2015 ማርች 10, ማክሰኞ

እየደመሰሱ መቅዳት

ለረዥም ዓመታት በአንድ ሬዲዮ ጣቢያ የሠራ ጋዜጠኛ ለአንድ ጥናት ወደ ጣቢያው ይሄዳል፡፡ ከ30 ዓመታት በፊት እርሱ ራሱ ያደረገው ቃለ መጠይቅ ነበር፡፡ ቃለ መጠይቁ የተደረገላት ሴት አሁን በሕይወት የለቺም፡፡ ለዚህ ነበር እርሷ የሰጠቺውን ቃል ፍለጋ ወደ ሬዲዮ ጣቢያው የሄደው፡፡ ያገኘው ግን የጠበቀውን አልነበረም፡፡ የተቀዳው ቃለ መጠይቅ የለም፡፡ ምነው? አለ ጋዜጠኛው፡፡ ‹‹ብዙ ካሴቶችን እየደመሰስን ቀድተንባቸዋል፡፡ በዚያ ምክንያት ያንን ቃለ መጠይቅ አሁን አታገኘውም›› አሉት፡፡ እርሱም በዚህ አዝኖ ወጣ፡፡
ለነገሩ እርሱ በካሴቱ አዘነ እንጂ ከኢትዮጵያ ታሪክ መገለጫዎች አንዱ እየደመሰሱ መቅዳት ነው፡፡ የሚመጣ መንግሥት ወይም ባለሥልጣን፣ ዐዋቂ ወይም ታዋቂ፣ ታሪክ ጸሐፊ ወይም ዐቅድ ነዳፊ ከእርሱ በፊት ለነበረው ነገር ዋጋ ሰጥቶ፣ የየራሱን ሥራ ከመሥራትና የዘመኑን አሻራ ከማኖር ይልቅ ያለፈውን መደምሰስ ይቀናዋል፡፡ 

ሀገር የማታልቅ ሕንጻ ናት፡፡ መሠረቷ ዛሬ አልተጣለም፡፡ መሠረቷ ከተጣለ ቆየ፡፡ እያንዳንዱ ትውልድ የየራሱን ድርሻ እየገነባ ይቀጥላል፡፡ የመጣው ሁሉ ባለው ላይ አዳብሮ፣ አሻሽሎ ወይም አሣምሮ የሚጨምር ከሆነ ሀገር እያደገች፣ እየበለጸገችም ትሄዳለች፡፡ የመጣው ትውልድ ሁሌም ከሥር ከመሠረቱ የሚያፈርሳት ከሆነ ግን ሀገር ባቢሎን ትሆናለች፡፡ ቅርስ እንጂ ሕይወት፣ ታሪክ እንጂ ዕድገት፣ ስም እንጂ ክብር አይኖራትም፡፡ ለጉብኝት እንጂ ለኑሮ አትሆንም፡፡ 
 ባቢሎን በታሪክ ቀድመው ከሠለጠኑ ሀገሮች ተርታ ነበረቺ፡፡ ነገር ግን የገዛት ሁሉ ከመሠረቷ እያፈረሰ እንደገና ሲሠራት፣ የመጣዉ ሁሉ እየደመሰሰ ሲቀዳባት ይሄው ዛሬም አላልፍላት ብሎ የጦር አውድማ ሆናለቺ፡፡ ስለ ኢራቅ ጥንታዊ ታሪክ የሚተረከውና የዛሬዋ ኢራቅ አይጣጣሙም፡፡ የመጡት ሁሉ በባቢሎን ካሴት ላይ እየደመሰሱ ሲቀዱ፣ መሠረት አልባ ጣራ ሊያቆመ ሲደክሙ፣ አሁን የመጡባት አሸባሪዎች ደግሞ ጨርሰው ታሪካዊ ቅርሶቿን በድጅኖ መናድ ጀመሩ፡፡ እየደመሰሱ መቅዳት ካንሰር መሆን ሲጀምር ይሄው ነው፡፡
ይኼ እፉኝታዊ ጠባይ ነው፡፡ እፉኝት የምትባል የእባብ ዘር አለች አሉ፡፡ አፈ ማኅፀኗ ጠባብ ነው፡፡ ከወንዱ ጋር ስትገናኝ የወንዱን አባለ ዘር ትቆርጠውና ወንዱ ይሞታል፡፡ ልጆቿን በማኅፀኗ ፈልፍላ ስትወልዳቸው ደግሞ ለመውጣት ስለማይችሉ ሆዷን እየቀደዱ እናታቸውን ገድለዋት ይወጣሉ፡፡ ልጆቹ ልጅ የሚሆኑት አባትና እናታቸውን ገድለው ነው፡፡ ያለፈውን ካልደመሰሱ መኖር አይችሉም፡፡
የመጣንበትንና የነበርንበትን ማንጠር ጠቢብነት ነው፡፡ መደምሰስ ግን እፉኝትነት፡፡ ማንጠር ማለት ደግሞ እንደ ቅቤ ነው፡፡ እናቶቻችን ቅቤ የሚያነጥሩት ለሁለት ነገር ነው፡፡ በአንድ በኩል ቅቤው ሲነጠር አንጉላው ተለይቶ ይቀራል፡፡ ቅቤውም ኮለል ብሎ ይወርዳል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ቅመማ ቅመም በመጨመር በቅቤው ላይ ጣዕም ያክሉበታል፡፡ ወይም ቅቤውን ላቅ ወዳለ ሌላ የጣዕም ደረጃ ያሸጋግሩታል፡፡ ማንጠር ሲባል እንደዚሁ ነው፡፡ በታሪካችን፣ በባሕላችን፣ ወይም በልማዳችን ውስጥ እንደ አንጉላ ያሉ ነገሮች ተጨምረው ከሆነ በዕውቀትና ምርምር፣ በግልጽ ወይይትና ክርክር እሳት ላይ ጥዶ ማንጠር ነው፡፡ አንጉላውን ከለየን በኋላ ደግሞ በነበረው እሴታችን ላይ ሌላ እሴት መጨመር፡፡ 
ቅቤን ማንም አያነጥረውም፤ ባለሞያ ይጠይቃል፡፡ አንጉላውን የማስወገጃ መንገዱ ራሱ ልዩ ሞያ ጠያቂ ነው፡፡አንጉላ መስሎን ቅቤዉን ጭምር እንዳያስወግደው እንደ ዶሮ ላባ ባለ ስስ ነገር እየለዩ ማንጠርን ይጠይቃል፡፡
ታሪካችንንና ባሕላችንን፣ ወጋችንንና ልማዳችንን ስንመረምርና አንጉላውን ስንለይ፣ እንደ ቅቤ አንጣሪው በሞያ መሆን አለበት፡፡ ስሜት ቦታ ሊያገኝ አይገባም፡፡ ቅቤ አንጣሪ ስሜት ውስጥ ከገባ ምች ይመታዋልና፡፡ አረሙን እንነቅላለን ብለን ስንዴውን ጨምረን እንዳንነቅለው ጥንቃቄ ያስፈልገዋል፡፡ ለጊዜያዊ የፖለቲካ ፍጆታ ብለን የምንሠራቸው ሥራዎች አዙሪት ውስጥ እንዳይጥሉን ጉዳዩን የሞያና የዕውቀት ጉዳይ ማድረግ ይገባናል፡፡ ‹ዕውቀት አጠር፣ ስሜት መር› ከሆነው ጉዟችን ይልቅ ‹ዕውቀት መር፣ ስሜት አጠር› ወደሆነው ሥልጣኔ ካልወጣን በስተቀር እዚያው ጨለማው ውስጥ ስንኳትን እንኖራለን፡፡ 
ቅቤ አንጣሪ ሰው ሞያ ብቻ ሳይሆን ጥንቃቄም ያስፈልገዋል፡፡ ምች እንዳይመታው፡፡ የቅቤ ምች ያጠናግራል ይባላል፡፡ ቅቤውን በጥንቃቄ ያነጠረቺ ባለሞያ ናት ‹‹ቅቤ አንጣሪዋ እያለቺ ጎመን ቀንጣሿን ምች መታት› ብላ የተሳለቀቺው፡፡ ነባሩን ነገራችንን ስናነጥር ሞያ ብቻ ሳይሆን ጥንቃቄም ወሳኝ ነው፡፡ የዘመን ምች መትቶ እንዳያጠናግረን፡፡ ጎጠኛነት፣ የፖለቲካ ፍጆታ፣ የሥልጣን ፍቅርና ጊዜያዊ ጥቅም የሚባሉ ምቾች አደገኞች ናቸው፡፡ እነዚህ ምቾች የመቱት ሰው ቅቤውን በሚገባ ማንጠር ቀርቶ ሌላ በሽታ በራሱ ላይ ይጨምራል፡፡ ጤነኛ የነበረው አንጣሪ ተጣሞ፣ ዓይኑ ጠፍቶ፣ ፊቱ ቆሳስሎ ይወጣል፡፡ ከዚያ በኋላ እርሱ ያለፈው ታሪኩን ሁሉ የሚያየው በማንጠሪያ ዓይኑ ሳይሆን በተጠናገረ ዓይኑ ነው፡፡ 
አሁን በደምስሶ መቅዳት ሥራ ላይ የተሠማሩት ብዙዎቹ ወገኖቻችን ምች የመታቸው ናቸው፡፡ ዓይነ ልቡናቸውን ምች ስለ መታው ቅቤውንና አንጉላውን መለየት አልቻሉም፡፡ አንጉላ መስሏቸው ሁሉንም ነባር ቅቤ ሊያስወግዱ የቋመጡ ናቸው፡፡ የዛሬውን መንግሥተ ሰማያት ለማሰኘት የትናንቱን ሲዖል ማድረግ፣ የእነርሱን ዘመን የተድላ ዘመን ለማድረግ አላፊውን ዘመን የመከራ ዘመን ማድረግ፣ የአሁኑን አስተሳሰባቸውን ዘመናዊ ለማድረግ ያለፈውን ሁሉ ኋላ ቀር ማሰኘት የግድ ይመስላቸዋል፡፡ ያለፈው የተቀዳበትን ካሴት አዳምጠው ቀጥሎ የራሳቸውን ከመቅዳት ወይም አዲስ ካሴት ከመጠቀም ይልቅ ደምስሰው ካልቀዱ አይረኩም፡፡ አዲስ ሲሠሩ ከሚደሰቱት በላይ ነባሩን ሲያጠፉ የሠለጠኑ ይመስላቸዋል፡፡
ሰው በአንድ ቦታ ስለተሰበሰበ ብቻ ሀገር አይሆንም፡፡ እንዲያ ቢሆን ኖሮ እሥራኤላውያን አሜሪካና ፖላንድ መኖር ይበቃቸው ነበር፤ ለፍልስጤማውያንም ዮርዳኖስና ሊባኖስ የሚኖሩት የካምፕ ኑሮ በቂ ነበር፡፡  ሰፊ መሬት ብቻውንም ሀገርን አይመሠርትም፡፡ እንዲያ ቢሆን ኖሮ አንታርክቲካ ሀገር ይሆን ነበር፡፡ ሀገር ግን ከሰውም ከመሬትም በላይ ናት፡፡ ሰው በመሬቱ ላይ ሲኖር የሠራው ታሪክ፣ ያካበተው ባሕል፣ የደነገገው ወግና ሥርዓት፣ ያዳበረው ቋንቋ፣ ያመጣው ለውጥ፣ የፈጠረው ዘዴ፣ የገነባው ሥነ ልቡና፣ የተከተለው እምነት፣ የእርስ በርሱ መስተጋብር፣ ዓለምን የሚያይበት ርእዮተ ዓለም፣ ሥነ ቃሉ፣ ሌላም፣ ሌላም፣ ሌላም ተዋሕደው የሚፈጥሩት ነገር ነው - ሀገር፡፡ 
 
እነዚህን የተሠራንባቸውን ነገሮች ነው ማንጠር የሚያስፈልገው፡፡ መጀመሪያ እንሰብስባቸው፣ እንመዝግባቸው፣ እንለያቸው፣እንዘግባቸው፣ እንቀርሳቸው፣ እንወቃቸው፡፡ ከዚያ እናጥናቸው፣ እንመርምራቸው፡፡ በመጨረሻም እናንጥራቸው፡፡ ገመዱ ውስብስብ ነው፡፡ ለዘመናት የተፈተለና የተገመደ፡፡ ርጋታ፣ ትዕግሥትና ጥበብ ይጠይቃል፡፡ ወስነን አይደለም ማወቅ ያለብን ዐውቀን ነው መወሰን እንጂ፡፡ አንዳንዴ መጀመሪያ እንወስናለን፣ ከዚያ እንሰይማለን፣ ቀጥለንም እንፈርጃለን፣ በመጨረሻም እንመታለን፡፡ በዚህ ሁሉ ሂደት ውስጥ ግን ዕውቀት፣ ጥናትና ማንጠር ቦታ አይሰጣቸውም፡፡ እንዴው ዝም ብሎ ‹ስቅሎ ስቅሎ› ነው፡፡ ‹ትዕዛዝ ከበላይ፣ እግር ወደላይ› ይሆናል መመሪያው፡፡
 
በዚህ መንገድ ስንቱን እየደመሰስን ቀዳን፡፡ ስንቱን ነባር ዕውቀት ሳንጠቀምበት እንደ ገናሌ ወንዝ ፈስሶ ፈስሶ ቀረ፡፡ ከሞኝ ደጃፍ ሞፈር ይቆረጣል የተባለው በራሳችን ላይ ደርሶ ብልሆቹ አውሮፓውያን የራሳችንን መጻሕፍት ሰብስበው፣ ባሕላችንን አጥንተው፣ ታሪካችንን ፈትሸው፣ ነባር ዕውቀቶችን መርምረው - በውስጣቸው ያገኙትን ጥበብ ለዘመናዊ ሥልጣኔያቸው ተጠቀሙባቸው፡፡ እኛ ግን እየደመሰስን ስንቀዳ፣ አንድም ትናንት ሳይኖረን ዛሬን እናቆማለን ብለን መከራ እናያለን፡፡ በጣም የሚገርመው ግን እኛ የትናንቱን ደምስሰን እየቀዳን፣ የነገዎቹ የኛን አይደመስሱም ብለን ማመናችን ነው፡፡ ይኼንኑ አሠራር አይደል እንዴ የምናቆያቸው፡፡   

የኢሬቻ በዓል በደብረ ዝቋላ እንደሚከበር የተላለፈው ዘገባ ማስተባበያ እንዲሰጥበት ተወሰነ

debra zeq
  • ለአፈጻጸሙ የወረዳው እና የዞኑ አስተዳደር ባለሥልጣናት ሓላፊነት ወስደዋል
  • ከመጋቢት ፭ ክብረ በዓል በፊት ማስተባበያው እንዲተላለፍ ከስምምነት ተደርሷል
  • ከኹሉም አካላት የተውጣጣ የሽማግሌዎች ኮሚቴ የችግሩን ቆስቋሾች ያጣራል
  • በክብረ በዓሉ ቀን የተጠናከረ ጥበቃ እንዲደረግ መመሪያ ተሰጥቷል
* * *
  • ‹‹ለእኛ ዐዲስ ነገር ነው፤ እዚኽ ቦታ ኢሬቻ የለም፤ በአራት ወይም በስምንት ዓመት አንዴ ዝናም እምቢ እንዳይለን ገዳሙን አስፈቅደን ከምንፈጽመው ሥርዐት ውጭ በተነገረው መልኩ የሚከበር በዓል የለም፡፡ ያስተላለፉት መጠየቅ አለባቸው፡፡››
/የአባ ገዳ ተወካዮች/
  • ‹‹ኅብረተሰቡን ከእኛ ጋራ ሊያጣሉ የሚፈልጉ ግለሰብ አመራሮች አሉ፡፡… ለተላለፈው መልእክት ሓላፊነት የሚወስድ አካል ካልተገኘ፣ የመጋቢት ፭ ክብረ በዓል ከመድረሱ በፊት በስሕተት የተላለፈ መኾኑ ይገለጽልን፡፡››
/የገዳሙ አስተዳደር/
  • ‹‹እናንተ ሰላም ፍጠሩ፤ [በክብረ በዓሉ] ከተለመደው ውጭ አንዳችም የሚደረግ አይኖርም፤ ጥበቃውም እንዲጠናከር ይደረጋል፤ የተላለፈውን ዘገባ አጣርተን በኦሮምኛ እና በአማርኛ ማስተባበያ እንዲሰጥበት እናደርጋለን፡፡››
/የዞን የአስተዳደርና ጸጥታ ሓላፊዎች/

2015 ማርች 5, ሐሙስ

በዝቋላ ገዳም ዙሪያ የተቀሰቀሰው የእሳት ቃጠሎ እየተዛመተ ነው


  • የሄሊኮፕተር እገዛ አልያም የውኃ ቦቴ መኪኖች ድጋፍ እየተጠየቀ ነው


በምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት በዝቋላ ደብረ ከዋክብት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም፣ ትላንት ጠዋት የተቀሰቀሰው የእሳት ቃጠሎ አሞራ ገደልበሚባለው አቅጣጫ መዛመቱ ተገለጸ፡፡
በሰሜን በኩል ወንበር ማርያም እየተባለ በሚጠራው የገዳሙ መውጫ ትላንት ጠዋት 2፡00 የተቀሰቀሰው ቃጠሎ፣ በአዱላላ ወረዳ ሠራተኞችና በነዋሪው ሕዝብ ርብርብ ማምሻውን መጥፋቱ ከተገለጸ በኋላ ነው አሞራ ገደል በሚባለው የገዳሙ ደቡባዊ ገጽ በዛሬው ዕለት 5፡00 ላይ ዳግመኛ መቀስቀሱ የተሰማው፡፡
በገዳማውያኑ የጥሩንባ ልፈፋ በተሰባሰበው የገጠሩ ነዋሪና የወረዳው አስተዳደር ሠራተኞች እሳቱን አፈር በማልበስና በቅጠል በመተምተም  ለማጥፋት የተቻለ ቢመስልም አንድ የገዳሙ መነኰስ በስልክ እንዳስረዱት፣ ‹‹በደንብ ሳይጠፋ ቀርቶ የታፈነ ነበር፡፡ ዛሬ አሞራ ገደል ጫካ ውስጥ ገብቷል፡፡ ዛፉ እርጥበት አለው፤ ጢሱ ያፍናል፡፡››  
ቃጠሎው፣ በአካባቢው ከባድ ነፋስ እየበረታ ከገደሉ ሽቅብና ወደ ጎን ወደ አዱላላ አቅጣጫ የተወሰነ የደኑን ክፍልና እዳሪ መሬት እየበላ በአስጊ ፍጥነት እየተስፋፋ እንደሚገኝ ተጠቅሷል፡፡ አኹን ባለው አካሔድ ሳይገታ ወደ ምሥራቅ ከዞረና ጠበል ሜዳውን ካገኘ ወደ ደኑ በጥልቀት ስለሚገባ በእጅጉ አውዳሚ እንደሚኾን የገዳሙ መነኰስ ተናግረዋል፡፡
ከቦታው ገደላማ መልክአ ምድራዊ ገጽታ አንጻር የሚያፍነው ጢስና የቃጠሎው ፍጥነት የመከላከል ሥራውን አስቸጋሪ እንዳደረገው ያስረዱት የገዳሙ መነኰስ፣ አመቺ የሚኾነው አስቸጋሪውን ዐቀበት በመውጣት ለሰው ኃይሉ ውኃ ማቅረብ በሚችሉ መኪኖች አልያም በአየር ርጭትበመኾኑ ከደብረ ዘይት አየር ኃይል የሄሊኮፕተር አልያም የቦቴ መኪኖች እገዛ በሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ በኩል እንዲጠየቅ አመልክተዋል፡፡
የትላንቱን ቃጠሎ ለመከላከል በተደረገው ርብርብ ከደብረ ዘይት ከተማ ተጉዘው ሌሊቱን ቃጠሎው በጀመረበት ስፍራው የደረሱ ምእመናንየእሳቱን መስፋፋት የሚገቱ የመከላከል ሥራዎችን ሲሠሩ አድረው መመለሳቸው ተገልጧል፡፡ የከተማው ሰንበት ት/ቤቶችና የማኅበረ ቅዱሳን የወረዳው ማእከል አባላት፣ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች እንዲኹም ምእመናን÷ መሬቱን ቆፍሮ በአፈር የመከተር፣ ተቀጣጣይ ጉቶዎችንና ቁጥቋጦዎችን የመመንጠር የመከላከል ሥራ እስከ ንጋት ድረስ ሲሠራ ማደሩ ታውቋል፡፡
ዛሬ ቀትር ላይ መዛመቱ የታወቀውን ቃጠሎ ለማጥፋት ከገዳማውያኑ የድረሱልን ጥሪ መተላለፉን የገለጸ አንድ ምእመን፣ በከተማው በስምንቱም አጥቢያ አብያተ ክርስቲያን ሰንበት ት/ቤቶችና በሠርክ ጉባኤያት ምእመናንንና በጎ አድራጊዎችን በመቅስቀስና በማስተባበር በአፋጣኝ ወደ ስፍራው ለመድረስ ጥረት እንደሚደረግ ተናግሯል፡፡


zequulla
በምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊበን ዝቋላ ወረዳ አዱላላ ከተማ በሚገኘው የዝቋላ ደብረ ከዋክብት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም ዙሪያ የእሳት ቃጠሎ መቀስቀሱን የገዳሙ መነኰሳት እየተናገሩ ነው፡፡
ከጠዋቱ 2፡00 ገደማ የተቀሰቀሰው የእሳት ቃጠሎው የጀመረው ወንበር ማርያም እየተባለ በሚጠራው በገዳሙ ሰሜናዊ አቅጣጫ ነው፡፡
ይህ አቅጣጫ፣ የገዳሙ ሞፈር ቤት የሚገኝበት መውጫ መንገድ ሲኾን በአኹኑ ሰዓት በበርካታ ቦታዎች ጭስ እንደሚታይ በመነኰሳቱ ተገልጧል፡፡
የቃጠሎው መንሥኤ በውል ባይታወቅም እሳቱ በአካባቢው ባለው ከባድ የነፋስ ኃይል ወደ ገዳሙ መውጫና በገዳሙ ዙሪያ እንዳይስፋፋ ተሰግቷል፡፡
ziquwala_17የአቅራቢያው ነዋሪ ኅብረተሰብ በጥሩንባ በተላለፈው የድረሱልን ጥሪ የተሰባሰበ ሲኾን ወደ ወረዳው ጽ/ቤትም ተደውሎ የአስተዳደሩ አባሎችና የፖሊስ ኃይል በስፍራው መድረሳቸው ተገልጧል፡፡ ‹‹ቃጠሎውን በቅጠልና በአፈር ለመከላከልና መዛመቱን ለመቀነስ የነፋሱን ጋብ ማለት እየተጠባበቅን ነው ብለዋል፤›› አንድ የገዳሙ መነኰስ፡፡
በጥንታዊውና ታሪካዊው ገዳም ዙሪያ የእሳት ቃጠሎ ሲደርስ የአኹኑ የመጀመሪያ አይደለም፡፡ መጋቢት ፲ ቀን ፳፻፩ ዓ.ም. በደረሰው የእሳት ቃጠሎ እንደ አርዘ ሊባኖስና የሐበሻ ጥድ ያሉት አገር በቀል ዛፎች በስፋት ወድመዋል፡፡ መጋቢት ፰ ቀን ፳፻፬ ዓ.ም. የተቀሰቀሰው ቃጠሎ ደግሞ ተኣምራዊና ግራ አጋቢ ጠባይዕ የታየበት ነበር፡፡ በምሥራቃዊ አቅጣጫ በሚገኘው የመንግሥት ደን ውስጥ ተከሥቶ በአንድ ገጽ ኃይሉ ሲቀንስ በሌላ አቅጣጫ እየተዛመተ ገዳሙን ጨርሶ ለማጥፋት በተቃረበበት ኹኔታ ከአዲስ አበባ፣ ከቢሾፍቱና ከአዳማ በተመሙ የሰንበት ት/ቤት ወጣቶች፣ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች፣ በጎ አድራጊ ምእመናንና አካላት መተባበር እንዲኹም በመከላከያና በፖሊስ ኃይሎች እገዛ መገታቱ የሚታወስ ነው፡፡
በመጪው መጋቢት ወር መጨረሻ በገዳሙ የጠበል – ሐይቅ የኢሬቻን በዓል ለማክበርና በደብረ ዝቋላ የአባ ገዳ ሐውልት ለመትከል በኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት የባህልና ቱሪዝም ቢሮ መታቀዱንና በመንግሥት ብዙኃን መገናኛ መገለጹን ተከትሎ ቤተ ክርስቲያናችን በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ በኩል ለክልሉ ርእሰ መስተዳድር በጻፈችው ደብዳቤ ተቃውሞዋን በማሰማት ላይ እንዳለች ይታወቃል፡፡DSC_0642[1]ጥንታዊውና ታሪካዊው የዝቋላ ደብረ ከዋክብት ጻድቁ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም ዛሬ በሚታወቅበት ቦታ ላይ ከተገደመ ከ700 ዓመታት በላይ አስቆጥሯል፡፡ በገዳሙ ደጅ ጠኚውን፣ አፈር ጠባቂውንና የአብነት ትምህርት መምህራንና ደቀ መዛሙርትን ሳይጨምር እስከ 350 መነኰሳትና መነኰሳዪያት እንደሚገኙበት ተዘግቧል፡፡

ሰበር ዜና:- በዝቋላ ገዳም ዳግም የእሳት ቃጠሎ ተቀሰቀሰ


የካቲት 24 ቀን 2007 ዓ.ም.
በእንዳለ ደምስስ
abune gebre menfes kidus 004በደብረ ከዋክብት ዝቋላ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ አንድነት ገዳም ደን ላይ በዛሬው እለት የእሳት ቃጠሎ መቀስቀሱን ከገዳሙ የደረሰን መረጃ ያመለክታል፡፡

ከተራራው ሥር ከወንበር ማርያም እና አዱላላ አቅጣጫ የተነሳው ቃጠሎ በገዳሙ ደን ላይ ጉዳት ያደረሰ ሲሆን፤ ማኅበረ መነኮሳቱና ተማሪዎች፤ እንዲሁም የአካባቢው ምእመናንን ባደረጉት ርብርብ ለጊዜው አፈር በማልበስ ለማጥፋት ተችሏል፡፡ ነገር ግን በአካባቢው ካለው ነፋሻማና ሞቃታማ አየር ምክንያት ዳግም እንዳይቀሰቀስ ገዳማውያኑ እየተጠባበቁ እንደሚገኙ የገዳሙ አበምኔት አባ ገብረ ማርያም ገልጸዋል፡፡

'ዛሬ ጠዋት እየኾነ ያለው እንዲህ ነው'

2015 ማርች 4, ረቡዕ

የሆሳዕና ደብረ ገነት ቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን ተቃጠለች


አትምኢሜይል
የካቲት 23 ቀን 2007 ዓ.ም.
በዘማች አዩኔ /ከሆሳዕና ማእከል/
001 hosaen mariamበኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሀድያ እና ስልጤ ሀገረ ስብከት የሆሳዕና ደብረ ገነት ቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን የካቲት 21 ቀን 2007 ዓ.ም ከቅዳሴ በኋላ ድንገተኛና ለጊዜው መንስኤው ባልታወቀ ሁኔታ ተቃጠለች፡፡

የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ወርኃዊ በዓል ለማክበር ምእመናን በቤተ ክርስቲያን ተገኝተው የቅዳሴ ሥነ-ሥርዓት እንደተጠናቀቀ እና ቡራኬ ተቀብለው ወደየቤታቸው በተመለሱ በ20 ደቂቃ ውስጥ ካህናት እና ዲያቆናት ገና በደጀ ሰላም እያሉ ከቤተ መቅደሱ ውስጥ ቃጠሎው እንደጀመረም ተናግረዋል፡፡

በወቅቱ ሁሉም የቤተ ክርስቲያኗ በሮች ከውጭ ተቆልፈው ስለነበር ቁልፎቹን በቅርበት ለማግኘት ስላልተቻለ እሳቱን ቶሎ በቁጥጥር ለማዋል አልተቻለም፡፡ በዚህም ምክንያት በውስጥ የነበሩት ንዋያተ ቅድሳት ሙሉ ለሙሉ ወድመዋል፡፡

የደብሩ ካህናትና ዲያቆናት የቤተ ክርስቲያኗን በር ሰብረው በመግባት በዕለቱ ቅደሴ የተቀደሰበትን ታቦት አፈር በማልባስ ከእሳቱ ለመከላከል ተችሏል፡፡

ከተመሠረተች ከአንድ መቶ ዓመት በላይ ያስቆጠረችው ቤተ ክርስቲያን በቃጠሎው ሙሉ በሙሉ ብትወድምም በቤተ መቅደስ ውስጥ የነበሩት ታቦታት ምንም ዓይነት ጉዳት ሳይደርስባቸው በእግዚአብሔር ቸርነት ተርፈዋል፡፡

ከቃጠሎው የተረፉት ታቦታት እሳቱ ከጠፋ ከሦስት ሰዓታት በኋላ በካህናት፣ በዲያቆናት እና ምዕመናን ታጅበው ለጊዜው ወደተዘጋጀላቸው ማረፊያ ገብተዋል፡፡

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሀድያ እና ስልጤ ሀገረ ስብከት የሆሳዕና ደብረ ገነት ቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን የተመሠረተችው በ1901 ዓ.ም ሲሆን፤ አካባቢው በሌሎች የእምነት ድርጅቶችና እና በ ኢ-አማንያን የተከበበ በመሆኑ ምእመናን በሃይማኖት በምግባር ጸንተው እንዲኖሩ በደብሩ በተለያዩ ጊዜያት ጉባኤ በማዘጋጀት የተጠናከረ የስብከተ ወንጌል አገልግሎት ሲሰጥበት የቆየ ቦታ ነው፡፡

e

2015 ፌብሩዋሪ 20, ዓርብ

ከመረጥሁት ጋር ቃል ኪዳኔን አደረግሁ መዝ.88-3

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ለእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከፍተኛ ክብር ትሰጣለች፡፡ ክብሯ ልዕልናዋን ዘውትር በጸሎት፣በምስጋና ትጠራለች፡፡በስሟ በዓላትን ታከብራለች፡፡አጽዋማትን በሰሟ ስይማ ልጆቿ እንዲጾሙ ታረድጋለች፡፡ልጇ ኢየሱስ ክርስቶስ ዓለምን ለማዳን ወደዚህ ዓለም ሲመጣ እርሷ የነበራትን የድኅነት ተሳትፎና ቃልኪዳን ትዘክራለች፡፡ በስሟ ጽላት ቀርጻ፣ቤተክርስቲያን ሰይማ፣በስዓላት፣ በመጻሕፍት አማለጅነቷን ክብሯን ለልጅ ልጅ ታስተላልፋለች፡፡
ከስሟ ጋር ዘርፍ /ቅጽል/ በማድረግ ንጽሕናዋን፣ ቅድስናዋን፣ ድንግልናዋን፣ ወዘተ ይወሳል ፣ይጣራል፣ይጸለያል፡፡ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን አመስጥረው ከተረጐሙት መካከል፡- ምልዕተ ጸጋ፡- እግዚአብሔር አባታችን አዳምን ከፍጥረት ሁሉ አልቆ በአርአያውና በአምሳሉ ፈጥሮት ነበር፡፡ ነገር ግን በኃጢአት ምክንያት የተሰጠው ሙሉ ጸጋ ተገፈፈ፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከፍጥረት ሁሉ ተመርጣ ከእናቷ ማኅፀን ጀምሮ እግዚአብሔር የጠበቃት፣ ያደረባት «የከተመባት ረቂቅ ከተማ» መሆኗን መልአኩ በመሰከረበት ቃል «ምልዕተ ጸጋ» እያልን እንጠራታለን፡፡ ሉቃ.1-26፡፡ እመቤታችን የተለየች ናትና «ጸጋ የሞላብሽ» /የጸጋ ግምጃ ቤት/ ተብላለች፡፡
እምነ ጽዮን፡- እግዚአብሔር ወልድ ኢየሱስ ክርስቶስን አባት «አባታችን ሆይ» ብለን እንደምንጠራው ሁሉ ወላዲተ አምላክንም እናታችን ብለን እንጠራታለን፡፡ ማቴ.6-9፡፡ ቅዱስ ዳዊትም «እምነ ጽዮን ይብል ሰብእ፡ ሰው ሁሉ እናታችን ጽዮን ይላል» በማለት እመቤታችን አማናዊት ጽዮን መሆኗን አስረድቷል፡፡ መዝ.86-5፡፡ እምነ ጽዮን ማለት እናታችን ጽዮን ማለት ነው፡፡ በመጀመሪያይቱ የሰው ልጆች ሁሉ እናት ሔዋን አማካኝነት ከርስታችን ወጥተን መጠጊያ አጥተን ነበር በዳግማዊቱ ሔዋን በድንግል ማርያም ደግሞ ወደ ርስታችን ተመልሰናልና እናታችን ጽዮን እንላታለን፡፡ ጽዮን ማለት አንባ መጠጊያ ማለት ነው፡፡
መጽሐፍ ቅዱስም ድንግል ማርያምን ጽዮን በማለት ይጠራታል፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት «እግዚአብሔር ጽዮንን መርጦአታልና ማደሪያውም ትሆን ዘንድ ወድዶአታልና እንዲህ ብሎ ይህች የዘላለም ማደሪያዬ ናትና በዚህች አድራለሁ፡፡» መዝ.131-13፡፡ በማለት የተናገረው ትንቢት ፍጻሜ ልዑል እግዚአብሔር ከሴቶች ሁሉ ለይቶ ድንግል ማርያምን ለእናትነት የመረጣት መሆኑንና ማደሪያውም ትሆነው ዘንድ የወደዳት መሆኑን የሚያስገነዝብ ነው፡፡ መዝ.47-12፤86-5፡፡
መድኃኒታችን በዕለተ ዓርብ በቀራንዮ በመስቀሉ ላይ ሳለ ለፍቁረ እግዚእ ዮሐንስ «እነኋት እናትህ» በማለት በደቀ መዝሙሩ አማካኝነት እናቱን ድንግል ማርያምን ሥጋውን ለቆረሰላቸው ደሙን ላፈሰሰላቸው ምእመናን እናት ትሆን ዘንድ ሰጥቷታልና ፡፡ ጽዮን የድንግል ማርያም ስም ነውና ጌታችን እናት አድርጎ የሰጠንን እመቤት እምነ ጽዮን /እናታችን ጽዮን/ እንለታለን፡፡
እመ ብርሃን፡- እመ ብርሃን ማለት የብርሃን እናት ማለት ነው፡፡ «እኔ የዓለም ብርሃን ነኝ» ያለውን ብርሃነ ዓለም /የዓለም ብርሃን/ መድኃኔ ዓለም ክርስቶስን የወለደች ናትና የብርሃን እናቱ /እመ ብርሃን/ ትባላለች፡፡ ዮሐ.8-22፡፡ ጌታውን ይወድድ የነበረና ጌታውም ይወደው የነበረ የከበረ ደቀ መዝሙር ቅዱስ ዮሐንስ «ለሰው ሁሉ የሚያበራው እውነተኛው ብርሃን ወደ ዓለም ይመጣ ነበር፡፡» በማለት የመሰከረለትን ጌታ በብሥራተ መልአክ በግብረ መንፈስ ቅዱስ አማናዊውን /እውነተኛውን/ ብርሃን ጌታችንን ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን ጸንሳ የወለደች በመሆኗ እመ ብርሃን እንላታለን፡፡ ሊቁ «እመ ብርሃን አንቲ ነዓብየኪ በስብሐት ወበውዳሴ፡- አምላክን የወለድሽ እመቤታችን ሆይ የብርሃን እናት ነሽና አንቺን በክብር በምስጋና እናገንሻለን» በማለት እንዳመሰገናት፡፡
ሰአሊተ ምሕረት፡- ሰዓሊተ ምሕረት ማለት ምሕረትን የምትለምን ማለት ነው፡፡ በቅዱስ ገብርኤል ምስክርነት እንደምናገኘው ድንግል ማርያም በእግዚአብሔር ፊት ሞገስን ያገኘች እመቤት ናትና ልመናዋ /ምልጃ ጸሎቷ/ ይሰማል የእናት ልመና አንገት አያስቀልስ ፊት አያስመልስ ነውና፡፡ ሉቃ.1-30፡፡
በእግዚአብሔር ፊት ሞገስ ያገኙ ቅዱሳን ምሕረት ቸርነትን ለምነው አግኝተዋል፡፡ ዘፍ.18-3፣ 23-32፡፡ እግዚአብሔር ሙሴን በፊቴ ሞገስን ስላገኘህ በስምህ ስላወቅሁህ ስለ ሕዝቡ የለመንኸኝን ሁሉ አደርጋለሁ ብሎታል፡፡ ዘጸ.33-12-20፡፡ «ስለ ሙሴ ቃልም ዘወትር ለሕዝቡ ይራራላቸው ነበር» ዘጸ.32-11-14፡፡ ሙሴ በእግዚአብሔር ፊት ሞገስ በማግኘቱ በለመነ ጊዜ እግዚአብሔር እንደ ቃልህ ይቅር አልሁ ይለው ነበር፡፡ ዘኁ.14-20፡፡ በመልአከ ብሥራት በቅዱስ ገብርኤል «በእግዚአብሔር ፊት ሞገስ አግኝተሻል» ተብሎ የተመሰከረላት ድንግል ማርያም የተሰጣት ሞገስ እንደ እናትነቷ ከሁሉ የበለጠ በመሆኑ አጠያያቂ አይደለምና ሰአሊተ ምሕረት እንላታለን፡፡ ማርያም ንጽሕት ድንግል ወላዲተ አምላክ ዠማዕምንት ሰአሊተ ምህረት ለውሉደ ሰብእ፡- ንጽሕት ድንግል ማርያም የታመነች አምላክን የወለደች ናት ለሰዎች ልጆችም የምሕረት አማላጅ ናት» /ውዳሴ ማርያም ዘዓርብ አንቀጽ 6/
እመቤታችን፡- እመቤት ማለት በአንድ ቤተሰብ መካከል አስተዳዳሪና ሓላፊ የሆነች ታላቅ ሴት ማለት ነው፡፡ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን «ማርያም» የሚለውን በምሥጢራዊ ዘይቤ ሲተረጉሙ እግዝእተ ብዙኃን /የብዙኀን እመቤት/ ብለው ተርጉመውልናል፡፡
በአዳምና በሄዋን አማካኝነት ወደ ዓለም የገባውን መርገም የሻረ ጌታ እግዚአብሔር ከእርስዋ በመወለዱ እምቤታችን /የብዙዎች እመቤት/ ትባላለች፡፡ ሮሜ.5-6-11፡፡ እንዲሁም ዓለም ሁሉ በዳነበት በክርስቶስ የማዳን ሥራ ያመን ክርስቲያኖች ሁሉ በክርስቶስ አንድ ቤተሰብ በመሆናችን ቅድስት እናቱ ድንግል ማርያም እመቤታችን ናት፡፡ ዮሐ.19-26፡፡ ልጇ ጌታችን ነውና እርሷም እመቤታችን ናት፡፡ ሉቃ.1-43፡፡
ቤዛዊተ ዓለም፡- የዓለም መድኃኒት ማለት ነው ድንግል ማርያም የዓለም መድኃኒት ኢየሱስ ክርስቶስን ያስገኘችልን በመሆኗ ቤዛዊተ ዓለም እንላታለን በልጇ ቤዛነት ድነናልና፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለቤዛ ዓለም /ለድኅነተ ዓለም/ በቀራንዮ ኮረብታ የቆረሰው ሥጋ ያፈሰሰው ደም ከድንግል ማርያም የነሣው በመሆኑ ቤዛዊተ ዓለም ትባላለች፡፡ ዕብ.9-22፡፡ የሕያዋን ሁሉ እናት ድንግል ማርያም ለሔዋን ካሣዋ እንደሆነች ሁሉ ለአንስተ ዓለም ሁሉ ካሣ ቤዛ ናት ስድበ አንስትን ወቀሳ ከሰሳ አንስትን አስቀርታለችና፡፡ እንዲሁም ለዓለሙ ሁሉ የምታማልድ በልመናዋ ፍጥረትን የምታስምርና መንግሥተ ሰማያት መርታ የምታስገባ በመሆኗ ቤዛዊተ ዓለም እንላታለን፡፡
ወላዲተ አምላክ፡- ወላዲተ አምላክ ማለት አምላክን የወለደች ማለት ነው፡፡ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል «ከአንቺ የሚወለደው ቅዱሱ የእግዚአብሔር ልጅ ይባላል፡፡» በማለት የጌታችንን አምላክ ወልደ አምላክነት የድንግል ማርያምን እመ አምላክ ወላዲተ አምላክነት አስረድቶአል፡፡ ሉቃ.1-35 ቅድስት አልሳቤጥም «የጌታዬ እናት ወደ እኔ ትመጣ ዘንድ እንዴት ይሆንልኛል?» ሉቃ.1-44 በማለት እንዳስረዳችው ድንግል ማርያም ጌታችንን የወለደች የጌታችን እናት ናትና ወላዲተ አምላክ እንላታለን፡፡ ድንግል ማርያም «ወላዲተ አምላክ» «አምላክን የወለደች» ተብላ እንድትጠራ ለመጀመሪያ ጊዜ በ431 ዓ.ም በኤፌሶን ከተማ በ200 ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን አማካኝነት ተዘጋጅቶ በቅዱስ ቄርሎስ አፈ ጉባኤነት የተመራው 3ኛው ዓለም አቀፋዊ የቤተ ክርስቲያን ሲኖዶስ ነው፡፡

በዚህ ጉባኤ የቀረበው የንስጥሮስ የክህደት ትምህርት «ድንግል ማርያም ወላዲተ አምላክ ልትባል አይገባትም» የሚል ሲሆን ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ንስጥሮሳዊውን ትምህርት አውግዘው ድንግል ማርያም ቅድመ ዓለም የነበረውን አምላክ ለዘመን በሥጋ ስለወለደችው በእውነት አምላክን የወለደች /ወላዲተ አምላክ/ ናት በማለት ትምህርተ ሐዋርያትን አጽንተዋል፡፡

በቤተ ልሔም በከብቶች ግርግም ከድንግል የተወለደው የዓለም ፈጣሪ እግዚአብሔር ነው፡፡ ስለዚህ ድንግል ማርያም ፣ እመ እግዚአብሔር ፣ ወላዲተ አምላክ ተብላ ትጠራለች፡፡ 1ዮሐ.5-20፤ ቲቶ.2-13፡፡

ቅድስተ ቅዱሳን፡- ይህ ስም ከፍጡራን በላይ ከፈጣሪ በታች ለሆነች ቅድስት ድንግል ማርያም ንጽሕናና ቅድስና መገለጫ ሆኖ የተሰጣት ልዩ ስም ነው፡፡ ቅድስተ ቅዱሳን ማለት ከተለዩ የተለየች ከተመረጡ የተመረጠች፣ ከተከበሩ የተከበረች ማለት ነው፡፡ ሊቁ ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊ ድንግል ማርያምን ባመሰገነበት ክፍል ተሰመይኪ ፍቅርተ ኦ ቡርክት እምአንስት አንቲ ውእቱ ዳግሚት ቀመር እንተ ትሰመይ ቅድስተ ቅዱሳን፡- ከሴቶች ሁሉ ተለይተሽ የተባረክሽ ሆይ የተወደድሽ ተባልሽ ከተለዩ የተለየሽ» በማለት ቅድስናዋን መስክሯል /የእሑድ ውዳሴ ማርያም አንቀጽ 1/
ከአንስተ ዓለም ተለይተው ቅድስናን ገንዘብ ያደረጉ በርካታ ሴቶች ቢኖሩም ድንግል ማርያም ግን የነዚህ ሁሉ ፊት አውራሪ /ግንባር ቀደም/ እና ከሌሎች አንስት የተለየች ቅድስት /ቅድስተ ቅዱሳን/ ትባላለች፡፡ «አንቺ ከሴቶች ሁሉ ተለይተሽ የተባረክሽ ነሽ» በማለት መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል መስክሮላታል፡፡ ሉቃ.1-28፡፡ ከዚህም ጋር በተግባረ ቃል ቅዱስ ኤፍሬም በውዳሴው «የዐቢ ክብራ ለማርያም እምኲሎሙ ቅዱሳን፡- ከቅዱሳን ክብር የማርያም ክብር ይበልጣል» / ዘረቡዕ ውዳሴ ማርያም አንቀጽ .7/ በማለት የድንግል ማርያምን ቅድስና መስክሯል፤ ከዚህም የተነሳ በከበረ ስሟ ቅድስተ ቅዱሳን እያልን እንጠራታለን፡፡
ንጽሕተ ንጹሐን፡- ነጽሐ ነጻ ካለው ግሥ የወጣ ሲሆን ንጽሕት ማለትም የነጻች የጠራች ማለት ነው፡፡ ቅዱሳት መጻሕፍት ስለ ንጽሕና «ዘንጹሕ ልቡ ወንጹሕ እደዊሁ፡- እጆቹም ልቡም ንጹሕ የሆነ»፣ «ብፁዓን ንጹሓነ ልብ ወይለብሱ ንጹሐ፡- ልበ ንጹሖች ብፁዓን ናቸው ንጽሕናን ይለብሳሉ»፣ «ሕያዋት ወንጹሓት፡- ሕያዋንና ንጹሓን»፣ «ንጽሕት ወብርህት፡- የነጻች የምታበራ» በማለት የንጽሕናን ሁኔታ ያስረዳሉ፡፡ መዝ.23፣ ማቴ.5-8፣ ራእ.15፣ ዘሌ.14-4፡፡ ውዳሴ ማርያም ዘአርብ፡፡
በዚህ ዓለም ከሚኖሩ ሴቶች የልማደ አንስት ኃጢአት ሰውነታቸውን ያላጐደፋቸው ወይም ያላረከሳቸው ብዙዎች ናቸው፡፡ ይሁንና ከገቢረ ኃጢአት ንጹሓን ይሁኑ እንጂ ከነቢብና ከሐልዮ ኃጢአት /በመናገርና በማሰብ ከሚሠራ ኃጢአት/ አልነጹም፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ግን ከገቢር ከነቢብ ከሐልዮ ኃጢአት ንጽሕት ስለሆነች ንጽሕተ ንጹሐን እንላታለን፡፡
ወትረ ድንግል /ዘላለማዊት ድንግል/፡- ቅድስተ ቅዱሳን ወላዲተ አምላክ ማርያም ጌታን ከመጽነሷ በፊት፤ ጌታን በጸነሰች ጊዜ፤ ከጸነሰችም በኋላ፤ ከመውለዷ በፊት፤ በወለደች ጊዜ፣ ከወለደች በኋላ ድንግል ናት ከዚህም የተነሳ ድንግል ዘላለም እንላታለን፡፡ ክህነትን ከነቢይነት ጋር አስተባብሮ የያዘው ሕዝቅኤል ዘላለማዊ ድንግልናዋን መስክሯል፡፡ ሕዝ.44-1-2፡፡
የአንጾኪያው ሊቀ ጳጳስ ቅዱስ ሳዊሮስ ስለ ቅድስት ድንግል ማርያም ዘላለማዊ ድንግልና በተናገረበት ክፍል «አምላክን የወለደች ማርያም ለዘለዓለሙ ድንግል እንደሆነች መውለዷም የማይመረመር ድንቅ እንደሆነ ከወለደችም በኋላ በድንግልና ጸንታ እንደኖረች አስረዳን» በማለት ስለ ዘላለማዊ ድንግልናዋ መስክሯል፡፡ ኢሳ.7.14፤ ሉቃ.1.27፡፡
ድንግል በክልኤ፡- በሁለት ወገን ድንግል ማለት ነው፡፡ በሁለት ወገን በሥጋም በነፍስም በሐልዮ /በሐሳብ/ በገቢር /በመሥራት/ በውስጥ በአፍአ ድንግል መሆኗን ያመለክተናል፡፡
ሌሎች ሰዎች ከገቢር ከነቢብ ቢጠበቁ ከሐልዮ /ከሃሳብ/ ኃጢአት መጠበቅ ግን አይቻላቸውም፡፡ ድንግል ማርያም ግን በሁለት ወገን ንጽሕት ቅድስት ናት ስለዚህ ድንግል በክልኤ /በሁለት ወገን ድንግል/ ትባላለች፡፡


ድንግል ወእም፡- እናትም ድንግልም ማለት ነው፡፡ እናትነትን ከድንግልና ጋር አስተባብሮ መገኘት ለፍጥረታዊ ሰው የማይቻል ቢሆንም ድንግል ማርያም ግን ሁለቱንም አስተባብራ ይዛለችና ድንግል ወእም ትባላለች፡፡
ሴቶች በልጅ ጸጋ ከከበሩ ድንግልናቸውን ያጣሉ በድንግልና ተወስነው ጸጋ እግዚአብሔርን ለማግኘት ከወሰኑ ደግሞ ከልጅ ጸጋ ይለያሉ፡፡ ሁለቱንም አስተባብረው ይዘው መገኘት አይሆንላቸውም፡፡ ድንግል ማርያም ግን ድንግልናን ከእናትነት እናትንትን ከድንግልና ጋር አስተባብራ ይዛ የተገኘች በመሆንዋ ድንግል ወእም እናትም ድንግልም ሆናለች፡፡ ሉቃ.1-26-38፡፡
ልጇ ክርስቶስም አምላክ ወሰብእ /ፍጹም አምላክ ፍጹም ሰው/ ሲባል እንዲኖር እርሷም ድንግል ወእም ስትባል ትኖራለች ስትወልደው ማኅተመ ድነግልናዋ እንዳልተለወጠ ሁሉ ባሕርየ መለኮቱ አልተለወጠም «እኔ እግዚአብሔር አልለወጥም» እንዳለ፡፡ ሚል.3-6፡፡


ኪዳነ ምሕረት፡- የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር መዓቱን በምህረት ቁጣውን በትዕግሥት በመመለስ የሰውን ሕይወት ለዘለዓለሙ ለመጠበቅ በመጀመሪያ ከስህተቱ በንስሐ ከተመለሰው ከአዳም፣ ቀጥሎም ከጻድቁ ከኖኅ፣ ከዚያም በእምነትና በምግባሩ ቀናነት የእግዚአብሔር ወዳጅ ተብሎ ከተሰየመው ከአብርሃም.... ከሌሎችም ቅዱሳን ጋር ለመላው የሰው ዘር የሚሆን የምህረትና የበረከት ቃል ኪዳን ገብቷል፡፡
«ከመረጥሁት ጋር ቃል ኪዳኔን አደረግሁ» መዝ.88-3 በማለት በተናገረው መሠረት ከምርጦቹ ጋር ቃል ኪዳን የሚያደርግ ልዑል አምላክ ከተመረጡ የተመጠረች በመሆኗ /ዋ/ ከእናቱ ከቅድስት ድንግል ማርያም ጋር የካቲት 16 ቀን ቃል ኪዳን ሰጥቷታል፡፡ ለዚህም በየዓመቱ የካቲት 16ቀን በዓለ ንግሥ ወር በገባ በ16 ቀን ወርኃዊ በዓሏን እናከብራለን፡፡
ይህንንም ለማመልከት ኪዳነ ምሕረት /የምሕረት ቃል ኪዳን የተቀበለች/ ትባላለች፡፡ በዚህም ምክንያት፡-
በእንተ ማርያም መሐረነ ክርስቶስ 
ቅድስት ሆይ ለምኝልን
በእንተ ስማ ለማርያም ወዘተ
በማለት የተሰጣትን ቃል ኪዳን መማጸኛ በማድረግ እንጠራታለን፡፡ ምሳሌዋ የሆነች ሐመረ ኖኅ /የኖኅ መርከብ/ በተሰጣት ቃል ኪዳን ከማየ አይኅ /ከጥፋት ውኃ/ ነፍሳትን እንደ አዳነች ቅድስት ድንግል ማርያምም በተሰጣት ቃል ኪዳን ከመከራ ሥጋ ከመከራ ነፍስ ታድነናለችና ኪዳነ ምሕረት /የምሕረት ቃል ኪዳን/ የተሰጠሽ እንላታለን፡፡


ከላይ የተጠቀሱት ሁሉም ምሥጢራዊና ትርጉም ያላቸው የእመቤታችን ስሞች የተገለጹት /የተነገሩት/ በራሱ በልዑል እግዚአብሔር እንዲሁም በቅዱሳን ነቢያት፣ በቅዱሳን ሐዋርያት፣ በቅዱሳን ጻድቃን ሰማዕታትና በሌሎችም ቅዱሳን አባቶች ነው፡፡
ይህም ምሥጢር የትምህርተ ሃይማኖት አንዱ አካል ሲሆን እኛም በቅዱሳን የተገለጸውን የእመቤታችንን ምሥጢራዊና ትርጉም ያላቸው ስሞች ተረድተን የትምህርተ ሃይማኖት ዕውቀታችንን ልናሳድግ ቅድስት ድንግል ማርያምንም ልናከብር እንዲገባን መገንዘብ አለብን፡፡ የቅዱሳንም አስተምህሮት ይህ ነውና፡፡
ረድኤቷ፣ በረከቷ፣ አማላጅነቷ አይለየን፡፡


አትምኢሜይል

ቅድስት(የዐቢይ ጾም ሁለተኛ ሳምንት)

የካቲት 12 ቀን 2007 ዓ.ም.


የዕለተ ሰንበት መዝሙር (ከጾመ ድጓ)
ግነዩ ለእግዚአብሔር ወጸውዑ ስሞ ወንግርዎሙ ለአሕዛብ ምግባሮ ሀቡ ስብሐተ ለስሙ አክብሩ 
ሰንበተ ተገበሩ ጽድቀ ዝግቡ ለክሙ መዝገበ ዘበሰማያት ኅበ ፃፄ ኢያማስኖ ወኢይረክቦ ሰራቂ ድልዋኒክሙ ንበሩ ዘበላዕሉ ጸልዩ ኀበ ሀሎ ክርስቶስ፡፡

ትርጉም:- ለእግዚአብሔር ተገዙ ስሙንም ጥሩ ሥራውንም ለአሕዛብ ንገሯቸው ለስሙም ምስጋናን ስጡ /አቅርቡ/ ሰንበትን አክብሩ እውነትንም አድርጉ ብል የማያበላሸው ሌባም የማያገኘው በሰማያት ያለ መዝገብን ለእናንተ ሰብስቡ፤ ተዘጋጅታችኹም ተቀመጡ ክርስቶስ ወዳለበት ወደ ላይ አስቡ፡፡

ምንባባት
መልዕክታት
1ኛ ተሰ.4÷1-12:- አሁንም ወንድሞቻችን ሆይ÷ በእኛ ዘንድ እንደ ታዘዛችሁ በሚገባ ትሄዱ ዘንድ÷ እግዚአብሔርንም ደስ ታሰኙ ዘንድ÷ ደግሞ እንደ ሄዳችሁ ከፊት ይልቅ በዚሁ ታበዙና ትጨምሩ ዘንድ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ እንነግራችኋለን፤ እንማልዳችኋለንም፡፡ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስም ያዘዝናችሁን ትእዛዝ ታውቃላችሁ፡፡

የእግዚአብሔር ፈቃድ ይህ ነውና፤ እርሱም ከዝሙት ትርቁ ዘንድ መቀደሳችሁ ነው፡፡ ሁሉም እያንዳንዱ ገንዘቡን ይወቅ፤ በንጽሕናና በክብርም ይጠብቀው፡፡ እግዚአብሔርን እንደማያውቁት እንደ አረማውያንም በፍትወት ድል አትነሡ፡፡ ይህንም ለማድረግ አትደፋፈሩ፤ በሁሉም ወንድሞቻችሁን አትበድሉ፤ አስቀድሜ እንደ ነገርኋችሁና እንደ አዳኘሁባችሁ÷ በዚህ ሁሉ እግዚአብሔር የሚበቀል ነውና፡፡ እግዚአብሔር ለቅድስና እንጂ ለርኲሰት አልጠራንምና፡፡ አሁንም የሚክድ÷ መንፈስ ቅዱስን የሰጣችሁን እግዚአብሔርን እንጂ ሰውን የካደ አይደለም፡፡

ባልንጀሮቻችሁን ስለ መውደድ ግን ልንጽፍላችሁ አያስፈልጋችሁም፤ እርስ በርሳችሁ እንድትዋደዱ ራሳችሁ በእግዚአብሔር የተማራችሁ ናችሁና፡፡ በመቄዶንያ ሁሉ ካሉት ወንድሞቻችን ሁሉ ጋር እንዲሁ ታደርጋላችሁ፤ ነገር ግን ወንድሞቻችን ሆይ÷ ትበዙና ትጨምሩ ዘንድ÷ ሥራችሁንም ታከናውኑ ዘንድ እንደ አዘዝናችሁም በእጃችሁ ትሠሩ ዘንድ÷ በውጭ ባሉት ሰዎችም ዘንድ ከማንም አንዳች ሳትሹ በሚገባ ትመላለሱ ዘንድ እንለምናችኋለን፡፡

1ኛጴጥ.1÷13:- ፍጻ. ስለዚህ የልቡናችሁን ወገብ ታጥቃችሁና ነቅታችሁ ኑሩ፤ ኢየሱስ ክርስቶስም ሲገለጥ የምታገኙትን ጸጋ ፈጽማችሁ ተስፋ አድርጉ፡፡ እንደሚታዘዙ ልጆች ባለማወቃችሁ አስቀድሞ የኖራችሁበትን ክፉ ምኞት አትከተሉ፡፡ ነገር ግን የጠራችሁ ቅዱስ እንደ ሆነ እንዲሁ እናንተም በአካሄዳችሁ ሁሉ ቅዱሳን ሁኑ፡፡ “እኔ ቅዱስ ነኝና ቅዱሳን ሁኑ” የሚል ተጽፎአልና፡፡ ለሰው ፊትም ሳያዳላ በእያንዳንዱ ላይ እንደ ሥራው የሚፈርድ አብን የምትጠሩት ከሆነ በሕይወታችሁ ዘመን ሁሉ በፍርሃት ኑሩ፡፡

ከአባቶቻችሁ ከወረሳችሁት ከማይረባና ከማይጠቅም ሥራችሁ የተቤዣችሁ በሚጠፋ በወርቅ ወይም በብር እንዳይደለ ታውቃላችሁ፡፡ ነውርና እድፍ እንደ ሌለው እንደ በግ ደም በክርስቶስ ክቡር ደም ነው እንጂ፡፡ ዓለም ሳይፈጠር የታወቀ÷ በኋላ ዘመን ስለ እናንተ የተገለጠ፡፡ ከሙታን ለይቶ በአስነሣው÷ ክብርንም በሰጠው በእግዚአብሔር በእርሱ ቃል ያመናችሁ÷ አሁንም እምነታችሁና ተስፋችሁ በእግዚአብሔር ይሁን፡፡

ሳትጠራጠሩ በፍጹም ልቡናችሁ ወንድሞቻችሁን ትወድዱ ዘንድ÷ ለእውነት በመታዘዝ ሰውነታችሁን አንጹ፤ እርስ በእርሳችሁም ተፋቀሩ፡፡ ዳግመኛ የተወለዳችሁት ከሚጠፋ ዘር አይደለም፤ በሕያውና ለዘለዓለም በሚኖር በእግዚአብሔር ቃል ከማይጠፋ ዘር ነው እንጂ፡፡

ግብረ ሐዋርያት
የሐዋ.10÷17-29፡- ጴጥሮስም ስለ አየው ራእይ ምን እንደሆነ ሲያወጣና ሲያወርድ ከቆርኔሌዎስ ተልከው የመጡ ሰዎች የስምዖንን ቤት እየጠየቁ በደጅ ቁመው ነበር፡፡

ተጣርተውም፡- ጴጥሮስ የተባለ ስምዖን በእንግድነት በዚያ ይኖር እንደሆነ ጠየቁ፡፡ ጴጥሮስም ስለ ታየው ራእይ ሲያወጣ ሲያወርድ መንፈስ ቅዱስ እንዲህ አለው÷ “እነሆ÷ ሦስት ሰዎች ይፈልጉሃል፡፡ ተነሥና ውረድ፤ ምንም ሳትጠራጠር ከእነርሱ ጋር ሂድ፤ እኔ ልኬአቸዋለሁና፡፡” ጴጥሮስም ወደ እነዚያ ሰዎች ወረደና÷ “እነሆ÷ የምትፈልጉኝ እኔ ነኝ፤ ለምን መጥታችኋል?” አላቸው፡፡

እነርሱም÷ “የመቶ አለቃ ቆርኔሌዎስ እግዚአብሔርን የሚፈራ ጻድቅ ሰው ነው፤ ቅዱስ መልአክ ተገልጦ አንተን ወደ ቤቱ እንዲጠራህ የምታስተምረውንም እንዲሰማ አዝዞታል፤” አሉት፡፡ እርሱም ተቀብሎ አሳደራቸው፤ በማግሥቱም ተነሥቶ አብሮአቸው ሄደ፤ በኢዮጴ ከተማ ከሚኖሩት ወንድሞችም አብረውት የሄዱ ነበሩ፡፡ በማግሥቱም ወደ ቂሳርያ ከተማ ገባ፤ ቆርኔሌዎስም ዘመዶቹንና የቅርብ ወዳጆቹን ጠርቶ ይጠብቃቸው ነበር፡፡

ጴጥሮስም በገባ ጊዜ ቆርኔሌዎስ ተቀበለው፤ ከእግሩ በታችም ወድቆ ሰገደለት፡፡ ጴጥሮስም÷ “ተነሥ እኔም እንደ አንተው ሰው ነኝ” ብሎ አነሣው፡፡ ከእርሱም ጋር እየተነጋገረ ገባ፤ ወደ እርሱም የመጡ ብዙ ሰዎችን አገኘ፡፡ ጴጥሮስም እንዲህ አላቸው÷”ለአይሁዳዊ ሰው ሄዶ ከባዕድ ወገን ጋር መቀላቀል እንደማይገባው ታውቃላችሁ፤ ለእኔ ግን ከሰው ማንንም ቢሆን እንዳልጸየፍና ርኩስ ነው እንዳልል እግዚአብሔር አሳየኝ፡፡ አሁንም ስለላካችሁብኝ ሳልጠራጠር ወደ እናንተ መጣሁ፤ በምን ምክንያት እንደ ጠራችሁኝ እጠይቃችኋለሁ፡፡”

ምስባክ
መዝ.95÷5 እግዚአብሔርሰ ሰማያተ ገብረ አሚን ወሠናይት ቅድሜሁ ቅድሳት ወዕበየ ስብሐት ውስተ መቅደሱ

ትርጉም፦ እግዚአብሔር ግን ሰማያትን ሠራ ምስጋና ውበት በፊቱ ቅዱሰነትና ግርማ በመቅደሱ ውስጥ ናቸው፡፡

ወንጌል
ማቴ.6÷16-24፡- “በምትጾሙበት ጊዜ እንደ ግብዞች አትጠውልጉ፤ እነርሱ እንደ ጾሙ ለሰው ይታዩ ዘንድ መልካቸውን ይለውጣሉና÷ እውነት እላችኋለሁ ዋጋቸውን ተቀብለዋል፡፡ እናንተስ በምትጾሙበት ጊዜ ራሳችሁን ቅቡ፤ ፊታችሁንም ታጠቡ፡፡ በስውር ለሚያይ ለአባታችሁ እንጂ÷ ለሰዎች እንደ ጾማችሁ እንዳትታዩ፤ በስውር የሚያያችሁ አባታችሁም ዋጋችሁን በግልይ ይሰጣችኋል፡፡

“ብልና ነቀዝ በሚያበላሹት÷ ሌቦችም ቈፍረው በሚሰርቁበት በምድር ለእናንተ መዝገብ አትሰብስቡ፡፡ ነገር ግን ብልና ነቀዝ የማያበላሹት÷ ሌቦችም ዘፍረው በማይሰርቁት በሰማይ ለእናንተ መዝገብን ሰብስቡ፡፡ መዝገባችሁ ባለበት ልባችሁ በዚያ ይኖራልና፡፡

“የሰውነትህ መብራቱ ዐይንህ ነው፤ ዐይንህ ብሩህ ቢሆን ሰውነትህ ሁሉ ጨለማ ይሆናል፡፡ ዐይንህ ግን ታማሚ ቢሆን ሰውነትህ ሁሉ ጨለማ ይሆናል፤ በአንተ ላይ ያለው ብርሃን ጨለማ ከሆነ ጨለማህ እንዴት ይበዛ! ለሁለት ጌቶች መገዛት የሚቻለው አገልጋይ የለም፤ ያለዚያ አንዱን ይወዳል፤ ሁለተኛውንም ይጠላል፤ ወይም ለአንዱ ይታዘዛል፤ለሁለተኛውም አይታዘዝም፤ እንግዲህ ለእግዚአብሔርና ለገንዘብ መገዛት አትችሉም፡፡

ቅዳሴ
ዘኤጲፋንዮስ
ዐቢይ ውእቱ እግዚአብሔር በዕበዩ ቅዱስ በቅዳሴሁ እኩት በአኮቴቱ ወስቡሕ ስብሐቲሁ . . .
ትርጉም፡- እግዚአብሔር በገናንነቱ ገናና ነው በቅድስናው የተቀደሰ ነው በምስጋናው የተመሰገነ ነው በክብሩም የከበረ ነው. . .

2015 ፌብሩዋሪ 18, ረቡዕ

21 የግብጽ ኮፕት ክርስቲያኖች ሰማእትነት ተቀበሉ


አትም ኢሜይል
የካቲት 10 ቀን 2007 ዓ.ም.
በእንዳለ ደምስስ
egypt copts21 የግብጽ ኮፕት ክርስቲያኖች ራሱን ኢስላሚክ ስቴት /ISIS/ እያለ በሚጠራው አሸባሪ ቡድን በምሥራቃዊ ሊቢያ ሲርት ውስጥ የካቲት 8 ቀን 2007 ዓ.ም. ሰማእትነት ተቀበሉ፡፡

አሸባሪ ቡድኑ በላከው የአምስት ደቂቃ የምሥል ወድምጽ መረጃ አጋቾቹ ሰውነታቸውን በጥቁር አልባሳት በመሸፈን፤ ታጋቾቹን ደግሞ ብርቱካናማ ልብስ በማልበስ ወደ የባሕር ዳርቻ በመውሰድና በጉልበታቸው በማንበርከክ ጭካኔ በተሞላበት ሁኔታ አንገታቸውን ቀልተዋቸዋል፡፡

በእምነታቸው ምክንያት የታገቱት እነዚህ የኮፕት ክርስቲያኖች ለሥራ ፍለጋ ከግብጽ ወደ ሊቢያ የሔዱ ሲሆን፤ በታጣቂዎቹ መታገታቸውን ቢቢሲ እና የተለያዩ ዓለም አቀፍ የመረጃ ምንጮች ዘግበዋል፡፡

የክርስቲያኖቹ መገደል ከፍተኛ ቁጣን የቀሰቀሰ ሲሆን፤ የተለያዩ የሃይማኖት ተቋማት፤ የሀገራት መሪዎች እንዲሁም የተለያዩ የመንግሥታት ሓላፊዎች ተቃውሟቸውን እየገለጹ ይገኛሉ፡፡

የግብጹ ፕሬዚዳንት አብዱልፈታህ አልሲሲ በሀገሪቱ ቴሌቪዥን ቀርበው በሰጡት መግለጫ “በክርስቲያኖቹ ግድያ ጊዜውን የጠበቀ አጸፋ ለመመለስና አስፈላጊውን እርምጃ ለመውሰድ ያሉንን አማራጮች ሁሉ እንድንጠቀም እንገደዳለን” ብለዋል፡፡
 

በተያያዘ ዜና የግብጽ ኮፕት ቤተ ክርስቲያን የክርስቲያኖቹን ሰማእትነት ለማዘከር በሀገር ውስጥ እና በውጭ ሀገር በሚገኙ አብያተ ክርስቲያናቷ ለሰባት ቀናት የሚቆይ ጾም፤ ጸሎትና ቅዳሴ እንዲደረግ አውጃለች፡፡

2015 ፌብሩዋሪ 17, ማክሰኞ

የዘወረደ ምንባብ (ዕብ.13÷7-17)


አትምኢሜይል
የእግዚአብሔርን ቃል የነገሩአችሁን መምህሮቻችሁን ዐስቡ፤ መልካም ጠባያቸውን አይታችሁ በእምነት ምሰሉአቸው፡፡ኢየሱስ ክርስቶስ ትናንትናና ዛሬ እስከ ዘለዓለምም የሚኖር እርሱ ነውና፡፡

 ሌላ ልዩ ትምህርት አታምጡ፤ ልባችሁ በመብል ያይደለ በጸጋ ቢጸና ይበልጣልና፤ በዚያ ይሄዱ የነበሩ እነዚያአልተጠቀሙምና፡፡ ድንኳኒቱን ሲያገለግሉ የነበሩ ካህናት ከእርሱ ሊበሉ የማይቻላቸው መሠዊያ አለን፤ ሊቀ ካህናቱ የሚሠዉትን እንስሳ ደም ስለ ኀጢአት ወደ ቅድስተ ቅዱሳን ያቀርብ ነበርና፤ ሥጋውንም ከሰፈር ውጭ ያቃጥሉት ነበር፡፡

ስለዚህም ኢየሱስ ሕዝቡን በደሙ ይቀድሳቸው ዘንድ ከከተማ ውጭ ተሰቀለ፡፡ አሁንም ተግዳሮቱን ተሸክመን÷ ወደ እርሱ ወደ ከተማው ውጭ እንውጣ፡፡ በዚህ የሚኖር ከተማ ያለን አይደለም የምትመጣውን እንሻለን እንጂ፡፡ በውኑ እንግዲህ በሰሙ አናምን ዘንድ የከንፈሮቻችን ፍሬ የሚሆን የምስጋና መሥዋዕትን በየጊዜው ለእግዚአብሔር ልናቀርብ አይገባንምን? ነገር ግን ለድሆች መራራትን÷ከእነርሱም ጋር መተባበርን አትርሱ፤ እንዲህ ያለው መሥዋዕት እግዚአብሔርን ደስ ያሰኘዋልና፡፡


 (ያዕ.4÷6 )
ነገር ግን ፈጣሪያችን የምትበልጠውን ጸጋ ይሰጣል፤ ስለዚህም “እግዚአብሔር ትዕቢተኞችን ይቃወማል፤ ለትሑታን ግን ጸጋን ይሰጣል” ይላል፡፡
እንግዲህ እግዚአብሔርን እሺ በሉት፤ ሰይጣንን ግን እንቢ በሉት፤ ከእናንተም ይሸሻል፡፡ እግዚአብሔርን ቅረቡት፤ ይቀርባችሁማል፤ እናንተ ኃጥኣን እጆቻችሁን አንጹ፤ ሁለት ዐሳብም ያላችሁ እናንተ ልባችሁን አጥሩ፡፡ እዘኑና አልቅሱ፤ ሳቃችሁን ወደ ልቅሶ÷ ደስታችሁንም ወደ ኀዘን መልሱ፡፡ በእግዚአብሔር ፊት ራሳችሁን ዝቅ አድርጉ፤ እርሱም ከፍ ከፍ ያደርጋችኋል፡፡


 (ሐዋ.25÷13- ) 
ከጥቂት ቀን በኋላም ንጉሥ አግሪጳና በር ኒቄ ወደ ቂሣርያ ወርደው ፊስጦስን ተገናኙት፡፡ በእርሱ ዘንድ ብዙ ቀን ከቈዩ በኋላ ፊስጦስ የጳውሎስን ነገር ለንጉሡ ነገረው፤ እንዲህም አለው÷ “ፊልክስ በእስር ቤት ትቶት የሄደ አንድ እስረኛ ሰው በእዚህ አለ፡፡ በኢየሩሳሌም ሳለሁም ሊቃነ ካህናትና የአይሁድ ሽማግሌዎች ወደ እኔ መጥተው እንድፈርድበት ማለዱኝ፡፡ አኔም፡- ተከሳሹ በከሳሾቹ ፊት ሳይቆም÷ ለተከሰሰበትም ምላሽ ይሰጥ ዘንድ ፋንታ ሳያገኝ ማንም ቢሆን አሳልፎ መስጠት የሮማውያን ሕግ አይደለም ብየ መለስሁላቸው፡፡

ከዚህም በኋላ፤ በዚሁ በተሰበሰቡ ጊዜ ሳልዘገይ በማለዳ በፍርድ ወንበር ተቀምጬ÷ ያን ሰው እንዲያመጡት አዘዝሁ፡፡ የከሰሱትም በቆሙ ጊዜ÷ እኔ እንደ አሰብሁት በከሰሱት ክስ የሠራው ምንም ነገር የለም፡፡ ስለ ሃይማኖታቸው ከሆነው ክርክርና ስለ ሞተው÷ ጳውሎስ ግን ሕያው ነው ስለሚለው ሰው ስለ ኢየሱስ ከሆነው ክርክር በቀር፤ ስለ ክርክራቸውም የማደርገውን አጥቼ ጳውሎስን ወደ ኢየሩሳሌም ሄደህ በዚያ ልትከራከር ትወዳለህን? አልሁት፡፡” አግሪጳም ፊስጦስን÷ “እኔም ያን ሰው ልሰማው እወደለሁ” አለው፤ ፊስጦስም÷ “እንግደያስ ነገ ትሰማዋለህ” አለው፡፡


በማግሥቱም አግሪጳና በርኒቄ በብዙ ግርማ መጡ፤ ከመሳፍንቱና ከከተማው ታላላቅ ሰዎች ጋርም ወደ ፍርድ ቤት ገቡ፤ ፊስጦስም ጳውሎስን እንዲያመጡት አዘዘ፡፡ ፊስጦስም እንዲህ አለ÷ “ንጉሥ አግሪጳ ሆይ÷ እናንተም ከእኛ ጋር ያላችሁ ወንድሞቻችን ሁላችሁ÷ ስሙ፤ አይሁድ ከእንግዲህ ወዲህ በሕይወት ይኖር ዘንድ እንዳይገባው በኢየሩሳሌምም ሆነ በዚህ እየጮሁ የለመኑኝ ይህ የምታዩት ሰው እነሆ፡፡ እኔ ግን ለሞት የሚያደርሰው በደል እንዳልሠራ እጅግ መርምሬ÷ እርሱም ራሱ ወደ ቄሣር ይግባኝ ማለትን ስለወደደ እንግዲህ ልልከው ቈርጫለሁ፡፡ ነገር ግን ስለ እርሱ ወደ ጌታዬ የምጽፈው የታወቀ ነገር የለኝም፡፡ ስለዚህ ከተመረመረ በኋላ የምጽፈውን አገኝ ዘንድ ወደ እናንተ ይልቁንም ንጉሥ አግሪጳ ሆይ ወደ አንተ አመጣሁት፡፡ የበደሉ ደብዳበቤ ሳይኖር እስረኛን ወደ ንጉሥ መላክ አይገባምና፤ ለእኔም ነገሩም ሆነ አስሮ መላኩ አስቸግሮኛል፡፡”



ነፍስና ሥጋ የውል ስምምነት ተፈራረሙ

አትምኢሜይል


የካቲት 10ቀን 2007ዓ.ም. 
በመ/ርት ጸደቀወርቅ አሥራት
ነፍስና ሥጋ እንደከዚህ በፊቱ ለሚጠብቃቸው ከባድ የሥራ ኃላፊነትና አለመግባባት የውል ስምምነት ተፈራረሙ። የውል ስምምነቱን የተፈራረሙት በዚህ ሣምንት የገባውን የዐቢይ ፆም ምክንያት በማድረግ ነው።

በውሉ ሥነ ሥርዐት ላይ ነፍስ እንደገለጸችው ከዚህ በፊት በአጽዋማት ጊዜ በመካከላቸው የሚፈጠረውን አለመግባባት ለመፍታት ውሉ ጠቃሚነቱ የጎላ ነው። ባለፉት ዓመታት ሥጋ የአጽዋማትን ወቅት ጠብቆ ነፍስ ተገቢውን ድርሻ እንዳትወጣ እንቅፋት እየሆነ ችግር ሲፈጥር መቆየቱን ገልጸው ስምምነቱ በመካከላችው ሰላም እንዲሰፍን ምክንያት ይሆናል ያሉን በስምምነቱ ሥነ ሥርዐት ላይ የተገኙት የነፍስ አባት ናቸው።
ከፊርማው ሥነ ሥርዐት በኋላ ባነጋገርነው ወቅት ስምምነቱን ተቀብሎ የነፍስን ሥራ ሳይቃወም ሊገዛላት መዘጋጀቱን ሥጋም ቢሆን አልሸሸገም። በሥነ ሥርዐቱ ላይ የተገኙት ሌሎች ምዕመናንም ሥጋን በቃልህ ያጽናህ እያሉ ከስብሰባው አዳራሽ ሲወጡ እንደተሰሙ “ሪፖርተራችን” ዘግቦልናል።

2015 ጃንዋሪ 27, ማክሰኞ

እመቤቴ ማርያም ሆይ፤ ምጡቅና ሩቅ ወደሚሆን የደስታ ቦታ ላረገ ሥጋሽ ሰላምታ ይገባል ይኸውም ኅብሩ ሊመረምሩት በማይቻል ዕንቊ የታነፀ ሕንፃ ይገኝበታል፡፡ መልክአ ማርያም





በዲያቆን ንጋቱ አበበ

 ቅዱሳን ሐዋርያት፤ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከእነርሱ በመለየቷ ፈጽመው ያዝኑ ነበር። ከእለታት በአንዱ ቀን ጌታችን መድሃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለቅዱሳን ሐዋርያቱ ተገለጠላቸውና እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን እንደሚያዩ ተስፋ ሰጣቸው። በዚያን ጊዜ ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌልን እየሰበከ፤ እያስተማረ፤ ሕዝበ ክርስቲያንን እያጽናና እስያ በምትባል ሃገር ነበር። ከዚያም በመንፈስ ቅዱስ ተነጥቆ፤ ተድላና ደስታ ከሰፈነባት ቦታ ወደ ገነት ሄደ። ጌታችን መድሃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን የ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሥጋዋ ካለበት ከዕፀ ሕይወት ሥር ተቀምጦ አየው። የንጽሕት አናቱንም ሥጋ ታወጣ ዘንድ ምድርን እንዲጠሯት ሰባቱን የመላእክት አለቆች አዘዛቸው። ቅድሳን መላእክቱም
እንደታዘዙት አደረጉ። ያን ጊዜም ከዕፀ ሕይወት በታች ካለ መቃብር የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሥጋ ወጣ። ጌታችንም

እንዲህ እያለ አረጋጋት። የተወደድሽ የወለድሽኝ እናቴ ሆይ ዘለዓለማዊ ወደ ሆነ መንግስተ ሰማያት አሳርግሽ ዘንድ ነይ። ያን ጊዜ በገነት ያሉ ዕፅዋት በሙሉ አዘነበሉ ሰገዱ። ቅዱሳን መላእክትም፤ ጻድቃን ሰማዕታትም እየሰገዱላትና ፈጽሞ አያመሰገኗት እያወደሷት በእልልታ ወደ ሰማይ አሳረጓት። ቅዱስ ዮሐንስም ከእርሷ በረከትን ተቀብሎ ሰግዶላት ተመልሶ ከሰማይ ወረደ። ቅዱሳን ሐዋርያትም ተሰብስበው ሳለ፤ ስለ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም እረፍት ፈጽመው እያዘኑ እየተከዙ ሳለ አገኛቸው። እርሱም እንዳየና እንደሰማ፤ ሥጋዋንም በታላቅ ክብር በምስጋና እንደ አሳረጓት ነገራቸው። ሐዋርያትም በሰሙ ጊዜ ቅዱስ ዮሐንስም አንዳየና እንደሰማ ባለማየታቸውና ባለመስማታቸው እጅግ አዘኑ። ፈጽመው እያዘኑ ሳሉ ጌታችን መድሃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተገለጠላቸውና ሰላም ለእናንተ ይሁን አላቸው። ሥለ እናቴ ማርያም ሥጋ ለምን አብዝታችሁ ታዝናላችሁ? እነሆ እርሷን በሥጋ ላሳያችሁ ልባችሁም ደስ ሊለው ይገባል አላቸው። ይህንንም ብሎ ከእርሳቸው ዘንድ ወደ ሰማያት አረገ። ቅዱሳን ሐዋርያትም አመት ሙሉ ቆዩ። የነሐሴም ወር በባተ ቀን ለሐዋርያት፤ ቅዱስ ዮሐንስ እንዲህ አላቸው። አምላክን የወለደች የእመቤታችንን ሥጋዋን ለማየት የተዘጋጀን አድርጎ ያሳየን ዘንድ ኑ ይህን ሁለት ሱባኤ በመጾም የክብር ባለቤት ጌታችንን ኢየሱስ ክርስቶስን እንለምነው። በልጇ በወዳጇ ቀኝ ተቀምጣ አይተን በሷ ደስ እንዲለን። በዚያን ጊዜም ቅዱስ ዮሐንስ እንዳላቸው ቅዱሳን ሐዋርያት ከነሐሴ ወር መጀመሪያ እስከ 16ተኛው ቀን ድረስ በጾም በጸሎት ሱባኤ ያዙ። ሱባኤ በያዙ በአስራ ስድስተኛው ቀንም ጌታችን መድሃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሁሉንም ቅዱሳን ሐዋርያት ወደ ሰማይ አወጣቸው። በታላቅ ክብር በተወደደ ልጇ ተቀምጣ፤ ከሥጋዋ ተዋሕዳ፤ ተነስታ እመቤታችንን አዩዋት። እጆቿንም ዘርግታ ቅዱሳን ሐዋርያትን ባረከቻቸው። እነርሱም ፈጽመው ተደሰቱ። ጌታችንም በከበረ ሥጋውና ደሙ ላይ ሠራዒ ሆነ። ቅዱስ እስጢፋኖስም አዘጋጀ። ቅዱስ ዮሐንስም በመፍራት ቁሙ አለ። ሁሉም ቅዱሳን ሐዋርያት በመሰዊያው ዙርያ ቆሙ። በዚያን ጊዜ ከቶ እንደርሱ ሆኖ የማያውቅ ታላቅ ደስታ ሆነ። ጌታችንም የቅዳሴውን ሥርዓት በፈጸመ ጊዜ ሥጋውንና ደሙን አቀበላቸው። ከዚያም በሱራፌልና በኪሩቤል ሠረገላ ተቀምጣ በምታርግ ጊዜ ጌታችን መድሃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እናቱ እመቤታችን ማርያምን እንዲህ ብሎ ተናገራት። በዚህች ቀን የሆነ የእርገትሽን መታሰቢያ በዓለም ውስጥ እንዲሰብኩ ልጆችስ ቅዱሳን ሐዋርያትን እዘዣቸው። መታሰቢያሽን የሚያደርግ ሁሉ ተጠብቆም በዚህች ቀን ቅዱስ ቁርባንን የሚቀበለውን ኃጢአቱን እደመስስለታለሁ። የእሳትን ሥቃይ ከቶ አያያትም። መታሰቢያሽን ለሚያደርግ ሁሉ፤ በዚህች ቀን ለድኆች በስምሽ ለሚመጸውት በቸርነቴ እጎበኘዋለሁ ብሎ ቃል ኪዳን ገባ። እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምም ልጇን ወዳጇን ጌታችንን እንዲህ አለችው። ልጄ ሆይ እነሆ በአይኖቻቸው አዩ፤ በጀሮቻቸውም ሰሙ፤ በእጆቻቸውም ዳሰሱ ሌሎች ታላላቅ ድንቅ ተአምራትንና ሥራዎችን አዩ ብላ ከነገረችው በኋላ ጌታችን ሰላምታ ሰጥቷቸው በታላቅ ደስታ ወደ ደብረ ዘይት ተመለሱ።
የተወደዳችሁ የእግዚአብሔር ልጆች ምዕመናን ሆይ የፈጣሪን እናት የ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን በፍጹም ደስታና በመልካም ምግባር መታሰቢያዋን እናደርግ ዘንድ ይገባናል እርሷ ስለ እኛ ወደ ተወደደ ልጇ ሁልጊዜ ትማልዳለችና።
ለልዑል እግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይሁን
በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት ይማረን። በረከቷ፤ ፍቅሯ፤ ጣዕሟ በእኛ በልጆቿ ላይ አድሮ ይኑር ለዘለዓለሙ አሜን።

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በሥጋ ከመሞቷ በፊት በጌታችን በመድሃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ መቃብሩ ቦታ ትጸልይ ነበር። መንፈስ ቅዱስም ለእመቤታችን ከዚህ ዓለም እንደምትለይ ነገራት። ጌታችንም በደብረ ዘይት ላሉ ደናግላን ነግሯቸዋልና ወደ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በፍጥነት መጡ። እርሷን መንፈስ ቅዱስ የነገራትን ነገረቻቸው።

           በዲያቆን ንጋቱ አበበ


እነሱም እንደመጡ ባየች ጊዜ እንዲህ ብላ ጸለየች። ልጄ ውዳጄ፤ ፈጣሪዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ልመናየን ተቀብለህ ደቀ መዝሙርህን ዮሐንስን በዚህች ሰዓት አምጣው፤ እንዲሁም በሕይወት ያሉትንና በሕይወት የተለዩንን ቅዱሳን በሙሉ ወደ እኔም አምጣቸው። አንተ የሕያዋን አምላክ ነህና፤ለአንተም ምስጋና ይሁን አሜን አለች። በዚያን ጊዜ በመንፈስ ቅዱስ ትዕዛዝ ቅዱስ ዮሐንስን ደመና ተሸክማ ወደ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም አደረሰችው። ቅዱስ ዮሐንስም እንደደረሰ ሰገደላትና በፊቷ ቆሞ እንዲህ አላት፤ ሰላምታ ይገባሻል ጌታችን መድሃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ወልደሽልናልና፤ ጸጋን የተመላሽ ሆይ ደስ ይበልሽ። አንቺ ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተሽ በክብር በምስጋና ወደ ዘለዓለም ሕይወት ትሄጃለሽና። እመቤታችንም ይህን በሰማች ጊዜ እጅግ ደስ አላት እንዲህ ብላ አምላኳንም አመሰገነችው። ጌታዬ አምላኬ ፈጣሪዬ ሆይ፤ ላንተ ክብር ምስጋና ይገባል። የለመንኩህን ሰጥተኸኛልና። አሁንም ነብሴን ተቀብለው ወደ ሰማይ ወደ አንተ ሊይሳርጓት ከሚመጡ መላእክቶችህ ጋር በመምጣትህ የምለምንህን ሁሉ ስጠኝ። በዚህን ጊዜ ከሰማይ እንዲህ የሚል ድምጽ መጣ፤ እነሆ አሁን መላእክት ይደርሳሉ። ቅዱሳን ሐዋርያትም ወደ ቅድስት ድንግል ማርያም ይደርሳሉ። ቅዱሳን ሐዋርያት ከዚህ ዓለም የተለዩትም፤ በሕይወት ያሉትም ሁሉ በአንድነት መጥተው ለእመቤታችን ሰገዱላት። እነርሱም አመሰገኗት እንዲህም አሏት። ጸጋን የተመላሽ ቅድስት ድንግል ማርያም ሆይ ደስ ይብልሽ ፈጣሪያችን ከዚህ ዓለም ለይቶ ቃል ኪዳን እንደሰጠሽ በክብር በምስጋና ከእርሱ ጋር ያሳርግሻልና አሏት። በዚህን ጊዜ እመቤታችን በአልጋዋ ላይ ተቀመጠች። ቅዱሳን ሐዋርያትንም እንዲህ አለቻቸው። ፈጣሪዬ ፈጣሪያችሁ ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ እኔ እንደሚመጣ እናንተንም እንዳየኋችሁ እንደማየው አሁን አወኩ። ከዚህ ከሥጋዬ ወጥቼ ወደ ዘለዓለም ሕይወት እሔዳለሁ። ነገር ግን እናንተ እኔ ከዚህ ዓለም እንደምለይ ማን ነገራችሁ? አወቃችሁ? ቅዱስ ጴጥሮስና ቅዱሳን ሐዋርያት በሙሉ ወደ አንቺ እንመጣ ዘንድ መንፈስ ቅዱስ አዘዘን፤ መጣን አሏት። እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምም ይን ነገር ከቅዱሳን ሐዋርያት በሰማች ጊዜ ድምጿን ከፍ አድርጋ አምላኳን አመሰገነች። እንዲህም አለች ከ እንግዲህ ወዲያ ትውልድ ሁሉ ያከብሩኛል ያመሰግኑኛል። ይህን ብላ እንደጨረሰች እጣን አምጥታችሁ በማጠን የፈጣሪዬን ስም ጥሩት አለቻቸው። እነሱም እንደታዘዙት አደረጉ። በዚህን ጊዜ ጌታችን ተገልጾ ብዙ ድንቅ ተአምራትን አደረገ። በሽተኞች ወደ እመቤታችን ወደ አለችበት ቤት በቀረቡ ጊዜ ከደዌአቸው ይፈወሱ ነበር። እመቤታችን ከሥጋዋ የምትለይበት ሰዓት ሲደርስ ቅዱሳን ሐዋርያትንና ደናግልን ትባርካቸው ዘንድ እያለቀሱ ለመኗት። እመቤታችንም እጇን ዘርግታ ባረከቻቸው። በዚህን ጊዜ ፈጣሪያችን ነፍሷን ከሥጋዋ ለይቶ በመለኮታዊ እጆቹ ይዞ በብርሃን ልብስ አጎናጽፎ ወደ ከፍተኛ መኖሪያ ከ እርሱ ጋር አሳረጋት። ሥጋዋን ግን እንደሚገባ ገንዘው፤ ወደ ጌቴ ሰማኒ ተሸክመው እንዲወስዷ ሐዋርያትን አዘዛቸው። ነፍሷ ከሥጋዋ ከመውጣቷ በፊት በሰው አንደበት ይህ ነው ተብሎ የማይነገር ብርሃን እያየች ነበር። እመቤታችንም ፈጣሪዋን ልጇን ወዳጇን እንዲህ ብላ ጠየቀችው። ልመናየን ትሰማ ዘንድ እለምንሃለሁ። በስሜ ወደ አንተ የሚለምነውን ሁሉ፤ ልመናውን ተቀበለው በመከራም ውስጥ ሁኖ ስሜን ጠርቶ ወደ አንተ የሚለምነውን ከመከራም ሁሉ አድነው፤ በሰማይም በምድርም በሥራው ላይ ሁሉ አንተ ከሃሊ ነህና መታሰቢያየን በውስጧ የሚያደርጉባትን የሁሉንም መስዋእታቸውን ተቀበል። ፈጣሪም እንዲህ ብሎ መለሰላት። የለመንሽኝን ሁሉ አደርግልሻለሁ። እመቤታችንም ከአረፈች በኋላ ጌታችን እንዳዘዘ ወደ ጌቴ ሰማኒ ሊወስዷት ሐዋርይት ገንዘው ተሸከሟት። አይሁድም በሰሙ ጊዜ ሥጋዋን ሊይቃጥሉ መጡ። ከ እነርሱም አንዱ ከምድር ይጥላት ዘንድ ይእመቤታችንን አልጋዋን ያዘ። ያን ጊዜ ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክ እጆቹን በእሳት ሰይፍ ቀጣውና እጆቹ በአልጋው ላይ ጠንጠለጠሉ። ያን ጊዜ በጌታችን አምኖ ወደ እመቤታችን እያለቀሰ እንዲህ እያለ ለመነ። የ እውነተኛ አምላክ ይጌታ ኢይሱስ ክርስቶስ እናት አንቺ በ እውነት ድንግል ይሆንሽ በ እኔ ላይ ይቅርታ ታደርጊ ዘንድ አለምንሻለሁ። በሐዋርይትም ልመና እጆቹ ተመልሰው እንደቀድሞው ደህና ሆኑ። እመቤታችን በቀብሯት ጊዜ ከዚያ ሶስት ቀን ኖሩ እረፍቷም የነበረው እሁድ ቀን ጥር 21 ነብር። ጌታችንም ብርሃናውይን መላእክትን ልኮ ሥጋዋን ከመቃብር ወስደው በገነት ውስጥ በዕፀ ሕይወት ሥር አኖሯት። ሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ ግን ያን ጊዜ አልነበረም በደመና ላይ ተጭኖ እርሱ ሲመጣ መላእክት ሲያሳርጓት እመቤታችንን አገኟት ። መላእክትም ለአምላክ እናት ለ እመቤታችን ድንግል ማርይም ና እጅ ንሳ አሉት እርሱም ሰገደላትና ተሳለማት ከ እርሷም ተባረከ ከዚህም በኋላ ወደ ሐዋርያት ደረሰ። እነርሱም እመቤታችንን ማርያምን እንደ አረፈችና እንደ ቀበሯትም ነገሩት። ቅዱስ ቶማስም ሥጋዋን እስከ ማይ አላምንም አላቸው። ሥጋውንም ይሳዩት ዘንድ ወደ መቃብሯት በአደረሱት ጊዜ ከመቃብሩ ውስጥ ሥጋዋን አላገኙም ደንግጠውም አደነቁ ያን ጊዜ ከመላእክት ጋር ወደ ሰማይ ስታርግ እመቤታችን እንዳገኛት ነገራቸው። ቅዱሳን ሐዋርያትም ይህን በሰሙ ጊዜ የ እመቤታችንን ዕርገቷን ኡ ስላላዩ እጅግ አዘኑ ሥጋዋን በምድር ውስጥ ይተው ዘንድ እንዳልወደደ መንፈስ ቅዱስ አስገነዘባቸው። ከዚህም በኋላ አንድ ጊዜ ደግሞ እርሷን ያሳያቸው ዘንድ እንዳለው ጌታችን ቃል ኪዳን በማድረግ ተስፋ ሰጣቸው። እነርሱም በተስፋ እስከ ነሐሴ 16 ቀን በተስፋ ኖሩ። የ እመቤታችንም የእድሜዋ ዘመን 64 ዓመት ነው። በአባትና በእናቷ ቤት 3 ዓመት፤ በመቅደስም 12 ዓመት፤ በዮሴፍም ቤት 34 ዓመት ከሦስት ወር ከጌታ ዕርገት በኋላ በወንጌላዊ ቅዱስ ዮሐንስ ቤት 14 ዓመት ነው። 

ይቆየን…………….

የሕይወት የድህነት አለኝታ የሆነች እርሷን እናቱን ለሰጠን እግዚአብሔር ምስጋና ይሁን።
 
የእመቤታችን በረከቷ ረድ ኤቷ ይደርብን አሜን!!!

2015 ጃንዋሪ 10, ቅዳሜ

የታክሲ ሾፌሮች፤ ረዳቶችና ተራ አስከባሪዎች ጉባኤ 8ኛ ዓመት ተከበረ


አትም ኢሜይል
ጥር 1 ቀን 2007 ዓ.ም.
በደመላሽ ኃይለ ማርያም
የብርሃናተ ዓለም ቅዱስ ጴጥሮስ ወጳውሎስ ቤተ ክርስቲያን ፍሬ ሃይማኖት ሰንበት ትምህርት ቤት ለታክሲ ሹፌሮች፣ ተራ አስከባሪዎችና ረዳቶቻቸው አገልግሎት እንዲሰጥ የመሠረተውን ጉባኤ 8ኛ ዓመት አስመልክቶ ታኅሣሥ 25 እና 26 ቀን 2007 ዓ.ም. “ለፍቅርና ለመልካም ሥራ እንድንነቃቃ እርስ በርሳችን እንተያይ” በሚል የመጽሐፍ ቅዱስ መሪ ቃል በቤተ ክርስቲያኑ ቅጥር ግቢ አባላቱና በርካታ ምዕመናን በተገኙበት ተከበረ፡፡

ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ የደብሩ አስተዳዳሪ እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በመርሐ ግብሩ ላይ የተገኙ ሲሆን፤ የታክሲ አገልግሎት ሥራን በሚመለከት ከቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ጋር አያይዘው “ኖላዊ” በሚል ርዕስ በተጋባዥ መምህራን ትምህርተ ወንጌል ተሰጥቷል፡፡

የታክሲ ሹፌሮች፣ ረዳቶቻቸው እና ተራ አስከባሪዎች ከማኅበረሰቡ ጋር ያላቸውን በጎ ያልሆነ ግንኙነት ለማሻሻል እና በክርስትና ሕይወታቸው ምሳሌ የሚሆኑ ዜጎችን ማፍራት እንዲቻል፤ እንዲሁም በእነሱ ቸልተኝነት እና ጥድፊያ በመኪና አደጋ እየጠፋ ያለውን የሰውን ሕይወት ለመቀነስ ታስቦ ጉባኤው መመስረቱን የሰንበት ትምህርት ቤቱ ሰብሳቢ ዲያቆን ያሬድ ያስረዳል፡፡

ዲያቆን ያሬድ አክሎም “የአባላቱን ቁጥር ከዚህ የበለጠ በማሳደግና በጉባኤው ውስጥ በማካተት ትምህርተ ሃይማኖት እንዲማሩ፤ የቤተ ክርስቲያኒቱን ዶግማ፤ ቀኖና እና ትውፊት እንዲያውቁ፤ በሥነ ምግባር የታነጹና ሥርዓት አክባሪዎች ሆነው ከማኅበረሰቡ ጋር ያላቸውን ግንኙነት ጤናማ ለማድረግ ከፈጣሪ ጋር እንጥራለን” ብሏል፡፡

ከተጋባዥ እንግዶች መካከልም የአዲስ አበባ ትራፊክ ፖሊስ ጽ/ቤት የሕዝብ ግንኙነት ሓላፊ ም/ኢንስፔክተር አሰፋ መዝገቡ ድንገተኛ፤ ለንስሐ እና ለኑዛዜ የማያበቃውን በትራፊክ አደጋ የሚደርሰውን ሞት ለመከላከል ምእመናን እና የታክሲ ሹፌሮች ጥንቃቄ እንዲያደርጉ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

በመጪው ዓመት ሃምሳኛ ዓመቱን የሚያከብረው ይህ የፍሬ ሃይማኖት ሰንበት ትምህርት ቤት እየሠራ ያለው ሥራ እጅግ በጣም ሊበረታታ የሚገባውና በሌሎችም ሰንበት ትምህርት ቤቶች ሊለመድና ሊሰራበት እንደሚገባ ጉባኤውን የተከታተሉ ምእመናን አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡

2015 ጃንዋሪ 9, ዓርብ

አባቶችና ምእመናን ‹‹ሸኚው ሸኚ ሲያጣ›› እስኪሉ ድረስ በመጣደፉ በእጅጉ ያዘኑበት የ106 ዓመት አረጋዊው የብፁዕ አቡነ አረጋዊ ሥርዐተ ቀብር ተፈጸመ



funeral of Abune Aregawi
ፎቶ: ማኅበረ ቅዱሳን

ዜና ሕይወቱ ወዕረፍቱ ለብፁዕ አቡነ አረጋዊ

ብፁዕ አቡነ አረጋዊ በ1901 ዓ.ም. ወልደው በፀለምት /ሰሜን ጎንደር/ ተወልደው ዕድሜአቸው ለትምህርት ሲደርስ ትምህርት ቤት ገብተው ንባብና ዳዊት እንዲኹም እስከ ፀዋትወ ዜማ አጠናቅቀው ከብፁዕ አቡነ ቄርሎስ ግብፃዊ ማዕርገ ዲቁናና ማዕርገ ቅስና ተቀብለዋል፡፡
በዋልድባ አብረንታንት ገዳም ገብተው ለዘጠኝ ዓመታት ያኽል (ከ1933 – 42 ዓ.ም.) ሥርዓተ ገዳሙን ከአጠኑና በግብዝና ከአገለገሉ በኋላ በዚኹ ገዳም መዓርገ ምንኵስናን ተቀብለዋል፡፡ ትምህርታቸውን በመቀጠል በሰሜን ምዕራብ ትግራይ በሚገኘው በደብረ ዓባይ ገዳም የደብረ ዓባይ መዝገበ ቅዳሴ ዜማ ተምረው በመምህርነት በቅተዋል፡፡
በ1943 ዓ.ም. በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ባስልዮስ ፈቃድና ትእዛዝ በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ገዳማትን እንዲያገለግሉ ተልከው ለአራት ዓመታት ያኽል አገልግለዋል፡፡ አኹንም በቅዱስ ፓትርያርኩ ፈቃድ ወደ ግብጽ ሔደው ለ16 ዓመታት ያኽል ነገረ መለኰትን በዓረብኛ ቋንቋ አጥንተው ተመርቀዋል፡፡funeral of Aba Aregawi 
ወደ ኢትዮጵያ ከተመለሱ በኋላ በሱዳን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን በሓላፊነት ለማገልገል ተልከው ለስድስት ዓመታት ያኽል በአስተዳዳሪነት ሠርተዋል፡፡ በዚኹ ሓላፊነት ሳሉም በ1968   ዓ.ም. ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት የኢትዮጵያ ፓትርያርክ ኹነው በተሾሙ ጊዜ በሱዳን የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንን ወክለው በመምጣት ለበዓሉ ከፍተኛ አስተዋፅኦ አድርገዋል፡፡
በ1972 ዓ.ም. በቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ወደ ሀገራቸው ተመልሰው በቅዱስ ፓትርያርኩ ፈቃድ የመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ሊቀ ሥልጣናት በመኾን አገልግለዋል፡፡
በጥቅምት ወር 1983 ዓ.ም. በሱዳን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳስ ኾነው በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ አንብሮተ እድ ተሾመዋል፡፡
ከመጋቢት 1985 ዓ.ም. ጀምሮ የኢሉባቦርና የጋምቤላ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ኾነው ለአንድ ዓመት ያኽል ሠርተዋል፡፡
ከየካቲት 1986 ዓ.ም. ጀምሮ የምስካየ ኅዙናን መድኃኔ ዓለም ገዳምና ት/ቤት የበላይ ሓላፊ ኾነው አገልግለዋል፡፡
ከሐምሌ 1968 ዓ.ም. ጀምሮ የሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ኾነው አገልግለዋል፡፡
ከግንቦት 1992 ዓ.ም. ጀምሮ ወደ አዲስ አበባ ተዛውረው የመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል የበላይ ሓላፊ ኾነው ሲሠሩ ቆይተዋል፡፡
በመጨረሻም በዚኹ ሥራ ላይ ሳሉ ባደረባቸው ድንገተኛ ሕመም ምክንያት በሕክምና ሲረዱ ቆይተው ጥር 1 ቀን 2007 ዓ.ም. በተወለዱ በ106 ዓመታቸው ከዚኽ ዓለም በሞተ ሥጋ ተለይተዋል፡፡
funeral of Aba Aregawi03
የቀብራቸው ሥነ ሥርዓትም በዚኹ ዕለት፣ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ባሉበትና የአድባራትና ገዳማት አስተዳዳሪዎች በተገኙበት ሥርዓተ ጸሎተ ፍትሐቱ ከተፈጸመ በኋላ በቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ተፈጽሟል፡፡
ልዑል እግዚአብሔር የብፁዕ አቡነ አረጋዊን ነፍስ ዕረፍተ መንግሥተ ሰማያትን ሰጥቶ በአብርሃም በይሥሐቅ በያዕቆብ አጠገብ ያኑርልን፤ በማለት እንሰናበታቸዋለን፡፡
About these ads

ሰበር ዜና – ብፁዕ አቡነ አረጋዊ ዐረፉ



  • ሥርዐተ ቀብሩ ዛሬ በ9፡00 በመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ይፈጸማል
His Grace Abune Aregawi
በተባሕትዎአቸውና በተመሰገነው ምንኵስናቸው የሚታወቁት የመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል የበላይ ጠባቂ ብፁዕ አቡነ አረጋዊ ዐረፉ፡፡ ብፁዕነታቸው ዛሬ፣ ዓርብ ጥር ፩ ቀን ፳፻፯ ዓ.ም. ጠዋት ያረፉት ለተሻለ ሕክምና በገቡበት ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ነው፡፡
ብፁዕነታቸውን ለኅልፈት ያደረሳቸው፣ ከአንድ ወር በፊት ለሐዋርያዊ ተልእኮ ወደ ደቡብ ሱዳን በሔዱበት ወቅት ያጋጠማቸው ቢጫ ወባ በኩላሊታቸውና በሳምባቸው ላይ ያስከተለው ጉዳት ነው፡፡
ከጉዟቸው መልስ ‹‹እኔ ንግግሬ ከእግዚአብሔር ጋራ ነው›› በማለት ያለሕክምና ርዳታ ለኹለት ሳምንት ያኽል በተዘጋ ማረፊያቸው የቆዩት ብፁዕነታቸው፣ በብፁዓን አባቶችና በቅርብ ወዳጆቻቸው ተማኅፅኖ በዘውዲቱ ሆስፒታል እና በሳንቴ የጤና ማእከል በተደረገላቸው ከፍተኛ ክትትል የተጎዳው ኩላሊታቸው አገግሞ እስከ ዛሬ ጠዋት ድረስ በተሻለ ኹኔታ ላይ ይገኙ እንደነበር ተጠቅሷል፡፡
ይኹንና ከዕድሜ አንጋፋነታቸው ጋራ ሕመሙ በሳምባቸው ላይ ባደረሰው ጉዳት የተፈጠረው ኢንፌክሽን ለኅልፈት እንደዳረጋቸው ተመልክቷል፡፡
በቅርበት የሚያውቋቸው ወገኖች÷ የዋልድባው መነኰስ ብፁዕ አቡነ አረጋዊ ሀብት ምክር ያላቸው፣ ታሪክ ዐዋቂና የታያቸውን በግልጽ የሚናገሩ መምህር ወመገሥጽ እንደነበሩ ይናገራሉ፡፡
www-st-takla-org-abune-paulos-in-alex-15-july-2007-017
አምስተኛው ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ በግብጽ ሐዋርያዊ ጉብኝት ባደረጉበት ሐምሌ ወር ፲፱፻፺፱ ዓ.ም.፣ ሐምሌ ፰ ቀን በጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ስም በተሠራው ቤተ ክርስቲያን በተገኙበት ወቅት፣ ብፁዕ አቡነ አረጋዊ የቅዱስነታቸውን ንግግር በልሳነ ዓረቢ እየመለሱ አሰምተው ነበር፡፡
የቀደምት ቅዱሳን አበውን ትውፊት በመከተል በግብጽ ገዳማት ለዐሥራ አምስት ዓመታት ያኽል በመቀመጥ ከአኃው መነኰሳት ጋራ መንፈሳቸውን ያስተባበሩት ብፁዕነታቸው፣ ልሳነ ዓረቢን አቀላጥፈው በመናገርም ይታወቃሉ፡፡ የቅድስት ሀገር ተሳላሚ ለመኾን የበቁትም በወጣትነታቸው ማለዳ ሳሉ ነበር፡፡
በፊት ስማቸው ሊቀ ሥልጣናት ገብረ ማርያም ገብረ ሥላሴ ይባሉ የነበሩት ብፁዕነታቸው፣ አቡነ አረጋዊ ተብለው ጥቅምት ፲፰ ቀን ፲፱፻፹፫ ዓ.ም. ኤጲስ ቆጶስነት የተሾሙት በአራተኛው ፓትርያርክ በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ አንብሮተ እድ ነው፡፡
ብፁዕነታቸው ቀድሞ ሊቀ ሥልጣናት በተባሉበት የመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል በበላይ ጠባቂነት ከመወሰናቸው በፊት፣ በሱዳን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ጳጳስ እንዲኹም የጎንደር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በመኾን አገልግለዋል፡፡
የብፁዕነታቸው ሥርዐተ ቀብር ዛሬ፣ ጥር ፩ ቀን ፳፻፯ ዓ.ም. ለረጅም ዓመታት በአገለገሉበት በመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል፣ በ9፡00 እንደሚፈጸም ተገልጧል፡፡
አምላከ ቅዱሳን እግዚአብሔር ለብፁዕ አባታችን ዕረፍተ ነፍስን ይስጥልን፡፡

2015 ጃንዋሪ 2, ዓርብ

“ወብዙኀን ይትፌሥሑ በልደቱ በመወለዱም ብዙዎች ደስ ይላቸዋል” ሉቃ.1፥14



አትም ኢሜይል
ታኅሣሥ 25 ቀን 2005 ዓ.ም.
ዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ
st. tekela
  • በዘመነ ብሉይ የእግዚአብሔር ድምፅና የመልአክ ብሥራት ብርቅ በነበረበት ወቅት ካህኑ ዘካርያስና ቅድስት ኤልሳቤጥ ልጅ መውለድ አጥተው ባረጁበት ዘመን የእግዚአብሔር መልአክ ካህኑ ዘካርያስን እንዲህ አለው፡፡
መልአኩም እንዲህ አለው “ዘካርያስ ሆይ፥ አትፍራ፤ ጸሎትህ በእግዚአብሔር ፊት ተሰምቶአልና፤ ሚስትህ ኤልሣቤጥም ትፀንሳለች፤ ወንድ ልጅንም ትወልድልሃለች፤ ስሙንም ዮሐንስ ትለዋለህ፡፡ ደስታና ሐሤትም ይሆንልሃል፤ በመወለዱም ብዙዎች ደስ ይላቸዋል፡፡ እርሱ በእግዚአብሔር ፊት ታላቅ ይሆናልና የወይን ጠጅና የሚያሰክርም መጠጥ ሁሉ አይጠጣም፤ ከእናቱ ማሕፀን ጀምሮም መንፈስ ቅዱስ ይመላበታል፡፡ ከእስራኤልም ልጆች ብዙዎችን ወደ አምላካቸው ወደ እግዚአብሔር ይመልሳቸዋል፡፡ እርሱም የአባቶችን ልብ ወደ ልጆች፥ የከሓድያንንም ዐሳብ ወደ ጻድቃን ዕውቀት ይመልስ ዘንድ፥ ሕዝብንም ለእግዚአብሔር የተዘጋጀ ያደርግ ዘንድ በኤልያስ መንፈስና ኀይል በፊቱ ይሄዳል፡፡”ሉቃ1፥13-18 ይህ ለመጥምቁ ዮሐንስ የተነገረ ቃል ቢሆንም ወላጆቹ (ካህኑ ዘካርያስና ቅድስት ኤልሳቤጥ) በእግዚአብሔር ፊት ጻድቃን እንደነበሩ በቅዱስ ወንጌል ተገልጿል /ሉቃ.1፥6-7/ እንደዚሁ ሁሉ ካህኑ ጸጋዘአብና ሚስቱ እግዚእ ሐረያ በእግዚአብሔር ሕግና ሥርዓት ይመሩ የነበሩ ደጋግ ክርስቲያኖች ነበሩ፡፡ ይህም ሊታወቅ በትሩፋት ሥራ፣ በጾም፣ በጸሎት፣ በምጽዋት የታወቁ ነበር፡፡ በተለይም የሊቀ መላእክት የቅዱስ ሚካኤል በዓልን ምክንያት በማድረግ ይመጸውቱ ነበር፡፡ የመልአኩም ጥበቃ ባለ ዘመናቸው ሁሉ አልተለያቸውም ነበር፡፡ ጌታችን በቅዱስ ወንጌል ላይ “መልካም ዛፍ ሁሉ መልካም ፍሬን ያፈራል፣” /ማቴ.7፥17/ እንዳለ፣ ለዓለም ሁሉ የወንጌልን ብርሃን የሚያበስር ሐዲስ ሐዋርያ በቅድስናና በክብሩ ከሃያ አራቱ ካህናተ ሰማይ ሃያ አምስተኛ ሆኖ ያመሰገነውን ጻድቅ ወለዱ፡፡ በሰሜን ሸዋ ጽላልሽ ልዩ ስሙ ኢቲሳ በተባለ ቦታ የተወለዱት ጻድቁ ተክለ ሃይማኖት በ12ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የተነሡና የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ትምህርት ከየመን እስከ ኬንያ ከሶማሌ እስከ ሱዳን ድረስ የተስፋፋበትን ወርቃማ ዘመንን ያስገኙ ጻድቅ አባት ናቸው፡፡
“ነገርን ከሥሩ ውኃን ከጥሩ” እንዲሉ የጻድቁን ታሪክ በአጭሩ እንደሚከተለው አቅርበነዋል፡፡

ቅዱሳኑ በትሩፋት ሥራ የተጠመዱ ነበሩ
ልጅ አጥተው ሲያዝኑ ይኖሩ የነበሩት ካህኑ ፀጋ ዘአብና ቅድስት እግዚእ ሐረያ፣ በየወሩ የቅዱስ ሚካኤልን በዓል ያከብሩ ነበርና መጋቢት 12 ቀን የተራበን ሲያበሉ ሞቶሎሚ ንጉሠ ዳሞት ሀገራቸውን ወርሮ ከእነርሱ ደረሰ፡፡ ጸጋ ዘአብም እንደማይምራቸው አውቀው አንከርት ወደሚባለው ባሕር ሮጡ፡፡ ከሞተሎሚ ጭፍሮች አንዱ ተከተላቸው፣ የማይደርስባቸው ሲሆን ሰይፉን ሊወረውርባቸው ቃጣ፡፡ ሰይፉ ከእጁ ተጠቅልላ ቀረች፡፡ በሌላ እጁ ሁለተኛ ሊወረውር ቢቃጣ አሁንም ተጠቅልላ ቀረች፡፡ እሳቸውም እንዳልተዋቸው አይተው ዘለው ከባሕር ገቡ፡፡ ከባሕር ውስጥ ሆነው እንዲህ አያሉ ይጮሁ ጀመረ…” ኀይል የምትሆነኝ ቅዱስ ሚካኤል፣ አምባ መጠጊያ የምትሆነኝ ቅዱስ ሚካኤል፣ ኀይልህ ወዴት ነው? ከኃሊነትህ ወዴት ነው? ተአምራት ማድረግህ ወዴት ነው? እንሆ መሞቻዬ ደረሰ፡፡ ዛሬ የሽብር ቀን ነው፡፡ ዛሬ የመከራ ቀን ነው፡፡ ዛሬ ጥፋት ተፈርዶብኝ፡፡ በበዓልህ ደስ ሳታሰኘኝ ታሳዝነኛለህን? እያሉ ያለቅሱ ጀመረ፡፡ እስመ ለመላእክቲሁ ይኤዝዞሙ በእንቲአከ ከመ ኢትትዐቀፍ በዕብን፤ እግርከ በመንገድህ ሁሉ ይጠብቁህ ዘንድ መላእክቱን ስለ አንተ ያዛቸዋልና፣ እግርህ በድንጋይ እንዳትሰናከል በእጆቻቸውም ያነሡሃል፡፡ እንዲል /መዝ.90፥11/ ቅዱስ ሚካኤል በውስጥ ሆኖ ተቀብሏቸዋል፡፡ “ወባሕርኒ ኮነቶ ከመ ደብተራ ዘድለት ለማኅደር” ይላል ባሕርም እንደ ድንኳን ሆነላቸው “ኦ ፍቁርየ ጸጋ ዘአብ አስመ አነ አዐቅበከ በይነ ዘይወጽእ እምሐቁከ፤ ወዳጄ ጸጋ ዘአብ ሆይ፥ ከአብራክህ ስለሚከፈለው ቅዱስ እጠብቅሃለሁና አትፍራ” አላቸው፡፡ ከዚህ በኋላ በሦስተኛው ቀን አውጥቶ ቤተ ክርስቲያን አድርሷቸዋል፡፡

በሌላ በኩል በሞቶሎሚ ወታደሮች የተማረኩት እግዚእ ሐረያ ለንጉሡ ሚስት ሊያደርጓቸው፣ ከቤተ መንግሥቱ አገቧቸው፡፡ ቅድስት እግዚእ ሐረያ ግን “ጌታዬ ፈጣሪዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ስንፍናዬን ለምን ተመለከትክ፡፡ በንጹሕ ሆኖ የሚያገለግል ባሪያህ ጸጋ ዘአብን ለምን አላሰብከውም አንተን ለሚክዱ ኃጥአን ለሚሆኑ ጠላቶች አሳልፈህ ለምን ሰጠኸኝ ሕግህን ሥርዓትህን ከማያውቅ ከሚያጸይፍ ባሪያ ልጅ ትሰጠኝ ዘንድ ወደድክን? ከዚያም ከንጹሕ አገልጋይህም ቢሆን አንተን ደስ የማያሰኝ ልጅ ካለሆነ ማኅፀኔን ዝጋው እልሃለሁ፡፡ አቤቱ የትድግና ባለቤት ዛሬ በእኔ ላይ ትድግናህን ግለጽ” በማለት ያመለክቱ ነበር፡፡ ጠባቂ መልአካቸው፡- ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ተገልጦ ከሠራዊት ሞቶሎሚ በመንጠቅ በክንፉ ታቅፎ ከዳሞት ዞረሬ በሦስት ሰዓት አደረሳቸው፡፡ በመጋቢት ሃያ ሁለት ቀን ጸጋ ዘአብ ከቤተ መቅደስ ገብተው ሲያጥኑና ስለ እግዚእ ሐረያ ሲለምኑ፣ መልአኩ ቅዱስ ሚካኤል ከቤተ መቅደስ አግብቶ ከዚያ ትቷቸው ወደ ሰማይ ዐረገ፡፡ ገድለ ተክለሃይማኖት ምዕ.12

በዚህ ሁኔታ በእግዚአብሔር ቸርነት፣ በመልአኩ ቅዱስ ሚካኤል ተራዳኢነት ደግም የተገናኙት ሁለቱ ቅዱሳን /ጸጋ ዘአብና እግዚእ ሐረያ/ መጋቢት ሃያ አራት ቀን ከአብራካቸው የሚከፈለውን ጻድቁ ተክለሃይማኖትን ፀነሱ፡፡ እነሆም ታኅሣሥ 24 ቀን ቅዱስ አባታችን ተወለዱ፡፡

“ገድለ ተክለሃይማኖት” የተባለው መጽሐፍ አባታችን ተክለሃይማኖት በተፀነሱበት መጋቢት 24 ቀን ለእናትና አባታቸው እግዚአብሔር ራእይ እንዳሳያቸው ይገልፃል፡፡ ቅድስት እግዚእ ሐረያ ያዩት ራእይ “የብርሃን ምሰሶ ከቤታቸው ውስጥ ቁሞ የሞሶሶው ራስ ከሰማይ ደርሶ በዓለም ያሉ ሕዝብ ሁሉ ነገሥታቱም ጳጳሳቱም በዙሪያው ቁመው እኩሌቶቹም ይሰግዱለታል፤ እኩሌቱቹም እሱን ጥግ አድርገው ይቀመጣሉ፡፡ በሱም ላይ ብዙ አዕዋፍ ተቀምጠውበታል፡፡እኩሌቶቹ ነጫጮች፣ እኩሌቶቹም ቀያዮች፣ እኩሌቶቹ አመድ አመድ ይመስላሉ፡፡ ዝጉርጉርም ናቸው፡፡ በሌላ በኩል ካህኑ ጸጋ ዘአብ ደግሞ በዚሁ ሌሊት ስላዩት ሕልም ለእግዚእ ሐረያ ሲነግሩ እንዲህ ብለዋል፡- “ከምንተኛበት አጎበር ሥር ፀሐይ ሲወጣ፥ስፍር ቁጥር የሌላቸው ብሩሃን ከዋክብት በክንፉ ላይ ተቀምጠው ለዓለሙ ሁሉ ሲያበሩ፣ ከብርሃኑም ብዛት የተነሣ ሀገሩ ሁሉ አበራ፡፡ ይህን ራእይ ዐይቼ ደንግጬ አለቀስኩ”

ከዚህ በኋላ መልአኩ ቅዱስ ሚካኤል የሁለቱንም ህልም ይተረጉሙላቸው ዘንድ ከእግዚአብሔር ተልኳል፡፡ በትርጓሜውም፡- “ከጸጋ ዘአብ ቤት ሲወጣ የታየው ፀሐይ ከአብራኩ የሚከፈለው ልጁ ተክለ ሃይማኖት ነው፡፡ በብርሃኑ ከምእመናን ላይ የኃጢአትን ጨለማ የሚያርቅ ይሆናል፤ በክንፉም ላይ ታዝለው፥የታዩት ከዋክብት በመንፈስ ቅዱስ በእርሱ ትምህርት ይወለዱ ዘንድ ያላቸው ልጆቹ ናቸው፡፡ የእግዚእ ሐረያ ሕልም ትርጉሙ እንዲህ ነው በቤታቸው የብርሃን ምሶሶ ቁሞ ራሱ ከሰማይ ደርሶ ያያቸው ልጅህ ነው፡፡ ነገሥታቱ ጳጳሳቱ ሲገዙለት ያየችውም በእውነት ነገሥታቱ ይሰግዱለታል፡፡ አሕዛብም ይገዙለታል፡፡ ለሁሉም መጠጊያ ይሆናል፡፡ ከነገሥታቱ በላይ ሆኖ ይኖራል፡፡ ተአምራቱ ከዛፍ ፍሬ ይበዛል ሥፍር ቁጥር የለውም፡፡ እንደሣዕረ ምድር ጸንቶ ይኖራል፡፡ ስሙም ለዘለዓለም ሲመሰገን ይኖራል፡፡ ሰማይ ከምድር በላይ እንደሆነ የሱም ስም አጠራሩ እንደሱ ካሉ ከቅዱሳን ምእመናን በላይ ሆኖ ይኖራል፡፡ የሕልማችሁ ትርጓሜ ይህ ነው፡፡” በማለት የሕልሙን ፍች አስታውቋቸዋል፡፡

በሚያስደንቅ ልዩ ልዩ ተአምራት በቅዱስ ሚካኤል ጥበቃና በእግዚአብሔር ቸርነት ከብዙ መከራ ተጠብቀው የኖሩት ሁለቱ ቅዱሳን ባልና ሚስት /ካህኑ ጸጋ ዘአብና ቅድስት እግዚእ ሐረያ/ ታኅሣሥ 24 ቀን ፃድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖትን ወለዱ፡፡

ከሠተ አፉሁ
ታኅሣሥ 26 ቀን /በተወለዱ ሦስተኛው ቀን/ በዕለተ ሰንበት ከጧቱ ሦስት ሰዓት ላይ እጆቻቸውን አንሥተው ወደ ሰማይ እየተመለከከቱ “አሐዱ አብ ቅዱስ አሐዱ ወልድ ቅዱስ አሐዱ ውእቱ መንፈስ ቅዱስ፤ ማለትም፦ ከወልድ ከመንፈስ ቅዱስ ጋራ በባሕርይ በሕልውና አንድ የሚሆን አብ በአካል በስም ልዩ ነው፣ ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ ጋራ በባሕርይ በህልውና አንድ የሚሆን ወልድ በአካል በስም ልዩ ነው፣ በህልውና አንድ የሚሆን መንፈስ ቅዱስ በአካል በስም ልዩ ነው” በማለት ሰማያዊያን  መላእክት ምድራውያን ጻድቃን ፈጣሪን በሚያመሰግኑበት ሥርዓት ሆነው አመሰገኑ፡፡ እናትየው እግዚእ ሐረያ ግን ይህንን በልባቸው እያደነቁ “ልጄ ፍሥሐ ጽዮን ምን ትላለህ ይህ ቃል የአባትህ ሥራ ነው፡፡ ላንተ ግን የሚገባህ ጡት መጥባት ነው” በማለት ተናገሩ፡፡ ጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ግን ክቡር ዳዊት “እም አፈ ደቂቅ ወሕፃናት አስትዳሎከ ስብሐት፡፡ በእንተ ጸላዒ ከመ ትንሥቶ ለጸላኢ ወለገፋዒ፤ ከሕፃናትና ከሚጠቡ ልጆች አፍ ምስጋናን አዘጋጀህ ስለ ጠላትህ ጠላትንና ቂመኛን ለማጥፋት” በማለት የተናገረው ቃል ተፈጽሞላቸዋል፡፡ መዝ.8፥2

“በመወለዱም ብዙዎች ደስ ይላቸዋል” ተብሎ በመጋቢ ሐዲስ በቅዱስ ገብርኤል የተነገረለት ዮሐንስ መጥምቅ /ሉቃ.1፥14/ ከእናት አባቱ አልፎ ብዙዎችን ከመድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያገናኘ የደስታ ምንጭ የሆነ ነቢይም ሐዋርያም ነው፡፡ በጻድቁ አቡነ ተክለሃይማኖት መወለድም፣ ለጊዜው ልጅ ባለማግኘት ለብዙ ዓመታት ሲያዝኑ ለነበሩ ወላጆቻቸው ታላቅ የምሥራችና ደስታ ሆኗል፡፡በፍጻሜው ግን ፈጣሪያቸውን ባለማወቅ በአጋንንት አገዛዝ ሥር ወድቀው የነበሩ በብዙ መቶ ሺህ የሚቆጠሩ ሰዎች በጸሎታቸው ኀይልና ግሩም በሆነው ትምህርታቸው ብርሃን ኢየሱስ ክርስቶስን ከባሕርይ አባቱ ከእግዚአብሔር አብና፣ ከባሕርይ ሕይወቱ መንፈስ ቅዱስ ጋር በአንድነት አውቀው ተረድተው ለስሙ እንዲገዙ አድርገዋል፡፡

ነቢዩ ኤርሚያስን ፈጣሪያችን ልዑል እግዚአብሔር ከእናቱ ሆድ ጀምሮ ለቅድስና ለክብር በነቢይነት እንደጠራው በመጻሕፋችን ተገልጦአል፡፡ /ኤር.1፥5/ ጻድቁ አቡነ ተክለሃይማኖትም ለኢትዮጵያ ሰዎች ሐዋርያ ሆነው ያገለግሉ ዘንድ በባለቤቱ በመድኀኔዓለም በኢየሱስ ክርስቶስ አንደበት “እስመ ረሰይኩከ ሐዲስ ሐዋርያ፤ አዲስ ሐዋርያ አድርጌ ሾሜሃለሁ” ተብሎ የተነገረላቸው ናቸው፡፡ በዚህም በጌታችን ቃል “በእኔ የሚያምን እኔ የምሠራውን ሥራ እርሱም ይሠራል ከዚያም የሚበልጥ ይሠራል” /ዮሐ.14፥12/ ተብሎ በተነገረው ቃል መሠረት፤ በሰው ሰውኛ ሊደረጉ የማይችሉ ታላላቅ ተአምራትን በመፈጸም ኢ-አማንያንን ወደ ሃይማኖት መልሰዋል፡፡ ተጋድሏቸውን የመዘገበው መጽሐፍ /ገድለ ተክለ ሃይማኖት/ እንደተመዘገበው በዛፍ ላይ አድሮ ሲያሰግዳቸውና ሲያስመልካቸው የነበረ ጋኔኑን አዋርደው እርሱን ከኢትዮጵያ ምድር አርቀው በአምልኮተ ባዕድ የነበሩ ሰዎችን ወደ ቤተ ክርስቲያን ኅብረት ቀላቅለዋል፡፡

ባለብዙ ገድል ጻድቁ ተክለ ሃይማኖት “ዳግማዊ ዮሐንስ” የሚል ስያሜ የተሰጣቸው ሐዋርያ ናቸው፡፡ ዮሐንስ መጥምቁ በተፀነሰ ጊዜ የአባቱን አንደበት የዘጋ፣ ሲወለድ ደግሞ የአባቱን አንደበት ዳግመኛ የከፈተ ነው፡፡ (ሉቃ.1፥62-66) መምህር ወመገስጽ ዘኢያደሉ ለገድ የተባለለት፥ ዮሐንስ መጥምቁ ንጉሥ ሔሮድስን ሳይፈራና ሳያፍር የገሰጸ እንደሆነ ሁሉ፤ አባታችን ተክለ ሃይማኖትም  እንደ ሞቶሎሚ ያሉ ጣዖት አምላኪና አስመላኪ ነገሥታትና ኀያላንን ሳይፈራ የተጠራለትን አገልግሎት በጽኑ መታመን የፈጸመ ነው፡፡

ፈጣሪያችን ከጻድቁ አባታችን ከተክለሃይማኖት በረከት ረድኤት ያሳትፈን፡፡ አሜን

በሊቀ ካህናት ክንፈ ገብርኤል አልታዬ ኅልፈት ‹‹ሐዘኑ የቤተ ክርስቲያን ነው›› /ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ/


  • ‹‹…ወንድማችንን እናውቃቸዋለን፤ በእውነቱ ለፌ ወለፌ የማይሉ ደረቅ ሊቅ ናቸው፤ በሃይማኖቱ ዘርፍ ከሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን፣ ከቀኖና ቤተ ክርስቲያን አንዲቱም ነጥብ እንዳትዛባ ከወንድሞቻቸው ጋራ ብዙ ትግል ያደረጉ አለኝታ ሊቅ ነበሩ፤ እርሳቸውን ማጣታችን ትልቅ ጉዳት ነው፤ ሐዘኑ የልጆቻቸውም አይደለም፤ ሐዘንተኛዋ ቤተ ክርስቲያን ናት፤ እግዚአብሔር ለዚኽች እናት ቤተ ክርስቲያን እርሳቸውን የመሰለ ይተካልን ከማለት በቀር ምንም ማድረግ አንችልም፡፡››
ከዘመናችን የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት መካከል መላ ዘመናቸውን ለሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን መጠበቅና መከበር በጽናት ሲያስተምሩ፣ ሲጽፉና ሲሟገቱ ኖረው ታኅሣሥ ፲፱ ቀን ፳፻፯ ዓ.ም. ወደ ዘላለም ዕረፍት የተጠሩት የሊቀ ካህናት ክንፈ ገብርኤል አልታዬ ሥርዓተ ቀብር ታኅሣሥ ፳ ቀን ፳፻፯ ዓ.ም. በመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ተፈጽሟል፡፡
የሊቁ ዜና ዕረፍት ከተሰማበት ጊዜ አንሥቶ ለሥርዓተ ጸሎተ ፍትሐቱና ሥርዐተ ቀብሩ በወጣው መርሐ ግብር መሠረት፣ ታኅሣሥ ፲፱ ቀን ለ፳ አጥቢያ ምሽት 3፡00 ጀምሮ በብዙ መቶዎች የሚቆጠሩና ከተለያዩ አድባራት የተሰባሰቡ ሊቃውንትና መዘምራን በመኖርያ ቤታቸው በመገኘት ሰዓታቱን ቆመው ማሕሌቱን ሲያደርሱ አድረዋል፡፡
ሊቁ አያሌ አገልግሎት የሰጡበት የሰበካቸው የቀበና መካነ ሕይወት ጻድቁ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ቤተ ክርስቲያን ካህናት ሰዓታቱንና ማሕሌቱን የመሩ ሲኾን ከጠዋቱ 12፡00 ጀምሮ ደግሞ ሥርዓተ ፍትሐቱን በማከናወን ጸሎተ ግንዘቱን ፈጽመዋል፡፡ በዚኹም ሰዓት መዘምራኑ አደራረሱን በዐቢይ ስብሐተ ነግህ አድርሰዋል፡፡
የሊቁ ዐፅም በመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል እንዲያርፍ በብፁዓን አባቶችና በቤተሰቡ ምክር በተወሰነው መሠረት÷ ከቀኑ 5፡00 ሲኾን ግራና ቀኝ ተሰልፈው መዝሙረ ሐዘን የሚያሰሙ የሰንበት ት/ቤት ተማሪዎችና ጥንግ ድርብ የለበሱ መዘምራን፤ ቃጭል የሚመቱ፣ መስቀልና ጃንጥላ የያዙ ዲያቆናት፤ ጽንሐሕና ጃንጥላ የያዙ ካህናት፤ የሊቁን ሥዕለ ገጽና የማዕርግ አልባሳት የሚያሳዩ ልኡካን፤ የአድባራት አለቆችና ሐዘንተኞች ምእመናን እንደ ቅደም ተከተላቸው አስከሬኑን የያዘውን መኪና በመሐል አድርገውና በክብር አጅበው ጉዞ ወደ ካቴድራሉ ኾኗል፡፡
Lique Kahinat Kinfe Gabriel Funeral service
አስከሬኑን የያዘው መኪና በካቴድራሉ ሲደርስ የደወል ድምፅ ተሰምቷል፤ በብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት መሪነትም ሥርዓተ ቅዳሴው ተከናውኖለታል፡፡ ጸሎተ ቅዳሴው እንዳበቃ አስከሬኑ ወደ ዐውደ ምሕረት ወጥቶ መርሐ ግብሩ በትንሣኤ ማሳተሚያ ድርጅት ዋና ሥራ አስኪያጅ ሊቀ ካህናት ብርሃኑ ገብረ ዐማኑኤል እየተመራ፣ ከየአድባራቱ የተሰባሰቡት ሊቃውንት ሰላም የተባለውን ድጓ አለዝበው ለዐሥራ አምስት ደቂቃ ያኽል አሸብሽበዋል፡፡ በማያያዝም ሊቁ በተለይም በየዓመቱ በኅዳር ጽዮን ማርያም ክብረ በዓል እየወረዱ የሚያገለግሏቸውና በርእሰ አድባራት ወገዳማት አዲስ ዓለም ደብረ ጽዮን ማርያም ገዳም ንቡረ እድ አባ ገብረ ሕይወት መልሴ የሚመሩ የገዳሟ ሊቃውንትም፡- አበ ኵልነ አባ ክንፈ ገብርኤል እያሉግሳዊ ጣዕመ ዝማሬ በሽብሻቦ አሰምተዋል፡፡
ከሊቀ ካህናት ክንፈ ገብርኤል ጋራ በሊቃውንት ጉባኤ ለረጅም ጊዜ አብረው እንደሠሩ የገለጹት መልአከ ታቦር ተሾመ ዘሪሁን ‹‹ወንድማችን ስለኾኑና አብረን ብዙ ዘመን ስለሠራን ኹላችንም ሐዘንተኞች ነን›› ካሉ በኋላ የሊቀ ካህናትን ታላቅነትና የኅልፈታቸውን አስደናቂነት የሚዘክር አንድ ሥላሴ ቅኔ አበርክተዋል፤ ወዳጃቸው መልአከ አርያም ሐረገ ወይንም አንድ መወድስ ቅኔ አሰምተዋል፡፡
የሊቁን ዜና ሕይወት ወዕረፍት የሚናገረው ታሪክ፣ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ጽ/ቤት የአስተዳደር ሓላፊ በነበሩትና አኹን ሰባኬ ወንጌል በኾኑት መልአከ ብርሃን ኢሳይያስ ወንድምአገኘኹ በንባብ ከተማ በኋላ የዕለቱ ትምህርት በሰሜን ምዕራብ ሸዋ – ሰላሌ ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ ተሰጥቷል፡፡ ሊቁ በት/ቤት ብዙ ከደከሙ በኋላ በተለይም ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን እንዳይዛባ በተገቢው መንገድ ያገለገሉና በሃይማኖት ጽናት የተከራከሩ አባት እንደነበሩ የመሰከሩት ብፁዕነታቸው፣ ተጠያቂውን ሊቅና ታላቁን ምሁር ማጣት ለቤተ ክርስቲያን ትልቅ ጉዳት እንደኾነ ገልጸዋል፡፡
የዐሥርት ዓመታት ድካም የሚጠይቀውን ትምህርት ተምሮ እንደሚገባው የሚያገለግል ሊቅ ለማግኘት ብዙ ጥረት የሚጠይቅ በመኾኑ፣ የዘመናት ባለቤት እግዚአብሔር በሕይወት የቀሩትን በጣት የሚቆጠሩ ሊቃውንት ዕድሜ አርዝሞ በጤና እንዲያቆያቸው፣ እንደ ሊቀ ካህናት ክንፈ ገብርኤል ድካማቸውን ፈጽመው በደኅና በተሸኙት ሊቃውንት እግር እንዲተካም ብፁዕነታቸው በትምህርታቸው ተማፅነዋል፡፡
የሊቁ ዕረፍት ክንፈ ገብርኤል ተብለው በተጠሩበት በመልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ክብረ በዓል ዕለት መኾኑ ግን የአካሔዳቸውን መልካምነት የሚያሳይ ትልቅ ምልክት እንደኾነ በመግለጽ ቤተሰቦቻቸውንና ሐዘንተኞችን አጽናንተዋል – ‹‹የክንፈ ገብርኤል ዋጋ ተከፍሏል ማለት ነው›› ሲሉም የቅዱሳን አምላክ ነፍሳቸው በተድላ ገነት እንዲያሳርፍ ጸልየዋል፤ የሊቁን ሥርዓተ ቀብር ለማስፈጸም በአገልግሎት ሲደክሙ ያደሩና የዋሉ ሊቃውንትንና መዘምራንንም ‹‹ለእናንተም ብድር ይግባችኹ፤ መቼም መሸኛኘት አይቀርም፤ ለእናንተም እንደዚኹ የሚያከብር ይላክላችኹ›› ሲሉ አመስግነዋቸዋል፡፡
His Grace Abune Qewostos
ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ፤ የሰሜን ምዕራብ ሸዋ – ሰላሌ ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ
በመንፈስ ቅዱስ ይመራ የነበረው ሊቁ ቅዱስ ያሬድ የእያንዳንዱን ቅዱስ አባት፣ የእያንዳንዱን ሊቅ ቅድስና፣ የሕይወት ታሪክ ቀደም ብሎ ስለታየው ምስክርነት ሰጥቷል፡፡ ‹‹ይህ ቅዱስ አባት ከሕፃንነቱ ጀምሮ ባለ ዘመኑ ኹሉ ከቤተ እግዚአብሔር ሳይለይ እግዚአብሔርን ያገለገለ ቅዱስ ነው፡፡ እናት አባት ለሌላቸው አባት ነው፡፡ ችግር ለጸናባቸው ባልቴቶች ችግራቸውን የሚያስወግድ ነው፡፡ በተቀደሰ ክህነት እግዚአብሔርን ያገለገለ የእግዚአብሔር አገልጋይ ነው፡፡›› ሲል ለብዙዎቹ መስክሯል፡፡ ከብዙዎቹ መካከል አንዱ አኹን ታሪካቸው በዝርዝር የሰማነው ሊቁ ሊቀ ካህናት ክንፈ ገብርኤል አልታዬ ናቸው፡፡
እኒኽ ታላቅ ሊቅ ቅዱስ አባት ዛሬ በጥሩ አካሔድ ነው የሔዱት፡፡ ሐዘኑ የቤተ ክርስቲያን ነው፤ የልጆቻቸውም አይደለም፡፡ ልጆቻቸውን አስተካክለዋል፤ ለወግ ለማዕርግ አድርሰዋል፡፡ ሐዘንተኛዋ ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ ተጠያቂ ሊቅ አጥታለች፤ ታላቅ ሊቅ ተለይቶናል፡፡
እኒኽ ታላቅ ሊቅ በትምህርት ቤት ብዙ ደክመዋል፤ ከት/ቤት በኋላ ቅድም በዜና ሕይወታቸው እንደተገለጸው በተገቢው መንገድ አገልግለዋል፡፡ ተጠያቂ ሊቅ ነበሩ፤ ለሃይማኖት የቆሙ ሊቅ ነበሩ፤ በሃይማኖቱም ዘርፍ ከሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን፣ ከቀኖና ቤተ ክርስቲያን አንዲቱም ነጥብ እንዳትዛባ ሽንጣቸውን ገትረው ይከራከሩ የነበሩ የቤተ ክርስቲያን ሊቅ፣ የቤተ ክርስቲያን ተጠያቂ፣ ታላቅ ምሁር እንደነበሩ እናውቃለን፡፡ እኒኽን ማጣት ትልቅ ሐዘን ነው፤ ትልቅ ጉዳት ነው፡፡
አዎ! ብዙዎች ባለዲግሪዎች አሉ፤ ዲግሪ ይፈለጋል፤ የሚናቅም አይደለም፡፡ ዳሩ ግን እንዲኽ እንደ እርሳቸው በቤተ ክርስቲያን ትምህርት ሳይደክሙ ወደ ቤተ ክርስቲያን ገብቶ በዲግሪው ብቻ ላገልግል ቢባል አይቻልም፤ ድግር ይኾናል ዲግሪው! የቤተ ክርስቲያን አካሔድ፣ ምስጢረ ሃይማኖቱ ከባድ ነው፡፡ ምስጢረ ተዋሕዶ ድካም ይጠይቃል፤ ኻያ፣ ሠላሳ፣ ዐርባ ዓመት የትምህርት ጊዜ ይጠይቃል፤ ኻያ፣ ሠላሳ፣ ዐርባ ዓመት ተምሮ ቤተ ክርስቲያንን እንደሚገባው የሚያገለግል ሊቅ ለማግኘት ስንት ጥረት ይጠይቃል? ትልቅ ጉዳት ነው፡፡
ትልቅ ጉዳት ነው፤ ወንድማችንን እናውቃቸዋለን፤ በእውነቱ ደረቅ ሊቅ ናቸው፤ ለፌ ወለፌ የማይሉ፣ ከወንድሞቻቸው ጋራ ቤተ ክርስቲያንን ለመጠበቅ ብዙ ትግል ያደረጉ አለኝታ ሊቅ ነበሩ፡፡ እርሳቸውን በማጣታችን አዝነናል፡፡ እግዚአብሔር ለዚኽች እናት ቤተ ክርስቲያን እርሳቸውን የመሰለ ይተካልን ከማለት በቀር ምንም ማድረግ አንችልም፡፡
ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን÷ በእውነቱ ከሌሊቱ ሰዓት ጀምራችኹ ያቀረባችኹት አገልግሎት፣ የከፈላችኹት መሥዋዕት እጅግ በጣም የሚያስመሰግን ነው፡፡ እግዚአብሔር ይባርካችኹ፤ ዋጋችኹን ይክፈላችኹ፤ ለእናንተም ብድር ይግባችኹ፡፡ መቼም መሸኛኘት አይቀርም፤ አይደለም? ለእናንተም እንደዚኹ የሚያከብር ይላክላችኹ፡፡
ልጆች ልታዝኑ አይገባችኁም፤ አስታማችኋል፤ እናውቃለን ተንገላታችኋል፤ መቼም ሥጋ የለበሰ መንገላታቱ አይቀርም፤ ነገር ግን አካሔዳቸው የቅዱሳን አካሔድ ነው፤ ደክመው ወጥተው ወርደው እጫፉ ላይ ደርሰዋል፤ ሰባ ሰማኒያ ዘመን አይደለም የተወሰነው፤ ሰባውን ጨርሰዋል፤ ትንሽ ነበር የቀራቸው በደኅና ተሸኝተዋል፡፡ በዚኽ ቅዱስ ቦታ ከወንድሞቻቸው አጠገብ እንዲያርፉ ብፁዕ ወቅዱስ አባታችን ፈቅደው መካነ መቃብራቸው ተዘጋጅቷል፡፡
እንግዲኽ መቼም ምንም ቢኾን ጉዳይ ሲፈጽም የኖረ ታላቅ ሰው የተለየ ዕለት እሰይ ተብሎ አይሸኝም፡፡ በእውነቱ እኛ የምንወደው ሽማግሌዎቹ ሊቃውንት አልጋቸው ላይ ተኝተውም ቢኾን እንዲጠየቁ እንጂ እንዲለዩብን አንሻም፡፡ እዚያው እየተከባከብን ጥያቄ ሲመጣ እስኪ መምህር እገሌን ጠይቁ እያልን ብንልክ ነው ደስ የሚለን፡፡ አኹንም በጣት የሚቆጠሩ አባቶች ሊቃውንት አሉ፤ የእነርሱን ዕድሜ እግዚአብሔር ያርዝምልን፤ የወንድማችንን የሊቁን ነፍስ በተድላ ገነት ያኑርልን፡፡
እግዚአብሔር ለወዳጆቹ ቃል ኪዳን ሲሰጥ፣ ‹‹በስምኽ የተጠራውን ከአንተ ጋራ ዋጋውን እከፍለዋለኹ›› አለ፡፡ ሊቁ ወንድማችን፣ ክንፈ ገብርኤል ተብለው ሲጠሩ ዕረፍታቸውን የመልአኩ የቅዱስ ገብርኤል በዓል በሚከበርበት ቀን አደረገው፡፡ ይህም አንድ ትልቅ ምልክት ነው፡፡ የክንፈ ገብርኤል ዋጋ ተከፍሏል ማለት ነው፡፡ የወንድማችንን የክንፈ ገብርኤልን ነፍስ በተድላ ገነት ያኑርልን፤ ለእናተንም የድካማችኹን ዋጋ ይክፈላችኹ፡፡

የሊቁ የሕይወት ታሪክ በሚነበብበት ወቅት በካቴድራሉ ደቡባዊ አንቀጽ ከሚገኝ ታላቅ የጥድ ዛፍ ላይ ማንም ሳይነካው አንድ ትልቅ ቅርንጫፍ ተገንድሶ መውደቁ ብፁዕነታቸው ከጠቀሱት የምልክት ጉዳይ ጋራ ተያይዞ የበርካታ ሐዘንተኞች መነጋገርያ ኾኗል፡፡ ይህንንም ድንቅ ከአስተዋሉት ሐዘንተኞች አንዱ የኾነው የነገረ ቤተ ክርስቲያን ተመራማሪው ዲያቆን ዳንኤል ክብረት የትልቁ ዋርካ ትልቁ ቅርንጫፍ በሚል ርእስ የሊቁን ዕረፍት አስመልክቶ በጡመራ መድረኩ ባሰፈረው ማስታዎሻ፡- ‹‹በቦታው የነበሩ፣ ይህንንም ነገር የተመለከቱ ኹሉ ታሪኩን በካሜራቸው ሲቀርፁና ከታላቋ ዋርካ ከቤተ ክርስቲያን ብዙዎችን የያዘው አንዱ ታላቅ ቅርንጫፍ ሊቀ ካህናት ክንፈ ገብርኤል ዛሬ መሰናበቱን በሐዘን ሲተረጉሙ ነበር፤›› በማለት አትቶታል፤ የቅርንጫፉን ቅጠልም ብዙዎች ተሻምተው ሲወስዱ መመልከቱን ጦማሪው በማስታዎሻው ገልጧል፡፡

good omen on the funeral service of Archpriest Kinfe Gabriel
ከታላቋ ዋርካ ከቤተ ክርስቲያን አንዱ ታላቅ ቅርንጫፍ ሊቀ ካህናት ክንፈ ገብርኤል ዛሬ ስለ መሰናበቱ…
ከርእሰ አድባራት ቁልቢ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን የበዓል አከባበር ጉዟቸው እንደተመለሱ ከስፍራው መድረሳቸው የተገለጸው ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ በሰጡት ቃለ ምዕዳን÷ ‹‹እግዚአብሔር አምላክ ጥሪውን ሲልክ ከሰዓቱ የሚያልፍ ባለመኖሩ ወንድማችን ከእኛ በሥጋ ተለይተዋል፤ በዐጸደ ነፍስ ግን ሕያው ናቸው፤ ለትውልድ የሚተርፍ ሥራ ሠርተዋልና›› በማለት ሐዘንተኞችን አጽናንተዋል፤ ለአስከሬኑ ዑደት ከተደረገ በኋላም በምሥራቃዊ አንቀጽ የተዘጋጀው መካነ መቃብር በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩና በብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ተባርኮ ሥርዓተ ቀብሩ ተፈጽሟል፡፡
ከሊቃውንት የተበረከቱ ቅኔዎች
 ሥላሴ ዘመልአከ ታቦር ተሾመ ዘሪሁን
እንዘ ሞት መሬታዊ ዘሰማያዊ ለእሊአኹ
መኑ አዘዘ ይዕዜ ወተአደወ ሥርዓተ
ገብርኤል በክንፉ ከመ ይጹር ሞተ
ወቤተ ክርስቲያን ዘኮንኪ ዘክንፈ ገብርኤል ቤተ
አስምዑ ምድረ ወሰማያተ
ይግበሩ ለኪ እምዕለት ዕለተ
ዘከማሁ አእላፈ ኖሎተ፡፡
መወድስ ዘመልአከ አርያም ሐረገ ወይን ደምሴ
እስራኤል አዕፅምት አመ ተጼወዉ መቃብረ አበው የኀድር
እንዘ በአካል ኢይፃሙ፡፡
ልዑከ ኤርሚያስ ባሮክ ለክንፈ ገብርኤል ዐፅሙ
በክሳደ ንስር አስቆቅዎ ለኤርሚያስ ከመ ተፈነወ
ጳውሎስ ማኅተሙ፡፡
ድቀተ እስራኤል ኀዘነ ልብ ከመ ለዘመን ቀርበ
ጽሑፈ ይንግሮሙ፡፡
ለዓለም
ዕረፍትሂ ዘይዕዜ ለአቤሜሌክ ንዋሙ
ለክንፈ ገብርኤል ይኤድሞ ወይትርአዮ በውስተ ሕልሙ፡፡
አምጣነ ፈነዎ ኤርሚያስ ባቢሎናዊ ሕማሙ
በቆጽለ በለስ ለሕሙማን ኃይላተ ፈጣሪ ይፈውሶሙ፡፡
የሊቁ በረከታቸው ይደረብን፤ እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን፤ አሜን፡፡


                                   በአውሮጳ   የካህናት አንድነት ማኅበር ሊቋቋም መሆኑ ታወቀ በ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከመላዋ አውሮጳ   የተውጣጡ ካህናት፡” የ...