2015 ጁን 29, ሰኞ

ክርስትናው እኛጋ ተግባሩ ግን…………………….


……….
ቦታው ሰሜን መዕራብ አውሮፓ ሀገረ ስብከት  ፊንላንድ ነው ደብረ አሚን አቡነ ተክለሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን  ሄልሲንኪ ከተማ   እሁድ ቅዳሜ ጉባኤ ነበረ የከተማዋን ፣ የሀገሩን ሁኔታ ስጠይቅ
1.      የሀገሩ ሕዝብ ሐሰት መናገር ጨርሶ አያውቅም አይሆንለትም
2.     ዕቃ ወድቆ ቢያገኝ በሚታይ ቦታ ያስቀምጣል እንጂ አይወስድም
3.     እናቶች ልጅ ይዘው ሲሄዱ የከተማው ባሶች፣ ቀላል ባቡሮቸ፣  ወዘተ …እንዲሁ ያለክፍያ ይወስዳሉ
4.     እናቶች ሲወልዱ እስከ ለሦስት ዓመት ያህል እንክብካቤ ይደረግላታል  ሌሎችም ምግባራትን እዚያ አገኘሁዋቸው  ምናለበት  ይህ ተግባር   ሃይማኖቱ ፣ሥርዓቱ፣ ሊቃውንቱ፣ ገዳማቱ፣ ካህናቱ፣ መነኮሳቱ፣ ቅዳሴው፣ ሳህታቱ፣ ማኅሌቱ፣ ባለበት በእኛው  ሀገር ቢተገበር ቀድሞ አበዊነ ሐዋርያት ያስተማሩት ከሃይማኖት በስተቀር ሁሉም አለ  ከእኛ ተገባሩ ተሰዶብናልና ወደ ሀገሩ ቢመለስልን ብዬ ተመኘቼ ነው፣

                         ከሄልሲንኪ ፊንላንድ



































2015 ጁን 28, እሑድ

እግዚአብሔር ያጣመረውን እንግዲህ ሰው አይለይ› የሚለውን በስዕል፣


ነገሩ እንዲህ ነው ሰኔ 17 2007 ዓ.ም ከምሽቱ 5 ሰዓት ተነስቼ በእኛው አውሮፕላን ወደ ጀርመን ፍራንክፈርት ለአገልግሎት ተጉዤ ነበር እንደደረስኩም  ቀሲስ አብርሃምና ዶ/ር አንኬ ተቀበሉኝ ክብር ያድልልኝ እላለሁ ከትንሽ እረፍት ቀጥሎ ከ አንኬ ጋር  ከተማዋን ለማየት በወጣሁ ጊዜ ያየሁትን  ትልቅ ወንዝ ከተማዋን ሰንጥትቆ ያልፋል ይልልቅ መርከቦች ፣ ጅልባዎች  ይሄዱበታል መሸጋገሪያ ድልድዮቹ ላይ የሀገር ቁልፎች ተቆልፎበታል  ምሥጢሩ ምንድነው › ጠየቅሁ እጮኛሞች፣ የልብ ጉዋደኞች፣ ናቸው የሚቆልፉት መክፈቻውን ወሃው ውስጥ ይጥሉታ  ፣መክፈቻውን ሰዎች ስለማያገኙት አይከፍቱትምና አይለየን ፣ማለታቸው ነው አሉኝ  ተቆልፎአልና. እግዚአብሔር ያጣመረውን እንግዲህ ሰው አይለይ ያለውን በስዕል ፣ ተስሎ ተመለከትነው

                                ከፍራንክፈርት ጀርመን

2015 ጁን 24, ረቡዕ

ሒዱ እንጂ ተቀመጡ አልተባልንም (ክፍል ኹለት)


በዲ/ን ዳንኤል ክብረት
(መዝረቅ ዘተዋሕዶ፣ ሰኔ 16 ቀን፣ 2007 ዓ.ም.)፡             - በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
ኹለተኛው በይሁዳ ነው!
ይሁዳ የኢየሩሳሌም አውራጃው ነው፡፡ የይሁዳ አውራጃ ዋና ከተማም ኢየሩሳሌም ነች፡፡ ከኢየሩሳሌም ይሁዳ ይከፋል፤ ከሰማርያ ግን ይሻላል፡፡ ምክንያቱም ኢየሩሳሌም ዋና ከተማዋ ነች፣ ጌታም የተወለደው በይሁዳ አውራጃ በቤተ ልሔም ነው፡፡ የተሰቀለው፣ የሞተው፣ የተቀበረው፣ ያረገው፣ መንፈስ ቅዱስን ለሐዋርያት የላከው በኢየሩሳሌም ከተማ ነው፡፡ ስለዚህ የኢየሩሳሌም ነገር በይሁዳ አውራጃ የተሻለ ይወራል፤ ይነገራል፡፡ የሚያውቁት ዘመድ ይኖራል፡፡ የሐዋርያትና የይሁዳ ቋንቋ ተመሳሳይ ነው፡፡ የይሁዳ ባሕልና የኢየሩሳሌም ባሕል ተመሳሳይ ነው፡፡ ከሰማርያ ቢሻልም ከኢየሩሳሌም ግን ይከፋል፡፡

ይሁዳ ምንድነው ይሁዳ? ይሁዳ አከባቢያችን ነው፡፡ ይሁዳ መንደራችን ነው፡፡ ይሁዳ ጓደኞቻችን፣ የምንሠራበት አከባቢ፣ የምንማርበት አከባቢ ነው፡፡ በየመንደሩ የሚሰበሰቡ ሰዎች ለወንጌል እንዲሰበሰቡ ማድረግ ይቻላል፡፡ አባቶቻችን ጽዋን፣ ሰንበቴን የመሠረቱት አንዱ ትልቁ ጥቅም በቅዱሳን ስም ተሰብስበን እንድንማር፣ እንድናውቅ፣ በይሁዳ ወንጌል እንዲሰበክ ነው፡፡
ታላቁ ሐዋርያ አባ ሰላማ ከሳቴ ብርሃን ማኅበረ ጽዮን የተሰኘችውን የመጀመሪያዋን የጽዋ ማኅበር በአክሱም ጽዮን ሲመሠርት ሦስት ዓላማ ነው የነበረው፡፡ የመጀመሪያው ዓላማ ከዚያ ከቅዱሱ ረድኤት በረከት ማግኘት፤ ኹለተኛው ዓላማ ወንጌልን መማር፤ ሦስተኛው ዓላማ ድኾችን መርዳት፡፡ ዛሬ ጽዋዎቻችን እነዚህን ዓላማዎች ይተግብራሉ? ትምህርት አለ? ድኾች ይረዳሉ? ወይስ ከተለያየ ቦታ ተሰብስበን በቤታችን የሰለቸነውን ምግብ እንደገና አምጥተን በልተን ነው የምንለያየው? አብያተ ክርስቲያናት ይረዳሉ? የሐዊረ ሕይወትንና የመሳሰለውን ጉባኤ’ኮ ማዘጋጀት ያለባቸው በየከተማው ያሉ ሰንበቴዎች፣ ጽዋ ማኅበራት፣ የጉዞ ማኅበራት አንድ ላይ ኾነው ነው፡፡ ይኼ ነዋ ዓላማቸው! ወንጌል እንዲሰበክ ማድረግ ነዋ ዓላማቸው! አባ ሰላማ ከሳቴ ብርሃን የሾማቸው የመጀሪያዎቹን ሰባት ኢትዮጵያውያን ሐዋርያት የሚያስፈልጋቸውን አሟልታ “ሒዱ፤ አስተምሩ” ብላ የላከችው’ኮ ያቺ ማኅበረ ጽዮን የተባለችው የጽዋ ማኅበር ናት፡፡ ዛሬ ጽዋዎቻችን ሐዋሪያዊነት አላቸው? ስብከተ ወንጌል ላይ ይሠራሉ? የጽዋ ማኅበርተኞች ይማራሉ? በየመንደራችንስ ትምህርት አለ?
በይሁዳ ማለት ይኼ ነው፡፡ ኹለተኛው ስምሪት ይኼ ነው፡፡ ጥቂት የሚያውቁ፣ ጥቂት የተማሩ፣ ጥቂት የገባቸው፣ መንደሩን የሚያውቁ ምእመናን አከባቢያቸውን ሰብስበው የሚያስተምሩበት ነው፤ ይሁዳ፡፡ ነጋዴዎች በንግድ አከባቢ ያሉትን ሰብስበው፣ ሾፌሮቹ በዚያ በሙያቸው ያሉትን ሰብስበው፣ ፓይለቶቹ በዚያ አከባቢ ያሉትን ሰብስበው፣ ሊስትሮዎቹ በሙያ የሚቀርባቸውን ሰብስበው፣ የመንግሥት ሠራተኞቹ በዚያ የሚቀርቧቸውን አሰባስበው፣ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችም እንደዚሁ፤ ሌሎችም የሚቀርቧቸውን ሰብስበው የሚያስተምሩበት ነው፡፡ “ኑ እንወቅ፤ ኑ እንማር፡፡ እኛ መጀመሪያ እንወቅ፤ ከዚያም እንሒድ፤ ሌላ ቦታ እንድረስ” የሚሉበት ነው፤ ይሁዳ፡፡
ምናልባት ሔደን ቆመን ላናስተምር እንችል ይኾናል፡፡ ነገር ግን ሞራል መኾን እንችላለን፡፡ የሐዊረ ሕይወትና የበእንተ ወንጌል ጉባኤ ተዘጋጅቶ ወደ ሌላ አከባቢ ስንሔድ እኛን ያዩ የዚያ አከባቢ ሕፃናት፣ ወጣቶች፣ በአጠቃላይ ምእመናን ምን እንደሚሰማቸው እስኪ አስቡት? ሰው’ኮ ከዕውቀት ከትምህረት እጥረት በላይ የሞራል እጥረት ይጎዷል፡፡ በተደጋጋሚ እርሱ ከሚያምነው የተለዩ ሰዎች የሞራል ጫና ሲያሳድሩበትና “አንተ’ኮ የለህም፤ የሚጠይቅህም የለም” ሲሉት በጣም ነው የሚጎዳው፡፡ እስረኛና በሽተኛ ትልቁ የሚርበው ጠያቂ ነው፡፡ አንድ በሽተኛ ተኝቶ፣ አንድ እስረኛም ታስሮ ሔዶ የሚጠይቀው ሰው ነው የሚርበው፡፡ ለዚህም ነው ጌታችን በማቴዎስ 25 ከጠየቃቸው ጥያቄዎች አንዱ፡- “ታስሬ አልጠየቃችሁኝም፤ ታምሜ አልጎበኛችሁኝም” የሚለው፡፡ ምክንያቱም አንድ የታመመና የታሰረ ሰው መጀመሪያ የሚፈልገው ምግብ ወይም ገንዘብ የሚሰጠው አይደለም፡፡ ሔዶ “እግዚአብሔር ያበርታህ፤ ደኅና ነህ ወይ?” የሚለውን ነው የሚሻው፡፡ የታመም ሰው “አይዞህ፤ በርታ! እግዚአብሔር ያጽናህ፤ እግዚአብሔር መድኃኒቱን ይላክልህ” የሚለው ሰውን ነው የሚፈልገው፡፡ ስለዚህ ምንም ባናደርግም መምጣት በራሱ ትልቅ ሐዋርያነት ነው፡፡ መጥቶ “እኛ የእናንተ አካል ነን፤ አብረናችሁ ነን፤ ከእኛ ጋር ናችሁ፤ ወገኖቻችን ናችሁ፤ ወገኖቻችሁ ነን” ማለት በራሱ ትልቅ ሐዋርያነት ነው፡፡
አሁን ትንሽ ተስፋ የምናየው በይሁዳ ያለው አገልግሎት ነው፡፡ ሰዎች ይሰበሰባሉ፤ የሚቀር ግን አንድ ነገር አለ፡፡ ብዙዎቻችን ለእንዲህ ዓይነቱ የመሔድ አገልግሎት የበረታን አይደለንም፡፡    
ሦስተኛው በሰማርያ ነው!
ለምንድነው ሰማርያ ያለው? ሰማርያ ከአይሁድ በብዙ ይለያል፡፡ በቋንቋ ይለያሉ፤ በባሕል ይለያሉ፡፡ በእምነት ይለያሉ፤ አምስቱን የሙሴ መጻሕፍት ብቻ ነውና የሚቀበሉት /ዮሐ.4/፡፡ ስለዚህ ወደ ሰማርያ መሔድ ማለት በባሕል፣ በቋንቋ፣ በእምነት፣ በአስተሳሰብ፣ በአለባበስ፣ በአመጋገብ ወደሚለዩ ሰዎች መሔድ ነው፡፡ ጣዖት የሚያመልኩ ሊኾኑ ይችላሉ፤ ባሕላዊ እምነት የሚያመልኩ ሊኾኑ ይችላሉ፤ ሌላም ነገር የሚያመልኩ ሊኾኑ ይችላሉ፡፡ ወደነዚያስ መቼ ነው የምንሔደው? “በይሁዳ እንዳትቀሩ፤ ወደ ሰማርያ ሒዱ” ነዋ የተባልነው፡፡
ብዙ ሐዋርያት ከሰማርያም አልፈው ነው የሔዱት፡፡ እነ ቅዱስ ቶማስ ሕንድ ሔደዋል፡፡ እነ ቅዱስ ጳውሎስ እስከ ሮም እስከ ስፔን ድረስ ሔደዋል፡፡
ኢትዮጵያውያን ሐዋርያትም እንደዚሁ ከሰማርያ አልፈው ሔደዋል፡፡ ዛሬ የተነሡ አንዳንድ ሰዎች ሰማርያ አልፋ የሔደች አይመስላቸውም፡፡ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ማይክራፎን ከመጣ ወዲህ ማስተማር የጀመረች ነው የሚመስላቸው፡፡ ከሞንታርቦ ዘመን ወዲህ ነው ታሪኳን የሚጀምሩት፡፡ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ግን የሞንታርቦ ዘመን ቤተ ክርስቲያን አይደለችም፡፡ ብዙዎች ሐዋርያት ተሰማርተዋል፡፡ ከመጀመሪያው ጀምሮ ወደማይታወቅ ቦታ ስምሪት ነበረ፡፡ አባ ሰላማ ከሳቴ ብርሃን ሰባት ሐዋርያትን እስከ ሱዳን ድረስ ልኳል፡፡ ከዚያ በኋላ የመጡት ዘጠኙ ቅዱሳንም ወደ ኢትዮጵያ ከመጡ በኋላ እንኳን በአክሱም ከተማ የተቀመጡት ኹለቱ ብቻ ናቸው፤ አባ ሊቃኖስና አባ ጰንጤልዮን፡፡ እርሱም ንጉሡ፡- “እኔንማ ትታችሁኝ ከሔዳችሁ ማን ይባርከኛል? ማን ይጸልይልኛል? እኔ ክፉ ከኾንኩ የእናንተ የወንጌል አገልግሎትም ክፉ መኾኑ አይደለም ወይ? እኔንምኮ ማስተማር አለባችሁ፤ እኛ መኳንንቱ እኛ ነገሥታቱ ሐላፊዎቹ ከከፋን አገር ትከፋለች፡፡ ስለዚህም እኔንም ማስተማር ሐዋርያዊ አገልግሎት ነው” ብሏቸው ነው፡፡ የቀሩት ሰባት ግን አክሱም መቀመጥ እንኳን እንደ ቅንጦት እንደ ምቾት ቈጥረዉት ወጥተው ነው የሔዱት፤ ከሔዱ ደግሞ አልተመለሱም፡፡ 
ከእነርሱም በኋላ የመጡት ሐዋርያት ወደማያውቁት አገር ነው የሔዱት፡፡ ታላቁ ኢትዮጵያዊ ሐዲስ ሐዋርያ አቡነ ተክለ ሃይማኖት መጀመሪያ 17፣ በኋላ (በአቡነ ፊልጶስ ዘመን) ያፈሯቸው 12ቱን ሐዋርያት ሀገረ ስብከት አካፍለው ነው የላክዋቸው፡፡ ማንም ወደተወለደበት አከባቢ አልሔደም፡፡ ተመልሶ በሰላም የመጣም የለም፡፡ በክፍል አንድ ትምህርታችን ያነሣነው አቡነ አኖሬዎስ ባሌን ተሻግሮ በዚያው ዐርፎ፡ ዐፅሙ ነው በደቀመዛሙርቱ የተመለሰው፡፡ አባ በጸሎተ ሚካኤል ዐፅሙ ነው ወደ ገዳሙ የተመለሰው፡፡ አቡነ ፊልጶስ ዐፅሙ ነው ወደ ገዳሙ የተመለሰው፡፡ ማንም የላመ የጣመ ያለበት የተመቸ ቦታ ላይ ልቀመጥ ያለ የለም፡፡ እንደሔዱ ነው የቀሩት፡፡ እንደተጓዙ ነው የቀሩት፡፡ ይኼ ነው ወደ ሰማርያ መሔድ፡፡
አሁን የሚቀረንና የምንወቀስበት ትልቁ አገልግሎት ይኼ ነው፡፡ እንደ ኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ኹለት ሺሕ ዓመት ታሪክ አፍሪካ በሙሉ ክርስቲያን መኾን ነበረበት፡፡ መሔድ ማስተማር ነበረብን!
ዛሬ በጠረፉ አከባቢ ያለው መልክ ትክክለኛ መልክ አይደለም፡፡ የሠሩ ሰዎች ሳይኖሩ ቀርተው አይደለም፤ ሠርተዋል፡፡ እነ ዕጨጌ ዕንባቆም ከየመን ተነሥቶ፣ ሃይማኖቱን ቀይሮ፣ ክርስቲያን ኾኖ፣ ደብረ ሊባኖስ ገብቶ፣ መንኩሶ፣ መንኖ፣ ከዛ ደግሞ 12ኛው የደብረ ሊባኖስ ዕጨጌ ኾኖ፣ እንደገና ተሰማርቶ በዐባይ በረኻ በወለጋ ያስተማረው ትምህርት የሚደግመው ጠፋ፡፡ እስከ አሶሳ ድንበር ድረስ አስተምሮ ነበር፤ ነገር ግን የሚደግመው ጠፋ፡፡ እነ አቡነ አኖሬዎስ እስከ ባሌ ድረስ ሔደው አስተምረው ነበር፡፡ በመተሐራና በወንጂ እነ አቡነ ኢዮስያስ ሔደው አስተምረው ነበር፡፡ በዳሞት፣ በከንባታ፣ በሀድያ እስከ ጋሞጎፋ ድረስ እነ አቡነ ታዴዎስ ተሰማርተው አስተምረው ነበር፡፡ በምሥራቅ ኢትዮጵያ እስከ ዛሬ ድረስ የሶማልያ ሀገረ ስብከት እስከምንለው ድረስ እነ አቡነ ሳሙኤል ዘደብረ ወገግ ሔደው አስተምረው ነበር፡፡ (የአቡነ ሳሙኤል ዋናው ገዳማቸውኮ ደብረ ወገግ አይደለም፡፡ ደብረ ኪሩብ የሚባል ነው፡፡ ዛሬ ምንም ነገር የለውም፡፡ አሰቦት ላይ ቆማችሁ ደብረ ኪሩብ ይታያችኋል፡፡ እርሳቸውም ሲያስተምሩ ያረፉት እዚሁ ደብረ ኪሩብ ላይ ነው፡፡ ዐፅማቸው በኋላ ነው የተመለሰው፡፡) ዛሬ ዓፋር የምንለው አከባቢ የእነ አባ አንበስ ዘደብረ ዓዘቦ ሀገረ ስብከት ነበር፡፡ (ደብረ ዓዘቦ ዛሬም ፍርስራሹ አለ፡፡ በረዶ የሚያፈላበት ትልቁ ተራራ ጫፍ ላይ ነው ገዳማቸው የነበረው፡፡ እዛ ላይ ኾነው ነው አከባቢውን ሲያስተምሩ የነበሩት፡፡) ማን ይተካቸው? ማን ይውረሳቸው? የለም! ኹላችንም የተመቸ ቦታ ላይ ተቀምጠን ያለነው፡፡ ከላይ እስከ ታች ያለነው ሰዎች ከኢየሩሳሌም ከከፋም ከይሁዳ ላለመውጣት ወስነናል፡፡
ምእመናንም ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ላይ ያለንን ሩጫ ያኽል ስብከተ ወንጌል ላይ የለንም፡፡ እስኪ ማን ነው ገንዘቡን፡- “እዚህ አከባቢ ያለው ሕዝብ ሊማር ይገቧል፡፡ ሐዋርያ ሊደርሰው ይገባል፡፡ የኛ ገንዘብ እዛ መዋል አለበት” የሚል? ያንን ስምሪት የሚተካ አልመጣም፡፡
ኹሌ የምንኮራበት፣ “እርሱም ለወገኖቹ ሐዋርያ ኾነ” ብሎ አውሳብዮስ የተናገረለት ኢትዮጵያዊው ጃንደረባ’ኮ ኢትዮጵያ ውስጥ አይደለም ብዙውን ያስተማረው፡፡ መጀመሪያ ኢትዮጵያ - አክሱም አከባቢ፣ ከዛ ኑብያ - የዛሬዋ ሰሜን ሱዳን፣ ከዚያ ቀጥሎ ናግራን - የዛሬዋ ደቡብ የመን፣ ከርሱ ቀጥሎ ፋርስ - የዛሬው ኢራንና ዒራቅ፣ ከዚያ ቀጥሎ ሕንድ፣ ከሕንድ ቀጥሎ ቻይና አጠገብ ሲኖል የምትባል ደሴት አስተምሮ ነው ተሰማርቶ ያረፈው፡፡ ይህን ዛሬ ማን ይተካው? ማን ነው የሚሰማራው? ይህ ስምሪት ስለጎደለ ነው ዛሬ ትልቅ አደጋ ውስጥ የገባነው፡፡
ሠርተው ነበር አባቶቻችን!!! ወንዶቹ ብቻ አይደሉም፤ ሴቶቹም ጭምር!!! ሴቶችን ለመቀበል በማይደፍረው ዘመን እንኳን ኦርኒና መክብዩ የሚባሉ የአቡነ ፊልጶስ ደቀ መዛሙርት ተሰማርተው ነበር፡፡ እነዚህ ኦርኒና መክብዩ እሳት የላሱ ወንጌላውያን ነበሩ፡፡ ጥቅምት 23 ነው የሰማዕትነትን ጽዋ የተቀበሉት፡፡ ስለ ሃይማኖታቸው የንጉሥ ወታደር ተሰልፎ፣ አንዱ ባታሌውን ጠርቅሞ፡- “ማስተማር የለባችሁም” ሲላቸው “እኛኮ ተናገሩ እንጂ ዝም በሉ አልተባልንም፡፡ ሒዱ እንጂ ተቀመጡ አልተባልንም፡፡ ታዲያ ለምን እንፈራለን? ጌታችን በጲላጦስ አደባባይ በንጉሡና በወታደሮቹ ፊት አልፈራም፤ እኛም ልጆቹ አንፈራም፡፡ እንዲያውም ቁሙ፤ እናንተንም እናስተምራችኋለን፡፡ ቁሙ! እኛን ለመግደል አይደል የመጣችሁ? ለማሰር አይደል የመጣችሁ? እንደዉም ባላችሁበት ቁሙ፤ ይኼን ትምህርትማ ሰምታችሁ መሔድ አለባችሁ” ነው ያሉት፡፡ በዚያ ዘመን ሴቶች እንዲህ የሚናገሩበት ዘመን ስላልነበረ “ምንድነው የመጣብን?” ብለው እጅግ ደንቋቸው ቆሙ፤ ሰሟቸው፡፡ ወደ 23 የፈጀ ትምህርት ነው ያስተማሯቸው፡፡ እናቶች ዛሬ ለ23 ቀን የሚኾን ትምህርት አላችሁ? ወይስ ለ23 ቀን የሚኾን የቡና …. አልጨርሰውም፡፡ አርኒና መክብዩ ግን ቆሙ፡፡ አስተምረዋል፡፡ እስከ ጠረፍ ድረስ ሔደው መስክረዋል፡፡
እነ እምነ ወለተ ጴጥሮስ ሱስንዮስ “አገሪቱን ወደ ካቶሊክነት እቀይራታለሁ” ባለ ጊዜ፣ ሊቀ ጳጳሱ አቡነ ስምዖን ሲገደሉ፣ ታላላቆቹ ሊቃውንት ሲታሰሩ፣ መምህራኑ በየገዳማቱ ሲሰደዱ ዞራ አስተምራለች፡፡ ባሏ የሱስንዮስ የጦር አዛዥ ነበር፡፡ ሊቀ ጳጳሱን ገድሎ፣ አክሊላቸውን (አስኬማቸውን) እና ልብሳቸውን እንደ ግዳጅ ይዞት ሲመጣ፡- “ይኼውልሽ! ዛሬኮ በጦርነት ላይ ዋልኩ፡፡ ካቶሊክነትን አልቀበልም ያሉትን ጳጳስ ገደልኩ” ሲላት፡- “አባቴን ገድለህ ከእኔ ጋር መኖር አትችልም፡፡ የእኔና የአንተ ግንኙነት በዚህ ላይ አበቃ፡፡ ሃይማኖት ነው የመሠረተው፤ እዚህ ላይ አበቃ፡፡ የአንተን ሚስት ነኝ እላለሁ፤ ግን የማን ልጅ ነኝ እላለሁ?” ብላ ነው ወጥታ በመላ ትግራይ፣ ወሎ፣ ጎጃም፣ ጎንደር ዞራ ያስተማረችው፡፡ ንጉሡ የሚያደርገው እስኪጠፋው ድረስ ድረስ ነው ያስተማረችው፡፡ እንዳይገድላት ወንድሞቿ የንጉሡ የቀኝ ግራ አዛዦች ናቸው፡፡ እርሷን ገድሎ ከእነርሱ ጋር መኖር ፈራ፡፡ ዝም እንዳይላት “እንዴ! ሴቷ እንኳን እንደዚህ ስታስተምር” ብለው ሊቃውንቱ ሞራል እየኾነቻቸው ተነሡበት፡፡ ዙራ አስተምራለች፡፡ እርሷ እንድታስተምር ትልቁን እገዛ ያደረጉት በተለይ በጣና ሐይቅ ይሠሩ የነበሩ ባለ ጀልባዎች ናቸው፡፡ ከዕንጨት ጋር እየደበቁ፣ ከሌላ ነገር ጋር እየደበቁ አገር አገር እያሻገሯት እንድታስተምር ያደረጉት፡፡ ዛሬ ወደየገዳማቶቻችን አድርሰው እንደሚመልሱን ሹፌሮች ማለት ነው! ከተጠቀምንበትኮ ይህም ትልቅ ሐዋርያነት ነው፡፡
ቢጨንቀው ንጉሡ “እስኪ አስተምራት” ብሎ ወደ አልፎንስሜንዴዝ ወሰዳት፡፡ እጅና እግሯን ታስራ ኹልጊዜ የኑፋቄ ትምህርት እንዲነበብላት ተደረገች፡፡ “ቀይራት፤ ባትሰማህም ንገራት” ተባለ፡፡ ደከመ፤ ነገር ግን ምንም ሊቀይራት አልቻለም፡፡ እንደዉም መጨረሻ ላይ እዚያ ቦታ መታሰሯን ያወቁ ሌሎች ጀግኖች መጡና እርሱ በሌለበት በሩን ሰብረው ገመዷን በጥሰው ይዘዋት ጠፉ፡፡ “ቀየርካት?” አለው፡፡ “የምትቀየር አይደለችም” አለው፡፡ ይዘዋት ከሔዱ በኋላ ደቀ መዛሙርቷ ጠየቋት፡፡ “ይኼን ያህል ጊዜ እርሱ የኑፋቄ ትምህርት ሲያስተምርሽ ከልብሽ ውስጥ አልገባም” ሲሏት “እርሱ የኑፋቄውን ሲያነብ እኔ ጸሎቴን አደርጋለሁ፤ ሰምቼው አላውቅም፡፡” እስኪ በየመሥሪያ ቤታችን፣ በየንግድ ቦታችን የሚጮኽ ነገር የለም ወይ? የሚወራ ነገር የለም ወይ? ታዲያ ያን ጊዜ ስንቶቻችን ነን ያቺን ሰዓት ለጸሎት የምንጠቀምባት? ነገር ግን ይህቺ ቤተ ክርስቲያን ወደ ካቶሊክነት ከመለወጥ የታደጋት የእነ እምነ ወለተ ጴጥሮስ ሐዋርያነት ነው፡፡  
ምእመናን ሆይ! ይኼን ነው በሰማርያ ማምጣት ያለብን! ጉሙዝ ሕዝብ ሔዳ አስተምራለች፡፡ ታስራ ወደ ጉሙዝ ሔዳለች፡፡ የሚያስራት ሰውዬ ለመጀመሪያ ጊዜ ስላላወቀ አሰራት፡፡ በኋላ ግን ሃይማኖቷን፣ ምግባሯን ቢያይ “ምን አድርገሽ ነው? ለምንድነው እኔ ጋር እሰራት ብለው የላኩሽ?” አላት፡፡ “እኔ ሃይማኖቴን ስለጠበቅኩ ነው፡፡ የአባቶቼን ሃይማኖት ስላከበርኩ ነው የታሰርኩት” ስትለው “እስኪ ይኼ ሃይማኖቴ የምትዪውን ንገሪኝ” አላት፡፡ መጀመሪያ ያስተማረችው እርሱን ነው፡፡ የለወጠችው እርሱን ነው፡፡ ከዚያ በኋላ እርሷ ሦስት ዓመት እዚያ ስትታሰር እርሱ የእርሷ ደቀ መዝሙር ነው የኾነው፡፡ እስር ቤት ልንገባ እንችላለን፤ ግን ስንት ደቀ መዛሙርትን እናፈራለን?
ሰማርያ ማለትኮ ይኼ ነው፡፡ እስርቤቶቹ፣ ሆስፒታሎቹ፣ የተለያዩ ቦታዎች፣ ከሀገር ወጥተን የምንሔድባቸው ቦታዎች ሰማርያ ናቸው፡፡ ኢትዮጵያውያን በብዙ ዓለማት ተሰማርተዋል፡፡ ነገር ግን እስከ አሁን ድረስ በየአጥቢያው ስትሔዱ እኛው ብቻ ነን፡፡ አንድ ቻይናዊ አምጥተናል? አንድ ሕንዳዊ አምጥተናል? አንድ ሜክሲኮአዊ አምጥተናል? እኛ ብቻ ነን፡፡ ለዚህም ይመስለኛል በውጪው ዓለም መባላትና መናከስ ያለው፤ እኛው ብቻ ነና! ትንሽ ብንቀላቀል ኖሮኮ ያም ቋንቋው ስለማይችል መሰዳደባችንን እንኳን ስለማይገባው ተስማምተን እንኖር ነበር፡፡ አላመጣንም፡፡ በሰማርያ ግን አስተምሩ ተብለናል፡፡ ለእነርሱ የሚኾን መዝሙር አለን? አዲስ ሰው ቢመጣ ለእርሱ የሚኾን መጽሐፍ አለን? ለእነርሱ የሚኾን ትምህርት አለን? ለእነርሱ የሚኾን ዝግጅት አለን?
ሰሜን ኬንያ የነበሩ ሕዝቦ በስደተኞቹ ካምፕ የነበረችውን ቤተ ክርስቲያን ሲያዩ ከጎሳው መሪ ጀምረው ተጠመቁ፡፡ “አሁን እኛ የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ. አማኞች ነን” አሉ፡፡ እምነታቸውን ትተው መምጣት፤ መጠመቁ አልቸገራቸውም፡፡ ነገር ግን የሚቀበላቸው ዝግጅት አልነበረም፡፡ ለእነርሱ የሚኾን ሰው አልነበረም፡፡ የሚበሉትን በልቶ፣ የሚጠጡትን ጠጥቶ፣ የሚኾኑትን ኾኖ የሚያስተምራቸው ሰው አልነበረም፡፡ አባቶቻችንኮ ወደ ባዕድ አገር ስትሔዱ “እንደነርሱ ኹኑ” ነበር ያሉን፡፡ “የሚበሉትን ብሉ፤ የሚጠጡትን ጠጡ፤ የሚለብሱትን ለብሳችሁ በቋንቋቸው ተናገሩና መልሷቸው” ነበር ያሉን፡፡ እንደዛ የሚኾን ሰው ግን አላተረፍንም፡፡ ብዙ ደቡብ አፍሪካውያን መጥተዋል፡፡ ነገር ግን ለእነርሱ የሚኾን አላዘጋጀንም፡፡ ይኼ ነው ሰማርያ ማለት፡፡ ነገ ትልቁ ሥራችንም ይኼ ነው፡፡ ይህን ጽሑፍ የምናነብ ሰዎች እንዲሁ አንብበን “በጣም ደስ ብሎናል፡፡ ጥሩ ጽሑፍ ነው” ብለን አይደለም መሔድ ያለብን፡፡ የቤት ሥራ ነው ይዘን የምንሔደው፡፡ ኹላችንም ይህን ጽሑፍ አንብበን በየመስካችን ካልተሰማራን ዝም ብለን ነው ከንፈር የምንመጠው፡፡ “እዚ ቦታ ላይ መናፍቃን እንዲህ አደረጉ፤ እዚህ ቦታ ላይ ከሐዲያን እንዲህ አደረጉ” ብንል ምን ያደርጋል? እንደ ሽሮ ወጥ ለጊዜው ከመቆጣት አልፈን ይኼ ነገር ነገ እንዳይደገም ምን እናድርግ ማለት አለብን፡፡ ይኼ ነው የሰማርያ ስምሪት፡፡ በሰማርያ ሒዱ የተባለው ይኼ ነው፡፡
አራተኛው ደረጃ በዓለም ዳርቻ ነው!
እስከ አሁን ያየናቸው ሦስቱም ይታወቃሉ፡፡ ኢየሩሳሌም ትታወቃለች፡፡ ይሁዳ ትታወቃለች፡፡ ሰማርያም ትታወቃለች፡፡ የዓለም ዳርቻ ግን የት ነው? አይታወቅም፤ ሰፊ ነው፡፡ እስከ ዓለም ዳርቻ ማለት እስከማትመለሱበት ቦታ ድረስ ማለት ነው፡፡ ሐዋርያት ከሔዱበት አልተመለሱም፡፡ የሐዋርያት ልጆችም አልተመለሱም፡፡ በኪደተ እግራቸው የባረኩት አገራቸው ኾኖ በዚያ አስተምረው ነው የቀሩት፡፡ የአንዳንዶቹ ዐፅማቸው፣ የአንዳንዶቹ ተረፈ ዐፅማቸው ነው የተመለሰው፡፡ የዓለም ዳርቻ ማለት ይኼ ነው!
በጠረፉ አከባቢ ትልልቅ ጉባኤዎች እጅግ የበዛ ዋጋ አላቸው፡፡ ስለዚህ ወደ ዓፋር፣ ወደ አሶሳ፣ ወደ ቦረና፣ ወደ ሶማሌ፣ ክርስቲያኖች ወደሚያንሱበት፣ አምስት ስድስት ኾነው ወደሚያስቀድሱበት መሔድ አለብን፡፡ ዕጣንና ጧፍ አንሷቸው “በቃ ማለቃችን ነው” ወደሚሉት መሔድ አለብን፡፡ “አይዟችሁ አለን፤ ብቻችሁ አይደላችሁም፡፡ ቦታ አራራቀን እንጂ ሃይማኖት አልለያየንም፡፡ ቦታ አራራቀን እንጂ ሥርዓት አንድ ነው፡፡ የእናንተ አገልግሎት የእኛ አገልግሎት ነው፤ የእናንተ ማስቀደስ የእኛም ማስቀደስ ነው” ብለን መሔድ አለብን፡፡ ሲኾን ከዛ አልፈን ወደ አፍሪካ አገራት፤ ይህቺን ቤተ ክርስቲያን አይቷት ሰምቷት ወደማያውቁት መሔድ አለብን!
ዛሬ በንግድ የሚሔደው ቻይና፣ ጃፓን፣ ዱባይ፣ ሕንድ፣ ወደ ሌሎችም እንሔዳለን፡፡ ታዲያ ስንት አስተማርን? ስንት አጠመቅን? ወይስ ዕቃ ብቻ ይዘን ነው የምንመጣው? የኦሪትን እምነት እንድናገኝ ያደረገንኮ ታምሪን የተባለ ነጋዴ ነበር፡፡ ዛሬም ታምሪን የኾኑ ነጋዴዎች ያስፈልጉናል፡፡ ቶማስን ሕንድ ድረስ የወሰደው ነጋዴ ነው፡፡ ስለዚህ የነጋዴ ሐዋርያት፣ የሹፌር ሐዋርያት፣ የምሁር ሐዋርያት፣ የባለሙያ ሐዋርያት ያስፈልጉናል፡፡ ሱቅ ከፍታችሁ የምትሸጡ፣ ሻይ ቤት ከፍታችሁ የምትሸጡ፣ ምግብ ሠርታችሁ የምትሸጡ ሑሉ ሐዋርያ ለመኾን መዘጋጀት አለባችሁ፡፡ እስከ ዓለም ዳርቻ ድረስ! እኛ ወደማናውቀው ድረስ መሔድ አለብን፡፡ ብዙ ይቀረናል፡፡ ጀመርነው እንጂ ገና ነን፡፡ ያለቀ እንዳይመስላችሁ! ዛሬ በጉባኤ ስለተሰባሰብን በዝተን ስንታይ የጨረስነው እንዳይመስላችሁ! ገና ብዙ አለ፡፡ ይኼን ተስፋ የሚያደርጉ በጣም ብዙ ሕዝቦች አሉ፡፡ ሒዱ እንጂ ተቀመጡ አልተባልንም፡፡
እንዴት እንሒድ?
አባቶቻችንን ሒደታቸውን በአራት መንገድ ነው የሔዱት፡፡
v  የመጀመሪያው በአካል መሔድ ነው፡፡  
v  ኹለተኛ ቅዱሳት መጻሕፍትን ጽፈው አስተምረዋል፡፡የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ዛሬ ተቃጥሎ፣ ተሰርቆ፣ አይጥ በልቶት፣ ምድር ቀብሮት እንኳን ሊያልቅ ያልቻለውን መጻሕፍት ጽፈዋል፡፡ ለዚህ ሐዋርያዊ ተልእኮ ሦስት አካላት ነበሩ፡፡ አንድ ሊቃውንቱ፤ ኹለት ጸሐፍቱ (የሚጽፉት)፤ ሦስት ደግሞ የሚያስጽፉት፡፡ ገድሉ መጨረሻ ላይ አይታችሁ ከኾነ “የጻፈ፣ ያስጻፈ” ይላል፡፡ ዛሬ እንደነዚህ ዓይነት ሐዋርያት ያስፈልጉናል፡፡ ለምንድነው የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት በየቋንቋው የማይተረጐመው? ሲቻል ሳይሸጥ (በተለይ ለዕጣንና ለጧፍ እንኳን መግዣ ለሌላቸው ምእመናን) ለምን አይሰጥም? ምን አለበት እኔና እናንተ ዐሥር ኾነን አንዳችን የአንድን መጽሐፍ፣ አንዳችን ሌላውን መጽሐፍ ማሰተሚያ በተለያየ ቋንቋ በኦሮምኛ፣ በሀዲያኛ፣ በከንባትኛ፣ በጉራጊኛ፣ በእንግሊዘኛ፣ በጀርመንኛ፣ በየቋንቋ ለምን አናስጽፍም? እዛ ሔደን ማስተማር ባንችል ለምን እንዲህ አድርገን የቤተ ክርስቲያኒቱ ትምህርት ወደየ አገራቱ እንዲደርስ አናደርግም? ለምን የካሴት ሐዋርያት አንኾንም? ለምን ትምህርቱ በካሴት ተባዝቶ በነጻ እንዲሔድ አናደርግም? ዛሬ እንደዉም የዲሽ ዘመን ነው፡፡ በዲሾቻችን ምን እየመጣ እንደኾነ እናውቃለን፤ ወረራው ቀላል አይደለም፡፡ ይኼም ዓይነት ሐዋርያ መምጣት አለበት፡፡ በቀላሉ የሚሔድ ሐዋርያ! አንድ ሰው ወደ እኛ እንዲመጣ አስተርጓሚ መጠበቅ የለበትም፡፡ እኛ ቶሎ ደርሰንለት ቶሎ አምኖ ቶሎ መጽደቅ አለበት፡፡ ጊዜ የለም አሁን፡፡ እርሱን መቼ ነው የምንሠራው?     
v  ሦስተኛው ማእከል የመመሥረት ሐዋርያነት፡፡ አባቶቻችን ለምን ይመስላችኋል ከሰሜን እስከ ደበቡ ከምዕራብ እስከ ምሥራቅ፡ በየቦታው ገዳማትን የተከሉት? ዛሬ ካሉት ገዳማትኮ በተለያዩ ጦርነቶች ምክንያት የጠፉ ገዳማቶቻችን ይበልጣሉ፡፡ በታሪክ የምናውቃቸው ዛሬ ግን በአካል ያላገኘናቸው በጣም ብዙ ሺሕ ገዳማት ነበሩ፡፡ አባቶቻችን እነዚህን ገዳማት የተከሉበት አንዱ ዓላማ ለስብከተ ወንጌል ስምሪት ማእከል እንዲኾኑ ነው፡፡ እዛ ያስተምራሉ፤ እዛ ይጸልያሉ፤ እዛው የምንኩስናው አገልግሎት ይሰጣል፡፡ ከዚያ የወጡ ደቀ መዛሙርትም ይሔዳሉ፤ ያስተምራሉ፤ ይሔዳሉ፤ በተራቸውም ገዳም ይተክላሉ፡፡ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ከሸዋ ነው የሔዱት፡፡ መጀመሪያ አባ በጸሎተ ሚካኤል አምሐራ፣ ከዚያ ሐይቅ፣ ከዛ ደብረ ዳሞ፣ ከዛ ኢየሩሳሌም፣ ከዚያ ግብጽ ሔደዋል፡፡ ተመልሰው መጥተው ግን የስምሪት ማእከል ነው ያቋቋሙት፡፡ የደብረ ሊባኖስ ገዳም እንዲሁ የተተከለ እንዳይመስላችሁ፡፡ ወደ ደቡቡም፣ ወደ ሰሜኑም፣ ወደ ምዕራቡም፣ ወደ ምሥራቁም ለመሔድ እጅግ እስትራቴጂያዊ ቦታ ነው፡፡ ደቀ መዛሙርቶቻቸው ወደ አራቱም አቅጣጫ የሔዱት አቡነ ተክለ ሃይማኖት ገዳሙን ለወንጌል አገልግሎት እንዲመች አድርገው ስለገደሙት ነው፡፡ እንዲህ ዓይነት የስምሪት ቦታ ያስፈልገናል፤ ማእከል፡፡ በሰሜኑም፣ በደቡቡም፣ በምሥራቁም፣ በምዕራቡም የምንኩስና ሕይወትን፣ የአብነት ትምህርትን፣ የስብከተ ወንጌል አገልግሎትን አንድ ላይ የሚሰጡ ማእከላት ያስፈልጉናል፡፡ ያለ ማእከል ሐዋርያ ማፍራት አንችልም፡፡ ነገሥታቱና መኳንንቱ ገንዘባቸውን ሲያወጡ የነበሩትኮ ዝም ብለው አይደለም፡፡ የሕንፃ ፍቅር ስላላቸው አይደለም፤ በፍጹም አይደለም! ያንን ማእከል አድርጎ ለማስተማር ነው፡፡ ሰዉ እንዲሰበሰብ እንዲሰማ ነው፡፡ እስኪ ገድላቱን አንብቧቸው፡፡ ወይም ሲነበቡ አድምጧቸው፡፡ ወይም ስታነቡ አስተውሏቸው፡፡ ገና ሲጀምሩ “በዚህ ቀን በቅዱስ እገሌ በዓል የተሰበሰባችሁ ወንድሞቼ ሆይ ስሙ፡፡ እገሌ የተባለውን ታሪክ እነግራችኋለሁ” ነው የሚሉት፡፡ ስሙ ለምን አለ? ሕዝቡ ተሰብስቦ ይነበብ ስለነበር፡፡ ዛሬኮ ወደነዚህ ማእከላት መጥተን ከቻልን በሰዓታቱ ተኝተን፣ ጎበዝ ነን ከተባልን ደግሞ እኛ ሌላ መዝሙር እየዘመርን፣ አንዳንዶቻችን የራሳችንን ቴፕ፣ አንዳንዶቻችንም ምን ምን የሚያክል ፍራሽ ለአንድ ሌሊት ይዘን ነው የምንሔደው፡፡ እንዴ! እንዲህ ከሆነ ለምን እንሔዳለን? አባቶቻችን ለንግሥ እንድንሰበሰብ ያደረጉን ዋና ዓላማቸው እንድንሰማ ነው፡፡ ሰምተንም ሐዋርያ እንድንኾን ነው፡፡ ዛሬ እነዚህን ማእከላት መሥራት አለብን፡፡ ቤተ ክርስቲያን ስንሠራ ይኼን ታሳቢ ያደረገ መኾን አለበት፡፡ ይኼ ነውኮ ሰማርያ የዓለም ዳርቻ የተባለው!
v  በየቋንቋው የሚያስተምሩ ደቀ መዛሙርትን የማሰማራት ሐዋርያነት፡፡ ከአዲስ አበባ ተነሥቶ ወደማያውቁት ቋንቋ፣ ወደማያውቁት ባሕል እየሔዱ ማስተማር አይቻልም፤ በአስተርጓሚ እያስተማርን አንችለውም፡፡ አያዛልቅም፡፡ ይልቁንስ ታላቁ ሐዋርያዊ አባት ቅዱስ አትናቴዎስ እንዳደረገው መኾን አለብን፡፡ ቅዱስ አትናቴዎስ አባ ሰላማ ከሳቴ ብርሃንን የኾነው አባ ሰላማ ልሾም ብሎ ስለሔደ ወይም አብርሃና አጽብሃ እንደዚያ ብለው ስለላኩት አይደለም፡፡ የተላከው ጳጳስ ይዞ እንዲመጣ ነበር፡፡ ነገር ግን ቅዱስ አትናቴዎስ ኹለት ዓመት አስተምሮ ነው ቋንቋውን፣ ባሕሉን በሚያውቀው አገር ጳጳስ አድርጎ ነው የላከው፡፡ ስለዚህ ከየቋንቋው እናምጣ፡፡ ከየባሕሉ እናምጣ፡፡ ከየአከባቢው እናምጣ፡፡ ከየሰዉ እናምጣ፡፡ አምጥተንም እናስተምራቸው፤ አስተምረንም እናሰማራቸው፡፡ በምታውቁት ቋንቋ፣ በምታውቁት ባሕል፣ በምታውቁት አሠራር አስተምሩ እንበላቸው፡፡ ገንዘብ ሲያስፈልጋችሁ እንሰጣለን፤ መጽሐፍ ሲያስፈልጋችሁ እንሰጣለን፤ የማስተማሪያ ነገሮች ሲያስፈልጋችሁ እንሰጣለን፤ ግን እናንተ ሐዋርያት ኹኑ፤ ሒዱ እንበላቸው፡፡ ይኼ ስምሪት ያስፈልጋል ዛሬ፤ የደቀ መዛሙርት ስምሪት፡፡ እነዚህን መጀመሪያ ማሠልጠን ከዚያ ለተልእኳቸው የሚያስፈልጋቸውን መስጠት ከዚያም መጎብኘት ያስፈልጋል፤ እንደ ቅዱስ ጳውሎስ፡፡ ስለዚህ እናሰማራ! ከአዲስ አበባ መዘምራን፣ ሰባክያን እየላክን አንችለውም፡፡ በዓመት ልንሠራ የምንችለውን ለምን ወደ ዐሥር ዓመት እናራዝሟለን? ሕዝቡም በቋንቋው ሲነገረው በቀላሉ ደስ ብሎት ነው የሚቀበለው፡፡ ሐዋርያት 72 ቋንቋ የተሰጣቸው አንዱ ዓላማኮ ለዚህ ነው፡፡
ይኼ ነው ኃላፊነታችን! በኢየሩሳሌም፣ በይሁዳ፣ በሰማርያ፣ እስከ ዓለም ዳርቻ የተባለው ይኼ ነው፡፡
እግዚአብሔር ከኢየሩሳሌም እስከ ዓለም ዳርቻ ድረስ ተሰማርተን፣ 30 60 100 ያማረ ፍሬ አፍርተን፣ ያለ ሐፍረት ቆመን “ጌታ ሆይ! ኹለት መክሊት ሰጥተኸን ነበር፤ እነሆ አራት አደረግነው፡፡ አምስት ሰጥተኸን ነበር፤ እነሆ ዐሥር አደረግነው” የምንልና “ና አንተ ታማኝ ባርያ ወደ ደስታው ግባ” ከተባለው ወገን እንዲያደርገን፣ ያ መክሊቱን ቀብሮ “አንተ ክፉና ሐኬተኛ፤ እኔ ካልዘራሁበት የምሰበስብ ካልተከልኩበት የማጭድ መኾኑን ካወቅክ ለምን ለሌላ አትሰጠውም ነበር? እሳትና ጥርስ ማፋጨት ወዳለበት ወርውሩት” ከተባለው እንዲጠብቀን የእግዚአብሔር ቸርነት የእመቤታችን አማላጅነት አይለየን፤ አሜን!!!  

2015 ጁን 18, ሐሙስ

በባዕድ ሀገር ስለ እምነቴ እንድመሰክር አብቅቶኛል

                                                    byማኅበረ ቅዱሳን አትም ኢሜይል
    ሰኔ 11 ቀን 2007 ዓ.ም.
                                                                                                                                                  በእንዳለ ደምስስ
11atletአትሌት ካልኢተ አብርሃም ትባላለች፡፡ ገና የ18 ዓመት ወጣት ናት፡፡ ከ2006 ዓ.ም. ጀምሮ ታይላንድ ውስጥ ለሚገኝ ሃቲያ ዩኒቨርስቲን ወክላ ትሮጣለች፤ ዩኒቨርስቲውም በዲግሪ መርሐ ግብር የሰውነት ማጎልመሻ /Physical Education/ ትምህርት እድል ሰጥቷት በመማር ላይ ትገኛለች፡፡ ከ43 በላይ ታይላንድ ውስጥ በሚደረጉ እንዲሁም ዓለም አቀፍ ውድድሮች ከ5 ሺሕ እስከ ግማሽ ማራቶን /21 ኪሎ ሜትር/ ድረስ በመሮጥ 40 ዋንጫዎችንና በርካታ የወርቅ ሜዳልያዎችን ለማግኘት ችላለች፡፡

ታይላንድ ውስጥ በምታደርጋቸው ውድድሮች አሸንፋ ስትገባ ለንጉሱና በቡድሂዝም እምነት ለተቀረጹት ምስሎች እንድትሰግድ ማስጠንቀቂያና መመሪያ ተሰጥቷታል፡፡ ነገር ግን በጥምቀት የእግዚአብሔር ልጅነትን ያገኘሁባትን ኦርቶዶክሳዊት እምነቴን አልክድም፤ እናንተም ላቆማችሁት ምስል አልሰግድም!!! በማለት ጸንታ በመቆሟ ትእዛዙንም ተላልፋ በማማተቧ በርካታ ፈተናዎችን አልፋለች፡፡ እግዚአብሔር ረድቶኝ በባእድ ሀገር ስለ እምነቴ ለመመስከር አብቅቶኛል ትላለች አትሌት ካልኢተ አብርሃም፡፡

ስለስደት፤ እንዲሁም ስለ ሩጫ ሕይወቷ እና አስተዳደጓ አነጋግረናታል እንደሚከተለው እናቀርበዋለን፡፡

ስለ አስተዳደግሽ ብታጫውቺን?
የተወለድኩት ከመቀሌ ከተማ 35 ኪሎ ሜትር ላይ በምትገኘው አዱግደም በሚባል ቀበሌ ነው፡፡ ያደግሁት ግን መቀሌ ከተማ ከአክስቴ ጋር ነው፡፡ እናቴ ከልጅነቴ ጀምሮ በቤተ ክርስቲያን እንዳድግ አድርጋኛለች፡፡ ወደ ቤተ ክርስቲያን ሲሄዱ እየተከተልኩ፤ እንዲሁም በየዓመቱ በሚከናወኑ የንግሥ በዓላት በመገኘት፤ ቤታችን ለካህናትና ምእመናን ጸበል ጸዲቅ ሲዘጋጅ እያየሁ ነው ያደግሁት፡፡

ወደ ሩጫው እንዴት ገባሽ?
ከአክስቴ ጋር እየኖርኩ በክረምት ወደ እናቴ ስሄድ ግቢያችን ውስጥ ተከራይተው የሚኖሩ ሯጮች ስለነበሩ ስለ ሩጫ ከእነሱ እየሰማሁ ሌሊት ዘጠኝ ሰዓት ላይ እየተነሱ ለልምምድ ሲሄዱ አብሬ እየሄድኩ ልብሳቸውን እየጠበቅሁ፤ ቀስ በቀስም ወደ ሩጫው እየተሳብኩ በግሌ ልምምድ ጀመርኩ፡፡ ነገር ግን በቤተሰብ በኩል ተቀባይነት ስላላገኘሁ ከአክስቴ ቤት ወጥቼ አንዲት ትንሽ ቤት ተከራይቼ ትምህርቴን እየተማርኩ የሩጫ ልምምዴንም እየሰራሁ ቀሪውን ጊዜዬን አቅሜ የፈቀደውን የቀን ሥራ፤ አትክልተኛም በሆን እየሠራሁ፤ በቀሪ ትርፍ ጊዜዬም መቀሌ ከተማ በሚገኘው መካነ ሰማዕት ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ትምህርት ቤት ገብቼ መማር ጀመርኩ፡፡

በሰንበት ትምህርት ቤቱ የነበረሽ ቆይታ ምን ይመስል ነበር?
ከ8ኛ ክፍል እስከ 10ኛ ክፍል በራሴ ወጪ እየተማርኩ በሰንበት ትምህርት ቤት በአገልግሎት እየተሳተፍኩ፤ የካህናት ልብሰ ተክህኖ የሰንበት ትምህርት ቤታች አልባሳት እያጠብኩ፤ በሩጫውም ቢሆን በተለያዩ መቀሌ ከተማ ውስጥ በሚደረጉ ውድድሮች መሳተፍ ጀመርኩ፡፡ ሰው ቤት ተቀጥሬም የሰራሁበት ጊዜ አለ፡፡ ይህን ያደረግሁት ሩጫው የሕይወቴ አንድ አካል አድርጌ ስለቆጠርኩት ነው፡፡ በልጅነት ልቦናዬም ቢሆን የሚደርሱብኝን ፈተናዎች መጋፈጥ ጀመርኩ፡፡ ለዚህም ሰንበት ትምህርት ቤቱ ለእኔ የተለየ ድጋፍ ያደርግልኝ ነበር በምክርም ሆነ በሚቸግረኝ ነገር ሁሉ ከጎኔ ነበሩ፡፡ መንፈሳዊ ጥንካሬ እንዲኖረኝ አድርጎኛል፡፡ በአዲሐቂ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የ10 ክፍል ትምህርቴን እንዳጠናቀቅሁ ትምህርቱን አቁሜ ሙሉ ጊዜዬን ለልምምድ፤ ለሥራ እና ለአገልግሎት በማዋል ራሴን ወደ ተሻለ ደረጃ ለማድረስ ጥረት አደረግሁ፡፡

ቤተ ክርስቲያንን በመጠጋቴ በልጅነት እድሜዬ መንፈሳዊ ጥንካሬ እንዲኖረኝ፤ እግዘዚአብሔርን መፍራት፤ የቅዱሳን አባቶቻችን ተጋድሎና ታሪክ በተለይም የሰማዕቱ ቅዱስ ጊዮርጊስ ገድል ቤተ ክርስቲያኑ ውሰጥ በየቀኑ ስለሚነበብ የቅዱስ ጊዮርጊስ ታሪክ በፈተና እንድጸና አድርጎኛል፡፡ ወደ ንስሓ እና ምስጢራትን ወደመካፈል መራኝ፡፡

በማኅበረ ቅዱሳን አዲሸሁ እንዲሁም ማይጨው ማእከላት ጋር የነበረሽ ተሳትፎ ምን ይመስል ነበር?
22atletበሩጫ በነበረኝ ተሳትፎ የመቀሌ ዞንን ወክዬ በ5ሺሕ ሜትር ተወዳድሬ አሸነፍኩ፡፡ ከዚያም ለትግራይ ሻምፒዮና ሽሬ ላይ በተካሄደው ውድድር ተካፍዬ ለፕሮጀክት በመመረጤ አዲሰ አበባ መጣሁ፡፡ አዲስ አበባ ስመጣ እንደጠበቅሁት ውጤታማ መሆን ባለመቻሌ አሰልጣኝ ፍለጋ ወደ ዐዲሸሁ ሄድኩኝ፡፡ ዐዲሸሁ እያለሁ ከተከራየሁት ቤት ፊት ለፊት የማኅበሩ ጽ/ቤት ስለነበር ወንድሞችና እህቶችን ማግኘት ቻልኩ፡፡ አንድ ቀን ተከትያቸው ቤተ ክርስቲያን ሲሄዱ አብሬ ሄድኩኝ፡፡ በኪዳነ ምሕረት ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሲያገለግሉ ስመለከት ቀረብኳቸው ፤ቀስ በቀስ እኔም ከእነሱ ጋር በአገልግሎት መሳተፍ ጀመርኩ፡፡ ነገር ግን ከተወሰኑ ወራት በኋላ ወደ ማይጨው አትሌቲክስ ማሰልጠኛ ማእከል ለመግባት ስላሰብኩ ወደዚያው ሳመራ ለማእከሉ አሳወቅሁ፡፡ ለማይጨው ማእከል የእኔ መምጣት ተነግሯቸው ስለነበር ፈልገው አግኝተውኝ አገልግሎትንና ልምምዴን ቀጠልኩ፡፡ በደብረ ስብሐት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ትምህርት ቤት ውስጥም መሳተፍ ጀመርኩ፡፡

በማይጨው ቆይታዬ ከማእከሉ ወንድሞችና እህቶች ብዙ ነገር ተማርኩኝ፡፡ ሰዎችን በክርስትና ሕይወታቸው ጸንተው እንዲኖሩ የመቅረጽ መንፈሳዊ ስጦታቸው ከፍተኛ ነው፡፡ የሚጋጥመኝን የገንዘብ ችግር በመቅረፍ፤ ትክክለኛውን መንገድ በማሳየት ባለውለታዎቼ ናቸው፡፡

በሩጫ ሕይወቴም መሻሻሎችን እንዳሳይና በክልሉ በተደረገ የ5ሺሕና 10ሺህ ሜትር ውድድር ጥሩ ውጤት ማምጣት ቻልኩኝ፡፡ በክለብ ለመታቀፍ ጥረቶችን ባደርግም አልተሳካልኝም፡፡ በርካታ ፈተናዎች አጋጥመውኛል፡፡ እኔ ግን ክርስትናዬ ስለሚበልጥብኝ፤ ሁል ጊዜ በጎ ጎዳናን ተከትዬ መሄድ ስላለብኝና ከክርስትና መንገድ ሊያስወጡኝ የሚችሉ ክፉ ነገሮችን በመጋፈጤ ወደ ስልጠና ማእከሉ ሳልገባ ቀረሁ፡፡

ተስፋ ሳልቆርጥ ወደ አዲስ አበባ መጥቼ 2005 ዓ.ም. በፕሮጀክት ታቅፌ ተወዳደርኩ አሸነፍኩ፡፡ የጃን ሜዳ አገር አቋራጭ ውድድርም ተሳትፌ ለማሸነፍ ቻልኩ፡፡ ነገር ግን ትኩረት የሚሰጠኝ በማጣት ተመልሼ ወደ ሀገሬ ሄድኩ፡፡ ሩጫውን እንዳልተወው እሱን ብዬ ብዙ ነገር አጥቼበታለሁ፡፡ በተለይም ቤተሰቦቼን፤ ትምህርቴንና የትውልድ ቦታዬን አሳጥቶኛል፡፡ እለህ ደግሞ ያዘኝ፡፡ አለኝ የምለው ቤተ ክርስቲያንና የማይጨው ማእከል ወንድሞችና እህቶች ናቸው፡፡ የልምምድ አልባሳት የሉኝም፤ ጫማ የለኝም፤ በጣም ተቸገርኩ፡፡

ወደ ታይላንድ ለመሄድ እንዴት ቻልሽ?
44atletበሰንበት ትምህርት ቤት አገልግሎት የሚያውቀኝ አንድ ወንድም ከአንዲት ታላንዳዊት የሯጮች ማኔጀር ጋር አገናኘኝ፡፡ በሀገሬ ያልተሳካልኝ በሰው ሀገር እንዴት ይሳካልኛል በማለት ጥያቄውን ለመቀበል ተቸገርኩ፡፡ ነገር ግን ከዋነኛ ዓላማዬ አንዱ የሆነውን በሩጫ አገሬን መወከል ስለነበር ልምድም ለመቅሰም እንደሚረዳኝ በማመን፤ እነሱም በዩኒቨርስቲ ደረጃ እንሚያስተምሩኝና ዩኒቨርስቲውን ወክዬ እንድወዳደር ግፊት ስላደረገችብኝ ወደ ታይላንድ ለመሄድ ወሰንኩ፡፡

ዋነኛ ጭንቀቴ የነበረው ቤተ ክርስስቲያን የሌለበት፤ የእግዚአብሔር ስም የማይጠራበት፤ የንስሓ አባት የሌለበት ስለነበር ሰጋሁ፡፡ የምሥጢር ተካፋይ ስለሆንኩም በጣም አሳሰበኝ፡፡፡ ነገር ግን መሥዋዕትነት መክፈል ስለነበረብኝ ያገኘሁትን እድል ለመጠቀም ወሰንኩ፡፡ ከማኔጀሬ ጋር ሆኜ በአውሮፕላን ከአዲስ አበባ ግብጽ፤ ከግብጽ ባንኮክ፤ ከባንኮክ ሃቲያ ዩኒቨርስተ ለመድረስ ዐራት ቀናት ፈጅቶብናል፡፡ ከምሽቱ ሁለት ሰዓት ገብተን ሌሊት 10 ሰዓት ውድድሩ ይካሔዳል፡፡ በጣም ደክሞኛል፤ ምግብ አልበላሁም፤ ከግብጽ ስንነሳ አንድ ኢትዮጵያዊ አግኝቼ ጭማቂ ሰጥቶኝ ስለነበር እሱን በውኃ እየበረዝኩ ጠጥቼ ነው የደረስኩት፡፡

የውድድሩ ሰዓት እየተቃረበ ሲመጣ ማናጀሬ በታይላንድ ሕግ መሠረት ብታሸንፊ በስታድየሙ ውስጥ ለቆሙት ለሀገሪቱ ንጉሥ እና ለቡድሃ እምነት የተቀረጹ ምስሎች መስገድ እንደሚገባኝ ይህ ደግሞ ግዴታ እንደሆነ አስጠነቀቀችኝ፡፡ ሰንበት ትምህርት ቤቴ ሲሸኙኝ ያሰሩልኝ መስቀል፤ ገድለ ጊዮርጊስንና ውዳሴ ማርያምን ይዤ እያለቀስኩ ጸሎት አደረስኩ፡፡ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ፍርፋሪ በልቼ፤ የምስጢር ተካፋይ አድርጋንኝ ለምን በእምነቴ ላይ ይመጡብኛል ብዬ ውድድሩ እስኪጀመር ድረስ በጣም አምርሬ አለቀስኩ፡፡ ወደ ውድድሩም ገባሁ፡፡ አንዲት ኢትዮጵያዊትና ኬንያውያን በብዛት ነበሩ፡፡ ነገር ግን በአንደኝነት ውድድሩን ጨረስኩ፡፡

አሸንፌ ስገባም ለድል ያበቃኝን እግዚአብሔር እያመሰገንኩ የተሰጠኝን ማስጠንቀቂያ ለመጋፈጥ በመወሰን አማተብኩ፡፡ ስታድየሙ በሕዝብ የቁጣ ጩኸት ተናጋ፡፡ የለበስኩት የሃቲያ ዩኒቨርስቲ መለያ ነው፤ በሌላ አነጋገር የታይላንድ መለያ እንደለበስኩ አድርገው ስለቆጠሩት እንዴት ለአምላካችንና ለንጉሣችን አትሰግድም በሚል ቁጣቸው አገረሸ፡፡ ዋንጫውንም ስቀበል አማትቤ ተቀበልኩ ቁጣቸው ከመጀመሪያው ባሰ፡፡ ማናጀሬ ለብቻ ወስዳ ለምን እንዲህ እንዳደረግሁ ጠየቀችኝ፡፡

እንዳሸንፍ ለረዳኝ አምላኬ ምስጋና ነው ያቀረብኩት፡፡ ለማላውቀውና እናንተ ላቆማችሁት ምስል አልሰግድም!! ካልፈለጋችሁኝ ወደ ሀገሬ መልሱኝ ብዬ በአቋሜ ጸናሁ፡፡ ከእግዚአብሔር ጋር ስትሆን ፈተና ሊገጥምህ ይችላል ነገር ግን መቋቋም ግዴታ ነው፤ ከክርስትና የተማርኩት ይህንን ነው፡፡ በባእድ ሀገር ብሆንም እምነቴን የሚያስክደኝ እንደሌለ ማሳየት ይጠበቅብኛል፡፡ ለዚህ ለዚህ ለምን ክርስቲያን ሆንኩ፤ ቅዱስ ጊዮርጊስ ለተጋደለላት፤ ቅዱሳን አባቶቼ በጽናት የቆሙላትን ስለ እውነተኛዋ እምነቴ እንዳልመሰክር ምን ሊያግደኝ ይችላል፡፡ በአቋሜ መጽናቴን በመረዳታቸውና እኔንም ማጣት ስላልፈለጉ በእምነቴ ላይ እንዳይመጡብኝ ተስማማን፡፡

ዩኒቨርስቲው የሰውነት ማጎልመሻ ትምህርትንና ተጓዳኝ ትምህርቶችን እየተማርኩ መኖሪያና ሌሎችም አስፈላጊ የሆኑ ቁሳ ቁሶችን አሟልተውልኝ እኖራለሁ፤ ልምምድ አደርጋለሁ፤ ውድድር ሲኖር እወዳደራለሁ፤ ማናጀሬ ከተለያዩ ሀገራት በሚዘጋጁ ውድድሮች ላይ እንድሳተፍ ታደርጋለች፡፡ እሰካሁን 43 እና ከዚያ በላይ ውድድሮችን አድርጌ 40ዎቹን በአንደኝነት ነው ያጠናቀቅሁት፡፡

ውድድሮቹ አልበዙብሽም?
የውድድሮቹ መብዛት በጣም አድካሚ እንደሆነ እረዳለሁ፡፡ ነገር ግን በተለያዩ ዓለም አቀፍ ውድድሮች ተወዳድሬ ጥሩ ውጤት በማምጣት ስሜን ማስመዝገብ ስለምፈልግ፤ ወደፊትም ለሀገሬ ኢትዮጵያ መወዳደር ስለምፈልግ የተሻለ ልምድና ሰዓት ማስመዝገብ ይጠበቅብኛል፡፡

ታይላንድ ውስጥ ኢትዮጵያውያንን ለማግኘት አልሞከርሽም?
በስምንት ወራ ቆይታዬ አንድ ኢትዮጵያዊ ብቻ ነው ያገኘሁት፡፡ በሀገሩ ውስጥ ኢትዮጵያዊም፤ ቤተ ክርስቲያንም ሆነ የንስሓ አባት ማግኘት አይቻልም፡፡ በዚህ ብዙ ተጎድቻለሁ፡፡

33atletካገኘሻቸው ዋንጫዎችና ሜዳልያዎች ለማኅበረ ቅዱሳን ማይጨው ማእከል፤ መቀሌ ለሚገኘው መካነ ሰማዕት ቅዱስ ጊዮርጊስ እና ለማይጨው ደብረ ስብሃት ቅድስት ሥላሴ ሰንበት ትምህርት ቤቶች ሰጥተሻል፡፡ ምክንያትሽ ምንድነው?
ሃይማኖቴን እንዳውቅ፤ ፈተና ቢገጥመኝ በትእግስት እንዳልፍ፤ የቅዱሳን አባቶቼን ተጋድሎና ስለ እምነታቸው የከፈሉት መሥዋዕትነት እንድረዳ በሕይወት እነሱን እንድመስል ስለረዱኝ፤ እንዲሁም በሥጋዊ ሕይወቴ በችግሬ ሰዓት የደረሱልኝ ሰለሆነ ባለውለታዎቼ ናቸው፡፡ ለውጤቴ ማማር የእነሱ ድርሻ ስላለበት ነው፡፡

በንግግርሽ ውስጥ ሁሌም ቅዱስ ጊዮርጊስን ትጠሪያለሽ ምሥጢሩ ምንድነው?
ቅዱስ ጊዮርጊስ በሕይወቴ ውሰጥ ያደረገልንኝ ዘርዝሬ መጨረስ አልችልም፡፡ የሚገጥሙኝ ፈተናዎችን ሁሉ ያለፍኩት በእሱ አማላጅነትና ፈጥኖ ደራሽነት ነው፡፡ ከሕፃንነቴ ጀምሮ ገድሉን እየሰማሁ ነው ያደግሁት፡፡ ታይላንድ ከመጣሁ በኋላም ስሜን የልዳው ኮኮብ ብዬ ነው የሰየምኩት፡፡ ይህ ድፍረት ነው ልባል እችል ይሆናል ካለኝ ፍቅር የተነሳ ያደረገረሁት እንጂ በትዕቢት አላደረግሁትም፡፡

ስደትን እንዴት ትገልጪዋለሽ?
ኢትዮጵያዊነትህን፤ ሃይማኖትህን፤ ቤተ ክርስቲያንን፤ ባሕልህን፤ ሕዝብህን ታጣለህ፡፡ በሄድክበት ዝና ልታገኝ ትችላለህ ነገር ግን ከሁሉም በላይ ቤተ ክርስቲያን ትናፍቅሃለች፡፡ እግዚአብሔር ይፍታህ የሚል በሌለበት ደስታ ይኖራል ብዬ አላስብም፤ ነገር ግን አላማህን እስክታሳካ ተፈትነህ ማለፍ አለብህ፡፡ በጣም የሚገርምህ ለቤተ ክርስቲያን ያለህ ፍቅር በስደት ስትኖር ይጨምራል፡፡ የኔ የምለው ሰው ስለሌለ በትርፍ ጊዜ እመቤታችንንን፤ ቅዱስ ጊዮርጊስን እየተማጸንኩ ከእነሱ ጋር እነጋገራለሁ፡፡ በባእድ ሀገር ቋንቋዬ እነሱ ናቸው፡፡ በየቀኑ ማታ ማታ ጸሎት አድርጌ ከመተኛቴ በፊት መኖሪያዬ ካለበት የሕንፃ ማማ ላይ ወጥቼ ፊቴን ወደ ምሥራቅ አዙሬ ኢትዮጵያዊው አቡነ ተክለ ሃማኖት ሆይ ይፍቱኝ እያልኩ ወደ ክፍሌ እመለሳለሁ፡፡

እስቲ ከገጠመኞችሽ አንዱን አካፍዪን?

ማናጀሬ ልጇ ከትምህርት ቤት ለሦስት ቀናት ወደ ቤት ሳይመለስ ሲቀርባት ማታ ጸሎት እያደረግሁ መጥታ እባክሽ ልጄ ወደ ቤት ከመጣ ሦስተኛ ቀኑ ነው፡፡ ለምትወጂው አምላክሽና ለልዳው ቅዱስ ጊዮርጊስ ለምኚልኝ ብላ ሻማ ሳበራ ስለምታይ ሻማ ይዛ መጥታ እራሷ ያበራችበት ጊዜ አልረሳውም፡፡

የወደፊት እቅደሽ ምንድነው?

ኢትዮጵያሀገሬን በዓለም አቀፍ ውድድሮች መወከልና ጥሩ ውጤት ማምጣት እፈልጋለሁ፤ ለዚህም ነው ጠንክሬ በመሥራት ላይ የምገኘው፡፡

የምታስተላልፊው መልእክት?
በቤተ ክርስቲያን ውስጥ መኖር፤ ማገልገል ለሥጋም ሆነ ለነፍስም የሚጠቅም ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን መልካም የሆነውን ሁሉ ዐቅፋ የያዘች ናት፡፡ ወደ ቤተ ክርስቲያን እንድጠጋ ከማር ከወተት የሚጣፍጠውን ቃለ እግዚአብሔር ትመግበናለች፤ ፈተናም ቢመጣ በእቅፍዋ ታስጠልለናለች፡፡ ወደ እግዚአብሔር እንቅረብ የሚያሳጣንም አንዳች ነገር የለም ነው የምለው፡፡

በመጨረሻም ከጎኔ በመሆን ለረዱኝ ወላጅ እናቴና ቤተሰቦቼ፤ ለሰንበት ትምህርት ቤቴ መካነ ሰማዕት ቅዱስ ጊዮርጊስ ለማኅበረ ቅዱሳን ማይጨውና ዐዲሸሁ ወረዳ ማእከላት፤ እንዲሁም በተለያዩ ሁኔታዎች ለረዱኝ ሁሉ ምስጋና ይድረሳቸው፡፡+++

2015 ጁን 17, ረቡዕ

ሒዱ እንጂ ተቀመጡ አልተባልንም (ክፍል አንድ)

    



በዲ/ን ዳንኤል ክብረት
      (መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ሰኔ 9 ቀን 2007 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
     ውድ የመቅረዝ አንባብያን! እንዴት አላችሁ? ይህ ጽሑፍ ዲ/ን ዳንኤል ክብረት ማኅበረ ቅዱሳን ሰኔ 7 ቀን 2007 ዓ.ም. ወደ ቡኢ ደብረ ሰላም በዓለ ወልድ ቤተ ክርስቲያን ባዘጋጀው የበእንተ ወንጌል መርሐ ግብር ላይ ያስተማረው ትምህርት ነው፡፡ ስብከቱ አንድ ሰዓት ከዐሥር ደቂቃ የሚፈጅ ስለኾነ ወደ ጽሑፍ ሲቀየር ትንሽ በዛ ይላል፡፡ በመኾኑም በኹለት ክፍል እንዳቀርበው ተገድጃለሁ፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ዲ/ን ዳንኤል ሲሰብክም የሚያነብ ስለሚመስል ብዙ የሚደጋገሙ ዐረፍተ ነገሮችን ስለሌሉበት፥ ያስተካከልኩት ነገር ቢኖር በጉባኤው ላልነበረ ሰው የማይረዱ ጥቃቅን ስንኞችን ብቻ ነው፡፡ ስለ ኹሉም መልካም መልካም ንባብ ይኹንላችሁ!!!

 ይህንን ቃል የተናገረው ከዛሬ 700 ዓመት በፊት በደቡብ እስከ ባሌ ድረስ ተዘዋውሮ ያስተማረው፣ ለስብከተ ወንጌል ሲል ሕይወቱን የገበረው፣ በኋላም በቤተ ክርስቲያኒቱ ትልቅ ፍሬ ያፈራው፣ የታላቁ ጻድቅ የአቡነ ተክለ ሃይማኖት ፍሬዎች ከኾኑት ከ12ቱ መምህራነ ወንጌል አንዱ የኾነው ታላቁ አኖሬዎስ ነው፡፡ ቅዱስ አኖሬዎስ በባሌ፣ በምዕራብ ሸዋ ኹለት ታላላቅ ገዳማት ነበሩት፡፡ ኹለቱም በ16ኛ መ.ክ.ዘ. መጀመሪያ አጋማሽ ላይ ግራኝ አገሪቱን ባጠፋበት ጊዜ እንደጠፉ እስከ አሁን አልተመለሱም፡፡ አንዱ ገዳሙ ብቻ በደቡብ ወሎ ከደሴ ከተማ 12 ኪ.ሜ. ርቀት ላይ ይገኛል፡፡
ይኼ ታላቅ ሐዋርያ በደቡብ ኢትዮጵያ ታላቅ ሥራ ከሠሩት 12ቱ መምህራን አንዱ ነው፡፡ እየተዘዋወረ ሲያስተምር በወቅቱ የአከባቢው ገዢ የነበረና ገና ክርስትናን ያልተቀበለ አገረ ገዢው አስጠርቶ፡- “በእኔ አገር እኔ ሳልፈቅድልህ እኔ የማላውቀውን አዲስ ሃይማኖት ለምን ታስተምራለህ? አንተንስ እዚህ ቦታ ምን አመጣህ?” ብሎ በጠየቀው ጊዜ፡- “ገና እስከማናውቃቸው ቦታዎች ድረስ እንሔዳለን፡፡ በእግዚአብሔር ጉባኤ አንድ የኾንነውን፥ ነገር ግን እኛ በአካል ያላወቅናቸው ወንድሞቻችንን እስክናውቅ ድረስ አንደክምም፡፡ የእግዚአብሔር አገር ሰፊ ነው፡፡ የእግዚአብሔር አገር እስኪያልቅ ድረስ አገልግሎታችን አያልቅም” አለው፡፡ አገረ ገዢውም፡- “ለምን አንድ ቦታ ተቀምጠህ አትሠራም? አገሩን እየዞርክ ለምን ትረብሻለህ?” ብሎ ሲጠይቀው “እኛ’ኮ ሒዱ እንጂ ተቀመጡ አልተባልንም” አለው፡፡ የዚህ ጽሑፍ ዋና ፍሬ ነገርም ይኼው ነው፤ መሔድ፡፡
ለዐሥራ ኹለቱ የመጀመሪያዎቹ ሐዋርያት የተሰጠው ስያሜም ከመሔድ ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ሐዋርያ ማለት ሒያጅ ማለት ነው፡፡ በሐዋርያነት አገልግሎት ትልቁና የመጀመሪያው ሥራ መሔድ ነው፡፡ ከሚያውቁት ወደማያውቁት፣ ከተከበሩበት ወዳልተከበሩበት፣ በባሕል፡ በቋንቋ፡ በሐሳብ ከሚግባቡት ወደማይግባቡት፣ ከቅርቡ ወደ ሩቁ መሔድ ነው፤ ሐዋርያነት፡፡ ጌታችንም ከማረጉ በፊት ለሐዋርያት ኹለት ትእዛዛት ሰጥጻቸው ነበር፡፡ አንዱ በሐዋርያት ሥራ 1፡8 ላይ የተመዘገበ ሲኾን ኹለተኛውም “ሒዱና በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኋቸው፣ ያዘዝኋችሁንም ኹሉ እንዲጠብቁ እያስተማራችኋቸው ደቀ መዛሙርት አድርጓቸው” የሚል ነው /ማቴ.28፡20/፡፡ ሦስት ኃላፊነቶችን ነው የተሰጣቸው፡፡ የመጀመሪያው መሔድ ነው፤ ኹለተኛው ማስተማር ነው፤ ሦስተኛው ተምረው ያመኑትን አጥምቆ ደቀ መዝሙር ማድረግ ነው፡፡ በዚሁ የወንጌል ሐሳብ መሠረት ደቀ መዝሙር ማድረግ ማለት ክርስቲያን ማድረግ ማለት ነው፡፡ ምክንያቱም እነዚህ ደቀ መዛሙርት በኋላ “መጀመሪያ በአንጾክያ ክርስቲያን ተባሉ” ይላልና /ሐዋ.11፡26/፡፡
ደቀ መዝሙር ማድረግ ክርስቲያን ማድረግ ነው፡፡ የመጀመሪያው ትእዛዛቸው ግን ሒዱ ነው የተባሉት፡፡ “በዚህ በኢየሩሳሌም፣ በምታውቁት ቦታ፣ በለመዳችሁት ቦታ፣ ዓሣ ስታደምጡበት በኖራችሁት ቦታ፣ ቋንቋዉን ባሕሉን በምታውቁት ቦታ፣ ብዙ ዘመዶች፡ ብዙ ወዳጆች ባልዋችሁ ቦታ እንዳትቀመጡ፤ ሒዱ” ነው የተባሉት፡፡ እንዲያውም በቅዱስ እስጢፋኖስ ላይ የመጀመሪያው ሰማዕትነት ሲደርስና ሐዋርያት በየቦታው ሲበተኑ የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ለዚህ የሚሰጡት ምክንያት “ሒዱና ዓለምን በሙሉ አስተምሩ” የተባሉት ሐዋርያት እንዴት እንደሚኬድ ስለማያውቁትና ለመንገዱም አዲስ ስለነበሩ በዚያች በኢየሩሳሌም ከተማ አንዲት ማኅበር መሥርተው ለ7000 ማኅበረ እስጢፋኖስ ተቀምጠው ነበር፡፡ ከመላው ዓለም የመጡ አይሁድ፣ በኢየሩሳሌም የነበሩትም አይሁድ አንድ ኾነው እዚያ ነበሩ፡፡ ለብዙ ቀናትም እዛ ተቀመጡ፡፡ በመጨረሻ ግን ቅዱስ እስጢፋኖስ በሰማዕትነት ሲያርፍና በቤተ ክርስቲያን ላይ ፈተና ሲመጣ ኹሉም በየመንገዳቸው ወንጌልን እያስተማሩ ሔዱ፤ ተበተኑ /ሐዋ.8/፡፡ ከኢየሩሳሌሙ ሊቀ ጳጳሱ ከቅዱስ ያዕቆብ በስተቀር ኹሉም ተበተኑ፡፡ ሐዋርያት ብቻ ሳይኾኑ በዛች በማኅበረ ቅዱስ እስጢፋኖስ አማካኝነት የተማሩት ሌሎች ምእመናንም ጭምር አገሪቱን ትተው በሔዱበት ጊዜ በየመንገዳቸው ወንጌልን እያስተማሩ ነው የሔዱት፡፡ ይኼ የሚነግረን የመጀመሪያው የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት እኔና እናንተም የተጠራንበት አገልግሎት መሔድ መኾኑን ነው፡፡ ታላቁ አኖሬዎስም “ሒዱ እንጂ ተቀመጡ አልተባልንም” ነው ያለው፡፡
“እንዴት ነው የምንሔደው?” የሚለውን ደግሞ ጌታችን ከማረጉ ከጥቂት ሰዓታት በፊት በሐዋ.1፡8 ጀምሮ ነግሯቸዋል፡፡ “ሒዱና አስተምሩ ብለኸናል፤ መሔድ ግን ምንድነው? እንዲሁ ዝም ብሎ መሄድ ነውን?” የሚለው የሐዋርያት ጥያቄ ነበርና፡፡ ለዚህ ጌታችን መሠረቱን መሥርቶላቸዋል፡፡ “በኢየሩሳሌም፣ በይሁዳ፣ በሰማርያ፣ እስከ ዓለም ዳርቻ ምስክሮቼ ትኾናላችሁ” በማለት፡፡ ይኼን ምስክርነት በአራት ደረጃ በአራት ምዕራፍ ከፍሎ ነው የነገራቸው፡፡ በኢየሩሳሌም፣ በይሁዳ፣ በሰማርያ፣ እስከ ዓለም ዳርቻ በማለት፡፡ በአንድ ጊዜ ወደ ዓለም ዳርቻ እንዲሔዱ አልነገራቸውም፡፡ በእነዚህ በአራቱ ደረጃዎች ግን እስከ መጨረሻው እስከ ዓም ዳርቻ ድረስ እንዲሔዱ ነግሯቸዋል፡፡ እስኪ አንድ በአንድ እንመልከታቸው፡፡
በኢየሩሳሌም ማለት ምንድነው?
ኢየሩሳሌም ከኦሪት ዘመን ጀምሮ የምትታወቅ የሰላም ከተማ ተብላ የተጠራች ከተማ ናት፡፡ ቤተ መቅደሱም ቤተ መንግሥቱም የነበረባት ከተማ ናት፡፡ የዳዊትና የሰለሞን ከተማ ናት፡፡ የመልከ ጼዴቅ ከተማ ናት፡፡ በክርስትና ደግሞ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታላቁን የማዳን ሥራ የፈጸመበት (የፈተረደበት፣ የተገረፈበት፣ የተሰቀለበት፣ የሞተበት፣ ከሙታን የተነሣበት፣ ያረገበትና መንፈስ ቅዱስን ለሐዋርያት የላከበት) ሥፍራ ነው፡፡ የመጀመሪያዋም ቤተ ክርስቲያን (ጉባኤ ምእመናን፣ ጉባኤ ካህናት) የተመሠረተባት ቦታ ናት፡፡ ለቅዱሳት ቦታዎች (ለጎልጎታ፣ ለደብረ ዘይት) በጣም ቅርብ ቦታ ናት፡፡ ሐዋርያትም የነበሩት፣ መንፈስ ቅዱስን የተቀበሉት፣ አገልግሎታቸውንም የጀመሩት በኢየሩሳሌም ነው፡፡ በኢየሩሳሌም የጀመሩት አገልግሎት ግን በኢየሩሳሌም እንዲጨርሱት አይደለም የታዘዙት፡፡ በዓለም ዳርቻ እንዲጨርሱት ነው የታዘዙት፡፡
ኢየሩሳሌም በዚያን ጊዜ ለክርስትናው ምቹ ናት፡፡ ቢያንስ ብዙ ክርስቲያኖች አሏት፡፡ በቅዱስ ጴጥሮስ ስብከት ያመኑት 3,000 ምእመናን ተጨምረዋል፡፡ ጌታችን መነሣቱን፣ ማረጉን የሚያውቁ ሌሎች ምእመናን አሉ፡፡ ማረፊያቸው ማለትም የማርያም ቤት እዚያ ነው ያለው፡፡ ጸሎት ለማድረግ የጌታችን መቃብር ቅርብ ነው፡፡ ከዚያ በተጨማሪ ቅዱሳን ሐዋርያት በበዓለ ጰራቅሊጦስ መንፈስ ቅዱስ ወርዶላቸው በ72 ቋንቋ ሲናገሩ ያዩ የሰሙ ምስክሮች አሉ፡፡ ስለዚህ ይኼ ቦታ ምቹ ነው፡፡ በዚህ ነው ስምሪቱን እንዲጀመር ጌታችን ያዘዘው፡፡
ኢየሩሳሌም ምንድነው? ኢየሩሳሌም ቤተሰብ ነው፡፡ የስብከተ ወንጌል ስምሪት የሚጀመረው ከቤተሰብ ነው፡፡ የመጀመሪያው ጉባኤ፣ የመጀመሪያው የወንጌል አገልግሎት፣ የመጀመሪያው ትምህርት መሰጠት ያለበት ከባል፣ ከሚስት፣ ከልጆች ነው፤ ከቤተሰብ፡፡ አሁን ብዙዎቻችን በሰርክ ጉባኤ፣ እንደ በእንተ ወንጌልና ሐዊረ ሕይወት ባሉ ጉባኤያት፣ በየገዳማቱ በሚደረጉ ጉዞዎች ልናገኘው የምንሞክረውን ትምህርት በዛ አልነበረም ማግኘት የነበረብን፡፡ ከቤት ውስጥ ነበር ማግኘት የነበረብን፡፡ ይኼኛው (የሰርኩና የሌላው ጉባኤ) ያገኘነውን የምንሠራበት፣ የምናጠናክርበት፤ “ሰው በእንጀራ ብቻ አይኖርም” እንደተባለ ወንጌል ምግብም ስለኾነ ይበልጥ የምንመገብበት እንጂ አዲስ ዕውቀት፣ መሠረታዊ ትምህርት የምናገኝበት አልነበረም መኾን የነበረበት፡፡ እንዲህ እየኾነ ያለው በኢየሩሳሌም አገልግሎት ስለሌለ ነው እንጂ፡፡ ከቤት ነበር መማር የነበረብን፡፡
ይኼንን ኹላችንም ከምናውቀው አንድ ታሪክ ምሳሌነት እንይ፡፡ ከታላቁ ኢትዮጵያዊው ሐዋርያ ከአቡነ ተክለ ሃይማኖት፡፡ አቡነ ተክለ ሃይማኖት፥ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ኾነው እንዲወጡ ያደረጋቸው አንዱ መሠረት በቤታቸው ያገኙት ትምህርት ነው፡፡ ገድላቸው እንደሚነግረን በሰባት ዓመታቸው ነው አባታቸው ቁጭ አድርገው ከመዝሙረ ዳዊት ጀምረው ከዚያም ብሉይንና ሐዲስን ሌሎችንም የቤተ ክርስቲያንን መጻሕፍት ጭምር ያስተማሯቸው፡፡ እስኪ ስንቶቻችን ነን በቤታችን ብሉይንና ሐዲስን ያለን? ስንቶቻችን ነን በቤታችን መጽሐፍ ቅዱስ የሚነበብልን ወይም የምናነብ? በስንቶቻችን ቤት ስንክሳር ይነበባል? በስንቶቻችን ቤት ገድለ ቅዱሳን ይነበባል? እዛ ስላልለመድነው ነው’ኮ ከፍ ስንል በቅዱሳት ገድላት ላይ ጥያቄ የምናነሣው፡፡ እንግዳ ትምህርት የሚመስለን ገና ከቤታችን ስላልለመድነው ነው፡፡
ለምንድነው እንጀራ ላይ ጥያቄ የማይነሣብን? ብዙዎቻችን በእንጀራ ላይ ጥያቄ የለብንም፡፡ ማንም ኢትዮጵያዊ እንጀራ ላይ ጥያቄ የለውም፡፡ እንደዉም አንድ ሰው ወደ ውጪ ሲሔድ ለመጀመሪያ ከቤተሰብ ላኩልኝ የሚለው እንጀራ ድርቆሽ ነው፡፡ ብዙ ነገር ይረሳል፤ እንጀራንና ሽሮን ግን አይረሳም፡፡ ለምን? ከሕፃንነታችን ጀምሮ፣ አንዳንዶቹ ሱስ ኾነባቸዋል እስኪሉን ድረስ ለእንጀራ ልዩ ፍቅር ያለን ስለ ምንም ምክንያት አይደለም፡፡ እንጀራ ውስጥ ምን ዓይነት ማዕድን እንዳለ እንኳን ያወቅነው በኋላ ነው፡፡ ለእንጀራ ልዩ ፍቅር ያለን እናቶቻችን፣ አባቶቻችን ከልጅነታችን አንሥተው ያጎረሱን ርሱ ስለኾነ ነው፡፡ ቅዱሳት መጻሕፍትን እንዲህ ከቤተሰብ ጀምረን ተምረን ቢኾን በኋላ እንግዶች አንኾንም ነበር፡፡ ለጥቅስ እንግዶች አንኾንም ነበር፡፡ ለስንክሳር፣ ለገድለ ቅዱሳን፣ ለቅዳሴው እንግዶች አንኾንም ነበር፡፡
(ጸጋ ዘአብ) አቡነ ተክለ ሃይማኖትን በሰባት ዓመታቸው ነው ብሉይንና ሐዲስን ሌሎችንም ቅዱሳት መጻሕፍት ጨምረው ያስተማሯቸው፡፡ በዛ ሰዓት ነው ትምህርት መጀመር የነበረበት፡፡ በቤተ ክርስቲያናችን ሥርዓት’ኮ “አንድ ልጅ ሰባት ዓመት ሲሞላው ጾም ይጀምራል” የሚባለውም ዝም ብሎ አይደለም፡፡ ትምህርቱም አብሮ ስለሚጀምር ነው፡፡ ትምህርቱም ከጾም፣ ከጸሎት ጋር መኾን ስላለበት ጭምር ነው፡፡ ያ የሰባት ዓመት ዕድሜ ቅዱሳት መጻሕፍትን የሚማርበት፣ በኢየሩሳሌም የሚሰጠውን የወንጌል አገልግሎት የሚጀምርበት ዕድሜ ነው፡፡
ዛሬ ይህን ጽሑፍ የምናነብ ቤተሰቦች ይህን ይዘን መሔድ አለብን፡፡ “ለማስተማር የሚችል ዕውቀት የለንም” ብንል እንኳን በየቤታችን ቅዱሳት መጻሕፍትን አምጥተን እንደ ጥንቷ ቤተ ክርስቲያን እራት ከመበላቱ በፊት እንዲያነቡ ማድረግ እንችላለን፡፡ በጥንቷ ቤተ ክርስቲያን እራት ከመቅረቡ በፊት (ያውም እንደዛሬ መብራት ሳይኖር) እሳት እየነደደ ወይም ደግሞ ሌሎች በእሳት የሚሠሩ መብራቶች እየነደዱ ልጆች ተነሥተው፣ ልጆች እስኪደርሱ ድረስ ደግሞ የተመደበ ካህን ወይም ዲያቆን ወይም መሪጌታ መጥቶ እዚያ ቤት ውስጥ ወይም ደግሞ በቤተ ክርስቲያናችን ዛሬ የቆሎ ተማሪዎች የምንላቸው የአብነት ተማሪዎች በየቦታው ሲሰማሩ አንዱ ሥራቸው ይኼ ነበር፡፡ እዚያ ቤት ተጠግቶ፣ ምግብ እየተሰጠው፣ እየተማረ፣ ለቤተሰቡ ደግሞ ቅዱሳት መጻሕፍትን እያነበበ፡፡ እራት ከመበላቱ በፊት ገድለ ቅዱሳን፣ ስንክሳር ተነቦ ነው እራት የሚበላው፡፡ 
በባሕላችን አንድ አባባል አለ፤ “እራትና መብራት አይንሳን” የሚል፡፡ ኢትዮጵያውያን ምሳ ስለማይበሉ ነውን? ቁርስ ይንሳን ማለታቸው ነውን? ለምድነው እራት ትልቅ ትኩረት የተሰጠው ለምንድነው? እራትና መብራት የተባለው ባሕላችን የገበሬው ባሕል ነው፡፡ ገበሬው ሲሠራ ነው የሚውለው፡፡ ምሳ የሚባለው በየዋለበት ሥፍራ ነው፡፡ የሚያጭደውም አጨዳ ቦታ፤ የሚያርሰውም እርሻ ቦታ፤ የሚነግደውም የንግዱ ቦታ ነው የሚበላው፡፡ ቤተ ሰብ የሚሰበሰበው እራት ላይ ነው፡፡ ከብት የያዘውም ከብቱን ይዞ ይመጣል፤ አራሹም ከግብርናው ይመለሳል፤ ቤት የዋለውም የቤት ሥራውን ጨርሶ ይጠብቃል፡፡ በኢትዮጵያውያን ባሕል እራት ትልቅ ነው፡፡ ከምግብነት ያለፈ የቤተሰቡን አንድነት የሚያስረዳ ነው፡፡
ይኼ የእኛ ባሕል ብቻ አይደለም፡፡ በባሕል የምንዛመዳቸው ሌሎች ምሥራቃውያንም ከምሳና ከቁርስ በላይ ትልቁ ትኩረታቸው እራት ነው፡፡ ጌታችንም በምሴተ ሐሙስ ሥጋዉንና ደሙን ለሐዋርያት የሰጠው በቁርስ አይደለም፤ በምሳ ሰዓት አይደለም፤ በእራት ነው፡፡ “የመጨረሻው እራት” የምንለውም ለዚያ ነው፡፡
እራት በእኛ ባሕል ትልቅ ቦታ አለው፡፡ የቤተሰቡ መሰብሰቢያ ነው፡፡ በዚያ ሰዓት ነው ቅዱሳት መጻሕፍት ይነበቡ የነበሩት፡፡ ዛሬ ይኼ ቤተሰብ ስለጠፋ ነው ብዙዎቻችን እያወቅነው፣ ፍቅሩ እያለን፣ እየወደድን መልስ ያጣነው፡፡ እመቤታችንን ማመን፣ ስለ እመቤታችን መቆርቆር፣ የእመቤታችን ስም ሲነሣ ደማችን እንዴት እንደሚሞቅ ኹላችንም እናውቋለን፡፡ ይኼንን የሚቃወሙ ሰዎች ኹለትና ሦስት ነገር ይዘው ሲመጡ ግን የሚኾን መልስ ያጣነው ፍቅሩ ጠፍቶብን አይደለም፡፡ ይኼ የቤተሰብ ማለትም ኢየሩሳሌም ውስጥ መሰጠት የነበረበት የወንጌል አገልግሎት ስለተቋረጠ ነው፡፡
ይህቺ ቤተ ክርስቲያን ዛሬ ትልቅ ደረጃ ላይ ደርሳ 40 እና 50 ሚልዮን ሕዝብ የሰበሰበችው እንዲህ እኛ እንደምናደርገው ዓይነት ጉባኤ አዘጋጅታ አይደለም፡፡ በቤተሰብ የሚያስተምሩ መምህራን ስለነበሯት ነው፡፡ የሌሎች ቅዱሳንንም ታሪክ ብናይ እንደዚህ ነው፡፡
(ጸጋ ዘአብ አቡነ ተክለ ሃይማኖትን) እስከ 15 ዓመታቸው ድረስ ለ8 ዓመታት ያህል ቅዱሳት መጻሕፍትን አስተምረው ነው ወደ ሊቀ ጳጳሱ የወሰዷቸው፡፡ “አሁን አውቀሃል፤ አሁን ቤተ ክርስቲያንን ማገልገል አለብህ” ብለው የቤተ ክርስቲያን ሊቅ ያፈሩት ራሳቸው ጸጋ ዘአብ ናቸው፡፡ ዛሬ ለቤተ ክርስቲያን ይህን የሚያፈራ ቤተሰብ አለን ወይ? “ልጄ መማር አለበት፤ ማወቅ አለበት፤ ነገ ወጥተህ መድረክ ላይ ወንጌል የምታስተምረው አንተ ነህ፤ ነገ ዲያቆን ካህን ጳጳስ ኾነህ የምታገለግለው አንተ ነህ፤ ነገ በገዳማት ገብተህ መናኝ መነኮሴ የምትኾነው አንተ ነህ፤ ነገ በየመሥሪያ ቤትህ ቁጭ ብለህ የቢሮ ሥራህን ስትሠራ የሃይማኖት ጉዳይ ሲመጣ ልክ እንደ ቅዱስ ጊዮርጊስ የምትመሰክረው አንተ ነህ” የምንል አለን ወይ?
ቅዱስ ጊዮርጊስኮ አባቱ ከልጅነቱ አንሥቶ አስተምሮ ስላሳደገው ነው የአባቱን መንግሥት ልረከብ ብሎ ሲሔድ ሰባዎቹ ነገሥታት እግዚአብሔር ላይ ሲያላግጡና ጣዖታትን ሲያመልኩ ሲያይ “አይ! ይኼን መንግሥት ተቀብዬ’ማ ሃይማኖቴን አልተውም” ብሎ ምስክርነትን መስጠት የጀመረው፡፡ ለምንድነው ዛሬ የቢሮ ሠራተኛው፣ የጥበቃ ሠራተኛው፣ ፖሊሱ፣ ዳኛው፣ ሹፌሩ፣ ፓይለቱ፣ ራዳቱ፣ ነጋዴው ምስክር መኾን ያቃተን? ፍላጎቱ ስለሌለን ነውን? አይደለም፡፡ ፍቅሩ ስለሌለን ነውን? አይደለም፡፡ ግን አልሠለጠንም፡፡
“አይ እዚ ጋር እንኳን ቀይ መስመር አለ” ነው ያለው ቅዱስ ጊዮርጊስ፡፡ “እዚህ ድረስ የአባቴን መንግሥት ለመውሰድ መጥቻለሁ፡፡ ከዚህ በላይ ግን ቀይ መስመር ይሰመራል፡፡” ክርስትና ይኼ ነው የሚፈልገው፤ ከዚህም በላይ፡፡ (ይህን) የሚል ነጋዴ፣ የሚል ባለሥልጣን፣ የሚል ምሁር፣ የሚል ሳይንቲስት ማፍራት የሚቻለው በቤተሰብ ውስጥ በሚሰጥ ትምህርት ነው፡፡ እኛ ቢያልፈን እንኳን፣ ዛሬ ይህን ጽሑፍ የምናነብ ሰዎች አልፎናል ብለን ብንጸጸት እንኳን ብዙዎቻችን ግን እንዳያልፋቸው ማድረግ አያቅተንም፡፡
ከዛ ነው መጀመር ያለበት፡፡ ሕፃናት ላይ ይበልጥ መሠረታችንን መመሥራት ያለብን፡፡ ሕፃናትን ነው ማነፅ ያለብን፡፡ እነርሱ በሚገባ ከተማሩ ጉባኤያት ባይደረግ እንኳን፣ ማይክሮፎን ባይተከል እንኳን፣ አዳራሾች ባይዘጋጁ እንኳን ምንም ጉዳት የለውም፡፡ ምንም ጉዳት የለውም!!!
እስኪ አስቡት! ሰንበቴው፣ ጽዋው፣ የቅዳሴ ሥነ ሥርዓቱ፣ የንግሥ ሥነ ሥርዓቱ ባይኖር ኖሮ በእኛ ስንፍና ምንድን ነበር የምንኾነው? የበእንተ ወንጌል ወይም የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር ለማዘጋጀት ስንት ጊዜ ነው ማስታወቂያ የሚነገረው? ቁልቢ ገብርኤል ለመሔድ ግን ማስታወቂያ ያስፈልጋል? በነሐሴ 24 የአቡነ ተክለ ሃይማኖት ንግሥ ለመሔድ ምንም ማስታወቂያ አያስፈልግም፡፡ መስከረም 21 ላይ ግሸን ለመሔድ ምንም ማስታወቂያ አያስፈልግም፡፡ ባይኾን “በዚህ ቦታ ተመዝገቡ” ለማለት ካልኾነ በስተቀር እንጂ ያን ቀን የግሸን በዓል እንደኾነ ኹሉም ያውቃል፡፡ ይህንን መሠረት ባይመሠርቱና በደማችን ውስጥ ባይተከል ኖሮ በየትኛው ኔትወርክ ነበር የምናመጣው? በየትኛው ማስታወቂያ ነበር ሰውን የምንሰበስበው? በየትኛው አሠራራችን ነበር ይህን የምናመጣው? ይህን ከታች ስለሠሩት ነው፡፡
በኢየሩሳሌም ማለት ይኼ ነው፡፡ ቤተሰብ ውስጥ ባልና ሚስት ሐዋርያ ኾነው ሲያስተምሩ ማለት ነው፡፡ እናትና አባት ለልጆቻቸው ሐዋርያ ሲኾኑ፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ለልጁ ለጢሞቴዎስ በጻፋቸው ኹለቱም መልእክቶቹ እየደጋገመ የሚናገረው ቃል አለ፡፡ የጢሞቴዎስ አያቱንና እናቱን ያነሣል፡፡ “ይህም እመነት ቀድሞ በኤትህ በሎይድ እናትህም በኤውንቄ ነበረባቸው፤ በአንተም ደግሞ እንዳለ ተረድቻለሁ” ብሎታል /2ኛ ጢሞ.1፡5/፡፡ ይኼስ ምንድነው የሚነግረን ቅዱስ ጢሞቴዎስ እንዲሁ የመጣ አይደለም፡፡ አያቱም እናቱም ያስተማሩት ትምህርት፣ በሕይወት አርአያ ኾነው ያሳዩት ሕይወት ነው በልቡ ውስጥ ያለው፡፡
ወላጆች መጾም ያለባቸው ለራሳቸው ብቻ አይደለም፡፡ የሚጾሙ ልጆች ማፍራት ከፈለግን የሚጾሙ ወላጆች መኖር አለባቸው፡፡ ወላጆች ቤት ውስጥ መጸለይ ያለባቸው ለራሳቸው ብቻ አይደለም፡፡ የሚጸልዩ ልጆች ማፍራት ከፈለግን የሚጸልዩ ወላጆች ማፍራት አለብን፡፡ ከዚያ በኋላ ነው ልጆቹ አብረው የሚጾሙት፡፡ ከካህኑ በፊት እናትና አባታቸውን ነዋ ያወቁት! ከሰባኪው በፊት እናትና አባታቸውን ነዋ ያወቁት! ስለዚህ እናታቸው ስትጾም ይጾማሉ፡፡
ለምን ይመስላችኋል ብዙ ወጣቶች 14 እና 15 ዓመት ሲሞላቸው በልጅነታቸው በፍልሰታም በምንም ስናቆርባቸው የነበረውን ቁርባን የሚተዉት? ልጆች ኾነው እናመጣቸዋለን፡፡ 15 ዓመት ሲሞላቸው ግን እምቢ ይላሉ፡፡ ለምን? እኛ ስንቆርብ አላዩማ! ስለዚህ የማደግ ምልክቱ የሚመስላቸው ቁርባንን ማቆም ነው፡፡ ሰው ቁርባን ተወ ማለት አደገ ማለት ነው፡፡ ወላጆቻቸው ስላደጉ ነዋ የማይቆርቡት፡፡ እንደዉም በብዙ ቤተ ክርስቲያን “ቅዳሴ ማለት የማይቆርቡ ወላጆች የሚቆርቡ ልጆች የሚያቆርቡበት ነው፡፡” ወላጆች አይቆርቡም፤ ልጆች ግን ይቆርባሉ፡፡ ቅዳሴው ያልተማረ የሚያስተምርበት፤ ያልቆረበ የሚያቆርብበት ብቸኛ ቦታ ነው፡፡ እየቆረብን ቢኾን እነርሱም አብረው ይመጡና ይቆርቡ ነበር፡፡
ይኼ ነው የመጀመሪያው መሔድ ማለት፡፡ በቤተሰብ ውስጥ ነው መሔድ የሚጀመረው፡፡ ሰው’ኮ ዝም ብሎ ከኾነ ቦታ አይሔድም፡፡ አንድ ሰው ሒድ ቢባል ካለበት ነው የሚነሣው፡፡ መነሻችን ቤተሰብ ስለፈረሰ ነው ትልቁ ችግር፡፡ አሁን መመለስ ያለብን ወደዚህ ነው፡፡ በስብከተ ወንጌል መርሐ ግብር ውስጥ መካተት ያለበት ይኸው ነው፡፡ ይህንን ጽሑፍ የምታነቡ የጽዋ ማኅበራት አላችሁ፤ ጉዞ ማኅበራት ውስጥ ያላችሁ አላችሁ፤ ሰንበቴው ውስጥ ያላችሁ አላችሁ፤ በተለያየ ማኅበራት ውስጥ ያላችሁ ሰዎች አላችሁ፡፡ ይህን ጽሑፍ አንብበን ስንጨርስ ማሰብ ያለብን ቤተሰብ ውስጥስ ምን እንሥራ? የሚል መኾን አለበት፡፡ እናት’ኮ ወደ ጉባኤ ትሔዳለች፤ ልጅ ግን አይሔድም፡፡ ባሎች ለብቻ ይሰበሰባሉ፤ ሚስቶች የሉም፡፡ አባቱ “ገብርኤል ነው” ብሎት ሲሔድ ነው እንጂ የሚያውቀው የት እንደሚሔድ አያውቅም፡፡ ለብቻው ነዋ የሔደው፡፡ እነርሱም ቤት ጽዋው ሲደረግ ለምን እየተደረገ እንደኾነ የሚነግረው ሰው የለም፡፡ እንደዉም ብዙ ልጆች ከቤታቸው ውስጥ የጽዋ መርሐ ግብር ሲደረግ፡- “እንግዶች ስለሚመጡ እንዳትበጠብጡ፤ ከዚህ ከመኝታ ቤት እንዳትወጡ፤ ውጭ ከኾናችሁም እንዳትገቡ፤ ድምጻችሁን እንዳታወጡ” ነው የሚባሉት፡፡ ቁጣው ነው የሚተርፋቸው፡፡ ስለዚህ ሌላ ነገር የተፈጠረ ነው የሚመስላቸው፡፡ “ዛሬ ቅዱስ ገብርኤልን ነው የምዘክረው፡፡ ዛሬ ተክለ ሃይማኖት ነው የምዘክረው፡፡ ዛሬ እመቤታችንን የምዘክርበት ምክንያት ይኼ ነው፡፡ አንተም ስታድግ ከእኔ ቀጥለህ ነው የምትሔደው፡፡ እንዲህ ብታደርጊ እንዲህ ነው” ብሎ የሚነግራቸው ሰው የለም፡፡
የብዙዎቹ በአዲስ አበባ ሰንበቴዎች ላይ የተደረገ ጥናት የሚነግረን ይኼ ነው፡፡ ከአጼ ምንሊክ ጀምሮ የተመሠረቱ ሰንበቴዎች አሉ፡፡ ለምሳሌ ሥላሴ ካቴድራል አጠገብ ያለው የበዓለ ወልድ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ያለው ሰንበቴ ከ100 ዓመት በላይ ኾኖታል፡፡ እነዚህ ሰንበቴዎች ከፊታቸው የተጋረጠው አደጋ ሰንበቴውን የመሠረቱት ወላጆች ልጆቸ እየተተኩ አይደለም፡፡ በረከታቸው ይደርብንና ብጹዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ካልእ ይህን በተመለከተ ያስተማሩት ትልቁ ትምህርት፡- “ወደ ሰንበቴውና ወደ ጽዋው ጠላውን፣ ዳቦውን፣ ቆሎውን ይዛችሁ ስትሔዱ እናንተ አትያዙት፡፡ ጠላውን አንድ ልጅ፣ ዳቦውን አንድ ልጅ፣ቆሎውን አንድ ልጅ ተሸክሞ ይሒድ፡፡ ይግባ፤ ይይ፡፡ ይኼ የአንተ ሰንበቴ ነው፡፡ ነገ ትወርሷለህ በሉት” የሚል ነው፡፡ ይኼን ያደረገ ሰው ስለሌለ የሚወርሰው ታጣ፡፡  
እኛ እንኳን ማንበብ ባንችል መጻሕፍቱን ገዝተንላቸው እንዲያነቡ የማናደርጋቸው ለምንድነው? በውድ ዋጋ ከፍለን ትምህርት ቤቶች ውስጥ የምናስተምራቸው ይኼንን ጭምር እንዲያነቡ አይደለም እንዴ? ፊዚክስና ኬሚስትሪ ብቻ እንዲያነቡ ነውን? ይኼንንም ጭምር እንዲያነቡ’ኮ ነው፡፡ ቆመው ማንበብ መልመድ አለባቸው፡፡ “ዛሬ አንተ ነህ ተረኛ፤ ዛሬ አንቺ ነሽ ተረኛ” ልንላቸው ይገባል፡፡ ኹለት፣ ሦስት ልጆች ባሉበት ቤት “አንተ የቅዱስ ሚካኤልን ትዘክራለህ፤ አንቺ ደግሞ እመቤታችንን ትዘክሪያለሽ፤ አንተ ደግሞ ተክለ ሃይማኖትን ትዘክራለህ፤ እኔ ደግሞ እገሌን እዘክራለሁ” ብለን ተካፍለን ካደረግን ልጆች ከልጅነታቸው አንሥቶ ፍቅረ ቅዱሳን ያድርባቸዋል፡፡ ይጠይቃሉ፡፡ “ለምንድነው በ24 ተክለ ሃይማኖት የኾነው?” ይላሉ፡፡ ይረዳሉ፡፡ “ለምንድነው ግን የቅዱስ ሚካኤል በዓል በ12 የሚውለው?” ይላሉ፡፡ ይረዳሉ፡፡ ማስረዳት ከቻልን ማስረዳት፡፡ ማስረዳት ካልቻልን ደግሞ “ይኼው መጽሐፉ አንብብ፤ እንደውም አንብብና ለኹላችንም ትነግረናለህ” እያልን ልናሳድጋቸው ይገባል፡፡ ሃይማኖታቸውን መመስከር፣ ስለ ቅዱሳን መናገር፣ ስለ ቤተ ክርስቲያን መናገር በእናትና በአባታቸው ፊት ይለምዳሉ፡፡ ነገ ትምህርት ቤት ቢሔዱ፣ ሌላ ትልቅ ቦታም ቢሔዱ ስለ ሃይማኖታቸው በየጉባኤው፣ በየወርክሾፑ፣ በየሚድያው የማይኾን ነገር ሲነገራቸው ዝም አይሉም፡፡ “አይ! እዚህ ጋር ሐሳብ አለኝ፡፡ ይኼ ትክክል አይደለም፡፡ ይኼ ሥርዓት አይደለም፡፡ በእኛ ቤተ ክርስቲያን እንዲህ አይደለም፡፡ አንተ እንደምትለው አይደለም!” ብለው የሚከራከሩ ሰዎች ይኾናሉ፡፡
ይኼ ስለጠፋ ነው ዛሬ ብዙ ቦታ ላይ የቤተ ክርስቲያን ስም ሲጠፋ እንኳን እያወቅነው፣ እየተናደድን፣ ፀጉራችንን እየነጨን ዝም የምንለው፡፡ “እንደው እግዚአብሔር ያሳይህ” እያልን እየረገምን ዝም የምንውለው ለዚሁ ነው፡፡
ኢየሩሳሌም ማለት ግን ይኼ ነው፡፡ በምታውቁት ቦታ፣ ስለ እኔ መናገር በማይቸግራችሁ ቦታ ጀምሩ ማለት ነው፡፡ ለሐዋርያት ከይሁዳ፣ ከሰማርያ፣ ከዓለም ዳርቻ ይልቅ በኢየሩሳሌም መመስከር ቀላል ነበር፡፡ ምስክር አለ፤ ማስረጃ አለ፤ ቦታው እዛው ነው፤ ሌላም ብዙ ምስክር መጥራት ይቻላል፡፡ እኛም በቤተሰባችን ውስጥ መመስከር ቀላል ነው፡፡ እንዲህ በአደባባይ ከመውጣታችን በፊት ከቤተሰባችን ውስጥ ነው ሃይማኖት ገንዘብ መደረግ ያለበት፡፡ ጸሎት እዛ ነው መለመድ ያለበት፡፡ ጾም እዛ ነው መለመድ ያለበት፡፡ ምጽዋቱ’ኮ እዛ ነው መለመድ ያለበት፡፡ በየቤታችን ሙዳዬ ምጽዋት አስቀምጠን ልጆች ከጸሎት በኋላ ገንዘብ እያስቀመጡ፥ ያንን የሙዳዬ ምጽዋት ገንዘብ ይዘው ነው እሑድ ዕለት ወደ ቤተ ክርስቲያን ሲመጡ የሚመጸውቱት፡፡ እንዲህ ከኾነ የሚሰጡ ልጆች እናፈራለን፡፡ እንዲህ ካልኾነ ግን ሙዳዬ ምጽዋትን የሚሰብሩ ልጆችን እናፈራለን፡፡ ከየት ያምጡት ታዲያ? ዛሬ’ኮ “ሙዳዬ ምጽዋት ምንድነው?” ቢባል “ገንዘብ በውስጡ ያለበት፤ ተሰብሮም ያ ገንዘብ የሚወሰድበት፤ እንደዉም ምንዛሪ ያለበት” ነው የሚመስላቸው፡፡ የሚሰጥ ነው የሚለውን እኛ ነን ማስተማር ያለብን፡፡ የጥንት ክርስቲያኖች እንደሚያደርጉት ዐቢይ ጾምና ፍልሰታ ላይ ቤተሰብ የማይጠቀሙበትን ልብስ ይሰበስቡና ኪዳነ ምሕረት በዓል ሲኾን ወይም ደግሞ የትንሣኤ በዓል ከመኾኑ በፊት ወስደው ለነዳያን ይሰጡ ነበር፡፡ ልጆቻችን ይህንን ነው በኢየሩሳሌም ማስተማር ያለብን፡፡ እንዲህ የምናደርግ ከኾነ ለሌላው ማዘን፣ ለሌላው መራራት ለምደው ያድጋሉ፡፡ እንዲህ ዓይነት ልጆች ካፈራን ቤታችን ውስጥ ሳንቲም የሚሰርቅ የሚነካ የለም፤ ቤታችን ውስጥ ርህራሄ ይኖራል፡፡ ይኼ ነው በኢየሩሳሌም የተባለው፡፡ የፈረሰውም ይኼ ነው፡፡
በይሁዳ እንቀጥላለን...    

2015 ጁን 12, ዓርብ

የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ለወንጌል የሰጠቺው ትኩረት፡- በ14ኛው መክዘ ወንጌል መነሻነት ሲዳሰስ


የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ወንጌል ወደ ግእዝ ቋንቋ መተርጎም የጀመረው በአባ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን ዘመን፣ የተጠናቀቀው ደግሞ በተሰዓቱ ቅዱሳን መሆኑን ይገልጣሉ[1]፡፡ እስካሁን በተደረጉት ጥናቶች የተገኘው ጥንታዊው የብራና የግእዝ መጽሐፍም የአባ ገሪማ ወንጌል ነው[2]፡፡ ይኼ ከ4-7 መክዘ ባለው ዘመን ውስጥ የተጻፈውና በአድዋ እንዳ አባ አባ ገሪማ ገዳም የሚገኘው ወንጌል ቤተ ክርስቲያኒቱ ወንጌልን ለመተርጎምና ለማስተማር የሰጠቺውን ጥንታዊ ትኩረት አመልካች ነው፡፡ በ6ኛው መከዘ የተነሣው ቅዱስ ያሬድ የደረሰው ድጓ ብሉይ ኪዳንን ከሐዲስ ኪዳን አስተባብሮ የያዘና ጥንታውያን የክርስቲያን ሊቃውንት (ቄርሎስ፣ አትናቴዎስ፣ ባስልዮስ፣ ዮሐንስ አፈወርቅ፣ ጎርጎርዮስ ዘእንዚናንዙና ዘኑሲስ) የተረጎሙትን ትርጓሜ በውስጡ ይዞ መገኘቱ መጽሐፍ ቅዱሱ ብቻ ሳይሆን ትርጓሜዎቹም በአኩስም የክርስትና ዘመን በሊቃውንቱ እና በሕዝቡ ዘንድ የታወቁና የተሰበኩ እንደነበር ያሳየናል፡፡ 
የእንዳ አባ ገሪማ ወንጌል

ክርስትና ብሔራዊ ሃይማኖት እንዲሆን ያደረጉትና የመጀመሪያዎቹ ኢትዮጵያውያን ክርስቲያን ነገሥታት የሆኑት ኢዛናና ሳይዛና ክርስትና ሲነሡ ‹አብርሃ እና አጽብሐ› ተብለው መጠራታቸው ወንጌልን ኢትዮጵያውያን የተቀበሉት ‹ብርሃናችን፣ ንጋታችን› ነው ብለው መሆኑን ይጠቁማል፡፡ የመጀመሪያውን ጳጳስ ፍሬምናጦስን የሰየሙበት ‹ከሣቴ ብርሃን› የሚለው ስያሜም የወንጌል መሰበክ እንደ ብርሃን መገለጥ ተደርጎ መወሰዱን ያመለክታል፡፡ ‹እኔ የዓለም ብርሃን ነኝ[3]› የሚለውን ቃል ያላወቀ ሕዝብ መቼም  ይህንን ስያሜ አይሰጥም፡፡ ይኼ ስያሜ ከወንጌል ሰባኪነት ጋር የተያያዘ በመሆኑ በዲማና አካባቢዋ ወንጌልን በብርቱ የሰበከው በኪሞስ ‹ተከሥተ ብርሃን› ›ብርሃን ተገለጠ› ተብሎ መጠራቱን ገድለ አቡነ ፊልጶስ ይነግረናል[4]፡፡
  የኢትዮጵያ ነገሥታት በሳንቲሞቻቸው ላይ የመስቀልን ምልክት ካደረጉ የመጀመሪያዎቹ የዓለም ነገሥታት መካከል ናቸው[5]፡፡ በአኩስም በተገኙት ሳንቲሞች በሳንቲሞቻቸው ላይ የመስቀልን ምልክት ያደረጉ ከ17 በላይ የአኩስም ነገሥታት ተገኝተዋል[6]፡፡ ይኼም ክርስትና በኢትዮጵያውያን ውስጥ ቦታ አግኝቶ የዕለት ተዕለት ሕይወት የሆነው ተሰብኮ ሳይውል ሳያድር መሆኑን አመልካች ነው፡፡ እነዚህ ነገሥታት በሳንቲሞቻቸው ላይ ከመስቀል ምልክት በተጨማሪ ስመ እግዚአብሔርን ጽፈዋል፡፡ 
                                                                   የአኩስም ዘመን ሳንቲሞች [7]
የወንጌሉን ሐሳቦች የሚገልጡ ‹ሰላምና ደስታ ለሕዝቡ ይሁን፣ ምሕረትና ሰላም፣ በእግዚአብሔር ጸጋ፣ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን፣ በክርስቶስ ድል የሚያደርግ› የሚሉትን ቃላትም አስጽፈውም ተገኝተዋል[8]፡፡ ምሕረት፣ ሰላም፣ ምስጋና፣ ጸጋ የሚሉት በአብዛኛው በቅዱስ ጳውሎስ መልእክታት ላይ የምናገኛቸው የሐዲስ ኪዳን ትምህርቶች በሳንቲሞቹ ላይ መጻፋቸው የወንጌሉን ስብከትና የስብከቱን ውጤት ያሳያል፡፡ ድል አድራጊነትን ለክርስቶስ መስጠታቸውም ኢየሱስ ክርስቶስን ማወቅና በሕይወት ውስጥ ቦታ መስጠት ከክርስትና መሰበክ ጀምሮ በሀገሪቱ የነበረ እንጂ የ20ኛው መክዘ ግኝት አለመሆኑን ያሳያል፡፡ 
ኢዛና በሦስት ቋንቋዎች ባስጻፈው የድንጋይ ላይ ጽሑፍ ኢየሱስ ክርስቶስን ‹የሰማይ ጌታ› ብሎ ጠርቶ ድሉ በእርሱ ርዳታ መገኘቱን ይገልጥልናል[9]፡፡ ኢዛና በሌላኛው የድንጋይ ላይ ጽሑፉም ‹በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ› ሲል በሥላሴ ላይ ያለውን እምነት ገልጧል[10]፡፡ ይህም አሚነ ሥላሴ በኢትዮጵያውያን ዘንድ የነበረውን ቦታ ይነግረናል[11]፡፡
በዛግዌ ዘመን ወርቃማ ጊዜ ላይ የምናገኘው ቅዱስ ላሊበላ በላስታ ሮሐ የሰማያዊቱንና ምድራዊቱን ኢየሩሳሌም ምሳሌ ሠርቷል፡፡ ይህም ቅዱስ ጳውሎስ በገላትያ መልእክቱ ኢየሩሳሌም ሰማያዊትና ኢየሩሳሌም ምድራዊት በማለት የከፈለው ትምህርት መሠረት ያደረገ መሆኑን አመላካች ነው[12]፡፡ ከሠራቸው ውቅር አብያተ ክርስቲያናት መካከል ‹ቤተ መድኃኔዓለም›፣ ‹ቤተ ዐማኑኤል›፣ ‹ቤተ መስቀል› የወንጌሉ ትምህርት ከሰዎች ኑሮ አልፎ ሥነ ሕንጻ ሲሆን ያሳዩናል፡፡ አንድን ነገር ዐውቆ፣ ያወቀውን አምኖ፣ ያመነውም ተረድቶ፣ በዓይነ ኅሊናም ስሎ ወደ ኪነ ሕንጻ ለመለወጥ ለነገሩ በአእምሮ ውስጥ ጥልቅ ቦታ መስጠትን ይጠይቃል፡፡ የገላትያ ሰዎች ይህንን ሥዕል አጥፍተው ነው በቅዱስ ጳውሎስ የተወቀሱት[13]፡፡ የልደት በዓል በላሊበላ ከጥንት ጀምሮ ያለውን ቦታ ስናይ እነዚህን ሰዎች ክርስቶስን አያውቁትም ብሎ ከመናገር በፊት ዘጠና ዘጠኝ ጊዜ ማሰብ እንደሚገባ ሕያው ምስክር ነው፡፡ 
ኢትዮጵያዊው ሐዋርያ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ከ700 ዓመታት በፊት በደቡብ ኢትዮጵያ ባደረጉት ስብከት ስመ ክርስቶስን ጠርተው ያስተምሩ፣ ሕዝቡም ክርስቶስን አንዲያውቅ ይሰብኩ እንደነበር የሚያስረዳን በገድላቸው ላይ በተጻፈው የደቡብ ስብከታቸው ውስጥ ከ52 ጊዜ በላይ ስመ ክርስቶስን ጠርተው ሲያስተምሩ ማንበባችን ብቻ ሳይሆን በዳሞት መጀመሪያ የተከሉት ቤተ ክርስቲያን በኢየሱስ ስም መሆኑንም ስናይ ነው፡፡ ወደ ሰሜን ለበለጠ ትምህርትና ተጋድሎ በሄዱ ጊዜ ለዐሥር ዓመት ያገለገሉበት ገዳም ሐይቅን የመሠረቱት አባት ‹ኢየሱስ ሞዓ› ተብለው መጠራታቸው የሚነግረንም ነገር አለ፡፡ ከሐይቅ በፊት ቢያንስ 200 ዓመት ቀድሞ የተሠራው ጥንታዊው የአካባቢው ቤተ ክርስቲያንም ‹እግዚአብሔር አብ› መባሉ የምሥጢረ ሥላሴው ትምህርት ሳይቋረጥ የቀጠለ መሆኑን ያሳያል፡፡  
የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ለመጀመሪያ ጊዜ የተጠቀመቺባቸው ሁለቱ ቅዳሴያት ‹ቅዳሴ እግዚእ› እና ‹ቅዳሴ ሐዋርያት› ናቸው[14]፡፡ ይህም ለጌታችን ትምህርትና ለሐዋርያት ስብከት የተሰጠውን ቦታ የሚያሳይ ነው፡፡ ምናልባትም ከውጭ የተተረጎሙት ቅዳሴያት እነዚህ ሁለቱ ብቻ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡
በአኩስም ዘመን ከተተረጎሙት የሃይማኖት መጻሕፍት መካከል አንዱ ነገረ ክርስቶስን የሚተነትነው ‹መጽሐፈ ቄርሎስ› መሆኑ፣ ኢትዮጵያውያን ከውጭ ተርጉመው ከተጠቀሙባቸው የሊቃውንት ጸሎቶች መካከል አንዱ የሆነው የአባ ኤፍሬም ውዳሴ ማርያም ከጠቅላላው ይዘት 63 በመቶው ኢየሱስ ክርስቶስን በተመለከተ ቤተ ክርስቲያን የምታምነውን እምነት መያዙ የሚነግረን ብዙ ነገር አለ፡፡
ከአኩስም ዘመን ጀምሮ ነገራተ ሕዝብ የሚመዘገቡት በወርቅ ወንጌል ነው፡፡ ራሱ ወንጌሉም ‹ወንጌል ዘወርቅ› ተብሎ መጠራቱ የወንጌሉን ቦታ ይገልጣል፡፡ በእንዳ አባ ገሪማ ወንጌል[15]፣ በደብረ ሊባኖስ ዘሺምዛና ወንጌል[16]፣ በጉንዳ ጉንዶ ወንጌል፣ በሐይቅ እስጢፋኖስ ወንጌል[17]፣ በክብራን ወንጌልና በደብረ ሊባኖስ ወንጌል የምናገኛቸው መረጃዎችም ይህንን ያስረግጡልናል፡፡
የክብራን ገብርኤል ወንጌል( British, Ms. 481)
ከክርስትና መግባት ጀምሮ ኢትዮጵያውያን የተጠቀሙበት የዘመን መቁጠሪያ አራቱን ዓመታት በአራቱ ወንጌላውያን ስም መጥራቱና የዐቢይ ጾም ስምንቱ እሑዶች ጌታችን በወንጌል ላይ በሠራቸው ሥራዎች መሠረት መሰየማቸው ወንጌልና የወንጌል ትምህርት ከጥንት ጀምሮ በኢትዮጵያ የያዘውን ጽኑ መሠረት አመልካች ነው፡፡ 
እነዚህ ሁሉ ነገሮች  ወንጌል፣ የወንጌል ትምህርትና የወንጌል መሠረት የሆነው ክርስቶስ በኢትዮጵያውያን ጠቅላላ ሕይወት ውስጥ ከሥጋና ደም ጋር የተዋሐዱ እንጂ እንደ እንግዳ ደራሽ እንደ ውኃ ፈሳሽ አለመሆናቸውን ያጠይቁልናል፡፡
ኢትዮጵያውያን ወንጌሉን በሚገባ አስጽፈውታል፣ ተርጉመውታል፣ ሥለውታል፣ አዚመውታል፣ ኪነ ሕንጻ አድርገውታል፣ ተጠርተውበታል፣ ከዚህም አልፈው መሥዋዕት ሆነውለታል፡፡ ወንጌል በኢትዮጵያ ውስጥ የነበረውን የዕውቀትና የክብር ቦታ ከሚያሳዩን ማስረጃዎች አንዱ ዘመናትን ተሻግረው እኛ እጅ የደረሱት የወንጌል ቅጅዎች ናቸው፡፡ እነዚህ ቅጅዎች በሚገባ የተጻፉ፣ በሐረግ ያሸበረቁ፣ በሥዕል የተገለጡ፣ ትንታኔ የተሰጠባቸው፣ ቀመር የተዘጋጀላቸው፣ ማውጫና ማብራሪያ የተሰጣቸው፣ ወንጌሎቹ በወንጌላውያኑ የተጻፉበትን ቦታና ዘመን የሚያመለክቱ ናቸው፡፡ በዚህ ጽሑፍ በ14ኛው መክዘ የመጀመሪያዎቹ ዓመታት የተጻፈውን የግእዝ ወንጌል መሠረት አድርገን ነገሩን እንዳስሳለን፡፡
አርባዕቱ ወንጌል ዘደብረ ጊዮርጊስ
መጽሐፉ የሚገኘው በዋልተርስ የሥነ ጥበብ ሙዝየም በቁጥር W 836 ተመዝግቦ ነው፡፡ በብዙ ገጾቹ ላይ ውኃ ፈስሶበት ለማንበብ ያስቸግራል፡፡ በአንድ ወቅት በትግራይ ደብረ መዐር የሚገኘው የቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ንብረት የነበረው ይኼ ወንጌል 516 የብራና ቅጠሎች ያሉት ነው፡፡ ወንጌሉ በ1973 እኤአ የሮበርትና ናንሲ ኑተር ገንዘብ ሆነ፡፡ በ1996እኤአ ደግሞ የአልተን ደብሊው ጆንስ ፋውንዴሽን ገዝቶ በሙዝየሙ አስቀመጠው፡፡ ወንጌሉን የጻፈው መጥሬ ክርስቶስ የተባለ ጸሐፊ ሲሆን አባ አርከ ሥሉስ በ18ኛው መክዘ ማርያም ጽኩዕ ለሚባል ደብር እንደሰጡት በማቴዎስ ሥዕል ሥር በጻፉት መግለጫ ይናገራል፡፡ ከዚያ በኋላ እንዴት የደብረ መዐር ጊዮርጊስ ንብረት እንደሆነ እንዴትም ከሀገር እንደወጣ አላወቅኩም፡፡
   
የወንጌሉ መግቢያ
                                                                 
መልእክተ አውሳብዮስ
አውሳብዮስ የታወቀውን የቤተ ክርስቲያን ታሪክ መጽሐፍ Ecclesiastical History የጻፈ አባት ነው፡፡ በዚህ ወንጌል ላይ አውሳብዮስ ቀርጲያኖስ ለተባለ ሰው አርባዕቱ ወንጌልን በተመለከተ የጻፈው ደብዳቤ ይገኛል፡፡ በደብዳቤው ላይ እንደተገለጠው አሞንስ አሌክሳንድራዊ የሠራውን የወንጌላት ቀመር ሰድዶለታል፡፡ አውሳብዮስም ለቀርጲያኖስ በዚህ ደብዳቤ ይገልጥለታል፡፡

የአውሳብዮስ ደብዳቤ
                                                                        

(1)አራቱ ወንጌላውያን የሚተባበሩበትን፣
(2)ማቴዎስ፣ ማርቆስና ሉቃስ የሚተባበሩበትን፣
(3)ማቴዎስ ሉቃስ ዮሐንስ የሚተባበሩበትን፣
(4)ማቴዎስ ማርቆስ ዮሐንስ የሚተባበሩበትን፣
 (5)ማቴዎስና ሉቃስ የሚተባበሩበትን፣
(6)ማቴዎስና ማርቆስ የሚተባበሩበትን፣
(7)ማቴዎስና ዮሐንስ የሚተባበሩበትን፣
(8)ሉቃስና ማርቆስ የሚተባበሩበትን
(9) ሉቃስና ዮሐንስ የሚተባበሩበትን
(10) አራቱንም በየራሳቸው ያላቸውን
ሠለስቱ ወንጌላት(ማቴዎስ፣ ማርቆስ፣ ሉቃስ) የሚተባበሩበት

ይኼ ቀመር ከጥንት ጀምሮ የቅዱሳት መጻሕፍት ጥናት በቤተ ክርስቲያናችን ይሰጥ እንደነበረ ያመለክታል፡፡ አራቱን ወንጌላውያን በየራሳቸው በትርጓሜ ከማጥናት ባለፈ አራቱ የሚገናኙበትንና የሚለያዩበትን እየተነተኑ በቀመር ማጥናቱ ለምን ተለዩ? የሚል ጥያቄ በአጥኝዎቹ ዘንድ ተነሥቶ እንደነበረ ያሳያል፡፡ ጥያቄውን ለመመለስ ሊቃውንቱ የደከሙትን ድካምም በየትርጓሜው ውስጥ የምናየው ነው፡፡ ‹ማቴዎስ እንዲህ አለ፤ ማርቆስም እንዲህ ብሏል፣ ሉቃስም እንዲህ ይላል፣ እንደምን ነው ቢሉ› የሚለው ዓይነት፡፡
ይህ ቀመር በመልእክተ አውሳብዮስ እንደተገለጠው የሚለያዩበትንና የሚገናኙበትን ለማጥናት ብቻ ሳይሆን አንዱን የወንጌል ታሪክ በተመለከተ በአራቱም ወንጌላውያን ያለውን ሐሳብ ለማየት የሚያገለግል፣ ከዚህም በላይ የወንጌሉን ልዩ ልዩ ክፍሎች በየታሪካቸው ዘውግ ለማጥናትና በቃል ለመያዝም የሚያስችል ነው፡፡
አርእስት
በአራቱም ወንጌሎች ላይ በየአንዳንዱ ምእራፍ ምን ምን ይዘት እንዳለ የሚያሳይ ርእስ አላቸው ፡፡ ርእሱ የሚጻፈው በላይኛው የብራናው ኅዳግ ላይ ሲሆን በርእሱ የተገለጠው የመጽሐፉ ክፍል የሚጀምርበት ቦታ ልዩ ምልክት በቀይ ቀለም ተደርጎበታል፡፡ ምልክቱ በሥዕሉ ላይ እንደምናየው ከላይ ቀለበት ያለው ወራጅ መሥመር ይደረግና መሐል ወገቡ ላይ የX ምልክት ይደረጋል፡፡ ይህም ወንጌሉን በጉዳይ በጉዳይ ከፋፍሎ የመማርና የማስተማር ባሕል እንደነበረ ያሳያል፡፡
  የአርእስት አሰጣጥ
   እንስሳት
በወንጌሉ ውስጥ የወንጌሉን ሐሳብ የሚገልጡ የእንስሳት ሥዕሎች አሉ፡፡ የመጀመሪያዋ ፒኮክ ወፍ ናት፡፡ የፒኮክ ወፍ በጥንት ክርስቲያኖች ዘንድ ትንሣኤ ሙታንን የምታመለክት ነበረች፡፡ ሌላዋ ደግሞ ጳልቃን ወይም ፔሊካን ተብላ የምትጠራው ስትሆን እርሷም ዛሬም ድረስ በትርጓሜያችን እንደሚነገረው የትንሣኤ ሙታን ምሳሌ ናት፡፡ ሌላም አንድ ወፍ አለች፡፡ ማን እንደሆነችና ትርጉሟንም ለማወቅ አልቻልኩም፡፡ ሌላዋ ሰጎን ናት፡፡ ሰጎን የክርስቲያኖችና የመንፈስ ቅዱስን ግንኙነት ለማሳየት የምትመሰል ወፍ ናት፡፡ ከወፎች በተለየ የምናገኘው እንስሳ በግ ነው፡፤ እርሱም የታረደው የክርስቶስ ምሳሌ ነው[18]፡፡
በመጽሐፉ ውስጥ ካሉት ወፎች(ፒኮክ)
                                                 
     ሰጎን

                                                                           
ምልክቶች
ከላይ ካየነው የ‹ቶ›[19] መሰል ምልክት በተጨማሪ ትምህርቱን፣ ተግሣጹን፣ ተአምሩን ለማመልከት ልዩ ልዩ ምልክቶችን ማድረጉን አውሳብዮስ ይገልጣል፡፡ በመጽሐፉም ውስጥ ያንን በመከተል በግራና በቀኝ በሚገኙ ኅዳጎች ላይ ምልክቶች ይገኛሉ፡፡ ከዚህም በተጨማሪ በአውሳብዮስ ቀመር ላይ ለእያንዳንዱ ቀመር የተሰጠው ቁጥር በወንጌሉ ውስጥም  በሚገኙበት በሚገኙበት ቦታ በቀይ ቀለም ቁጥሩ በግእዝ ተጽፏል፡፤ ይህም የወንጌላቱን ጥናት የሚያቀል ነው፡፡
  
አዲሱ ርእስ የሚጀምርበት የ‹ቶ› መሰል ምልክት
                                                  
    ሥዕል
በያንዳንዱ ወንጌላዊ መግቢያ ላይ የወንጌላዊው ሥዕል አለ፡፡
ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃስ
                                                                   

የማቴዎስ ወንጌል ከመጀመሩ በፊት ደግሞ የጌታችንን ሥነ ስቅለት(በጉ ከመስቀሉ በላይ ይታያል)[20] የሚያሳይ ጥንታዊ ሥዕል፣
 
   የሥነ ስቅለቱ ሥዕል፣ ክርስቶስ በበግ መስለውት
                                                     

 የጌታችንን ትንሣኤ የሚያሳይ ሥዕል(በሁለት ሴቶች መካከል ሆኖ)፣
የጌታ ትንሣ፣ ቅዱሳት አንስት ግራና ቀኝ
የጌታችን ዕርገትና በዙፋኑ ላይ መቀመጥን የሚያሳዩ ሥዕሎች አሉ፡፡ 
 ጌታችን ዐርጎ በዙፋኑ ሲቀመጥ
ከዚህም በተጨማሪ ጸሐፊው የአርባዕቱን ወንጌል ኅብረት በዲያግራም ገልጦታል፡፡ 
 
 የአርባዕቱ ወንጌልን አንድነት ለመግለጥ የተሳለ ዲያግራም
የመጻሕፍቱ ክፍሎች ማውጫ
ከማርቆስ ወንጌል ጀምሮ የመጻፍቱን ልዩ ልዩ አርዕስት ለማውጣት የሚያስችል ማውጫ ተዘጋጅቶላቸዋል፡፡ ማውጫዎቹ የመጽሐፉን ገጽ የሚጠቀሙ ሳይሆኑ ጉዳዩንና ቅደም ተከተሉን ብቻ የሚያሳዩ ናቸው፡፡
የማቴዎስ ወንጌል ማውጫ

መሥፈርና መቁጠር
ወንጌሉ የእያንዳንዱን ወንጌላውያን አርእስተ ነገር ቆጥሮና ሠፍሮ ያስቀምጣል፡፡ በዚህ መሠረት
ጠቅላላ የወንጌላውያኑ አርእስተ ነገር 218 ሲሆን
ማቴዎስ 68
ማርቆስ 48
ሉቃስ 83
ዮሐንስ 19
እንዳላቸው ያትታል፡፡ ጠቅላላ ቃሎቻቸውም 90 ሺ 700 (፺፻፯፻) መሆናቸውን ይናገራል፡፡ ይህም ነገር የወንጌሉ ጥናት ከ600 ዓመታት በፊት የደረሰበትን ደረጃ የሚገልጥ ነው፡፡
 
የማርቆስ ወንጌልን የአርእስት ቁጥር የሚያሳይ መረጃ
ማጠቃለያ
ከላይ ያየናቸውን ነጥቦች ስንመረምራቸው የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ለወንጌለ ክርስቶስ ትምህርትና ጥናት የነበራትን ዋጋ፣ ከዚህም በላይ ለወንጌሉ ጌታ ለኢየሱስ ክርስቶስ ያላትንም ቦታ የሚያሳይ ታሪካዊ መረጃ ነው፡፡ ወንጌሉን ይህንን ያህል ሠፍሮና ቀጥሮ፣ ተንትኖና አፍታቶ ለማወቅ የተፈለገውም የሚያስገኘው ምድራዊ ጥቅም ኑሮ አልነበረም፡፡ ክርስቶስን ዐውቆ በክርስቶስ መንገድ ለመኖር ስለተፈለገ እንጂ፡፡ ቤተ ክርስቲያኒቱ ያፈራቻቸው ቅዱሳንም ይህንን በመሰለው የወንጌል ትምህርት ታንጸውና በስለው የወጡ እንደነበሩ የ13ኛው መክዘን የሐይቅ እስጢፋኖስ ወንጌል ከአቡነ ተክለ ሃይማኖት ታሪክ ጋር፣ የደብረ መጣዕን ወንጌል ከአባ ሊባኖስ ታሪክ ጋር፣ የክብራንን ወንጌል ከአባ ዘዮሐንስ ታሪክ ጋር፣ አያይዞ ማሰብ ይቻላል፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ ይህቺን ቤተ ክርስቲያን ወንጌል አልሰበከችም፣ ክርስቶስንም አታውቀውም ብሎ እንደመናገር ያለ ከባድ ኃጢአት ሊኖር አይችልም፡፡

                                   በአውሮጳ   የካህናት አንድነት ማኅበር ሊቋቋም መሆኑ ታወቀ በ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከመላዋ አውሮጳ   የተውጣጡ ካህናት፡” የ...