2014 ኖቬምበር 14, ዓርብ

የማያለቅስ ልጅ


ፎቶ - ሐራ ተዋሕዶ

ቅዱስ ሲኖዶስ የቤተ ክርስቲያንን ሕግ በተመለከተ አሠረ ሐዋርያትን የተከተለ ሆኖ እንዲጸድቅ አድርጓል፡፡ አባቶቻችን በቤተ ክርስቲያን ላይ ግለሰባዊ አምባገነንነትን አልፈቀዱም፡፡ ጸሎተ ሃይማኖቱም ‹ነአምን በአሐቲ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እንተ ላዕለ ኩሉ ጉባኤ ዘሐዋርያት›› በማት ቤተ ክርስቲያን ጉባኤ ዘሐዋርያት መሆንዋን ያመለክታል፡፡ በ50/51 ዓም በኢየሩሳሌም የተሰበሰበችው ሲኖዶስም ‹እኛና መንፈስ ቅዱስ› አለች እንጂ  ‹እኔ› የሚል ግለሰባዊ ድምጽ አልተሰማባትም፡፡
ኢትዮጵያውያን አበው የቅዱስ ሲኖዶስን ሥርዓት ብቻ ሳይሆን ሌሎችን የቤተ ክርስቲያን የአመራር ሥርዓቶች ከግለሰብ አምባገነንነት ለማውጣት መልካም የሆነ ሥርዓት ሠርተዋል፡፡ ቅዳሴው በአምስት ልዑካን እንዲሆን፣ አጥቢያው በሰበካ ጉባኤ እንዲመራ፣ ገዳማት በምርፋቅ (ጉባኤ አበው) ወይም በማኅበር እንዲመሩ፣ ጵጵስናን አንድ ጳጳስ (ፓትርያርክ እንኳን ቢሆን) ብቻውን እንዳይሰጥ፣ ቢያንስ ሦስት አበው ሊኖሩ እንደሚገባ፤ አንድ አባት ብቻውን ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን እንዳይለውጥ፤ አድርገው የሠሩበት አንዱ ምክንያት ግለሰባዊ አምባገነንነትን ለመቋቋም እንዲቻል ነው፡፡

ይህንን ማኅበራዊና ጉባኤያዊ የሆነ የቤተ ክርስቲያን አሠራርና አመራር ለማስወገድ በየዘመናቱ ጥረት ተደርጓል፡፡ የዚህም ምክያቱ ግልጽ ነው፡፡ ግለሰባዊ የሆነ አመራር ለሦስት ነገሮች የተጋለጠ ነውና፡፡ የመጀመሪያው ክህደትንና ኑፋቄን ለማስገባት ይመቻል፡፡ አንዱ ወሳኝ ሌላው ‹ኦሆ በሃሊ› ስለሚሆን እርሱ ትክክል ነው ያለው ትክክል፣ ስሕተት ነው ያለው ደግሞ ስሕተት ይሆናል፡፡ ቤተ ክርስቲያን ጉባኤያዊት በመሆንዋ አንዳንድ ግለሰቦች በየዘመናቱ ያመጡትን ክህደት በጉባኤ ተመልክታ በጉባኤ ለማውገዝ ጠቅሟታል፡፡ ደገኛ ትምርትና ድርሰት ሲገኝ ደግሞ እንዲሁ በጉባኤ ተመልክታ ለመቀበል ረድቷታል፡፡ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ መጽሐፈ ምሥጢርን ጽፎ በጨረሰ ጊዜ ጉባ ሊቃውንቱ ተመልክተው ‹አማንኬ ዮሐንስ አፈወርቅ ወቄርሎስ አፈ በረከት ተንሥኡ በመዋዕሊነ፡፤ ኢትዮጵያ ተመሰለት በቁስጥንጥንያ፤ ወተአረየታ ላዕለ እስክንድርያ - በእውነት ዮሐንስ አፈወርቅና አፈ በረከት የሆነው ቄርሎስ በዘመናችን ተነሥተዋ፡፡ ኢትዮጵያም ቁስጥንጥንያን መስላለች፤ ከእስክንድርያም ልቃ ከፍ ከፍ ብላለች›› ብለው ምስክርነታቸውን ሰጥተው ነበር፡፡
ሁለተኛው ደግሞ ለሌሎች አካላት ቁጥጥር ስለሚመች ነው፡፡ ጌታችን አስቀድሞ ኃይለኛውን ማሠር እንዳለው መሪውን የያዘ ቤተ ክርስቲያኒቱን አን ልቡ ለመዘወር ይመቸዋል፡፡
ይኼ ነገር በዘመነ ሱስንዮስ ጊዜ ታይቷል፡፡ ሮማውያን ግብጻዊውን ጳጳስ በሮማዊ ጳጳስ በመተካት ቤተ ክርስቲያኒቱን በሮማዊ ጳጳስ ለማስመራትና ለመቆጣጠር ፈልገው ነበር፡፡ ነገር ግን የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ጠባይ ማኅበራዊና ጉባኤያዊ በመሆኑ ጉባኤ ሊቃውንቱ ከግብጹ ጳጳስ ጋር ሆኖ ተቃወማቸው፡፡ ጳጳሱና ሊቃውንቱም እስከ ደም ማፍሰስ ድረስ መሥዋዕት ሆኑ፡፡ ጥቅምት 19 ቀን 1621 ዓም በምዕራብ ጎጃም በምትገኘው ደብረ መዊዕ የተሰበሰቡት የቤተ ክርስቲያን ማኅበርተኞች ለዚህ ማስረጃ ናቸው፡፡ በዚህ የደብረ መዊዕ ጉባኤ እስከ 7000 የሚደርሱ ምእመናን፣ ካህናት፣ መነኮሳትና ሊቃውንት ተሰባስበው ነበር፡፡ የጉባኤው መሪዎችም እነ አባ ተስፋ ኢየሱስ፣ አባ ዘጊዮርጊስ ዘዋሸራ፣ አባ እንጦንዮስ፣ አባ ግርማ ሥሉስ ዘውይት ነበሩ፡፡ የጉባኤው አፈ ጉባኤ ደግሞ አባ ግርማ ሥሉስ ነበሩ፡፡በዚህ ጉባኤ የተገኙት ሁሉ ንጉሡንና አዲሶቹን ሮማውያን የሃይማኖት መሪዎች ተቃውመው እንደ አንድ ልብ መክረው እንደ አንድ ቃል ተናግረው በተዋሕዶ ጸኑ፡፡ የንጉሥ ሱስንዮስም ጦር ጥቅምት 19 ቀን ከብቦ ፈጃቸው፡፡ 
እነዚህ ጽኑአን ጉባኤተኞች ነበሩ በኋላ ዐፄ ሱስንዮስ ሐሳባቸውን እንዲቀይሩና ‹ፋሲል ይንገሥ፣ ሃይማኖት ይመለስ› እንዲሉ ያደረጋቸው፡፡ ቤተ ክርስቲያን እንደ መኪና መሪውን የያዘ መኪናውን ወደ ፈለገው ሊወስደው የሚችልባት ቦታ ብትሆን ኖሮ ዘመነ ሱስንዮስን መሻገር ባልቻለች ነበር፡፡ 
ሦስተኛው ምክንያት ደግሞ ዘመን የፈቀደለት ሁሉ ልቡ የወደደውን በቤተ ክርስቲያን ላይ እንዳይጭን ነው፡፡ በተለያዩ ዘመናት የተነሡ መንግሥታት ለራሳቸው የሚመቻቸው መሪ በቤተ ክርስቲያን ላይ ለማስቀመጥ ሞክረው ነበር፡፡ የቤተ ከርስቲያን አሠራር፣ ሕግና ሥርዓት ግን በአንድ ሰው የሚዘወር ባለመሆኑ ገመዱን ከመበጣጠስ ያለፈ ጀነሬተሩን ማቋረጥ አልተቻላቸውም፡፡ የቤተ ክርስቲያን ውሳኔዎችም በጉባኤ እንጂ በአንድ ሰው ኅሊና ብቻ የሚወሰኑ ባለመሆናቸው አስተዳደራዊ ጥቅም ከማግኘትና በደል ከማድረስ ባለፈ አጥንቷን ለመስበር ዐቅም አላገኙም፡፡ 
ይህንን ታሪካዊና ቤተ ክርስቲያናዊ ሐሳብ ጠንቅቆ በመረዳት የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ቤተ ክርስቲያኒቱን ወደ ግለሰባዊ አምባገነንነት የሚወስደውን  መንገድ በማረም የቤተ ክርስቲያኒቱ ራስ ክርስቶስ፣ የቤተ ክርስቲያኒቱም የበላይ ወሳኝ አካል ቅዱስ ሲኖዶስ መሆኑን በሕገ ቤተ ክርስቲያን አጽንቶታል፡፡ 
የሀገራችን ሰው ሲተርት ‹የማያለቅስ ልጅ በእናቱ ጀርባ ይሞታል› ይላል፡፡ ይራበው አይራበው፣ ይታፈን አይታፈን፣ ይመመው አይመመው፣ ይመቸው አይመቸው አይታወቅምና፡፡ ምናልባትም ዝምታው እንደ ጨዋነት ታስቦለት ዘወር ብሎ የሚያየው ላይኖርም ይችላል፡፡ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት በቤተ ክርስቲያን ላይ፣ በቅዱስ ሲኖዶስ ላይና በሊቃነ ጳጳሳት መብት ላይ፣ ቤተ ክርስቲያንን ሊያገለግሉ በተነሡ ማኅበራትና ወጣቶች ላይ፣ በየገጠሩ በተሠማሩና የመከራ ገፈት በሚቀምሱ ካህናትና ምእመናን ላይ የሚደርሰውን በደልና ጫና እየሰሙና እያዩ ዝም ቢሉ በእናታቸው ጀርባ ላይ ሆነው መሞታቸው የማይቀር ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያኒቱን መብት ለማስከበር ደግሞ አስቀድሞ የቅዱስ ሲኖዶሱ መብት መከበር አለበት፡፡ ያልቆመ አንገት ራስን አይሸከምም እንዲሉ፡፡
የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት አንድ ሆነው የቅዱስ ሲኖዶሱን መብት እንዳስጠበቁትና ቤተ ክርስቲያኒቱንም ከግለሰብ አገዛዝ እንደታደጓት ሁሉ በአጠቃላይ የሰበካ ጉባኤውና በቅዱስ ሲኖዶሱ ጉባኤ የቀረቡትን በቤተ ክርስቲያን ላይ እየደረሱ ያሉ ችግሮችን አንድ ሆነው ለመፍታት በቀጣይ  መነሣት አለባቸው፡                                                                                                           

2014 ኖቬምበር 6, ሐሙስ

አሁን እንኳን እንንቃ! . . የተሐድሶ መናፍቃን ስውር ሴራ (VCD No 2)

  • «ኦርቶዶክስ እውነተኛ ቤተ ክርስቲያን ነበረች፤ ነገር ግን የተጫኑባት ገለባዎች አሉ፡፡ ስለዚህ ተሐድሶ ያስፈልጋታል፤ የጥንቷን ቤተ ክርስቲያን መመለስ አለብን»
  • «የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ስሕተት ናት፤ ትክክል አይደለችም»
  • ባለአደራዎች የሆኑ ብፁዓን አባቶቻችን ዛሬም ታላቅ ሓላፊነት አለባቸው፡፡ የተሐድሶ እንቅስቃሴ አንዱ ስልት በአባቶችና በልጆች መካከል መለያየትን መዝራት እንደሆነ ልብ ሊሉት ይገባል
  • የተሐድሶ ኑፋቄው ያልተቋረጠ ጥቃት ዋነኛ ዓላማ፤ ምእመናንን ከእናት ቤተ ክርስቲያን እቅፍ በማስኰብለል የበግ ለምድ ለለበሰ ተኩላ አሳልፎ መስጠት ነው
ውድ የቤተክርስቲያን የስስት ልጆች ሆይ፤ ከዚህ በፊት በተደጋጋሚ እንደተነገረው ቤተክርስቲያናችንን ለመውረስ ረቀቅ ያለ ዘዴ ቀይሰው እየተንቀሳቀሱ ያሉት መናፍቃን የእኛው በሆኑ ግን ለሆዳቸው ባደሩ ጥቂት የማይባሉ ባንዳዎች ሰርገው በመግባት በርካታ ጥፋት እያደረሱ ይገኛሉ፡፡ ይህ ሲነቃባቸውም “ተሀድሶ የለም” እያሉ የዋሁን ህዝብ ሊያታልሉ ይሞክራሉ፤ ስለዚህ እኛ ልጆቿ ልጅነታችንን በምግባራችን ልናረጋግጥና በቃችሁ ብለን ልናስቆማቸው ይገባል፡፡ ይህ ቪድዮ እውነታውን አውቀን እንድንጠነቀቅ በማህበረ ቅዱሳን የተዘጋጀና 4 ክፍሎች ያሉት ሲሆን በመመልከትና ላላዩት እንዲያዩት share በማድረግ እናታችን የምትጠብቅብንን ሀላፊነት እንድንወጣ የእግዚአብሔር ቸርነት፣ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት፣ የቅዱሳን ጸሎት አይለየን፡፡

ስለ ቤተክርስቲያን ካሰቡ ያንቡት ምስሉንም ይመልከቱና የራስዎን ሃላፊነት ብቻ ይወጡ

የተሐድሶ መናፍቃን ስውር ሴራ ክፍል 1

(ስምዐ ጽድቅ ሚያዝያ 1-15 2003 ዓ.ም)  የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ያሳለፈቻቸው ዘመናት ሁሉ አልጋ በአልጋ አልነበሩም፡፡ ሐዋርያዊ ተልእኮዋን ለማሳካት ዘርፈ ብዙ መንፈሳዊ አገልግሎቷን በመፈጸም ያለፈችባቸው ዘመናት በፈተናዎች የታጀቡ ናቸው፡፡ የፈተናው ዓይነትና መጠን፣ ጠባይና መገለጫው እንደየጊዜና ሁኔታው እየተፈራረቀባት፤ በቅዱሳን ሰማዕትነት፣ በሊቃውንት መምህራኗ፣ በአባቶች ካህናቷ፣ በአገልጋዮቿ ተጋድሎ ልጆቿ እየተጠብቁ በመሠረቷ ጸንታ ትገኛለች፡፡

የተሐድሶ መናፍቃን ስውር ሴራ ክፍል 2



የተሐድሶ መናፍቃን ስውር ሴራ ክፍል 3


የተሐድሶ መናፍቃን ስውር ሴራ ክፍል 4





አጽራረ ቤተ ክርስቲያን የሚያደርሱባት ጥቃት ግፊትና ተፅዕኖ አሁንም ሌላው ፈተና ነው፡፡ ከዚህ ቀደም «የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ስሕተት ናት፤ ትክክል አይደለችም» በማለት ከውጪ ሆነው ምእመናንን በማጠራጠርና ግራ በማጋባት ሲያስኰበልሉ የነበረው ጥረታቸው እንዳልተሳካ ተረዱት፡፡ ስለዚህ ቤተክርስቲያኒቷን ሙሉ በሙሉ ለማዳከምና ሐዋርያዊ ተልእኮዋም ተደናቅፎ ሕልውናዋን ለማሳጣት ለዘመናት የደከሙት ድካም ከግብ እንዳልደረሰ ሲገነዘቡት የተለየ ስልት ቀይሰው እየተንቀሳቀሱ ነው፡፡

ትምህርተ ሃይማኖቷ እምነቷና ሥርዐቷ ምሉዕ የሆነውን ቅድስት ቤተ ክርስቲያን፤ ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ርትዕት ሃይማኖት «እናድሳለን» በሚል ስልት ወደ ውስጧ ሠርጐ በመግባት ልጆቿን እስከ ሕንፃ ቤተክርስቲያኗ እንረከባለን ይላሉ፡፡

የበግ ለምድ የለበሱ ተኩላዎቻቸውን በማሰማራት በጎቿን በኑፋቄያቸው እያሳሳቱ ከመንጠቅ፣ በተለያዩ ርዳታዎች ስም እየደለሉ ከማስኰብለል ጀምሮ፤ ትምህርተ ሃይማኖትና ሥርዐቷን በማጣጣል፣ ቅዱሳት መጻሕፍቷን በማራከስ፣ መልካም ስምና ገጽታዋን በማጠልሸት የሚያደርጉት የጥፋት ጥረታቸው ዛሬም እንደቀጠለ ነው፡፡ በእናትነት እቅፏ ውስጥ ጡቷን ጠብተው ማዕዷን ተሳትፈው አድገው፤ ነገር ግን ንጹሕ እናትነቷን ክደው በውስጧ ሆነው በኑፋቄያቸው የሚቦረቡሯት ብዙዎች ናቸው፡፡

የተሐድሶ መናፍቃኑ እንቅስቃሴ፤ ቤተ ክርስቲያንን ለመለወጥ ወራጁ ውኃ ላይ ሳይሆን ምንጩ ላይ መሥራት ነው፤ በሚል ስልት፤ ምንጮች ናቸው የሚሉትን በመለየት ስስ ብልቶች ያሏቸውን መርጠው እየሠሩ ነው፡፡ በእነርሱ አባባል፤ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ወራጁ ውኃ ምእመናን ሕዝበ ክርስቲያኑ፤ ምንጮች ደግሞ፤ ሐዋርያዊ ተልእኮዋን ለማሳካት የዘርፈ ብዙ መንፈሳዊ አገልግሎቶቿ መሠረቶች የሆኑት፤ ገዳማትና አድባራቷ፣ የሊቃውንቷ፣ አገልጋይ ካህናቷና መምህራነ ወንጌሏ መፍለቂያዎች የሆኑት አብነት ትምህርት ቤቶች፣ መንፈሳዊ ኰሌጆቿ፣ የካህናት ማሠልጠኛዎቿ፣ መምህራኑና ደቀመዛሙርቱ፣ በየደረጃው የሚገኘው የቤተክህነት አስተዳደር ነው፡፡ ሰንበት ት/ቤቶች፣ መንፈሳውያን ማኅበራትና ጽዋ ማኅበራት ሁሉ የዚህ ስልታቸው ማስፈጸሚያ ዒላማዎቻቸው ናቸው፡፡

በእነዚህ ምንጮች ውስጥ ኦርቶዶክሳዊ መስለው ሠርገው እየገቡ፣ ለቤተ ክርስቲያን ተቆርቋሪ ሆነው በመታየት፣ በመዋቅሯ ውስጥ ቦታ እየያዙ የተሠወረ ሤራቸውን በስልት ለማስፈጸም ጥረት እያደረጉ ነው፡፡ ቀስ በቀስ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ሥርዐት፣ መዋቅራዊ አሠራርና መመሪያ እየጣሱ የትምህርት ጉባኤያቱን ኦርቶዶክሳዊ ላህይና ይዘታቸውን እየቀየሩ ነው፡፡ ከዚህ ቀደም በዐደባባይ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን «አሮጊቷ ሣራ መታደስ መለወጥ አለባት» እያሉ ሲያውኳት እንዳልቆዩና ለይቶላቸው እንዳልወጡ ሁሉ፤ አሁን ደግሞ በውስጧ ሆነው ተቆርቋሪ መስለው፤ «ኦርቶዶክስ እውነተኛ ቤተ ክርስቲያን ነበረች፤ ነገር ግን የተጫኑባት ገለባዎች አሉ፡፡ ስለዚህ ተሐድሶ ያስፈልጋታል፤ የጥንቷን ቤተ ክርስቲያን መመለስ አለብን» እያሉ በ«ምናለበት» ስብከት እየደለሉ በማታለል ለሃይማኖቱ ግድ የለሽ ምእመን ለመፍጠር ይተጋሉ፡፡

ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ የባሕርይ አምላክነት፣ ነገረ ማርያም፣ ነገረ ቅዱሳን፣ ጾም፣ ጸሎት፣ ስግደት... ወዘተ እንዲነሣባቸው አይፈልጉም፡፡ ስለ እነዚህ ጉዳዮች ማስተማር ለሕይወት የማይጠቅም እንደሆነ በመቀስቀስ ከምእመናን ዘንድ ማስረሳትና ሳያውቀው ለተሐድሶ ኑፋቄ ቅሰጣና የስሕተት ትምህርት ልቡን በመስጠት ተገዢ የሆነ ትውልድ መፍጠር በገሀድ የሚታይ ጥረታቸው አካል ነው፡፡

ሕዝበ ክርስቲያኑ በአባቶቹ ላይ ያለው እምነትና ተስፋ እንዲሸረሸር፣ አሠረ ክህነቱን፣ ሥርዐተ ምንኩስናን፣ የቤተክርስቲያኒቱን አስተዳደር እንዲጠላ በዚያው ተገፍቶ ጭራሹን ከቤተ ክርስቲያን እቅፍ እንዲወጣ ወይም እንዲኰበልል ለማድረግ የተለያዩ ዘዴዎችን እየተጠቀሙ ይሠራሉ፡፡

የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ትምህርተ ሃይማኖት፤ የዶግማና ሥርዐቷን ድንበር ለማጥፋት፤ መዋቅራዊ የአሠራር ሥርዐቷንና መመሪያዋን በድፍረት እስከመጣስ እየደረሱ ይታያል፡፡ እነዚህን ሁሉ የስሕተት ትምህርቶቻቸውን ለማሠራጨት፤ አድራሻና ባለቤት በሌላቸው የኅትመት ውጤቶች፤ መጻሕፍት፣ በራሪ ወረቀቶች ፣ የድምፅ ወይም የምስል ወድምፅ ካሴቶች ጭምር ይጠቀማሉ፡፡

ይህ የተሐድሶ ኑፋቄ እንቅስቃሴ ከግለሰብ ወደ ቡድን፣ ከቡድን ወደ ማኅበር ወይም ድርጅት ከዚያም ወደ ብዙ ድርጅቶች እያደገ መጥቷል፡፡ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ሐዋርያዊ ተልእኮ ለማደናቀፍና መንፈሳዊ አገልግሎቷን በማወክ ልጆቿንም ለማስኰብለል የሚደረገው ርብርብ ከፍተኛ ነው፡፡

በሕገ መንግሥታዊው ሥርዐታችን አንድ ዜጋ የፈለገውን እምነት የመከተል መብቱ የተረጋገጠ ነው፡፡ ሆኖም በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ስም እና ሽፋን በውስጧ ሆኖ እምነቷን፣ ሥርዐትና ትውፊቷን መጣስ እንዲሁም ከመመሪያዋ ውጪ መንፈሳዊ አገልግሎቷን ማወክ፣ ምእመናኗን እያሳሳቱ ማስኰብለል ሕጋዊ ተግባር እንዳልሆነ ሁሉም የሚገነዘበው ጉዳይ ነው፡፡ ስለዚህ የተሐድሶ ኑፋቄን ሤራ ምንነትና ሊያስከትል የሚችለውን ጥፋት በትክክል መረዳት ያስፈልጋል፡፡

በክርስቶስ ደም ተመሥርታ በእግዚአብሔር ቸርነት በቀደሙት ቅዱሳን አባቶች መንፈሳዊ ተጋድሎ እዚህ የደረሰች ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ባለአደራዎች የሆኑ ብፁዓን አባቶቻችን ዛሬም ታላቅ ሓላፊነት አለባቸው፡፡ የተሐድሶ እንቅስቃሴ አንዱ ስልት በአባቶችና በልጆች መካከል መለያየትን መዝራት እንደሆነ ልብ ሊሉት ይገባል፡፡ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ተሸሽገው መዋቅሯን ሽፋን አድርገውም ሆነ መልካም ስሟን እየተጠቀሙ ነገር ግን በስውር ተልእኮ ሤራቸውን ለማስፈጸም ቀን ከሌሊት እየተጉ ላሉት አመቺ የሆኑ ክፍተቶችን በጥንቃቄ መድፈን አለባቸው፡፡ በማናቸውም የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ጉዳዮች የቅዱስ ሲኖዶስን መንፈሳዊ ልዕልናና ሓላፊነት ማስከበር፣ ውሳኔዎቹን ማስፈጸም፣ የቤተ ክርስቲያንን መዋቅራዊ አሠራርና መመሪያዎች ተግባራዊነት መከታተል፣ ውጤታማ ማእከላዊ አሠራርን ማስፈን ይገባል፡፡

የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ቀኖናዋና ሕግጋቷ ተጠብቆ ዘርፈ ብዙ መንፈሳዊ አገልግሎቷ በተሳካ ሁኔታ እንዲከናወን በቁርጠኛነት መቆም አለባቸው፡፡በየደረጃው ያሉ የቤተ ክርስቲያን አባቶች ሊቃውንትና አገልጋዮች፤ ቆሞሳት፣ ቀሳውስት፣ ዲያቆናት፣ ሰባክያነ ወንጌል፣ ዘማርያን ሁሉ፤ በውጭም ሆነ በውስጥ ተደራጅቶ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን እውነተኛ ልጆች ምእመናንን ለመበተን ያለመታከት እየሠራ ያለውን የተሐድሶ ኑፋቄ እንቅስቃሴ ለመግታት ሃይማኖታዊ አደራና ሓላፊነታቸውን ለመወጣት መንቃት ይገባቸዋል፡፡ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ላይ የተቃጣው የተሐድሶ ሤራ አይመለከተኝም ወይም አላውቀውም በሚል ተገልለን የምንቆይበት ጉዳይ አይደለም፡፡ በመንፈስ ቅዱስ ጥበብ፣ በጾም በጸሎት በመትጋት፤ ምእመናንን መጠበቅ፣ ትምህርተ ሃይማኖቷን ስብከተ ወንጌልን ጠንክሮ ማስተማር፣ ሥርዐቷን፣ ትውፊቷንና ታሪኳን ምእመናን በሚገባ እንዲረዱት ማድረግ ይጠበቅባቸዋል፡፡

የሰበካ ጉባኤያቱን እንቅስቃሴና አደረጃጀት፣ የሰንበት ት/ቤቶችን የዕለት ተዕለት አገልግሎትና ሒደት መከታተል፤ የገዳማትና አድባራቱን እንቅስቃሴ በቅርብ ማወቅ፤ የአብነት ት/ቤቶቻችንን ሁኔታ ድክመትና ጥንካሬ መገንዘብ፣ ለሚፈጠሩ ችግሮች በሚመለከታቸው የቤተክርስቲያኒቱ አካላትም ሆነ በየሐላፊነት ደረጃቸው መጠን በወቅቱ መፍትሔ መስጠት ያስፈልጋል፡፡

ሰንበት ት/ቤቶቻችንና የዓውደ ምሕረት ጉባኤያትን ማጠናከር ስብከተ ወንጌሉን ማስፋፋት ቀሳጮች ገብተው ስውር ተልእኰአቸውን ለማስፈጸም እንዳይጠቀሙበትና ጉዳት እንዳያስከትሉ በቅርብ መቆጣጠር ተገቢ ነው፡፡

የቤተክርስቲያኒቱን መንፈሳዊ አገልግሎት ለመደገፍና ለማጠናከር ሥርዐቷንና መመሪያዋን አክብረው የተቋቋሙ መንፈሳውያን ማኅበራት ለዚህ የተሐድሶ ኑፋቄ እንቅስቃሴ በማወቅም ይሁን ባለማወቅ ሰለባ እንዳይሆኑ ከፍተኛ ጥንቃቄ ሊያደርጉ ይገባል፡፡ አባላቱ ለዚህ የቅሰጣ ተግባር እንዳይጋለጡ መከታተል፣ በትምህርተ ሃይማኖት የሚጠነክሩበትንና በመንፈሳዊ ሕይወት የሚያድጉበትን መንገድ ማመቻችትና ጠንክሮ መሥራት አለባቸው፡፡ ጽዋ ማኅበራትም የተሐድሶ ኑፋቄው ስውር ተልእኮ ዒላማ መሆናቸውን ተገንዝበው የትምህርት ሥርዐታቸውንና የአገልግሎት ሒደታቸውን ሁሉ፤ በቤተ ክርስቲያን ሥርዐት፣ በአባቶች ትክክለኛ ትምህርትና የቅርብ ክትትል መሠረት እንዲያከናውኑ ያስፈልጋል፡፡

የተሐድሶ ኑፋቄው ያልተቋረጠ ጥቃት ዋነኛ ዓላማ፤ ምእመናንን ከእናት ቤተ ክርስቲያን እቅፍ በማስኰብለል የበግ ለምድ ለለበሰ ተኩላ አሳልፎ መስጠት ነው፡፡ ከዚያም ባሻገር ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ሕልውና ለማሳጣት በሚደረገው የጥፋት ተልእኮ ማሰለፍ ነው፡፡ ምእመናን በማወቅም ሆነ ባለማወቅ እናታቸውን ለተሐድሶ ኑፋቄ ሤራ አሳልፈው ላለመስጠት ወይም ሕልውናዋን ለማሳጣት በሚደረገው የጠላት ሤራ ላለመሰለፍ መጠንቀቅ አለባቸው፡፡ የቅድስት ቤተክርስቲያናቸውን ትክክለኛ ድምፅ በጥንቃቄ ለይተው በመገንዘብ በእምነታቸው ጸንተው ሊቆሙ ይገባል፡፡

ቅድስት ቤተክርስቲያናችንን ከተሐድሶ ኑፋቄ ሤራና የጥፋት ተልእኮ መጠበቅ፣ በኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ሃይማኖታችን ጸንተን መገኘት የሁላችንም ሓላፊነት ነው፡፡ በቤተ ክርስቲያንም ሆነ በእግዚአብሔር ዘንድ ከተጠያቂነት ለመዳን እንንቃ፡፡


እንደ እግዚሐብሔር መልካም ፍቃድ ማህበረ ቅዱሳን በተሐድሶ ዙሪያ ያዘጋጀውን ‹‹የተሐድሶ መናፍቃን ዘመቻ በኢትዮጵያ ቤተክርስትያ ላይ›› መፅሀፍ ስካን አድርገን በpdf መልክ መፅሀፉን አግኝተው ማንበብ ላልቻሉ ሰዎች ራሳቸውን ፤ ቤተሰባቸውን እና ቤተክርስትያንን ነቅተው እንዲጠብቁ ብሎጋችን ላይ post አድርገነዋል ፡፡



አርዕስት፡-‹‹የተሐድሶ መናፍቃን ዘመቻ በኢትዮጵያ ቤተክርስትያ ላይ››


አዘጋጅ፡- የማህበረ ቅዱሳን ዶክመንቴሽን ክፍል
የታተመበት ጊዜ፡- ሚያዚያ 2003
የገፅ ብዛት:- 103
Soft Copy Size:- 20 MB
ዋጋ:- 15 ብር

 ‹‹እኛ ይህን መፅሀፍ እርስዎ ጋር በማድረስ ሀላፊነታችንን ተወጥተናል እርስዎ ላላነበቡት እንዲያነቡት በማድረግ ሃላፊነትዎን ይወጡ፡፡››

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

‹‹ሀሰት አንናገር እውነትን አንደብቅም››
 

2014 ኦክቶበር 13, ሰኞ

‹ቀራንዮ፣ መድኃኔዓለም፣ ካህናቱ›

                                                                                  
ቅዱስ ጳውሎስ ተከስሶ በቂሣርያው ገዥ በፊስጦስ ፊት በቀረበ ጊዜ አይሁድ ለብቻቸው ቀርበው በቅዱስ ጳውሎስ ላይ ይፈርድበት ዘንድ ጎትጉተውት፣ እነርሱ ማስረጃ ያሉትንም አቅርበውለት፣ ሕጋቸውንም ጠቅሰው ማሳመኛ አቅርበውለት ነበር፡፡ አሕዛባዊው ገዥ ፊስጦስ ግን እግዚአብሔርን እናውቃለንም፣ እንፈራለንም ከሚሉት አይሁድ ተሽሎ ያሉትን ከማድረግ ራሱን ከለከለ፡፡
ከጥቂት ቀናት በኋላ ንጉሥ አግሪጳና በርኒቄ ወደ እርሱ በመጡ ጊዜ ጉዳዩን አቀረበላቸው፡፡ ፊስጦስ አይሁድ ያቀረቡትን ስሞታ፣ ውትወታና ክስ ተቀብሎ በቅዱስ ጳውሎስ ላይ ያልፈረደበትን ምክንያት ለአግሪጳ ሲገልጥለት ‹‹ተከሳሹ በከሳሾቹ ፊት ለፊት ሳይቆም፣ ለተከሰሰበትም መልስ ይሰጥ ዘንድ ፈንታ ሳያገኝ፣ ማንንም ቢሆን አሳልፎ መስጠት የሮማውያን ሥርዓት አይደለም›› ብሎ መሆኑን ነግሮታል (የሐዋ.25÷16)፡፡
ይህ በሮማውያን ዘመን እጅግ የታወቀውን ራስን በእኩል ደረጃ የመከላከል መብት በተመለከተ ሮማዊው ታሪክ ጸሐፊ አፒያን (95-165ዓም) በጻፈው Civil War በተሰኘው መጽሐፉ (3:54) ላይ ‹‹የምክር ቤት አባሎች፣ ሕጉ የተከሰሰ ሰው የተከሰሰበትን ሰምቶ በእርሱ ላይ ከመፈረዱ በፊት መልስ የመስጠት መብት አለው ይላል›› ሲል አሥፍሮት ነበር፡፡ ፊሊክስ የጠቀሰው ይኼንን ነው፡፡ አበው በትርጓሜያቸው ‹አሕዛብ ፍርድ ይጠነቅቃሉ›› ሲሉ የመሰከሩት እንዲህ ያለው የሮማውያንን ሕግ ነው፡፡ ለዚህ ጥንቁቅ የፍርድ ሥርዓትም ሲሉ አያሌ የሮማውያንን የፍተሕና የፍርድ ሐሳቦች በቤተ ክርስቲያን የፍትሕ ሥርዓት ውስጥ (በቀኖና) እንዲገቡና እንዲሠራባቸው አድርገዋል፡፡


ይህንን የምትተረጉምና የምታስተምርን ቤተ ክርስቲያን እንወክላለን የሚሉ ሰዎች ናቸው ሰሞኑን ተሰብስበው ተከሳሹ በሌለበት ፍርድ ሲሰጡ ያየናቸው፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን ተሳሳተ ተብሎ እንኳን ቢሆን ቤተ ክርስቲያኒቱ ለአርዮስና ለንስጥሮስ፣ ለመቅዶንዮስና ለሰባልዮስ የሰጠችውን መብት ቤተ ክህነቱ ለማኅበረ ቅዱሳን ሊነፍገው አይገባም ነበር፡፡ በቀደዱላቸው ቦይ መንጎድ፣ ተጠልቷል ብለው በሚያስቡት ላይ መፍረድ ሃይማኖታቸው የሆነ፤ ፓትርያርኩን ምን ያስደስታቸዋል እንጂ የትኛው እውነት ነው ለሚለው የማይጨነቁ ሰዎች የክስ መዓታቸውን ሲያዘንቡ ማኅበሩ መልስ እንዲሰጥ ዕድል ሊሰጠው ይገባ ነበር፡፡ ነገር ግን ሰዎቹ ለበዓሉ የሚስማማውን ቀለም ትተው ለባለ ሥልጣኑ የሚስማማውን ቀለም መረጡ፡፡ ሊቁ ክፍለ ዮሐንስ ‹ካህን ከመሆን እረኛ መሆን ይሻላል› እንዳለው ከቤተ ክህነት ፊልክስ ተሽሏል፡፡
ፊሊክስ ለቅዱስ ጳውሎስ፣ ሠለስቱ ምእት ለአርዮስ፣ ማኅበረ ኤፌሶን ለንስጥሮስ የሰጡትን ዕድል ቤተ ክህነቱ ለማኅበረ ቅዱሳን ለመስጠት ፈቃደኛ አልሆነም፡፡ ለምን?
ሰዎቹ እውነቱን ለመጋፈጥ ዐቅም አንሷቸዋል ማለት ነው፡፡ የሚሉት ነገር የሆኑ አካላትን ስለማስደሰቱ እንጂ እውነት ስለመሆኑ ርግጠኞች አይደሉም፡፡ ስለዚህም ተከራካሪያቸውን ለመስማትና የእነርሱ ‹እውነት› ሲሞገት ለማየት ዐቅም ያንሳቸዋል፡፡ ወይም ደግሞ
ከክርክሩ በፊት ውሳኔውን ወስነው ጨርሰዋል፡፡ ፓትርያርክ አቡነ ቴዎፍሎስን ለደርግ አሳልፈው የሰጡት የቤተ ክህነት ሰዎች እንዲህ ነበር ያደረጉት፡፡ ፓትርያርኩን አሳልፈው ሰጥተዋል፡፡ ውሳኔውን ወስነዋል፡፡ ነገር ግን ለውሳኔው ምክንያት መፈለግ ነበረባቸው፡፡ ስለዚህም አቡነ ቴዎፍሎስ ሠሩ ያሏቸውን ጥፋቶች ለብቻቸው ተሰብስበው፣ ‹በደላቸውን› ዘርዝረው፣ እርሳቸው መልስ ሊሰጡ በማይችሉበት ሁኔታ ለደርግ አስተላለፉ፡፡ እነዚህ ሰዎች ለብቻቸው መሰብሰብ የፈለጉት፣ የፓትርያርኩንም መልስ የመስጠት መብት የነፈጉበት አንዱ ምክንያት ፓትርያርኩ በሚሰጡት መልስና በሚያቀርቡት ማስረጃ እውነታቸው ነፋስ ያየው ገለባ እንዳይሆንባቸው ነው፡፡ ወይም
እነዚህ ሰዎች የራሳቸውን ሥራ አይደለም እየሠሩ ያሉት፡፡ ቤተ ክርስቲያኒቱን ሲበጠብጡ የኖሩት ካህናተ ደብተራ (ከቤተ ክህነት ደመወዝ እየወሰዱ ለቤተ መንግሥት ሲሠሩ የኖሩ ካህናት ነን ባዮች) ዋናው መለያቸው የሚሠሩት የራሳቸውን ሥራ አለመሆኑ ነው፡፡ የመለካዊነት ጠባይ ስላላቸው ሌሎች ተናገሩ የሚሏቸውን ይናገራሉ፣ ፈጽሙልን የሚሏቸውን ይፈጽማሉ፤ አውግዙልን የሚሏቸውን ያወግዛሉ፤ አጽድቁልን የሚሏቸውንም ያጸድቃሉ፡፡ የሚሠሩት ሥራ የላኳቸውን ሰዎች ማርካቱን እንጂ የሚያስከትለውን ነገርና የሚያስከፍለውን ዋጋ አያውቁትም፡፡ እነዚህ ነበሩ አባ በጸሎተ ሚካኤልን ያሰደዱት፣ እነዚህ ነበሩ አባ ፊልጶስን ያንከራተቱት፣ እነዚህ ነበሩ እጨጌ ዕንባቆምን ለልብነ ድንግል ከስሰው ምንም ባላጠፋው ጥፋት ‹ጉንጽ› በተባለው ዓለም በቃኝ እስር ቤት ያሳሠሩት፤ በኋላም ለሀገሪቱ ጥፋትን ያመጡት፡፡ ጥይት የመታው ሰው ተናድዶ ‹‹ምነው እንዲህ ታበላሸኝ›› ቢለው ‹‹እባክህ እኔ አይደለሁም፣ እኔ ተተኮስኩ እንጂ ተኳሹ ሌላ ነው፤ እኔ መልክተኛ ነኝ›› አለው፡፡ ‹‹ተኳሹ የት አለ?›› ቢለው ‹‹እርሱማ አይታይም ተደብቆ ነው የሚተኩሰው፤ እርሱ ስለሚደበቅኮ ነው እኔ የመጣሁት›› አለው ይባላል፡፡
ወይም እነዚህ ሰዎች ስንፍናቸውን የሚያሳይባቸውን፣ ድካማቸውን የሚገልጥባቸውን፣ ሊያጠፉት ወድደዋል፡፡ ሰውዬው ዶሮውን በጦም አርዶ ለምን አረድከው ቢባል ‹‹እሱ ነው ጠዋት እየተነሣ መንጋቱን የሚያሳብቅብኝ፣ አርፌ እንዳልተኛበት፡፡እርሱ ባይጮህ ኖሮ መንጋቱን ማን ያውቅ ነበር? ተኛህ ብሎስ ማን ይከሰኝ ነበር›› አለ አሉ፡፡ ከመንቃት ይልቅ ማንቂያውን ማጥፋት፡፡ የ13ኛው መክዘ የደቡብ ሐዋርያ አቡነ አኖሬዎስ ታላቁ በካህናተ ደብተራ ተከስሶ ወደ ንጉሥ ሰይፈ አርእድ የቀረበበት ክስ አስቂኝ ነበር፡፡ ‹‹ከንጉሡ የሚበልጥ ቤተ ክርስቲያን ሠርቷል›› ነበር የተባለው፡፡ ጉዳዩን ሊያጣራ የሄደው የጉዳም አለቃ ያገኘው ቤተ ክርስቲያን ግን እንደተባለው አልነበረም፡፡ ነገር ግን ከክሱ ንጹሕ መሆኑ ቅጣቱን አላስቀረለትም፡፡ ከገዳሙ ወጥቶ በወለቃ በረሃ እንዲከራተት ሆኗል፡፡ ምናለ ከንጉሡ የሚበልጥ ቤተ ክርስቲያን ቢሠራ? የሚያስመሰግነው እንጂ የሚያስነቅፈው አልነበረም፡፡ ለካህናተ ደብተራ ግን ይኼ ስንፍናቸውን ይገልጠዋል፣ እንደ አውራ ዶሮውም መተኛታቸውን ያሳይባቸዋል፡፡
ቅዱስ ሲኖዶሱ አሁን መስቀለኛ መንገድ ላይ ቆሟል፡፡ የሚቀርቡት ክሶች ለምን ቀረቡ ማለት አይቻልም፡፡ ነገር ግን በአይሁድ አደባባይ ፍርድ ሲጓደል፣ እንደ ጲላጦስ ሚስት የሚያስጠነቅቅ ያስፈልጋል፡፡ ገለልተኛ አካል አቋቁሞ የተባሉትን ያጣራ፡፡ ራሱ የማኅበሩ አመራር ለተከሰሰበት መልስ ይስጥ፡፡ አሕዛባዊው ፊሊክስ ለቅዱስ ጳውሎስ የሰጠውን መብት ሲኖዶሱ ለማኅበሩ መስጠት አለበት፡፡ ተጣርቶ በተገኘው ማስረጃና ምስክር መሠረት ውሳኔ ይሰጥ፡፡ ጥፋተኛው ይታረም፤ እውነተኛው ይገለጥ፡፡
በዐፄ ኃይለ ሥላሴ ዘመን ቀራንዮ መድኃኔዓለም አለቅነት ተሾመው የሄዱትን አባት ካህናቱ አስቸገሯቸው፡፡ ለጥቂት ጊዜ የተላኩበትን ሊሠሩ ሞከሩ ግን አልሆነም፡፡ በመጨረሻም ለንጉሡ እንዲቀይሯቸው አመለከቱ፡፡ ንጉሡም ምነው ምን ገጠመህ? ቢሏቸው ‹‹ካህናቱም ካህናቱ፣ ቀራንዮም ቀራንዮ፣ መድኃኔዓለምም መድኃኔዓለም›› አሉ ይባላል፡፡ ሰቃይ ተሰቃይና የመስቀያ ቦታ አንድ ሲገናኙ ያ ነው ክፉ ዘመን፡፡
ማኅበሩን እንደ ተቋም፣ እንደ ጽ/ቤትና እንደ ድርጅት ማፍረስ ቀላል ነው፤ እንደ አስተሳሰብ፣ እንደ አመለካከት፣ እንደ የአገልግሎት መሥመርና አተያይ ግን ማፍረስ አይቻልም፡፡ ዛሬ ማኅበሩን በማፍረስ የሚጀመረው አጥር ንቅነቃ ግን መጨረሻው ሲኖዶሱን በማደንበሽ እንዳይጠናቀቅ ያሰጋል፡፡ ባለቤቱን ካልናቁ ነውና፡፡ 

2014 ኦክቶበር 10, ዓርብ

ማኅሌተ ጽጌ (Part One

 
 
ማኅሌተ ጽጌ፤ ምንጩ ትርጉሙ መልእክቱ 
           ይህ ድርሰት በማንኛውም ጊዜ የሚጸለይ ቢሆንም በተለየ ሁኔታ በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የሚውለው ከመስከረም 26 እስከ ኅዳር 5 ቀን ድረስ ባለው የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም የስደት ዘመን ነው፡፡ በዚህ ወቅት በየሳምንቱ እሑድ ሌሊት በሙሉ የእመቤታችንን ከልጇ ጋር ወደ ግብፅ መሰደድና መንከራተት እያሰቡ የሚደረስ ምሥጋናና ጸሎት ነው፡፡
             በሀገራችን የመስከረምና የጥቅምት ወራት የአበባ ወራት /ዘመነ ጽጌ/ ናቸው፡፡ ይህም ወቅት ተራሮች በአበባ የሚያጌጡበትና ለዓይን ማራኪ የሚሆኑበት ጊዜ ነው፡፡ በዚህም ዘመን ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ «ስለ ልብስስ ስለምን ትጨነቃላችሁ) የሜዳ አበቦች እንዴት እንዲያድጉ ልብ አድርጋችሁ ተመልከቱ፡፡ አይደክሙም፣ አይፈትሉም፤ ነገር ግን እላችኋለሁ ሰሎሞንስ ስንኳ በክብሩ ሁሉ ከእነዚህ እንደ አንዱ አልለበሰም፡፡ እግዚአብሔርን ዛሬ ያለውን ነገም ወደ እቶን የሚጣለውን የሜዳን ሣር እንዲህ የሚያለብሰው ከሆነ እናንተ እምነት የጐደላችሁ እናንተንማ ይልቁን እንዴት እንግዲህ ምን እንበላለን ምንስ እንጠጣለን) ምንስ እንለብሳለን) ብላችሁ አትጨነቁ ...» /ማቴ.5÷28-33/ በማለት የተናገረውን ቃል በማሰብ መጨነቅ የሚገባን መንግሥተ ሰማያት ለመግባት እንጂ በዚህ ዓለም ስላለው ነገር እንዳልሆነ ተራሮችን በአበባ ያለበሰ አምላክ በአርአያውና በአምሳሉ የፈጠረንን እኛን ለኑሮ የሚያስፈልገንን ምግብና ልብስ እንደማይነሳን እያሰብን የምንዘክርበት ወቅት ነው፡፡
                እንዲሁም ክቡር ዳዊት «ተዘከር እግዚኦ ከመ መሬት ንሕነ ወሰብእሰ ከመ ሳዕር መዋዕሊሁ ወከመ ጽጌ ገዳም ከማሁ ይፈሪ፤ አቤቱ እኛ አፈር እንደሆን አስብ ሰውስ ዘመኑ እንደሣር ነው እንደ ዱር አበባ እንዲሁ ያብባል ነፋስ በነፈሰበት ጊዜ ያልፋልና» /መዝ.12÷14-16/ በማለት እንደ ተናገረው የሰው ሕይወት በሣር ይመሰላል፡፡ ሣር አድጐ አብቦ ከዚያ በኋላ ይደርቅና በነፋስ አማካኝነት የረገፈው ሣር እየተነሣ የነበረበት ቦታ ስንኳ እስከማይታወቅ ድረስ ይሆናል፡፡ ሰውም ከአደገ በኋላ በሕማም ፀሐይነት ይደርቅና በሞት ነፋስነት ይወሰዳል፡፡ ከዚያ በኋላ ወደ መቃብር ሲወርድ የነበረበት ቦታ ይዘነጋል፡፡ ስለዚህ ዘመነ ጽጌ ሰው ዘመኑ እንደ አበባ በቶሎ የሚረግፍ መሆኑን በማሰብ ይህ ዘመን ሳያልፍ መልካም ሥራ ለመሥራት ትንሣኤ ኅሊና የሚነሣበት ጊዜ ነው፡፡ ቅዱስ ያሬድ ለዘመነ ጽጌ የሠራው ድጓም ይህንኑ የሰውን ዘመን አጭርነት የሕይወቱን ኢምንትነት በዚህ ሕላዌ የተፈጠረ ሰው በዚህ ዓለም ክፉ ሥራ መሥራት እንደሌለበት ሁልጊዜ በተዘክሮተ ሞት እንዲኖር የሚያስረዳ ነው፡፡
                     በዘመነ ጽጌ ቅዱስ ያሬድ ከደረሰው ድጓ በተጨማሪ ከላይ እንደተጠቀሰው 14ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የተነሣ አባ ጽጌ ድንግል ከዚሁ ዘመን ጋር የተያያዘ ድርሰት ደርሷል፡፡ ይህ ድርሰት በግጥም መልክ የተደረሰ በአብዛኛው አምስት ስንኞች ያሉት ሲሆን ብዛቱም 15 ያክል ነው፡፡ ይህም ድርሰት «ማኅሌተ ጽጌ» በመባል የሚታወቀው ነው፡፡ ፍሬ ከአበባ አበባም ከፍሬ እንደሚገኘው ሁሉ ማኅሌተ ጽጌም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምንና ልጇን መድኃኒታችንና አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስን በአበባና በፍሬ እየመሰለ የሚያስረዳ ድርሰት ነው፡፡ እርሷን በአበባ ሲመስል ልጇን በፍሬ እርሷን በፍሬ ሲመስል ደግሞ ልጇን በአበባ እየመሰለ ይናገራል፡፡ ነቢዩ ኢሳይያስ «ትወጽእ በትር እምሥርወ እሴይ ወየዓርግ ጽጌ እምጉንዱ፤ ከእሴይ ግንድ በትር ይወጣል፤ ከሥሩም ቁጥቋጦ ያፈራል»  /ኢሳ.11÷1/ ብሎ ከእሴይ ዘር የምትገኘውን እመቤታችንን በበትር ከርሷ የሚገኘውን ክርስቶስን ደግሞ በጽጌ መስሎ ትንቢቱን ተናግሯል፡፡ አባ ጽጌ ድንግልም ድርሰቱን በዚሁ አንጻር በመቀመር እያንዳንዱን መልክዕ እመቤታችንንና ልጇን አስተባብሮ በጽጌና በፍሬ በመመሰል የእግዚአብሔርን ድንቅ ሥራ በምሥጢር በታሪክ፣ በጸሎትና በመሳሰለው መልክ ድንቅ በሆነና በተዋበ ሁኔታ አዋሕዶ ደርሶታል፡፡
                                                                                                                  
                     እመቤታችን ጣዕሟንና ፍቅሯን እንዲሁም ምስጋናዋን ሲናፍቁ የነበሩትን ቅዱስ ኤፍሬምንና አባ ሕርያቆስን ውዳሴዋንና ቅዳሴዋን እንደገለጸችላቸው ለፍቅሯ ሲሳሳ ለነበረው ለአባ ጽጌ ድንግል ደግሞ ይህንን ማኅሌተ ጽጌን እንዲደርስ አድርጋዋለች፡፡ ከላይ እንደተገለጸው ማኅሌተ ጽጌ በመልክዕ አደራረስ ሥርዓት የተደረሰ ሲሆን ይህንንም ለመመልከት እንዲያመች በሚከተሉት ክፍሎች ከፋፍሎ ማቅረብ ይቻላል፡፡
1. ጸሎት
            በዚህ አገባብ ጸሎት ስንል በተለየ ሁኔታ ጸሎትነቱ የጐላውን ለማየት እንጂ ድርሰቱ በሙሉ ጸሎት ነው፡፡ ሌሎቹንም እንዲሁ ታሪክ፣ ተግሳጽ፣ ምሥጢር ተብለው መከፈላቸው በበዛውና በጐላው ለመግለጽ ነው እንጂ ሁሉም በሁሉ አለ፡፡ በጸሎትነታቸው ጐልተው ከሚታዩት ውስጥ የተወሰኑትን እንመለከታለን፡፡
1.1.  አንብርኒ ማርያም ውስተ ልብኪ ከመ ሕልቀት፣
ወከመ ማዕተብ ፁርኒ በመዝራዕትኪ ልዕልት፣
በእንተ ርስሐትየሰ ኢትመንንኒ ንግሥት፣
እስመ ወሀብኩ ንብረትየ ለፍቅርኪ ሞት፣
ዘአሰገርዎሙ ለሰማዕት በጽጌሁ ሕይወት፡፡
              ጠቢቡ ሰሎሞን «የምእመናንንና የክርስቶስን ነገር በምሥጢር በተናገረበት በመኃልይ መጽሐፉ «እንደ ማኅተም በልብህ እንደ ማኅተም በክንድህ አኑረኝ» /መኃ.9÷6/ ይላል፡፡ ይኸውም የምእመናንንና የክርስቶስን አንድነት የሚገልጽ ነው፡፡ «አንብርኒ ማርያም ውስተ ልብኪ ከመ ሕልቀት፤ ወከመ ማዕተብ ፁርኒ በመዝራዕትኪ ልዕልት» ማለቱ እመቤታችንን እንደ


ማኅተም በልብሽ አኑሪኝ በማለት በእናትነትሽ፣ በአማላጅነትሽ አትርሽኝ ካለ በኋላ «በእንተ ርስሐትየሰ ኢትመንኒ ንግሥት» ይላል፡፡ ይኸም ማለት አትርሽኝ በልብሽ አኑሪኝ ብዬ የምለምንሽ አንቺ እንዳትረሽኝ የሚያደርግ መልካም ሥራ ኖሮኝ አይደለም፡፡ ስለዚህ በሰውነቴ ክፋት ምክንያት በኃጢ አቴና በወራዳነቴ ምክንያት እኔን ከማሰብ ከልቡናሽ አታውጪኝ በማለት እመቤታችን በርኅሩኅ ልቧ «መሐር ወልድየ ወተዘከር ኪዳንየ» እያለች እንድታዘክረን የሚያሳስብ ጸሎት ነው፡፡
ሶበ አተቦ ለማይ በቅዳሴኪ እንዘ ይጼሊ፣
ረሰዮ ኅብስተ ጽጌ ሃይማኖት ሳሙኤል ዘሐቅለ ዋሊ፣
ምሕረተ ወፍትሐ ለተአምርኪ አኀሊ፣
ሥረዪ ኃጢአትየ ወእጸብየ አቅልሊ፣
እስመ ኩሎ ገቢረ ማርያም ትክሊ፡፡
            አባ ሳሙኤል ዘዋልድባ ቅዳሴ ማርያምን እየደገሙ ውኃው በተአምራት ኅብስት ይሆንላቸው ነበር፡፡ ይህን ተአምር ከአደነቀ በኋላ «ማርያም ሆይ ሁሉን ማድረግ ትችያለሽና ኃጢአቴን አስተስርይልኝ» ይላል፡፡ ጌታችን «እውነት እላችኋለሁ የሰናፍጭ ቅንጣት የሚያህል እምነት ቢኖራችሁ ይህን ተራራ ከዚህ ወደዚያ እለፍ ብትሉት ያልፋል፤ የሚሳናችሁም ነገር የለም» /ማቴ.17÷1/ በማለት ላመነ የሚሣነው ነገር እንደሌለ ተናግሯል፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም መልአኩ «ትጸንሻለሽ፣ ትወልጃለሽ ...» ብሎ ባበሠራት ጊዜ ይህ እንደምን ይሆንልኛልብላ ስትጠይቅ «ለእግዚአብሔር የሚሳነው ነገር የለም» ሲላት በፍጹም እምነት ይኩነኒ በከመ ትቤለኒ እንደቃልህ ይሁልኝ» በማለት የተቀበለች ናት፡፡ ይህንንም ቅድስት ኤልሳቤጥ መንፈስ ቅዱስን ተመልታ «ከጌታ የተነገረላት ቃል ይፈጸማልና የታመነች ብፅዕት ናት» /ሉቃ.1÷453 ብላ መስክራለች፡፡ ላመኑ ሁሉ የሚቻል ከሆነ እመቤታችን ግን ቅዱሳን ሁሉ የሚማጸኑትን አምላክ በሥጋ ወልዳ ያስገኘች ስለሆነች ለእርሷ የሚሳናት ነገር የለም፡፡ ስለዚህም ነው ላንቺ የሚሳንሽ ነገር የለምና ኃጢአቴን አስተስርዪልኝ፣ የከበደኝን ሁሉ አቅልይልኝ በማለት የለመነው፡፡

                                   በአውሮጳ   የካህናት አንድነት ማኅበር ሊቋቋም መሆኑ ታወቀ በ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከመላዋ አውሮጳ   የተውጣጡ ካህናት፡” የ...