ቀናት እየሮጡ ነው፡፡ ዓመታቱም እየነጐዱ ነው፡፡ የዕድሜዬ መንገድም እየተጋመሰ ነው፡፡ ታድያ ምን በጐ ምግባር ያዝኩ? ከዚኽ ምድር የማልፍበት ቀን እየቀረበ ነው፡፡ ታድያ ምን የጽድቅ ሥራ ሠራኹ? በዚኽ ዕድሜዬ መሥራት የነበረብኝ ምግባር ትሩፋት ዕድሜዬ ሲገፋ ማድረግ አልችልም፡፡ ታድያ ዕድሜዬ ሲገፋ ማድረግ የማልችላቸውም የጽድቅ ሥራዎች (ፆም፣ ጸሎት፣ ስግደት፣ አገልግሎት፣… ዕድሜ ሲገፋ ይከብዳሉና) እንዳቅሜ እያደረግኩ ነውን?”
ተወዳጆች ሆይ! አዲስ ዓመት ሲመጣ እነዚኽን ነገሮች በጥንቃቄ ልናስብባቸው ይገባናል፡፡ ይኽን እያደረግንም ስለቀጣዩ ዓመት እናስብ፡፡ ይኽን የምናደርግ ከኾነ “ቀኖቻቸውም በከንቱ አለቁ፤ ዓመቶቻቸውም በችኰላ” አይባልብንም /መዝ.78፡3/፡፡ ዕለት ዕለት በዓልን እናድርግ ብዬ የገለጥኩላችኹም ይኸው ነው፡፡ የእኛ በዓል ዘወትር መኾን ይገባዋል፡፡ የክርስቲያኖች በዓል በዓመታትና በቀናት ብቻ መወሰን የለበትም፡፡ ቤተ ክርስቲያንም በሳምንት፣ በወር፣ በዓመት የሚከበሩ በዓላት እንዲኖሩ ማድረጓ ዘወትር ከዚኹ ልንርቅ እንደማይገባ ማሳሰቧ እንጂ ሌላ አይደለምና፡፡ ይኽን በዓል በየዕለቱ ማድረግም ለኹሉም ይቻላል፤ ለድኻውም ለባለጸጋውም ይቻላል፡፡ በዓልን ለማድረግ (የጽድቅ ሥራን ሠርቶ ሐሴት ለማድረግ) የሚያስፈልገው ቅን ልቡና እንጂ ገንዘብ አይደለምና፡፡ ወዳጄ ሆይ! ገንዘብ የለኽምን? ፈሪሐ እግዚአብሔርን ገንዘብ አድርግ፡፡ ፈሪሐ እግዚአብሔርን ገንዘብ የምታደርግ ከኾነ ገንዘብ ካላቸው በላይ ባለጠጋ ነኽ፡፡ “እንዴት?” ትለኝ ይኾናል፡፡ እኔም እንዲኽ ብዬ እመልስልሃለኹ፡- የእነዚያ (የባለጠጐቹ) ገንዘብ ያልቃል፡፡ ያንተ ግን ብል አይበላውም፡፡ ጊዜ አይለውጠዉም፡፡ አያልቅም፡፡ ወደ ሰማያት፣ ወደ ሰማየ ሰማያት፣ ወደ ምድር፣ ወደ አየራት፣ ወደ እንስሳቱ ዓይነት፣ ብዙ የብዙ ብዙ ወደሚኾኑት ዕፅዋት፣ ወደ ደቂቀ አዳም በጠቅላላው፣ ወደ መላዕክት፣ ወደ መላዕክት አለቆች፣ ወደ ኀይላት ተመልከት፡፡ እነዚኽ ኹሉ የአምላክኽ ፍጥረቶች ናቸው፡፡ የእነዚኽን አምላክና መጋቢ ባርያ መኾን ድኻ መኾን አይደለምና ድኻ አይደለኽም ብዬ እነግርኻለኹ፡፡
 ተወዳጆች ሆይ! ቀናትን ቈጥሮ በዓል ማድረግ የክርስቲያን ግብር አይደለም፤ የአሕዛብ ግብር እንጂ፡፡ እንዴት? የክርስቲያኖች ተፈጥሮ በቀንና በወር የተገደበ አይደለምና፡፡ አገራችን ሰማይ ነው፡፡ ግብራችን ሰማያዊ ነው፡፡ ኅብረታችንም ከሰማያውያን መላዕክት ጋር ነው፡፡ በዚያ መዓልት ለሌሊት ስፍራውን አይለቅም፡፡ ሌሊትም በተራው ለመዓልት አይለቅም፡፡ እዚያ ኹሌ መዓልት ነው፡፡ እዚያ ኹል ጊዜ ብርሃን ነው፡፡ ስለዚኽ “ከክርስቶስ ጋር ከተነሣችኁ ክርስቶስ በእግዚአብሔር ቀኝ ተቀምጦ ባለበት በላይ ያለውን እሹ” እንደተባልን ኹል ጊዜ ማሰብ ያለብን ይኽንን ነው /ቈላስ.3፡1/፡፡ ክርስቲያናዊ ተፈጥሮአችን ከዚኽ ምድራዊ አቈጣጠር በላይ ነው፡፡ በንጽሕና በቅድስና እየኖርን ዘወትር በዓልን የምናከብር ከኾነም የዚኹ ዓለም ሌሊት ለእኛ ሌሊት አይደለም፤ መዓልት ነው እንጂ፡፡ ዘመናችንን በሙሉ በገቢረ ኀጢአት፣ በስካር፣ በዘፈን የምናሳልፈው ከኾነ ግን መዓልቱ ለእኛ መዓልት አይደለም፤ ሌሊት ነው እንጂ፡፡ ፀሐይዋ ብትወጣም ልቡናችን ገና በድቅድቅ ጨለማ ውስጥ ይኖራልና ቀን እንደወጣ አይቈጠርም፡፡
ይቀጥላል…

                                   በአውሮጳ   የካህናት አንድነት ማኅበር ሊቋቋም መሆኑ ታወቀ በ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከመላዋ አውሮጳ   የተውጣጡ ካህናት፡” የ...